በተወዳጁ የስፖርት መድረክ እግር ኳስ በተጫዋቾች ላይ የዘረኝነት ጥቃት ከደጋፊዎችና ከሌሎች አካላት ሲሰነዘር ማየት አዲስ አይደለም፡፡ በተጫዋቾች ላይ የሚሰነዘሩ የዘረኝነት ጥቃቶች ተጫዋቾች ተወዳጁን ስፖርት እንዲጠሉት ከማድረግ ባሻገር ከስፖርቱ ራሳቸውን እስከ ማራቅ የደረሰ ተፅዕኖ እንደሚያሳድር በተደጋጋሚ ሲነገርም እውነት አይመስልም ነበር፡፡
በተጫዋቾች ላይ የሚደርሰው የዘረኝነት ጥቃት ከስፖርቱ ሜዳ ከመገለል ባለፈ ተፅዕኖው ሕይወትን እስከ ማጥፋት ድረስ የከፋ እንደሚሆንም ብዙዎች ጠርጥረው አይውቁም፡፡ ባሳለፍነው ሳምንት ከወደ ጣሊያን የተሰማው አስደንጋጭ ዜና ግን በተጫዋቾች ላይ የሚደርስ የዘረኝነት ጥቃት ተፅዕኖው እስከ ምን ድረስ እንደሚዘልቅ ለዓለም ሕዝብ ያሳየ ሆኖ አልፏል፡፡
ትውልደ ኢትዮጵያዊው የቀድሞ የኤሲ ሚላን ተጫዋች ባሳለፍነው ሳምንት በአሳዛኝ ሁኔታ ሕይወቱን ማጥፋቱ አሁንም ድረስ የበርካቶች መነጋገሪያ ሆኖ ቀጥሏል፡፡ በኢትዮጵያ የተወለደውና በታዳጊነቱ ኤሲ ሚላን አካዳሚን ተቀላቅሎ የነበረው ሰዒድ ቪሲን በ20 ዓመቱ ራሱን አጥፍቶ መገኘቱ ተዘግቧል።
እኤአ መስከረም ወር 2000 ላይ በኢትዮጵያ የተወለደው ሰዒድ በልጅነቱ በጣልያናዊያን ቤተሰቦች በማደጎነት ወደ አገሪቱ ካመራ በኋላ በ2014 የኤሲ ሚላን አካዳሚን ተቀላቅሎ ተጫውቷል፡፡ በቀጣይም ወደ ቤንቬንቶ አምርቶ ነበር። ሆኖም ከዘረኝነት ጋር በተያያዘ በሚደርሱበት ጥቃቶች ምክንያት በ2016 እግር ኳስ መጫወት አቁሞ አትሌቲኮ ቪታሊካ በተባለ አማተር ቡድን እየተጫወተ በአስተናጋጅነት ሕይወቱን ለመግፋት ተገዷል፡፡ ሆኖም በመስተንግዶ ሲሰራ ከደንበኞች የሚደርስበት የዘረኝነት ጥቃት ሥራውን እንዲተው አስገድዶታል። በመኖሪያ ቤቱ ሕይወቱ አልፎ የተገኘው ሰዒድ ራሱን ማጥፋቱ የተዘገበ ሲሆን፤ ኮሪዬሬ ዴላ ሴራ ደግሞ ወጣቱ ከመሞቱ በፊት ፅፎ ያስቀመጠውን መልዕክት ማግኘቱን ይፋ አድርጓል።
የሰዒድ መልዕክት ‹‹በየሄድኩበት ሁሉ ሰዎች በጥርጣሬ፣ በሥጋት እና በመጠየፍ እንደሚመለከቱኝ ይሰማኛል። እኔ እዚህ ተሰድጄ አልመጣሁም፤ በማደጎ ተወስጄ እንጂ። ልጅ እያለሁ በዙርያዬ ያሉ ሁሉ ይወዱኝ እንደነበር አስታውሳለሁ። በየሄድኩበት ቦታ ሁሉ ሰዎች በደስታ እና የአክብሮት ስሜት ያወሩኝ ነበር፣ አሁን ግን ያ ሁሉ ተቀይሯል›› የሚል ነበር። ‹‹ከኳስ ራሴን ካገለልኩ በኋላ ሥራ አግኝቼ ነበር። ሆኖም ሰዎች በተለይም በዕድሜ የገፉት በእኔ ለመስተናገድ ፍቃደኛ አልነበሩም›› ሲልም በመልእክቱ ያብራራል።
‹‹በርካታ ወጣት (ነጭ) ጣልያናዊያን በእኔ ምክንያት ሥራ ማግኘት እንዳልቻሉ በማሰብ ተጠያቂ ያደርጉኛል። በውስጤ የሆነ ነገር ተቀይሯል። ጥቁር በመሆኔ የማፈር እና ተሰዶ የመጣ ሰው መባልን የመፍራት ነገር። እኔን የማያውቁ ሰዎችን እንደነሱ (ነጭ እና ጣልያናዊ) መሆኔን ማሳመን እንዳለብኝ ይሰማኛል። እነሱን መምሰሌን ለማሳየት በጥቁሮች ላይ ያነጣጠሩ መጥፎ ቀልዶችን እቀልድ ነበር። ግን ይኼ ፍራቻ ነው›› ሲል በመልእክቱ የገለጸው ሰኢድ፣ ‹‹በሰዎች ዓይን ውስጥ የምመለከተውን ለስደተኞች ያለ ጥላቻን መፍራት። ሰዎች እንዲያዝኑልኝ አልፈልግም። ለራሴ ማስታወስ የምፈልገው ያሳለፍኩት አስቸጋሪ ጊዜ መሞትን በዚህ ስቃይ ውስጥ ከመቆየት የተሻለ ሆኖ ካገኙት ሰዎች ጋር ሲነፃፀር ከውቅያኖስ ጠብታ ውሀ የመጭለፍ ያህል ትንሽ መሆኑን ነው›› ይላል።
በወጣቱ ሞት ብዙሀኑ የጣልያን የእግር ኳስ ቤተሰቦች ሀዘናቸውን ገልጸዋል፡፡ የቀድሞ ክለቡ ኤሲ ሚላን፣ የከተማ ተቀናቃኙ ኢንተር ሚላን እንዲሁም የህይወቱ የመጨረሻ ጊዜያትን ለመዝናናት ይጫወትበት የነበረው አትሌቲኮ ቪታሊካ ሀዘናቸውን በይፋ ከገለፁት መካከል ይገኙበታል።
የቀድሞ የኤሲ ሚላን ወጣት ቡድን አጋሩ እና በአዳሪ ትምህርት ቤት ጓደኛው የነበረው ጂያንሉዊጂ ዶናሩማም በቪሲን ሞት ሀዘኑን የገለፀ ሌላው ተጫዋች ነው። ‹‹ጓደኛዬ ነበር። ፈገግታውን በፍፁም ልረሳው አልችልም›› ሲል የኤሲ ሚላን እና ጣልያን ብሔራዊ ቡድን ግብ ጠባቂ ተናግሯል።
በዘረኝነት ጥቃት ስሟ በክፉ በምትነሳው ጣልያን ትልልቅ ስም ካላቸው ማርዮ ባሎቴሊ እና ኬቭን ፕሪስ ቦአቴንግ እስከ ዝቅተኛ ደረጃ የሚኖሩ ስደተኛ እና በማደጎ የተወሰዱ ግለሰቦች ድረስ የዘረኝነት ጥቃት ሲደርስባቸው ቆይቷል። በቅርቡ እንኳ በጣልያን ለአስር ዓመታት የኖረችው አጊቱ ጉደታ የተባለች ኢትዮጵያዊት በደረሰባት ጥቃት መገደሏ ይታወሳል።
የዘረኝት ጥቃቶች፣ ዘለፋዎችና መዘዛቸው ዛሬ…ዛሬ በመላው ዓለም በስፖርቱ ላይ ተጽዕኗቸው ከመቼውም ጊዜ በላይ ጎልቶ እየታየ ነው፡፡ በተለይ በአለማችን እጅግ ተወዳጅ የሆነው እግር ኳስ፣ በተለያዩ ሊጎች ከጥቁር ተጫዋቾች መበራከት እና ተጽዕኖ ፈጣሪነት ጋር ተያይዞ ዘረኝነትም በዚያው ልክ እያየለ መጥቷል፡፡ የተወዳጁ ስፖርት አስቀያሚ ገጽታ – ዘረኝነት – በ2018/19 የውድድር ዓመት ብቻ በእንግሊዝ ወደ 47 በመቶ ከፍ ማለቱን የዩኬ ንግስት የህግ ጉዳዮች ሚኒስቴር ዲፓርትመንት ‘ሆም ኦፊስ’ ይፋ ያደረገው ጥናት ያሳያል፡፡ ከዓመት በፊት በተካሄዱ ጨዋታዎች ከዘረኝነት ጋር የተያያዙ የጥላቻ ወንጀሎች ሪፖርት ቁጥር ከ131 ወደ 193 ከፍ ብሏል፡፡
በርግጥ አገራት በማህበራዊና ፖለቲካዊ ቀውስ እየተናጡ በሚገኙበት በዚህ ወቅት የእግር ኳስ ዘረኝነት እየጨመረ መምጣት ብዙም የሚደንቅ ክስተት ነው ተብሎ አይታመንም፡፡ የእንግሊዝን የብሬግዚት ጉዳይ እና በየጊዜው እየተቀየረ የመጣውን የአሜሪካ ፖለቲካ እንኳን ለአብነት ብንመለከት ዘርና ብሔርን የተመለከቱ ክርክሮች ማዕከላቸው እየሆነ መምጣቱ ተጽዕኖው አድማሱን እያሰፋ ለመምጣቱ ማሳያ ነው፡፡ ከዘረኝነቱ ጋር ተያይዞ የእግር ኳስ ሜዳዎች ገጽታም ከወትሮው እየተቀየረ መጥቷል፡፡ በየጨዋታዎች የሚመደቡ ፖሊሶች ቁጥር በከፍተኛ መጠን እየጨመረ መምጣቱን ጥናቱ ያሳያል፡፡ በአንዳንድ ጨዋታዎች ለ50 ደጋፊ አንድ ፖሊስ እስከ መመደብም ተደርሷል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን በስታዲየሞች ላይ መጠቀምም ከተጀመረ ቆይቷል።
አሁን…አሁን ደግሞ የዘረኝነት ጥቃቶችን በማህበራዊ ሚዲያ ድረ ገጾች መልቀቅም እየተለመደ እንደመጣ ነው የ‘ሆም ኦፊስ’ ጥናት የሚያመለክተው፡፡ ለዚህም ፈረንሣዊው አማካይ የማንቸስተር ዩናይትድ ተጫዋች ፖል ፖግባና ሌላኛው እንግሊዛዊ የቡድን አጋሩ ማርከስ ራሽፎርድ ክለቡ ውጤት ርቆት አጣብቂኝ ውስጥ በገባበት ወቅት ያገኟቸውን የፍጹም ቅጣት ምቶች በማምከናቸው ከራሱ ከክለቡ ደጋፊዎች በተለያዩ የማህበራዊ ሚዲያዎች የተሰነዘረባቸው ዘር ተኮር ዘለፋ ጥሩ ማሳያ ነው፡፡
በስታዲየሞች ደጋፊዎች በብዛት የሚያሰሟቸው የዘረኝነት ዘለፋዎች እና ጥቃቶች፣ ጨዋታዎች እስኪቋረጡ ያስገደዱባቸው ጊዜያት እና ስፍራዎች ጥቂት የሚባሉ አይደሉም፡፡ ያለፉትን ለታሪክ ትተናቸው በ18ኛው ሳምንት የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የታህሳስ 12 ቀን 2012 ዓ.ም የቶተንሃም እና የቼልሲን ጨዋታ ክስተትን ለአብነት እንመልከት። ቶተንሃም በገዛ ሜዳው 2 ለ 0 በተሸነፈበት በዚያ ጨዋታ ሁለተኛ አጋማሽ ከቼልሲው ተከላካይ አንቶኒዮ ሩዲገር ጋር በተያያዘ ደቡብ ኮሪያዊው ሰን ሄዉንግ ሚን በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጣ፡፡ የቶተንሃሙ አጥቂ የቀይ ካርድ ሰለባ የሆነው በምስል በታገዘ ዳኝነት (ቫር) ጭምር በሁለቱ ተጫዋቾች መካከል በነበረ ግጭት የጫማውን መርገጫ ማንሳቱ ከተረጋገጠ በኋላ ነበር፡፡
ይኼን ተከትሎ ብዙም ሳይቆይ ሩዲገር የቶተንሃም ደጋፊዎች ሰለባ ሆነ፡፡ በቆዳው ቀለም መጥቆር ብቻ ደጋፊዎቹ የዝንጀሮ ድምጽ እያሰሙ እረፍት ነሱት፡፡ ድርጊቱን የክለቡ አምበል ሴዛር አዝብሊኬታ ለዳኛው አሳወቀ፡፡ ደጋፊዎቹም ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ ሦስት ጊዜ ማስጠንቀቂያ ደርሷቸዋል፤ ምንም እንኳን መልሳቸው ጆሮ ዳባ ልበስ ቢሆንም፡፡
ይባስ ብለው የተለያዩ ቁሳቁሶች ሲወረውሩ ጨዋታው ለተወሰነ ጊዜ እንዲቋረጥ ተደረገ፡፡ ጨዋታው ካበቃ በኋላ ድርጊቱ በከፍተኛ ደረጃ አነጋጋሪ ሆነ፡፡ የአገሪቱ እግር ኳስ ማህበር፣ ፕሪሚየር ሊጉና ስፖርቱ የሚመለከታቸው ሁሉ ማጣራት መደረግ እንዳለበት እና ድርጊቱን የፈፀሙ እንደሚቀጡ ድምጻቸውን ከፍ አድርገው አሰሙ፡፡ ቶተንሀም ጉዳዩን በማጣራት ላይ እንደሚገኝ እና ውጤቱን ተከትሎ ጠንካራ ርምጃ እንደሚወስድ ቢያሳውቅም አሳማኝ ማስረጃ አላገኘሁም በሚል ጉዳዩ ተድበስብሶ ቆየ።
ይሁን እንጂ ብዙም ባልተለመደ መልኩ በጉዳዩ ላይ የዩናይትድ ኪንግደም መንግስትም ጣልቃ እንደሚገባ ማሳወቁ አይዘነጋም። በጨዋታዎች ላይ የሚከሰተውን እጅግ አፀያፊ የዘረኝነት ድርጊት ለመከላከል የስፖርቱ ባለስልጣናት አቅም ካነሳቸው መንግስት ጣልቃ በመግባት ርምጃ ለመውሰድ እንደሚገደድ በወቅቱ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ቃል አቀበይ ሳይቀሩ ተናግረዋል፡፡
በወቅቱ የቶተንሃም አሰልጣኝ የነበሩት ጆሴ ሞሪንሆን ጨምሮ በርካታ አሰልጣኞች ድርጊቱን አጥብቀው ተቃውመዋል፡፡ ሞሪንሆ በሰጡት አስተያየትም ‹‹የእግር ኳስ ዘረኝነት የማህበረሰቡ ሰፊ ችግር ነፀብራቅ ነው›› ብለዋል፡፡ ‹‹ዘረኝነትን አምርሬ እቃወማለሁ፡፡ የዘረኝነት ጥቃት ሲፈፀም በጣም ነው የማዝነው፡፡ ዘረኝነትን ለመከላከል የሚወሰድ ማንኛውንም ርምጃ እደግፋለሁ፡፡›› ሲሉም አሰልጣኙ መናገራቸው ይታወሳል።
በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ በርካታ የዘረኝነት ጥቃቶች በየጨዋታው ይሰነዘራሉ፡፡ በቅርቡ አንድ የ41 ዓመት ግለሰብ የማንቺስተር ዩናይትዱን አማካይ ፍሬድን እና አጥቂውን ሊንጋርድን በመዝለፍ ለእሥራት ተዳርገዋል፡፡ በተመሳሳይ ወቅት የ13 ዓመት ታዳጊ የበርንሌይ ደጋፊ በቶተንሀሙ ደቡብ ኮሪያዊ ሰን ሄዉንግ ሚን ላይ ያነጣጠረ የዘረኝነት ምልክት በማሳየቱ ከስታዲየም የተባረረበት አጋጣሚም የሚረሳ አይደለም።
በሌሎች ሊጎችና የአውሮፓ ጨዋታዎችም ዘረኝነት እየተስፋፋ መጥቷል፡፡ ዘረኝነት ከተንሰራፋባቸው ስፍራዎች አንዷ በሆነችው ጣሊያን በአንድ የፀረ-ዘረኝነት ቅስቀሳ መርሀ ግብር ላይ የዝንጀሮ ምስሎችን ይዞ በመውጣት ዘረኝነትን ለመቃወም የተደረገው ጥረት ከፍተኛ ተቃውሞ ማስከተሉ ይታወቃል። የተወዳጁ ስፖርት አስቀያሚ ገጽታ መባባሱ ቀርቶ፣ እልባት የሚያገኝበት ጊዜም ብዙዎች የሚናፍቁት ሆኗል፡፡
እግር ኳስ በተወዳጅና አዝናኝነቱ በዓለም ህዝብ ዘንድ ትልቅ ክብር መጎናፀፍ የቻለ ስፖርት ነው። እግር ኳስ ድንበር አልባነቱም ህዝቦች ያለ ልዩነት እንዲቀራረቡና በአንድ ቋንቋ እንዲግባቡም አድርጓል። በርካታ አገራት መልካም ገጽታቸውን የገነቡበት አንደኛው መሳሪያ እንዲሁም ከፍተኛ ገንዘብ የሚያንቀሳቅስ የንግድ አካልም ሆኗል። ባለሃብቶችን በቀላሉ መሳብ የቻለው እግር ኳስ በርካታ ተጫዋቾችንም ባህር አቋርጠው እንዲጫወቱ አስችሏቸዋል። ነገር ግን ስፖርቱ ሰለጠነ በሚባልበት በዚህ ዘመን መጥፎ ጎን ሆኖ የመጣው የዘረኝነት ጉዳይ የአገራትን ገፅታ ሳይቀር ጥላሸት ከመቀባት መላቀቅ አልቻለም።
በቃላት፣ በምልክት፣ በድምጽ እንዲሁም በሌሎች መንገዶች የሚከናወነው የዘረኝነት ጥቃት በተጫዋቾች ላይ በሚያደርሰው የስነ ልቦና ጫና ምክንያት ከሚወዱት እግር ኳስ ሊያርቃቸው እንደሚችል በርካቶች ቀድመው ስጋታቸውን ሲገልፁ ነበር። የቅርቡን ለማስታወስ ያህልም፤ ማንቸስተር ዩናይትድን ተሰናብቶ ኢንተር ሚላንን የተቀላቀለው ሮሜሉ ሉካኩ በአንድ ጨዋታ ላይ የቅጣት ምት ማግኘቱን ተከትሎ ተመልካቾች የጦጣ ድምጽ ያሰሙበት አሳዛኝ ድርጊት የሚዘነጋ አይደለም።
ፓውል ፖግባ፣ ታሚ አብርሃም እና ኩርት ዙማም ይህ ዓይነቱ ጥቃት በቅርቡ የደረሰባቸው ተጫዋቾች ናቸው። የእንግሊዝና የቦርሲያ ዶርትመንድ የክንፍ ተጫዋቹ ጃደን ሳንቾም በአውሮፓ ዋንጫ ማጣሪያ ጨዋታ ላይ ተመሳሳይ ጥቃት ተፈጽሞበታል። ይህንን ተከትሎም ተጫዋቹ በሰጠው አስተያየት «ይህ ነገር መቆም አለበት፤ ምክንያቱም የትኛውም ተጫዋች ጥቃት እየደረሰበት እግር ኳስን መጫወት ስለማይፈልግ። የተጫዋቾችን በራስ መተማመን የሚያወርድ ከመሆኑም ባሻገር ለስፖርቱ ያላቸውንም ፍቅር ያሳጣል» ሲል ሳንቾ መናገሩ ይታወሳል።
«ሁላችንም ደስተኛ መሆን አለብን፤ ማድረግ ያለብንንም ለማድረግ የዘረኝነት ጥቃቱ ሊቆም ይገባል። ደጋፊዎች የሚናገሯቸውን መለየት ይገባቸዋል፤ ምክንያቱም እኛም ሰው ነን። ሰዎች ታዋቂ በመሆናችን ይህ ዓይነቱ ነገር ሲከሰት በዝምታ እንደምናልፍ ያስባሉ። ነገር ግን ለምንድነው እግር ኳስ የምንጫወተው ብለን እንድናስብ ያደርገናል» ሲል በተጎዳ ስሜት ድርጊቱን አውግዟል።
የቀድሞ የማንቺስተር ሲቲ እና የአሁኑ የጣሊያን ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሮቤርቶ ማንቺኒ በበኩላቸው፤ «እንዲህ ያለው የዘረኝነት ጥቃት ያበቃ መስሎን ነበር፤ ነገር ግን አሁንም እንደ እንግሊዝ ሁሉ በጣሊያንም ይስተዋላል። ይህንን ስህተት የሚፈጽሙ ሰዎችም ማጥፋታቸውን በጊዜ ሂደት ይረዳሉ። እንደሚመስለኝ ከሆነም ተግባሩን የሚፈጽሙት ተመሳሳይ ሰዎች ይመስሉኛል» ሲሉ ገልፀዋል።
ቦጋለ አበበ
አዲስ ዘመን ግንቦት 6 ቀን 2013 ዓ.ም