ሞገስ መኮንን ይባላል። ትውልዱና እድገቱ አማራ ክልል ዋግኽምራ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞን፣ ዳና ወረዳ ልዩ ስሙ አምደ ወርቅ ከተማ ነው። ለቤተሰቡ አምስተኛ ልጅ ሲሆን ወንድ እርሱ ብቻ ነው። በልጅነቱ ምንም አይነት የአካል ጉዳት አልነበረበትም። እንደማንኛውም የአካባቢው ልጆች ሙሉ ጤናማ ሆኖ ያደገበትን መንደር አቀበትና ቁልቁለት ወጥቶ ወርዷል። በለመለመው መስክ ፈንጥዟል። ወንዝ እየወረደ ከጓደኞቹ ጋር ውሃ ተራጭቷል። ማገዶ በመስበር፣ ከብት በመጠበቅ ወላጆቹን እያገዘ አድጓል። በዚያን የልጅነት እድሜው በሬ ጠምዶ ከማረስ ውጭ ያልሰራው ስራ እንደሌለ ይናገራል።
ሞገስ የ11 ዓመት ልጅ እያለ የገጠመው የጤና እክል የአካል ጉዳተኛ አድርጎታል። ጉዳዩ እንዲህ ነው፤ ህክምና ለማግኘት በአካባቢው ወዳለ አንድ ጤና ጣቢያ ይሄዳል። ለህመሙ ማስታገሻ የተወጋው መርፌ ደምስሩን ይነካውና እግሩ ይሸማቀቃል። ህመሙ ከቀን ወደ ቀን እየተባባሰበት ይሄዳል፤ ወገቡ መብረክረክ እግሮቹም አለመታዘዝ ይጀምራሉ። እንደውም መርፌ የተወጋበት የቀኝ እግሩ እየሰለለ ይሄዳል። ያ መንደሩን እንደልቡ ሲያካልል የሚውለው ብላቴና እንደቀልድ የአልጋ ቁራኛ ይሆናል። በሰው ድጋፍ መነሳትና መቀመጥ፤ በሰው ድጋፍ መራመድ ይጀምራል። ትምህርቱም ይቋረጣል። በልጃቸው ድንገተኛ የጤና እክል ግራ የተጋቡት ቤተሰቦቹ አንዴ ወደ ህክምና አንዴም ወደ ጸበል እያመላለሱት ያስታምሙታል። ሞገስ ግን ሳይሻለው ይቀራል። እንደውም እቤት መዋል ይጀምራል።
ሞገስ እቤት መዋል በጀመረበት ጊዜ ምርኩዝ ይዞ ለመንቀሳቀስ ይጥራል። ቀስ እያለም ከቤቱ እልፍ ብሎ ሲጫወትበት ያደገውን መስክ አቀበትና ቁልቁለት እየወጣና እየወረደ ምርኩዝ ይዞ መራመድን ይለማመዳል። ልምምዱን ከጨረሰ በኋላ በልጅነቱ የሚያከናውናቸውን ተግባራት ለመፈጸም ይጣጣር ጀመር። ከሩጫና ዝላይ ውጭ ያሉ ተግባራትን ሁሉ መፈጸም መቻሉ ተስፋ ይሰጠውና ያቋረጠውንም ትምህርት ይጀምራል። እንደድሮው አይሁን እንጂ ትምህርት ቤት ሲሄድ ምርኩዙን እንደያዘ ከጓደኞቹ ጋር ቀለል ያሉ ጨዋታዎችን ይጫወታል። ከትምህርት ቤት ሲመለስ ከብቶችን ያግዳል፤ አረም ያርማል።
ሞገስ ያጋጠመው የአካል ጉዳት እንደጓደኞቹ በነጻነት ሊያንቀሳቅሰው ባለመቻሉ ይሠማው ነበር። በተለይም ትምህርት ቤት ሲሄድ በስፖርት ክፍለ ጊዜ ተማሪዎች እንደልባቸው ሲሮጡና ሲገለባበጡ እርሱ ያንን ማድረግ ባለመቻሉ ያዝን ነበር። ሞገስ በትምህርቱ ጎበዝ ተማሪ እንደነበር ይገልጻል። የስፖርት መምህሩ በነጻ የሚሰጠው ማርክ ያናድደው ነበር። ከዚያ ሁሉ ተማሪ መሃል እርሱ ብቻ አካል ጉዳተኛ መሆኑና የሰው ዓይን ማረፊያ መሆኑ ጥሩ ስሜት አይፈጥርበትም ነበር። በዚህ የተነሳ ከትውልድ ሀገሩና ከሚያውቀው ማህበረሰብ ፊት እርቆ መኖርን ይመኝ ነበር። አባቱ በልጅነቱ ስለሞቱበት እናቱም በግብርና የሚተዳደሩና ኑሯቸው ከእጅ ወደ አፍ መሆኑ በተወለደበት መንደር የመኖር ህልሙን ያደበዝዝበታል። በገጠር አካል ጉዳተኛ ሆኖ መኖር ተስፋ አይሰጥም፤ መኖር የሚቻለው ወላጆች እስካሉ ድረስ ነው፣ ያለበለዚያ ግን ለልመና መዳረግ ነው የሚለው ወጣቱ የገጠር ህይወቱን ትቶ ወደ ከተማ ለመሄድ ያስባል። እንደ ክራንችና ሌሎች ድጋፎችን ከበጎ አድራጎት ድርጅቶች በማግኘት ትምህርቱን ተምሮ የነገውን ህይወቱን ለማለምለም በማሰብ ልክ የስድስተኛ ክፍል ትምህርቱን እንደጨረሰ ወደ አዲስ አበባ ይመጣል።
አዲስ አበባ እንደመጣ በሚያውቁት የሀገሩ ሰዎች ቤት ያርፍና እርዳታ የሚያደርጉለትን በጎ አድራጎት ድርጅቶች ያፈላልጋል። ከዚያም ቲቻይር የአካል ጉዳተኞች ሰርቪስ ወደ ሚባል ድርጅት በመሄድ አርቲፊሻል እግር ለማሰራት ደጅ መጥናት ይጀምራል። ነገር ግን እስከ ሃምሳ ሺህ ብር ያስፈልግ ስለነበር ያሰበው ሳይሳካ ይቀራል።
ሞገስ አንድ ድርጅት ባደረገለት ድጋፍ የእንጨት በትሩን ትቶ በክራንች መሄድ ይጀምራል። የአዲስ አበባን ኑሮ መቋቋም ያልቻለው ታዳጊ በፍጥነት ወደ ስራ ይገባል። ከአከፋፋዮች ላይ ጧፍና ሻማ እየተረከበ በመቸርቸር ትርፏን ለራሱ እያስቀረ የተረከበበትን ገንዘብ እየመለሰ አዲስ ህይወትን ይጀምራል። ቀን ቀን እየሰራ ማታ ማታ እየተማረ ስምንተኛ ክፍል ይደርሳል። አምስት ዓመት በጧፍ ንግድ ካሳለፈ በኋላ በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ወረዳ ስምንት ከመሰል ጓደኞቹ ጋር ተደራጅቶ የስራ ቦታ ይጠይቃል። መርካቶ አሁን እየሰራበት ባለው አብዶ በረንዳ አካባቢ አስፋልት ዳር ቦታ ተሰጥቶት እንደ ካልሲ፣ ቲሸርት፣ ቁምጣ፣ ሻርፕ፣ ፒጃማና የመሳሰሉ አልባሳትን መነገድ ይጀምራል።
ሞገስ ሁልጊዜ ማለዳ ከሚኖርበት ኮልፌ ቀራኒዮ /የሺ ደበሌ ሰፈር/ ታክሲ ተሳፍሮ ወደ መርካቶ ይገሰግሳል። ቀኑን ሙሉ ሲሸጥ ውሎ ማታ እቃውን እየከፈለ ከሚያሳድርበት ቤት አስገብቶ ወደ ቤቱ ይመለሳል። ወደ ቤቱ ሲሄድና ሲመጣ ለታክሲ አስር አስር ብር ያወጣል። በቀን ሃያ ብር ያወጣል ማለት ነው። ሞገስ እቃ ለሚያሳድርበት መጋዘን በወር አንድ ሺህ ብር ይከፍላል። ተከራይቶ ለሚኖርበት ቤት ደግሞ ሁለት ሺህ ብር ይከፍላል። እቃውን ለሚያስገቡለትና ለሚያወጡለት ወዛደሮችም በየቀኑ ከሃያ እስከ ሰላሳ ብር ይከፍላል። ሞገስ ነግዶ ያገኘውን ገንዘብ በዚህ መልክ ስለሚያወጣ እጁ ላይ የሚቀረው ትንሽ ገንዘብ ነው። በስራው ባህሪ ምክንያት ትምህርቱንም ለማቋረጥ ተገዷል፤ በዚህም ሁሌ ይቆጫል። እርሱ ያጣውን ትምህርት ታናናሾቹ እንዳያጡ እያለ የአቅሙን ይረዳቸዋል። እንደውም ታናሽ እህቱን ከሀገር ቤት አምጥቶ እያስተማራት ይገኛል። እርሷም ምግቡን በማዘጋጀትና ልብሱን በማጠብ ትረዳዋለች።
የንግድ ስራው አዋጭ ቢሆንም ወጪው ከአቅሙ በላይ ስለሆነበት ኑሮው ከእጅ ወደ አፍ እንደሆነ ይናገራል። ያም ሆኖ ባገኛት ገንዘብ እራሱንና እህቱን እያኖረ መሆኑ ያስደስተዋል። ከምንም በላይ ደግሞ የሰው እጅ አለማየቱ ያኮራዋል። አካል ጉዳተኞች ይቅሩና ሙሉ አካል ያላቸው ሰዎች ምጽዋት በሚጠይቁበት በዚህ ዘመን ሰርቶ ማደሩ እንደሚያረካው ይገልጻል።
ሞገስ ሸቀጦችን እያመጣ የሚሸጠው ከኮልፌ አጣና ተራና ከዱባይ ሰፈር ነው። እዚያ ድረስ ሄዶ ከአንዱ ቦታ አንዱ ቦታ እየተዟዟረ እቃ መግዛት አድካሚ እንደሆነ ይናገራል። በሌባ የተዘረፈበት መጥፎ አጋጣሚ እንዳለም አጫውቶኛል። አንድ ቀን ሞገስ እዚያው ኮልፌ ግምቱ 12ሺህ ብር የሚሆን እቃ ገዝቶ ሰራተኛ በማሸከም ወደ ታክሲ መሳፈሪው ቦታ ይሄዳል። እቃ ተሸካሚው ከሌሎች ጓደኞቹ ጋር እየተመሳጠረ የስርቆት ስራ የሚሰራ ነበር። ሞገስ መጀመሪያ መረጃው አልነበረውም፤ እቃውን የተሸከምው ልጅ ከፊት ሞገስ ከኋላ ሆነው ይሄዳሉ። ድንገት ከየት መጡ የማይበሉ ሁለት ልጆች የሞገስን ክራንች በእግራቸው ይመቱትና ሞገስ ይወድቃል። ከወደቀበት እስኪነሳ ድረስ እቃውን የያዘው ሰው ፍጥነቱን ጨምሮ ከአይኑ ይሠወራል። በዚያን እለት በእጁ ያለችውን ገንዘብ አራግፎ ባዶ እጁን ወደ ቤቱ የገባበትን አጋጣሚ ሁሌም ያስታውሰዋል። ሌላም ጊዜ እንዲሁ ሙከራ ተደርጎበት መትረፉን ይናገራል።
ሞገስ የስራ ቦታው መጠለያ ስለሌለው ጸሐይና ዝናብ እየተፈራረቁበት እንደሚሰራ ይናገራል። በተለይም የክረምቱ ወቅት በስራው ላይ ከፍተኛ ጫና እንደሚያሳድርበትና የገበያውም ሁኔታ ቀዝቃዛ መሆኑን ይገልጻል። አንዳንድ ጊዜ ዣንጥላ እያየዘ ለመሸጥ ቢሞክርም የሰዎች እንቅስቃሴ ስለሚገታ ምንም ነገር ሳይሸጥ የሚውልበት ጊዜ ሊኖር እንደሚችል ይናገራል። ኮንቴነር ውስጥ የመስራት እድል ቢያገኝ ግን ከዚህ ሁሉ እንግልት እንደሚድን፤ ለእቃ ማስቀመጫ የሚያወጣውን ወጪም እንደሚያተርፍ ይገልጻል።
መርካቶ እርሱ በሚሰራበት አካባቢ የሰዎች እንቅስቃሴ ስለሚበዛ ክራንቹን ይዞ ወዲህ ወዲያ ለማለት እንደሚቸገር ይናገራል። በተለይም በዝናብ ወቅት አካባቢው ስለሚጨቀይ ክራንቹ እያንሸራተተው የወደቀባቸው ጊዜዎች ብዙ ናቸው። በአንድ ወቅት የቀኝ እጁ ክፉኛ ተጎድቶ ስራውን አቋረጦ ህክምና እስከመከታተል ደርሷል። አሁን ድረስ እጁን እንዳልተሻለው ይገልጻል።
ሞገስ አሁን የሚሰራበትን ቦታ ለማግኘት ሶስት ዓመት ያህል ውጣ ውረድ ማሳለፉን ይናራል። ከቀበሌ እስከ ክፍለ ከተማ፤ ከክፍለ ከተማ እስከ ከንቲባ ጽህፈት ቤት ተመላልሷል።
አካል ጉዳተኛ ሊደገፍ እንደሚገባው የሚገልጽ አሰራር ቢኖርም ተግባራዊ ሲደረግ አይታይም ይላል። ባለድርሻ አካላት ጥያቄዎችን ከመመለስ ይልቅ ቀጠሮ እየሰጡ ማመላለሱን እንደስልት ይጠቀሙበታል የሚለው ሞገስ ሊፍት በሌላቸው ህንጻዎች እነርሱን ለማግኘት አራተኛና አምስተኛ ፎቆ መውጣትና መውረድ አስቸጋሪ እንደሚሆንበት ይገልጣል። በዚህ የተነሳ በስራ መግቢያና መውጫ ሰዓት መሬት ላይ እየጠበቀ ለማናገር መገደዱን ይናገራል።
ሞገስ በአካል ጉዳተኛ ማህበር ስር ተደራጅቷል። የድጋፍ ደብዳቤዎችንም አስጽፏል። ነገር ግን ከጓደኞቹ ጋር በመሆን ብድር ቢጠይቅ እንኳ ምላሽ የሚሰጠው አካል አለማግኘቱን ይናገራል። ኢትዮጵያ አካል ጉዳተኝነትን አስመልክቶ የቀረቡ ዓለም አቀፍ ህጎችን ለማስፈጸም የተስማማች ቢሆንም መሬት ላይ ያለው እውነታ ግን በተቃራኒው ነው። እርሱና መሰሎቹ ግን በራሳቸው ጥረት ኑሯቸውን ለማሸነፍ እየታገሉ መሆናቸውን ያስረዳል።
ሞገስ እንደማንኛውም ሰው ትዳር ይዞ፣ ቤተሰብ መስርቶ የመኖር ህልም አለው። ግን የሚያገኘውን ገንዘብ በአብላጫው ለቤት ኪራይ ስለሚያውል ህልሙን እውን ለማድረግ እየከበደው እንዳለ ያሳውቃል። የድጋፍ ደብዳቤ አስጽፎ በርካታ ጊዜ የመኖሪያ ቤት ጥያቄ ቢያቀርብም ምላሽ የሚሰጠው አላገኘም። ዛሬ አቅም እያለው ሰርቶ እራሱን መለወጥ ባለመቻሉ ነገ የሰው ሸክም እንዳይሆን ስጋት ገብቶታል። ሞገስ መንግስትን ጨምሮ ጥረቱን የሚደግፉ ሰዎች እንደሚያስፈልጉት ይገልጻል።
ከልመና ሰርቶ መብላት የአእምሮ ሰላም እንደሚሰጥ የሚናገረው ወጣቱ ከዚህ ቀደም ለምኖ እንደማያውቅ ወደፊትም የፈለገ ነገር ቢቸገር ችግሩን በስራ እንጂ በልመና መሻገር እንደማይፈልግ ያስረዳል። ግን ደግሞ አካል ጉዳተኞች ሰርተው ለመኖር የሚያደርጉትን ጥረት ማገዝ ከባለድርሻ አካላት ይጠበቃል ይላል። ሞገስ አካል ጉዳተኛ ነኝ ብሎ የሰው እጅ ከመጠበቅ ይልቅ ኑሮውን ለማሸነፍ የሚያደርገውን ጥረት እያደነቅን፤ አይዞህ ባይ ረዳት እንዲገጥመው እየተመኘን እንሰናበተዋለን። በቀጣይ ሌላ ባለታሪክ ይዘን እስከምንገናኝ ቸር እንሰንብት።
ኢያሱ መሰለ
አዲስ ዘመን ሰኔ 12/2013