ሰዓቱ ከጠዋቱ 2፡40 ላይ ይላል። ሙሽሪት ለሙሽራው ዝግጁ ሆና እየጠበቀች ሳለ ደብዳቤ ከእጇ ደረሰ ። የደብዳቤው መልእክት ሙሽራው መቅረቱን የሚገልጽ ነበር ። የባለጠጋ ሰው ልጅ ታሪክ በመሆኑ እንደ ባለጠጋነታቸው ለሰርጉ በሚገባ ተዘጋጅተዋል ። የጠዋቱ 2፡40 ሰዓት የመርዶ ሰዓት ሆነ ። ሙሽሪት በሃዘን ውስጥ ነች፤ አንዳች ነገር ማድረግ አለባት ። ማድረግ የወደደችው አንድ ነገር በቤቱ ውስጥ ያሉት ሰዓቶች በሙሉ 2፡40 ላይ እንዲቆሙ ማድረግ ነው ። ሰዓቶቹ ቆሙ ። በመቀጠል የሙሽርነት ልብሷን እንደለበሰች ለመኖር ወሰነች። ከሰዓት ቀናት፤ ከቀናት ወራት፤ ከወራት ዓመታትም ተቆጠሩ ። ሙሽሪት ለሰርጓ የለበሰችውን ለብሳ መኖሯን ቀጠለች ። የእርሷ ህይወት በሞላ በዚያች ክፉ ቀን 2፡40 ላይ እንድትቆም ሆነ ። ይህ ታሪክ ታላቁ ጥበቃ/Great Expectations የተሰኘ ታሪክ ነው ። ትላንትናውን እንጂ ዛሬዋንም ሆነ ነገን ከመኖር 2፡40 ላይ ቆሞ የመጠበቅ ህይወት ።
ይህን ታሪክ በመነሻነት አድርገን ትላንት ላይ ከመቆም ትላንትናን መጋፈጡ የተሻለ እንደሆነ እናንሳ። በተለይም ደግሞ በአስተዳደጋችን ውስጥ ስላለፈ ትላንት።
ከትላንት ቤተሰብ
ዛሬ ላይ እንደግለሰብ በመቆማችን ውስጥ ቤተሰባችን ያለው ድርሻ የበረከተ ነው ። ከአንድ ትውልድ ወደሌላኛው ትውልድ የሚሸጋገር ተመሳሳይ ነገር እናስተውል ይሆን? ዛሬ በምንኖረው ህይወት ውስጥ የትላንት ቤተሰብ አሻራ ይታየን ይሆን?
ለጥያቄዎች ምላሽ ከመስጠታችን በፊት በቅድሚያ ከራሳችን ጋር መሆንን ይጠይቃል። ከራሳችን ጋር ሆነን ነገሮችን መመርመር፤ ማስተካከል የሚገባንን ነገር ለማስተካከል እርምጃን መራመድ ። ትላንትን መመርመር በተለይም ከቤተሰብ የወሰድነው ነገር ላይ መስራት ትኩረት ያልተሰጠው ሆኖ ይታያል። ትላንትን ለመመርመር የሚፈልገው አቅም አለ፤ ከራስ ጋር የመሆን አቅም ። ከራስ ጋር በመሆን የሆነውን ሁሉ ለትምህርት ማድረግ የምንችልበትን እድል እናገኛለን። ከቤተሰብ ትላንት ውስጥ ደስ የሚያሰኝ በረከት እንዲሁም የማያስፈልገንን ሸክም ተሸክመን ይሆናል ። ወደ ትላንት በመመልከት ከራስ ጋር ለመሆን በመፍቀድ ውስጥ ውስጣዊ ሰውነታችን ውስጥ የሚሰማንን ድምጽ አዳምጠን ወደ ነጋ መሸጋገር የሌለበትን ልንለይ እንችላለን።
እያንዳንዱ ቤተሰብ ከሌላው ቤተሰብ የሚለይበት የራሱ የሆነ መለያ አለው። ቤተሰቡ የሚመራበት መርህ፤ ነገሮችን የሚመለከትበት መንገድ፤ እርስበርስ ያለ ግንኙነት ወዘተ የቤተሰቡን መልክ ይወስናል።
የቢቨር–ስርዓት ሞዴል/The Beaver System Model/
ቤተሰባችንን ለመረዳት የሚረዳን ቤቨር-ሥርዓት የተሰኘ ሞዴል አለ ። ቤተሰቦችን በአምስት የጤና ደረጃ ውስጥ እንደሚታዩ የሚያስረዳ ሞዴል ነው ። ከከፍተኛ ጤና መታወክ ወደ ጤናማነት በሚሄድ ቅደም ተከተል የተደራጀ ነው ።
ደረጃ አምስት፡– በህመም ውስጥ ያለ ቤተሰብ
በጣም የተረበሸ ቤተሰብ ማለት ነው ። እውነተኛ የሆነው አመራር የሌለው፤ ቀውስ የሞላበት፣ ያልተረጋጋ፣ ግራ መጋባት ውስጥ ያለ እንዲሁም ነውጥ መገለጫው የሆነ ቤተሰብ ነው ። ግጭትን በአግባቡ ለይቶ መፍታት የማይታሰብበት የቤተሰብ አይነት ነው ። ነገሮችን በግልጽነት መመልከት የማይቻልበት አይነትም ቤተሰብ ነው ።
ደረጃ አራት፡– በድንበር ውስጥ የሚኖር ቤተሰብ
ሚዛን የጎደለው አምባገነናዊ አመራር ያለበት ቤተሰብ ነው ። እንደ ደረጃ አምስት በከፍተኛ ግርግር ውስጥ የሚኖር ቤተሰብ ባይሆንም አምባገነናዊ በሆኑ ሕጎች ተወጥሮ የሚኖር ነው ። ሕጎቹም ጥቁርና ነጭ የሆኑ ሕጎች ናቸው ። ግትርነት ያለበት አስተሳሰብ፣ ስሜት እና ሁሉም የቤተሰቡ አባላት ሊተገብሩት የተገባ የህይወት አካሄድን የሚከተል ቤተሰብ ነው ። ግለሰቦች እኔ በዚህ ሀሳብ መስማማት አልችልም ብለው ሃሳባቸውን መግለጽ የማይችሉበት አይነትም ነው ። እጅግ ጥብቅ በሆነ ድንበር ውስጥ ታጥሮ የሚኖር ቤተሰብ ።
ደረጃ ሦስት፡– መመሪያ ተኮር ቤተሰብ
ይህ ቤተሰብ በቀውጢ ውስጥ ያለም እንዲሁም አምባገነናዊም አይደለም ። ከአራተኛው ደረጃ አንጻር ሲታይ በአንጻራዊነት ጤናማ ሆኖ ሊታይ የሚችልም ነው ። የቤተሰቡ አባል የተወደደ መሆኑ የሚገባው እንዲሁም ስለራሱም ጥሩ ስሜት እንዲሰማው የሚያደርግ ከባቢ ያለበት ሁኔታ የተፈጠረለት ቤተሰብ ነው፤ ነገርግን ይህ የሚሆነው የተነገሩ ወይንም ያልተነገሩ የቤተሰቡን መመሪያዎች በመተግበር ውስጥ ነው ። ቤተሰባዊ መመሪያዎች በመካከል ባለ መዋደድ በኩል የሚፈጸም ነው። የምትወደኝ ከሆነ የእኔ ፍላጎት እንደሆኑ የምታስባቸውን መመሪያዎች መፈጸም አለብህ የሚል አይነት ቤተሰብ ነው። የማይታየው መዳኛ ሥርዓቱ የሥርዓቱ መመሪያዎች እንጂ የግለሰቡ አስፈላጊነት አይደለም ። የተወሰነ ደረጃ የዛቻና ማስፈራራት መንፈስ የሚንጸባረቅበትም ነው ።
ደረጃ ሁለት እና አንድ፡- ተመጣጣኝ/the adequate እና ልከኛ/the optimal ቤተሰብ
በእኒህ ቤተሰቦች ውስጥ የሚኖሩ አባላት አንዳቸው አንዳቸውን የሚንከባከቡ፤ መልካም ስሜት ያላቸው፤ በመካከላቸው ጤናማ ግንኙነት ያለበት ነው ። በወላጆች አርአያነት የሚሆን መልካም ስሜት፣ መተማመን ወደ ሌሎች የቤተሰብ አባላትም ተዛምቶ በአስቸጋሪ እና በግጭት ወቅት ሳይቀር በብርታት እንዲቆሙ የሚያደርጋቸው እሴቶቹ የሞሉት ቤተሰብ ነው ። በደረጃ ሁለት እና በደረጃ አንድ መካከል ያለውን ልዩነት በቀላሉ የሚገልጸው አንድ ቃል ነው እርሱም ቤተሰባዊ ደስታ ነው። የደረጃ አንድ ቤተሰብ አባላት አንዳቸው ለአንዳቸው ደስታ ምክንያት ሆነው የሚገኙ ናቸው ።
አምስቱን ምድቦች ተመልክተን እኔ ያደኩበትን ቤተሰብ ከአምስቱ ምድቦች የትኛው ምድብ በአግባቡ ይገልጸዋል? የእኔ ቤተሰብ ዛሬም ድረስ ተጽእኖ ያሳደረብኝስ በምን ጉዳይ ነው?ብለን ጠይቅ ።
ለጥያቄው መልስ በምናፈላልግበት ጊዜ ቤተሰባችን ውስጥ የሚተገበረው አስርቱ ትእዛዛት ይመጡልናል ።
የቤተሰብ አስርቱ ትእዛዛት
ብዙ ጊዜ የቤተሰቦቻችን በህይወታችን ውስጥ ያላቸውን አሻራ አሳንሰን እናየዋለን ። በእርግጥ የቤተሰቦቻችንን ተጽእኖ በህይወታችን ውስጥ የምናየው በእድሜያችን እየገፋን ስንሄድ ነው ። እያንዳንዱ የቤተሰባችን አባል ወይንም አብረናቸው ያደግን ሰዎች በሕይወታችን ውስጥ አሻራ አላቸው ። ባህል፣ ሚዲያ እንዲሁም ነገሮችን የምንተረጉመበት መንገድ በህይወታችን ላይ አሻራ እንዳላቸው ማለት ነው ። ይህ አይነቱ ባህሪያዊ መልክን ትእዛዛት ብለን ልናያቸው እንችላለን ። የቀን ተቀን እንቅስቃሴያችንን የሚወስኑ ባህሪያት ስለሚሆኑ እንደ ትእዛዝ እንያቸው ። አንዳንዶቹ የሚነገሩና ግልጽ ናቸው ። ነገርግን አብዛኛዎቹ የማይነገሩ ናቸው ። ትእዛዙትም በውስጣችን በአእምሮችን ውስጥ የሚታተተሙ ናቸው ።
የሚቀጥሉትን አስርቱን ትእዛዛት እንመልከት። በቤተሰብ ውስጥ የምንማራቸው ሳይጻፉ ከሚተገቡት የምንቀዳቸው ትእዛዛት ናቸው ። ስለ ገንዘብ፣ ግጭት፣ ግብረስጋ ግንኙነት፣ ሃዘን፣ ቁጣ፣ ቤተሰብ፣ ግንኙነት፣ የተለያዩ ባህሎች፣ ስኬት እና ስሜት የተደነገጉ ትእዛዛት ።
1. ገንዘብ – ዛሬ ላይ ስለገንዘብ ያለን መረዳትን ስንፈትሽ የሚሰጠን ትርጉም ምን ይመስላል? ገንዘብ ደህንነት እንዲሰማን የሚያደርግ የተሻለው መሳሪያ እንደሆነ እንረዳ ይሆን ? ወይንስ ብዙ ገንዘብ በኖረን መጠን የበለጠ ተፈላጊ መሆናችንን የሚያረጋግጥ የሚመስለን ? የመከናወን መቻል ማረጋገጫ ገንዘብ እንደሆነ ትእዛዝ ያደረገ ሰው ይህን ትእዛዝ ይዞት ይጓዛል።
2. ግጭት – ግጭት አፈታት ላይ በቤተሰብ ህይወት ውስጥ ያልተጻፈ ትእዛዝ ይተገበራል ። በየትኛውም ዋጋ ግጭትን አስወግድ፣ሰዎች በአንተ እንዲቆጡ አታድርግ፣ ጩኸት የበዛበት ቀጣይነት ያለበት ትግል የተለመደ ነው ወዘተ የሚሉ ግጭት ተኮር የሆኑ ትእዛዛት።
3. ግብረስጋ ግንኙነት – ሴክስ በግልጽነት ሊወራ አይገባውም፣ወንድ እንደፈለገው መሆን ይችላል፤ ሴት ደግሞ ጭምት ትሁን ወዘተ የሚሉ እንዲሁ የቤተሰብ ያልተጻፈ አስርቱ ትእዛዛት ሆነው የሚነበቡ ናቸው ።
4. ሃዘን – ሃዘን የደካማነት ምልክት ነው፣ ድብታ ውስጥ መግባት አልተፈቀደልህም እና ሃዘንን በፍጥነት መተውና ወደፊት መሄድ አለብህ የሚሉት ትእዛዛት ደግሞ ለእውነተኛ ውስጣዊ ስሜታችን ጆሮ ዳባልበስ ብለን ታምቀን እንድንኖር የሚያደርጉ ትእዛዛት ናቸው።
5. ቁጣን መግለጥ – ቁጣ አደገኛና መጥፎም ነው፣ ነጥብ ለማስቆጠር በቁጣ ጊዜ መፈንዳት ያለበትን አፈንዳው ፣አሽሙር ቁጣን ለማስተንፈስ ተቀባይነት ያለው መንገድ ነው ወዘተ የሚሉ አይነት ትእዛዛት ተደንግገዋል።
6. ቤተሰብ – ቤተሰቦችህ ለዋሉልህ ሁሉ እዳ አለብህ፣የቤተሰብህን ገመና ወደ አደባባይ አታውጣ፣ ለቤተሰብና ለባህል ያለህ ሥፍራ ከሁሉም ነገር በፊት ይቀድማል ወዘተ ደግሞ ሌሎች በቀጥታ ቤተሰብን የተመለከቱ ትእዛዛት ናቸው፣
7. ግንኙነት – ሰዎችን አትመን፤ ይጥሉሃልና፤ ማንም ሰው ከእዚህ በኋላ ሊጎዳኝ አይችልም፤ ተጋላጭነትን አታሳይ
8. ለተለያዩ ባህሎች ያለን ምልከታ – ከሚወዱህ ሰዎች ጋር ብቻ የቅርብ ጓደኛ ሁን፣ ከሌላ ብሔር ወይንም ባህል አታግባ፣አንዳንድ ባህሎች ወይንም ብሔሮች እንደ እኔ ጥሩ አይደሉም ወዘተ
9. ስኬት – ስኬት ማለት ምርጥ ት/ቤት ውስጥ መግባት ነው፣ስኬት ብዙ ገንዘብ መስራት መቻል ነው፣ ስኬት ማግባትና ልጆችን መውለድም ነው ወዘተ
10. ስሜት – የሆኑ አይነት ስሜቶች ሊኖሩህ አይገባም ወዘተ
ከዚህ በላይ የቀረቡት ትእዛዛት በቀጥታ የአንባቢው ቤተሰብ መገለጫ ላይሆኑ ይችላሉ። ነገርግን የራሳችን ቤተሰብ ውስጥ ያሉትን ትእዛዛት እንድንለይ ግን እገዛ ያደርግልናል።
በቤተሰብ አስርቱ ትእዛዛት ውስጥ የተቀረጸ አንድ ሰው ከቤተሰቡ ተለይቶ ህይወትን በራሱ በሚመራበት ወቅትም ያለፈው የቤተሰቡ ጉዞ የሚይዘው ይሆናል። በአዎንታዊም ሆነ በአሉታዊ መንገድ ከቤተሰቡ የሚቀበለው ዛሬውን የሚነካው በመሆኑ ወደ ትላንት እንዲመለከት ያስገድደዋል።
ወደ ትላንት መመልከት በትላንት ላይ ለመቆም ሰዓቱን 2፡40 አድርጎ ህይወትን በሙሉ አቁሞ በመገኘት ሳይሆን ዛሬንና ነገን ለማበጀት በሚሰራ መንገድ መሆን አለበት።
ቤተሰባችን በዛሬ ህይወታችን ላይ ያለውን ተጽእኖ ለመመርመር ስንፈቅድ በተሻለ ዛሬያችንንም ሆነ ማዳን እንችላለን ። ይህ እንዲሆን የቤተሰብን ኃይል መረዳት ይገባናል። ቤተሰባችን ከአምስቱ ደረጃዎች በየትኛውም ቢገኝ የራሱ አስርቱ ትእዛዛቱ ምንም ይሁን ምን በእያንዳንዱ የቤተሰብ አባል ላይ ተጽእኖ እንዳለው እንረዳለን።
የቤተሰብ ሃይል
መጽሐፍ ቅዱስ ቤተሰብ ሲል የሚያስበው ከሦስት እስከ አራት ዙር ያሉ የቤተሰብ ትውልዶችን ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም ቤተሰብ የሚይዘው ወንድሞች፣ እህቶች፣ አጎቶች፣ አክስቶች፣ አያቶች፣ ቅድመ-አያቶች፣ ሌሎችም ምናልባትም ወደ ኋላ ሁለት መቶ ዓመታትንም ጭምር የሚሄድ ይሆናል ።
በምድር ላይ ስንኖር ተጽእኖ ማሳደር አቅም ካላቸው ውጫዊ አካላት መካከል ዋናው ቤተሰብ ነው። በወጣትነታቸው ቤተሰባቸውን ለቀው በመውጣት ራሳቸውን ከቤተሰባቸው ታሪክ ወጣቶች ሳይቀሩ ከቤተሰቡ ስለራቁ ብቻ ከቤተሰቡ ተያይዞ ከሚመጣው ተጽእኖ አያመልጡም ።
በአንድ ትውልድ ላይ የሚከሰት ነገር በሚቀጥለው ትውልድም ይቀጥላል። በአንድ ትውልድ የሚወሰዱ ውሳኔዎች እና የሚከናወኑ ድርጊቶች የሚከተሉትንም ይነካል።
በዚህ ምክንያት ከአንድ ትውልድ ወደሌላ ትውልድ ባለው ሂደት ውስጥ ፍቺ፣ የአልኮል ጥገኝነት፣ የሱሰኝነት ባህሪ፣ አግባብ ያልሆነ ጾታዊ ግንኙነት ህይወት፣ ደካማ ጋብቻ፣ ሥልጣንን አለማክበር፣ ከሚጠበቀው ውጭ የሆነ እርግዝና፣ የተረጋጋ ህይወት የመምራት አቅም ማጣት ወዘተ እኒህ ባህሪያቶች ከትውልድ ትውልድ ሲተላለፉ ይስተዋላል። ሳይንቲስቶች እና ሶሾሎጂስቶች ለዓመታት እየተከራከሩበት ያለው ጉዳይ ይህ የሚሆነው በተፈጥሮ/nature (i.e. DNA) ወይንስ በከባቢ ሁኔታ ተጽእኖ/nurture (our environment) ወይንስ በሁለቱም የሚለው ላይ ነው።
እኛ ሳናውቅ ከትላንት ተሸጋግሮ የሚመጣ መስመር በዛሬ ግንኙነታችን ውስጥ ተጽእኖ ሊኖረው ይችላል። ምናልባት የአንድ ግለሰብ የራሱ ሁኔታ ሊመስለን ይችላል፤ በፍጹም ግን አይደለም። ከሦስት እስከ አራት ትውልድ የተሸጋገረ ሊሆን ይችላል።
አሳዛኙ ነገር የታሪካችንን አሉታዊ ተጽእኖ መሻር ወይንም መደምሰስ አለመቻላችን ነው ። የቤተሰባችን ያለፈው ታሪክ በውስጣችን ይኖራል፤ በተለይም ለመቅበር በሚሞክሩት ውስጥ። የምንከፍለው ዋጋ ከፍተኛ ነው። እውነቱ ብቻ አርነት ያወጣናልና ትላንትን ተመልክቶ ስለዛሬና ነገ ተብሎ ማከም ተገቢ ነው። ከቤተሰብ ትላንት ያልነው ለዚሁ ነው ።
በአገልጋይ ዮናታን አክሊሉ
አዲስ ዘመን ሐምሌ 17/2013