የስዕል ጥበብ ከጎበኘው ቤተሰብ ነው የተገኘችው። ሥነ-ጥበብ በሰጣት ነፃነት ልክ ከአፍሪካ ቀንዷ ምድር የወጡ ውብ የእጅ ሥራዎቿ በአለም አደባባይ እንዲታዩ ለማድረግ ሰርታለች።
ገና በአፍላ እድሜ በተለያዩ ቁሳቁሶች ላይ በተለያዩ ቀለማት ድንቅ ኢትዮጵያዊ ውበትን የምትፈጥረው ወጣት ሰዓሊ ዮርዳኖስ አባተ ትባላለች ። ወጣቷ አዲስ አበባ ልደታ ቤተክርስቲያን ጀርባ ነበር ይችን ምድር የተቀላቀለቻት። በ1980 ምድርን የረገጠችው ወጣት የመጀመሪያ ደረጃና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቷን በበቀለ ወያ እና ተስፋ ኮኮብ ትምህርት ቤት ቆይታ አድርጋለች።
ወጣቷ ከአፏ መነጠል የሚከብዳትን እናቷን የጥበብ መምህሬ እያለች ትጠራለች ። ህፃን ሆኗ እናቷ በአለላ የምትሰራቸውን ስፌቶች እየተመለከተች ያደገችው ይች ልጅ አምስትና ሰድስተኛ ክፍል ስትደርስ ለገና ስጦታ የሚሆኑ አበቦችን በመስራት እጇን ያፍታታች መሆኗን ትናገራለች። በስጦታ የተጀመረው የሥዕል ስራ በአቢሲኒያ የሥነ ጥበብ ትምህርት ቤት በመቀላቀል መሰረታዊ የስዕል እውቀቶችን ጨብጣለች። በተጨማሪ የንግድ ሥራ ትምህርት የወሰደችው ወጣት ሰው በተፈጥሮ የተሰጠውን ፀጋ በተገቢው መልኩ ሊጠቀምበት፣ በሚፈልገው ልክ መኖር የሚገባው መሆኑን ታምናለች።
ይህች ወጣት መንታ እህት ያላት ሲሆን በኢንቴሪየር ዲዛይን በፎቶግራፍ ሥራ መሰማራቷን ትናገራለች። ታዲያ የዮርዳኖስ ቤተሰብ ለጥበብ የተጠራ፤ ጥበብን በተገቢው መልኩ መጠቀምን የሚያውቅ ቤተሰብ ቢባል ያንስበት ይሆን?
ዮርዳኖስ ሥራዎቿን በጣም አሳድጋ የአገር ገፅታን የሚያሳይ በማንነት ላይ የተመሰረተ ስዕል ለመስራት የቻለችው በልጅነቷ መንትዮችን የሚረዳ አንድ የውጭ ግብረ ሰናይ ድርጅት ውስጥ በበጎ ፈቃደኝነት የምታገለግል እንግሊዛዊት አስተማሪ ልጆቹ ባህላቸውን በማወቅ የራሳቸውን ነገር በመያዝ መውጣት እንዲችሉ በምታደርግላቸው ድጋፍ ነበር።
ይህች ሴት የኢትዮጵያን የአሳሳል ጥበብ ልጆቹ ይዘው ከዘመናዊ ጋር በማቀናጀት ፈር ቀዳጅ የሆነ እርዳታ ያደረገችላት ሲሆን ብዙ ሰዎች ሊወዱት የሚችሉ ለገበያ የሚሆኑ አይነት ሥራዎችን ቅድሚያ በመስጠት የምትሰራ መሆኑን ትናገራለች።
ዮርዳኖስ ሥራዎቿን በሸክላ ላይ በእንጨት በሸራ (canvas) በመስታወት እናም በተጨማሪ ግድግዳዎች ላይም ትስላለች ። ይህም ሲባል የተፈጥሮ ቅርፅ ያላቸው እንጨቶችን ከአጣና ተራ አካባቢ ለሥራ የማይሆኑ ለማገዶ ተብለው የተተው እንጨቶችን በማንሳት ለሥራ የምትጠቀመባቸው መሆኑን ትናገራለች። ̋እንጨቶች ጎረባብጠው የተፈጥሮ ቅርፃቸውን ይዘው ስመለከት ምን አይነት ጥበብ ብጠቀም ይሄን አይፈለግም ተብሎ የተጣለ ወልጋዳ አሳምረዋለሁ የሚል ሀሳብ ውስጤ ይመጣል” የምትለው ዮርዳኖስ ይሄን አይፈለጌ የተባለ እንጨት በውብ ጥበብ አሳምራ መመልከት በጣም ታላቅ ደስታ የሚፈጥርላት መሆኑን ትገልፃለች።
ከዚህም በተጨማሪ የቤት ውስጥ ባህላዊ ቁሳቁሶች የእሷ የጥበብ አሻራ ያረፈበትን ሥራ ለመስራት ማለትም ወንበሮች ሳጥኖች ሌሎች የአናፂ እርዳታን የሚፈልጉ ሥራዎችን አናፂዎችን በመቅጠር የምታሰራው ይች ልጅ ከእናቷ በወረሰችው የቀለማት ጫወታ ውበትን አክላ ለገበያ ታቀርባቸዋለች። የዮርዳኖስ የአሳሳል ጥበበ ሙሉ በሙሉ ባህላዊ የሚባል አለመሆኑን ትናገራለች። ̋ለኔ ስእል ነፃነት የሚጠይቅ ነው። በፈለኩት ጊዜ ያለ ገደብ፣ ያለ ጥንቃቄ በነፃነት በቀለሞች መተንፈስ የምፈልገውን ያህል እንድተነፍስ ዘመናዊም ባህላዊም በተለይ ግን የአገር ስሜት ያለው የኢትዮጵያዊነትን መንፈስ የሚናገሩ አገርኛ እጅ ያረፈባቸው የአሳሳል ስልቶች የተሻለ ለነፍሴ ይቀርባሉ” ትለናለች።
ወጣቷ ዮርዲ አርትስ ኢትዮጵያ የሚባል ድርጅትአላት። በዚህ ድርጅት ውስጥ ዘመናዊ የእጅ ስራዎች ለሽያጭ ይቀርቡበታል። በእጅ የተሰሩ ባህላዊ የእጅ ሥራዎችን ከእናቷ እንደወረሰች የምትናገረው ወጣት ውስጧን እያሰደሰተ የምትሰራው ሥራ ለመኖሪያም እንዲሆናት የምትጥር መሆኗን ትናገራለች። የኪነ-ጥበብ ምርቶችን በቅንጦት እና ፋሽን በተመጣጠነ ልዩ ኢትዮጵያዊ ንክኪ ያሉዋቸውን ሥራዎች ትሰራ እንደነበር የምትናገረው ወጣት የእናቷ በልጅነቷ ይሰሩት የነበው የስፌት ሥራ ጥበብ በስዕሎቿ ላይ የራሱን አስተዋፅኦ እንዳደረገ ትናገራለች።
በወጣቷ ዮርዲ አርትስ ውስጥ እርካታ የሚያስገኙ የትም ያልታዩ ያልተለመዱ አይነት አስደናቂ የቤት እና የቢሮ እቃዎችን በማዘጋጀት ለገበያ ታቀርባለች ። ስዕሎቹ ሲታዩ የኢትዮጵያ ባህል እንዲሰማ የሚያደርጉ መሆኑን የምትናገረው ወጣት የግድግዳ ጌጣጌጦችን የጥበብ አሻራ ያለፉባቸውን ቁሳቁሶችን በመስራት የዚህ አይነት ጥበብ ፍቅር ያላቸው ሰዎችን ወደ የዮርዲ ጥበብን ጎራ እንዲሉ ትጋብዛለች፡፡ ውብና ውድ የሆኑ ዕቃዎችን በጣም በተመጣጣኝ ዋጋ እንሸጣለን የምትለውዮርዳኖስ በሷ እምነት ሰው መስራት በሚችለው ነገር ተጠቃሚ መሆን አለበት ብላ ታስባለች።
ወጣት ሰዓሊያን በተለይ ስዕል ሲጀመሩ ጥበብ ነፃነትን ይፈልጋል በሚል እሳቤ እንደ ሌላው ሰው በሕግና በሥርዓት መታሰር የመሰላቸውን የአኗኗር ዘዬ በመተው ራስን ወደ መጣል፤ ለየት ያሉ እስታይሎችን የመከተል ሁኔታ ያሳያሉ። ይህ ወጣቶቹ የሚቀበሉበት ሁኔታን ይወስነዋል። በአለባበስ ደረጃ የወጣቶች ነፃነት የጠበቀ ሲሆን፤ ወጣቶች የራሳቸው እምቅ እቅም እያላቸው በሱስ ውስጥ ራሳቸውን ሲገልፁ ይታያል። ያ ትክክል አይደለም የምትለው ወጣት ጥበብ በተፈጥሮ የተሰጠ ከመሆኑም በላይ ጥበብ በሌላ ተጨማሪ ነገር አይገለፅምና ሰው በነፃነት ይኖር ዘንድ ገደብ ባይጣልበትም ተጨማሪ ነገር ወደ ራሱ በማስገባት ሌላ አዛዥ ኃይል፤ ከስሜት ውጪ የሆነ ነገር መጨመር በኔ እምነት ትክክል አይደለም ትላለች።
”በርካታ ሰዓሊያን ስዕል እየሰሩ በድህነት ሲማቅቁ ይታያል። ይህን የሰራሁት ለስሜቴ ነው በሚል ሀሳብ ማለት ነው። በእኔ አቀባበል ለስሜቴ የሚሆን፤ መቼምልሸጣቸው የማልፈልጋቸውን ስራዎች ቢኖሩም ግን ፈጣሪ በለገሰኝ ጥበብ መኖር በምፈልገው ልክ መኖር አለብኝ” የሚል እምነት እንዳላት ትናገራለች ። ወጣቷ ለገበያ የሚሆኑ ሥራዎች መሥራት፤ የእኔ ሥራዎች በዓለም ዙሪያ መዳረስ እንዲችሉ ስለሚያደርግ እጅግ የሚያኮራ መሆኑን ነው የምትናገረው።
“እንደ በርካታ ሰዓሊያን ሙዴ አልመጣም የምልበት ሁኔታ የለም፤ ለኔ ሥራ ከሆነ ሥራ ነው፤ ሁሉንም ወድጄ ፈቅጄ በአዳዲስ ሀሳቦች ተሞልቼ ነው የምሰራው፤ የራሴ የምለው ሥራ ደግሞ የስሜቴ ነው የሚል እምነት አለኝ።”
በአገራችን ዘመናዊ አርት ማለትም እንደ አብስትራክት ያሉ ሥራዎችን ሰዓሊያኑ በስፋት ሲሰሩ ይታያል። በተለይም የኢትዮጵያ አርት በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚፈለገውን ያህል እውቅና ስለሌለው እሱን የማስተዋወቅ ሥራ ላይ መስራት ያስደስተኛል የምትለው ወጣት የኢትዮጵያዊነትን ቀለም ለአለም እያስተዋወቀች ትገኛለች።
“እኔ በልጅነቴ ግብረ ሰናይ ድርጅት ገጥሞኝ በበጎ ፈቃደኞች መማሬ እጅግ በጣም ያስደስተኛል” የምትለው ዮርዳኖስ ስለዚህም በክረምት ወቅት በህፃናት ማሳደጊያ ውስጥ ለሚገኙ የስዕል ፍቅር ላላቸው ልጆች ስዕልን በነፃ የማስተማር ስራ ትሰራለች ። በተረፈ ደግሞ አቅም ላላቸው ልጆች በክፍያ በግል የማስተማር ሥራዎችን ለገቢ ማግኛነት ምርጫዋ አድርጋለች።
ሰዓሊዎች በአብዛኛው በራሳቸው ፍላጎቶች ውስጥ ሆነው ለአዲስ ቤተሰብ ምስረታ ትኩረት አይሰጡም ስል ላነሳሁት ጥያቄ እንዲህ የሚል ምላሽ ሰጥታኛለች። ̋ እኔ በባህሪዬ ነፃነትን የምሻ ሰው ነኝ ። ተጨማሪ ሰው በህይወትሽ ውስጥ ሲመጣ የምትፈልጊውን ያህል ነፃነት አታገኚም፤ ለምሳሌ፡- ሌሊት ላይ መስራት ስፈልግ ተረበሽኩ የማይል፤ በሥራዎቼ ላይ እምነት፣ ፍላጎት፣ መረዳትም ያለው ሰው ማግኘት ከተቻለ የትዳር አጋር አስፈላጊ ነው፡፡” የምትለው ዮርዳኖስ ቤተሰብ መመስረት ለሴት ልጅ ከባድ እንደሆነም ትገነዘባለች። “እያንዳንዱን ኃላፊነት ሴቶች ላይ የሚጣሉ ስለሆነ ከጥበብ ስራ ጋር ፈታኝ ይሆናል። የጥበብ ሰው ጭንቅላቱ ነፃ መሆን ይኖርበታል። ሳይጨነቅ ሳይወጣጠር መሥራት ሰለሚኖርበት እጅግ በጣም የተለየ የጥበብ መረዳት ያለው አጋር ካልተገኘ ቤተሰብ ምስረታ ቢቀር ይሻላል” የሚል እምነትም እንዳላት ትናገራለች።
ሁልጊዜም የስዕል ሥራ ካለ ኤግዚቢሽኖች የግድ ናቸው የምትለው ወጣት በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ የተለያዩ አውደ ርዕዮችን ታዘጋጃለች። የመጀመሪያ ኤግዚቢሽን ያሳየችው ሀበሻ አርት ጋላሪ ሲሆን ይህ ከሌሎች ሰዓሊዎች ጋር በመጣመር የተዘጋጀ የመጀመሪያው ሥራዋን ይዛ ሕዝብ ፊት የቆመችበት ገጠመኝ ነበር። ከዛ አሊያንስ ኢትዮ ፍራንሲስ በተዘጋጀ አውደ ርእይ የስዕል ሥራዎችን ያሳየች ሲሆን ቀጥሎም ብቻዋን በርካታ አውደ ርእዮችን ማዘጋጀት ችላለች።
ከዚህም በተጨማሪ በቅርቡ በእስካይ ላይት ሆቴል የሴቶች አውደ ርእይ “ውሜን ኮፊ” በሚል ርእስ ስእሎችን ለጨረታ ማቅረቧን ታሰረዳለች ። በሌላ በኩል አገሯን ወክላ ቻይና በመሄድ የስዕል ሥራዎቿን ለማሳየት በቅታለች። ዮርዲ አርት በሚባል የራሷ መሸጫ ቦታዎች ወደ ውጭ አገራት እየተላኩ የሚሸጡ ሥራዎችን በራሷ በመስራት ለገበያ ታቀርባለች።
ድንቅ ጥበብ፤ ከንግድ ከህሎት ጋር በማጣመር በበቂ እየኖሩ ለስሜት መስራትን በአንድ አቀናጅታ የምትሰራው ወጣት ህይወትን በምቾትና በጥበብ አይን እየተመለከተች መኖር የዘወትር ህልሟ ነው።
አስመረት ብስራት
አዲስ ዘመን ሐምሌ 18/2013