በሀገር ዕድገትና በማህበረሰብ ልማት ላይ ትልቅ ሚና እንዳለው እና በእውቀትና ክህሎት የበለፀገ ዜጋን ለማፍራት ሳይንስና ቴክኖሎጂ ድርሻው ከፍተኛ ነው። ቀድመው በዚህ ዘመን ሳይንስ የማይተካ ሚና እንዳለው የተረዱ ሃገራት ሳይንስና ቴክኖሎጂን በማሳደግና ከቱርፋቱ በመጠቀም የኢኮኖሚ አቅማቸውን ማፈርጠም ችለዋል። ታሪክ እንደሚነግረንና አሁንም እንደምናየው ሳይንስና ቴክኖሎጂ በዓለማችን ላይ ባደጉት እና በማደግ ላይ ባሉ ሀገሮች መካከል በተጨባጭ ልዩነት መፍጠር መቻሉን ነው። ይህም በደረስንበት ዘመን በየትኛውም ዘርፍ አገራዊ አቅምን ለማጎልበት ዋንኛ መሳሪያ ሳይንስ መሆኑ የማይካድ ሃቅ ያደርገዋል። በመጪው ጊዜ ደግሞ የዘርፉ ተጽዕኖ አሁን ካለንበት ደረጃ ከእጥፍ በላይ እንደሚሆን ሁኔታዎች ይጠቁሙናል። በተጨባጭም አመላካች ናቸው። በዚህ ረገድ በዓለም ሃገርት መካከል የተፈጠረውን የስልጣኔ ርቀት ለማቀራረብ በተለይ ታዳጊ አገራት የሳይንስና ቴክኖሎጂ ምጥቀት ተሳትፏቸውን ማዳበር የግድ መሆኑን ሁኔታዎቹ ያመላክታሉ። ስለዚህ ታዳጊ አገሮች ዘመኑ መጓዣው ቴክኖሎጂ፤ መራመጃው ሳይንስ በመሆኑ መፃኢ ዘመንን የተሻለ ለማድረግ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ላይ ብርቱ ጥረት ማድረግ የሚገባቸው ስለመሆኑ መረዳት ይቻላል። ይህን ጊዜው የሚጠይቅ፣ የሚያስገድድ በመሆኑ የሰው ሃይልን በዘርፍ በብዛት እና በብቃት በማጠንከር ተወዳዳሪ መሆንን ይጠይቃል። በተጨማሪም ተወዳዳሪነትን ማሳደግ የግድ ይላል።
ከዓለም የስልጣኔ አካሄድ እና ከመጪው ጊዜ ጋር አብሮ ለመራመድ ከምንም በላይ ዘላቂ መፍትሄዎች ላይ ማተኮር መቻሉ ውጤት እንደሚኖረው ይታመናል። በጊዜያዊነት ከሚደረጉ ጥረቶች ባሻገር ዘላቂ በሆነ መልኩ ክፍተቶችን መሙላት የሚያስችሉ መርሃ ግብሮችን ተግባራዊ ማድረግን ይጠይቃል። የሳይንስና ቴክኖሎጂ ትምህርትን ከታች ጀምሮ ማስተማር ወደዚህ ውጤት የሚያንደረድር መሆኑን የተለያዩ ሃገራት ተሞክሮዎቹ ያስረዳሉ። ትምህርት ደግሞ ለቴክኖሎጅ መሻሻል ዋነኛው መክፈቻ ቁልፍ መሆኑን ጠቅሰን፤ ወደ አህጉረ እስያ እንሻገር።
በአለማችን የቴክኖሎጂን አቅም አሟጠው የኢኮኖሚ አቅማቸውን ካፈረጠሙ እና የማህ በረሰባቸውን አኗኗር ወደ ላቀ ደረጃ ካደረሱት ሃገራት መካከል እነ ጃፓን፣ ቻይና ኮሪያ እና የመሳሰሉት ናቸው። እነዚህ ሀገራት የትናንት ታሪካቸውን ቀይረው ኃያላንና ያደጉ ሀገራት ተርታ ላይ መመደብ የቻሉበት ሚስጥሩ ሳይንስና ቴክኖሎጂ መሆኑን መረጃዎች ይነግሩናል። ሃገራቱ ለሳይንስና ቴክኖሎጂ እጅግ ከፍተኛ ወጪን በመመደብ መስኩን ለመምራት በፉክክር ከመስራት ባሻገር በመስኩ የተማረ የሰው ኃይል ለማፍራት ከፍተኛ ትኩረት ሰጥተው ሰርተዋል። ሃገራቱ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ላይ ብቻ ያተኮሩ የትምህርት ተቋማት አቋቁመው ሰፊ ቁጥር ያለው የተማረ የሰው ኃይል ማፍራት ከመቻላቸው ጋር ይያያዛል። በተለይ በትምህርት ተቋማት ውስጥ ከታች ጀምሮ መሰረት እንዲይዙ የሚያስችል ሥርአት መዘርጋት መቻላቸው በቂ የተማረ የሰው ኃይል ማፍራት ያስቻላቸው ስለመሆኑ ነው። ከዚህ ነባራዊ እውነታ በመነሳት የኢትጵያን አካሄድ እንመልከት።
ኢትዮጵያም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ለሳይንስና ቴክኖሎጂ በሰጠችው ልዩ ትኩረት የተለያዩ እመርታዊ ለውጦችን በማስመዝገብ ላይ የምትገኝ ቢሆንም፤ አሁንም በዘርፉ ቀዳሚ ከሆኑ አገራት ጋር ስትነፃፀር እጅግ በራቀ ደረጃ ላይ ትገኛለች። የቴክኖሎጂ አቅም ግንባታ መሠረቱ የተማረ የሰው ኃይል እንደሆነ ይታወቃል። ስለዚህ በመስኩ የተማረ የሰው ኃይል ለማፍራት ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶት መስራት እንደሚገባ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ሙያተኞች ይናገራሉ። በርግጥም የሳይንስና ቴክኖሎጂ ትምህርትን ከታች ጀምሮ ማስተማር ወደዚህ ውጤት የሚያንደረድር እንደሆነ ከላይ ከተነሱት ተሞክሮዎች መረዳት ይቻላል። በሃገራችን ይህን ዓይነቱን ሥርዓት መፍጠር እንደሚገባ ከሚያምኑት መካከል ደግሞ የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ ይጠቀሳል። በሀገራችን የሳይንስ ዕውቀትንና ባሕልን የማሳደግና የማስፋፋት ተግባርን በዋናነት ትኩረት ሰጥቶ በመስራት የሚታወቀው አካዳሚው የሳይንስና ቴክኖሎጂ ትምህርትን ከታች ጀምሮ ማስተማር ከፍተኛ ቁጥር ያለው የተማረ የሰው ኃይል ለማፍራት እንዲሁም ለቴክኖሎጂ አቅም ግንባታ ጉልህ ሚና እንደሚኖረው ያምናል። አካዳሚው ችግሩን ለማቃለል የበኩሉን አበርክቶ ለማድረግ እየጣረ ይገኛል። ከጥረቶቹ መካከል ደግሞ ከሦስት ዓመታት በፊት ግንባታው የተጀመረው በኢትዮጵያ በዓይነቱ የመጀመሪያ የሆነው የልጆች የሳይንስ ማዕከል ይጠቀሳል። ማዕከሉ ሐምሌ 9 ቀን 2013 ዓ.ም ተጠናቆ በይፋ ተመርቋል። ይህም ኢትዮጵያዊያን ህጻናትን በተመቻቹ የቴክኖሎጂ ቁሳቁሶች በመታገዝ ስለ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ፅንሰ-ሐሳብና አሠራር ዕውቀት እንዲያገኙ የሚያስችል እድል መሆኑን ብዙዎች ሲናገሩ ተደምጠዋል።
የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚው ፕሬዚዳንት ፕሮፌሰር ፅጌ ገብረማርያም ፤ የሳይንስ ዕውቀትንና ባሕልን የማሳደግና የማስፋፋት ተግባር አካዳሚው በዋናነት ትኩረት ሰጥቶ ከሚሰራቸው ተግባራት መካከል እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ በዚህ መሰረት በኢትዮጵያ በዓይነቱ የመጀመሪያ የሆነውን የልጆች የሳይንስ ማዕከል መገንባቱን ነው ያስታወቁት። ማዕከሉ የሳይንስ ዕውቀትንና ባሕልን ለማሳደግ፤ ህጻናት በተመቻቹ የቴክኖሎጂ ቁሳቁሶች እየተዝናኑ ስለሳይንስና ቴክኖሎጂ ፅንሰ-ሐሳብና አሠራር ዕውቀት እንዲያገኙ እንዲሁም ለዘርፉ ያላቸውን ዝንባሌ እንዲያሳድጉ ታቅዶ ሊቋቋም እንደተቻለም ነው ያብራሩት። የማዕከሉ ግንባታ ከተጀመረ በሦስት ዓመት የተጠናቀቀ ሲሆን፤ ለግንባታው የጀርመን ባህል ማዕከል 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር፣ የኢትዮጵያ የሳይንስ አካዳሚ መንግስት የሳይንስ ዘርፍን ለማጠናከር ከስጠው 40 ሚሊዮን ብር 7 ነጥብ 3 ሚሊዮን ብር እና የጀርመኑ የሳይንስ ማዕከል በፌኖሜንታ ሰባት ሚሊዮን ብር ወጪ ተገንብቶ ለአገልግሎት መብቃቱን ይገልጻሉ።
አገራችን ወቅቱ በሚፈልገው የእድገት አቅጣጫና ፍጥነት እንድትጓዝ ለማድረግ የሳይንስ እውቀት ማበልፀጊያ ተቋማት ግንባታ የሳይንስ ማህበረሰብ ምስረታና የአገር በቀል እውቀት አጣምሮ መስራት እንዳለበት ገልፀው ለዚህ አላማ ስኬት የኢትዮጵያ መንግስት፣ የጀርመን የባህል ተቋም እና ጀርመን ሀገር የሚገኘው ፌኖሜንታ ሳይንስ ማዕከል የቴክኒክና የፋይናንስ ድጋፍ ማድረጋቸው የሚመሰገን ነው ሲሉ ነበር ያመላከቱት፡፡
የሳይንስ አካዳሚው ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፕሮፌሰር ተከተል ዮሐንስ ደግሞ የበርካታ አገር በቀል እውቀቶች፣ የጥንታዊ ታሪክ ቅርሶችና የተፈጥሮ ጸጋ ባለቤቶች ነን። እነዚህን በሳይንሳዊ መንገዶች በማዘመን ለህብረተሰባችን ህይወት መሻሻል የጀመርናቸውን ውጥን ተግባራት ከግብ ለማድረስ የሁሉም ባለድርሻ አካላት ብርቱ ርብርብ እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል፡፡
በሀገራችን በዓይነቱ የመጀመሪያ የሆነውን የልጆች የሳይንስ ማዕከል ከአጋር ድርጅቶች ጋር በመቀናጀት ማቁቋሙ የሚበረታታ መሆኑን ያነሱት የሴቶችና ህጻናት ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ወ/ሮ አለሚቱ ኡሞድ፤ የኢትዮጵያ መንግስት ለሳይንስና ቴክኖሎጂ ልማት በሰጠው ልዩ ትኩረት በርካታ ተስፋ ሰጪ ውጤቶችን ማስመዝገብ እንደተቻለ ይነገራሉ። ይህ የሳይንስ አካዳሚ ይህንኑ በማጠናከር የነገ ሀገር ተረካቢ የሆኑትን ሕፃናት በሳይንስና ቴክኖሎጂ እውቀት ተኮትኩተው እንዲያድጉና ለሀገራቸው ሁሉን አቀፍ ልማትና ብልጽግና ጉልህ ሚና የሚጫወት ስለመሆኑም ነው ያመላከቱት።
ዳንኤል ዘነበ
አዲስ ዘመን ነሐሴ 3 ቀን 2013 ዓ.ም