የብዙ ሺህ ዓመታት ታሪክ ባለቤት፣ የነጻነትና የሉዓላዊነት ተምሳሌት፣ የኩሩና ጀግና ህዝቦች እናት፣ የውብ ብሔሮችና የአስደማሚ ባህሎች ሙዳይ፣ የተፈጥሮ ጸጋ ባለቤት፣ የብርቅዬ እንስሳትና አዕዋፋት መገኛ ናት አገራችን ኢትዮጵያ። እነ በላይ ዘለቀ፣ የነገረሱ ዱኪ፣ የንጉስ ጦና፣ ባልቻ አባነፍሶና አሉላ አባነጋ እናት፣ የእነ ዓባይ፣ የእነ አዋሽ፣ የዋቢ ሸበሌና ጣና መፍለቂያና መገኛ የሕብረ ብሔራዊ ውበት ባለቤትም ናት እናት አገራችን። ኢትዮጵያ ዛሬ በሥልጣኔ ማማ ጫፍ የረገጡ አገሮች ሳይፈጠሩ በሥልጣኔ ስሟ የተጠራ፣ የአኩሪ ታሪኮች ማህደርም ናት። የዓለምን ታሪክና ሥልጣኔ የሚያጠኑ አካላት በአስረጂነት ታሪካቸውን ከሚያነሱላቸው አገራትም ኢትዮጵያ በቀዳሚነት ትሰለፋለች።
ይህን ያህል ገናና ታሪክ ያላት አገራችን ኢትዮጵያ የተለያዩ ምክንያቶችን መደርደር ቢቻልም በሂደት የወረደችበት ደረጃ ግን ታላቅነቷን የሚመጥን እንዳልሆነ ለማንም ግልጽ ነው። በቂ የዝናብ መጠን፣ በአብዛኛው ለእርሻ አመቺ የሆነ መሬትና በርካታ የውሃ አካላት ባለቤት የሆነችው አገራችን በምግብ ሰብል እንኳን ራሷን መቻል ተስኗት ዛሬም ድረስ ስንዴ፣ ዘይትና ሌሎች ምግብ ነክ ምርቶችን ከውጪ በከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ታስገባለች። ታታሪና ሥራ ወዳድ ህዝብና ሃብት ለመፍጠር ምቹ የሆነ የተፈጥሮ ሃብት ብትታደልም ለዘመናት ሁለቱን አቀናጅቶ ወደ ውጤት ለመቀየር የተደረገው ጥረት ውጤታማ ባለመሆኑ እንደ ሃገር ልታገኝ የሚገባትን ጥቅም በበቂ ሁኔታ እያገኘች አይደለም።
በተለይም ከለውጥ አመራሩ በፊት በነበረው ኢፍትሃዊና ጨቋኝ አስተዳደር ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የሚገባው መሰረት ባለመጣሉ የዴሞክራሲ ሥርዓትን ግንባታን እንደ አዲስ ሀ ብሎ ለመጀመር አስገድዷል።ያለፈውን ጥንካሬ በማጎልበትና ድክመቶችን ነቅሶ በማረም እንጂ በመቆዘም ለአገር የሚተርፍ አንዳችም ውጤት አይኖርም ብሎ የተነሳው የለውጥ አመራር በመደመር ህሳቤ አገራዊ አቅሞችንና ትስስሮችን በማቀናጀት በመላ ሃገሪቱ አጓጊ የልማት እንቅስቃሴዎችን ከጀመረ ሶስት ዓመት ሞልቶታል። በእነዚህ የለውጥ ዓመታት ከታዩ በጎ ውጤቶች አንዱ ደግሞ ፕሮጀክቶችን ጀምሮ መጨረስና የተጓተቱን አርሞ ለፍሬ በማብቃት ረገድ የተገኘው ውጤት በምሳሌነት የሚጠቀስ ነው። የለውጥ አመራሩ አገሪቱን ባስተዳደረባቸው ሶስት ዓመታት እንደሃገር ብዙ ፈታኝ ተግዳሮቶች የገጠሙን ቢሆንም በዚህ ሁኔታ ውስጥ ተሁኖም እንኳን እጅግ በርካታ የስኳር፣ የማኑፋክቸሪንግና አግሮ ኢንዱስትሪ፣ የትምህርት፣ የጤና፣ የውሃና የመንገድ ፕሮጀክቶች ለፍጻሜ ማብቃት ተችሏል።
የመላ ኢትዮጵያውያን አሻራ ያረፈበትና እንደዓይናቸው ብሌን የሚመለከቱት ታላቁ የህዳሴ ግድብ ከዝርፊያና ከመቆም ደረጃ ወጥቶ የመጀመሪያውን የሃይል ፍሬ ለማፍራት የተቃረበው በለውጥ አመራሩ በተደረገለት ፍቱን መፍትሄ ነው። ባለፈው ሰሞን የተመረቀውን ጣና በለስ ስኳር ፋብሪካን ጨምሮ ሰባት የስኳር ፋብሪካዎች ተጠናቀው ለውጤት የበቁትም እንደ ሃገር እየተለመደ ከመጣው ፕሮጀክቶችን በተያዘላቸው የጊዜ ገደብ የማጠናቀቅ አቅም ጋር ተያይዞ ነው።
በዚህ ሰሞን በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ በኦሮሚያ፣ በአማራ፣ በደቡብ፣ በሲዳማ፣ ሶማሌና ሌሎች ክልሎች እየተመረቁና ለፍሬ እየበቁ ያሉ አጃኢብ የሚያሰኙ የልማት ፕሮጀክቶች ምረቃ “ሳንጨርስ አንጀምርም፤ ከጀመርን እንጨርሳለን” በሚል መርህ በመመራት ላይ ያለው የልማት እንቅስቃሴ ውጤቶች ናቸው። እናም ዛሬ ላይ ባዕዳንና ባንዳዎች ተቀናጅተው አገራችንን ከመቼውም ጊዜ በላቀ አጣብቂኝ ውስጥ ቢከቱም የተጀመሩና ለፍጻሜ የበቁ አጓጊ ፕሮጀክቶችን እንዲሁም የህዝባችንን የልማትና የዕድገት ፍላጎት ስንመለከት እውነትም የኢትዮጵያ ትንሳዔ እንደቀረበና መጪው ጊዜ ለኢትዮጵያ ብሩህ እንደሆነ ያመላክተናል።
በተለይም ደግሞ መጪውን ክረምት ወደ አዕምሯችን ስናመጣና የሚከናወኑ ታላላቅ ሁነቶችን ስናስብ አገሩን እንደሚወድና ለመልካምነቷ እንደሚጓጓ አንድ ዜጋ ልባችን በሃሴትና በደስታ ይሞላል። እውነት ነው መጪው ክረምት በብዙ መልኩ ለኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ወሳኝ ወቅት ነው። ይህንን የምንለውም ተጨባጭ ማሳያዎችን በማንሳት ነው። መጪው ክረምት በኢትዮጵያ የዴሞክራሲና የምርጫ ታሪክ ለየት ያለውንና ታሪክ ለዋጩን ምርጫ የምናካሂድበት ወቅት ነው። ለዚህም ነፃ ተቋማት ተደራጅተው ፓርቲዎች በነጻነት ተንቀሳቅሰው ህዝብ የሚሰጣቸውን ድምጽ ለመቀበል ዝግጁ ሆነዋል። ህዝቡም በተለያዩ መንገዶች የቀረቡለትን የፓርቲዎች አማራጭ አድምጦ ሰኔ 14 ቀን በነፃነት ለሚፈልገው ፓርቲ ያለምንም ውክቢያና ጫና ድምጹን ለመስጠት ዝግጁ ሆኖ በጉጉት እየጠበቀ ነው። ይኸ ዝግጅትም የአገራችንን መፃዒ ዕድል ብሩክ ከሚያደርጉ ሁነቶች አንዱና ዋንኛው ነው።
ሌላውና መላ ኢትዮጵያውያን ከዚህ ከመጪው ክረምት የሚጠብቁት ትልቅ ሁነት የታላቁ ህዳሴ ግድብ የውሃ ሙሌትና የመጀመሪያዎች ሁለት ዩኒቶች ሃይል ማመንጨት ነው። ይኸንንም ሥራ የታችኞቹን የተፋሰሱን አገራት በማይጎዳ መለኩ ለማከናወንና ከሃብታችን የመጠቀም መብታችን በማንም የማይገሰስ መሆኑን ለማሳየት አስፈላጊው የቅድመ ዝግጅት ሥራ በስኬት በመከናወን ላይ ይገኛል። ይኼም መጪው ክረምት ለኢትዮጵያ ብልጽግና ወሳኝ መሆኑን ማሳያ ነው። ስድስት ቢሊዮን ችግኞችን በአገር ውስጥ አንድ ቢሊዮን ችግኞችን ደግሞ በጎረቤት ሃገራት የመትከልና ከዚህ ቀድሞ የተተከሉትን የመንከባከብና የማሳደግ ሥራም የሚሰራው በመጪው ክረምት ነውና ክረምቱ ኢትዮጵያን አረንጓዴ የማልበስ ወሳኝ ሥራ የሚሰራበት ትልቅ ወቅት ያደርገዋል። ለአገራችን ልማትና ለህዝቧ ኑሮ መሰረት የሆነው የግብርና ልማታችን የሚፋጠንበትና ለመጪውና ቀጣይ ዓመታት የምግብ ቅሪት የምንቋጥርበት ብሎም ለኤክስፖርት ገቢያችን በቂ ምርት የምንይዝበት ወቅትም መጪው ክረምት እንደመሆኑ በየደረጃው ካለ አመራር እስከ አርሶ አደሩ አንድም መሬት ጦም ማደር የለበትም ብሎ ለስኬቱ መዘጋጀቱ ለኢትዮጵያ ብልጽግና ሌላው መሰረት ነውና ስኬቱ በጉጉት የሚጠበቅ ነው።
በአጠቃላይ በአገራችን ከዕለት ዕለት እየተሻሻለና እያደገ የመጣው የፕሮጀክቶች አፈጻፀም እንዲሁም በመጪው ክረምት የሚከናወኑ ታላላቅ ሃገራዊ ሁነቶች በእርግጥም መጪው ጊዜ ለኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ብሩህ መሆኑን የሚመሰክሩ ናቸው! ለአገራችን ልማትና ለህዝቧ ኑሮ መሰረት የሆነው የግብርና ልማታችን የሚፋጠንበትና ለመጪውና ቀጣይ ዓመታት የምግብ ቅሪት የምንቋጥርበት ብሎም ለኤክስፖርት ገቢያችን በቂ ምርት የምንይዝበት ወቅትም መጪው ክረምት እንደመሆኑ በየደረጃው ካለ አመራር እስከ አርሶ አደሩ አንድም መሬት ጦም ማደር የለበትም ብሎ ለስኬቱ መዘጋጀቱ ለኢትዮጵያ ብልጽግና ሌላው መሰረት ነውና ስኬቱ በጉጉት የሚጠበቅ ነው።
በአጠቃላይ በአገራችን ከዕለት ዕለት እየተሻሻለና እያደገ የመጣው የፕሮጀክቶች አፈጻፀም እንዲሁም በመጪው ክረምት የሚከናወኑ ታላላቅ ሃገራዊ ሁነቶች በእርግጥም መጪው ጊዜ ለኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ብሩህ መሆኑን የሚመሰክሩ ናቸው!
አዲስ ዘመን ግንቦት 5 ቀን 2013 ዓ.ም