በትምህርት ሴክተር 30 ዓመታት ሠርተዋል:: በ1982 ዓ.ም ‹‹አገርህን እወቅ›› የሚል መፅሐፍም ለህትመት አብቅተዋል:: በትምህርት ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያ ሆነው አገልግለዋል:: ከአገር ወጣ ብለው ተሞክሮ ወስደዋል፤ ስለቴክኖሎጂ ልምድ ተለዋውጠዋል፤ ከአንታርቲክ በስተቀር ዓለምን ዞረዋል:: ሰዎች ስለኢትዮጵያ መገንዘብ አለባቸው ብዬ ሣስብ በርካታ ባህል፣ አኗኗርና ቋንቋ የሚበዛበትን የደቡብ ኢትዮጵያን ክፍል ቢጎበኙ ብዙ እውቀት መሸመት ይችላሉ የሚል ሃሳብ አላቸው:: በዚህ አካባቢ ያለው አኗኗር፣ ባህል፣ ቋንቋና መልክዓ ምድር በአብሮነት እንዴት ተቻችሎና ተከባብሮ መኖር እንደሚቻል የሚያሳይ ነው:: እንደ ኢትዮጵያ ደግሞ ተጎብኝቶ የማያልቁ ሃብቶች ባለቤት መሆናችንም ለመገንዘብ ያግዛል ይላሉ::
በአሁኑ ወቅትም ከታሪክ ጋር አቆራኝተው በሰየሙት የሐራምቤ ዩኒቨርሲቲ ባለቤትና ሥራ አስፈፃሚ ሆነው እየሠሩ ነው:: ሐራምቤ ከአፀደ ህፃናት ጀምሮ እስከ ስምንተኛ ክፍል ትምህርት ቤቶች አለው:: በመጀመሪያ ኮሌጅ ከዚያ ዪኒቨርሲቲ ኮሌጅ ከወርሐ ጥቅምት ጀምሮ ደግሞ ዩኒቨርሲቲ ሆኗል ከመንግሥት ባገኘው እውቅና::
የአፍሪካ አገራት ከቅኝ ግዛት ነፃ በሆኑ ማግስት አንድነታቸውን አጠናክረው ለመኖር አዲስ አበባ ላይ ጉባዔ ሲካሄድ በርካታ ቤቶች ተሰርተው ነበር:: በወቅቱ ከተገነቡት መካከል ኢትዮጵያ ሆቴል እና ከፊት ለፊት ደግሞ ሐራምቤ ሆቴል የተገነቡ ሲሆን በወቅቱ የአፍሪካ ሀገራት መሪዎችም ያረፉት በሐራምቤ ሆቴል ነበር:: ሕብረቱ ሲመሰረትም የነበረው መዝሙር ሐራምቤ! ሐራምቤ! የሚል ነበር :: ትርጉሙም አብረን እንሥራ የሚል ነው :: ለዩኒቨርሲቲው ከዚህ በመነሳት ስያሜውን እንደሰጡትና በዚህም በአብሮነት መሥራት ለኢትዮጵያ ወሳኝ ጊዜ ስለመሆኑ አጥብቀው ይመክራሉ ::
የዛሬው እንግዳችን አቶ ፈይሳ አራርሳ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ላይ የግልም ሆኑ የመንግሥት የትምህርት ተቋማት ሚና ምን መሆን እንዳለበት እና በሀገር የኢኮኖሚ ዕድገት ላይ መወጣት ስለሚጠበቅባቸው ኃላፊነት ብሎም የዘርፉ ፈተናዎች እና መልካም አጋጣሚዎችን አስመልክቶ ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ ዝግጅት ክፍል ጋር ያደረጉትን ቆይታ በዚህ መንገድ አቅርበነዋል::
አዲስ ዘመን፡– ‹‹ሐራምቤ›› በስዋሃሊኛ አብረን እንሥራ የሚል ትርጉም እንዳለው ተናግረዋል:: አሁን ኢትዮጵያ ያለችበት ሁኔታ ‹‹ሃራምቤ›› የሚለውን መፈክር ያስፈልጋት ይሆን ?
አቶ ፈይሣ፡– ኢትዮጵያ ሀገራችን ብዙ ቋንቋ፣ ባህል፣ ወግ፣ አመጋገብ፣ አጋጌጥ፣ አኗኗር፣ ትውፊት፣ እና ሃይማኖት ያለባት ሀገር ናት:: ይህ ደግሞ ውበት ነው:: በጥንካሬ ከተወሰደ እና በደንብ መጠቀም ከተቻለ የአንዱ አካባቢ ስኬት ለሌላውም ስኬት ነው:: ሌላው ቀርቶ የአፍሪካ አገራት ቅኝ ገዥዎች ለማባረር እና በጋራ እንሥራ ‹‹ሃራምቤ›› ለማለት የበቁት በአንድነት በመተባበራቸው ነው:: ያ! ባይሆን ኖሮ ለዘመናት በቅኝ ግዛት ስቃይና አስቸጋሪ ምጥ ውስጥ ይኖሩ ነበር:: አንድ አገር ውስጡ ሠላምና አንድነት ካለው በሌላ አገር ጫና ውስጥ አይወድቅም:: የሚተናኮለው አካል አይኖርም:: ውስጣዊ አንድነት፣ ሠላምና ጥንካሬ ከመቼውም በበለጠ ዋጋ አለው:: ስለዚህ ኢትዮጵያም ውስጣዊ አንድነቷ በጠንካራ ዓለት ላይ እንደተገነባ ቤት መሆን አለበት::
የአንድ አገር ሠላም የሚለካው በውስጥ ሠላም ነው :: በአገራችን ነባራዊ ሁኔታ ስንመለከትም ብዙ የምናስተውላቸው ነገሮች አሉ:: ሠላምና መረጋጋት በጣም የሚያስፈልግበት ወቅት ላይ እንገኛለን:: በተለይም ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ በመጀመሩና አሁን የደረሰበትን ሁኔታ ሲመለከቱ በርካቶች አኩርፈዋል:: ይህችን አገር በተለያየ መንገድ መጉዳት የሚፈልጉ አንድነቷን በማናጋት መተናኮል የሚሹ የኢትዮጵያ ጠላቶች በርካቶች ናቸው:: አንዱን በማስታጠቅና ሌላውን በማስገደል እኩይ ተግባር የሚሰሩ እና እረፍት ማሳጣት የሚፈልጉ አካላት አሉ::
የኢትዮጵያ ጠላቶች የውስጥ ሠላም በማሳጣት መንግሥት ሌላ ሥራ እንዳይሰራና በዚህ ላይ እንዲጠመድ እንዲሁም ከፍተኛ አመራሮች ሥራቸውን በአግባቡ እንዳይወጡ የሚያደርጉ አካላት ናቸው:: ይሁንና በአግባቡ መረዳዳት ከተቻለ እና ፈተናዎችን እንደ መልካም አጋጣሚ መጠቀም ከተቻለ ልዩነቶችን ወደ አንድነትና ወደ ላቀ ጥቅም መቀየር ይቻላል:: በዓለም ላይ ከኢትዮጵያ በላይ ልዩነት እያላቸው ዕድገታቸው በጣም የተፋጠነ አገራት አሉ :: ይህ የሚያሳየው ልዩነቶች መኖራቸው አገራትን እንደማይከፋፍልና በአግባቡ መያዝ ከተቻለ ወደ መልካም አጋጣሚ መቀየር እንደሚቻልም ጭምር ነው ::
አዲስ ዘመን፡– በብዝሃነት ውስጥ ሆነው የሀገራቸውን ኢኮኖሚ ዕድገት ያፈጠኑ አገራት አካሄድ እንዴት ነበር?
አቶ ፈይሣ፡– ነገሮችን በሚገባ ማወቅና መፍትሄ ማስቀመጥ ይገባል:: መከባበር፣ መቻቻል ካለ እና በጋራ መሥራት ከተለመደ ከሚጠበቀው በላይ ብዙ ርቀት መጓዝ ይቻላል:: ይህ ከሆነ ደግሞ የውጭ ጠላቶችም እያፈሩ የሚሄዱ ይሆናል :: ከኢትዮጵያ በላይ ብዙ ቋንቋ የሚነገርባቸው አንዳንድ ሀገራት ፈጣን ዕድገት እያስመዘገቡ ነው :: ለምሳሌ ኢንዶኔዥያ 1ሺ700 ቋንቋዎች ይነገሩባታል:: ከቻይና፣ ህንድ እና አሜሪካ በመቀጠል ከ270 ሚሊዮን ሕዝብ በላይ በመያዝም በዓለም አራተኛው ባለ ብዙ ሕዝብ ባለቤት ሀገር ናት :: እንግዲህ በዚህ ሁሉ ቋንቋ እና ልዩነቶች ውስጥ ይህች አገር ትልቅ ዕድገት አስመዝግባለች :: ሕዝቦቿ ተከባብረውና ተቻችለው ስለሚሠሩ በዓለም በሃብት ከናጠጡ 20 ቀዳሚ ሀገራት ተርታ መሰለፍ ችላለች :: የምጣኔ ሃብት ዕድገቱም ብዙ እጥፍ እያደገ የበርካቶችን ቀልብ መሳብ የቻለ ነው::
ኢትዮጵያም ከኢንዶኔዥያ ብዙ መማር ትችላለች:: ብዙ ቋንቋ፣ ብሔረሰብና ባህል መኖሩ የሚያኮራ ነው:: ልዩነታችን ወደ አንድነት ከመጣ ለጠላቶቻችን ሥጋት የሚሆን እንጂ ለእኛ አያስፈራም:: አንድነት ደግሞ ትልቅ ትንሽ ሳይል ከመሠረቱ ማደግ አለበት:: ይህ አስተሳሰብ እንዲሰርፅ ደግሞ በትምህርት ቤቶች፣ በማህበረሰብ፣ በሚዲያው እና በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ውስጥ ከታች ጀምሮ መኮትኮት፣ ማሳደግ፣ ማስረፅና ማስፋት ይገባል:: ሕዝብ ለሕዝብ ያለው ትስስር እና ‹‹ፐብሊክ ዲፕሎማሲ›› ለኢኮኖሚው ዕድገት የጎላ ሚና አለው::
አዲስ ዘመን፡– ‹‹ፐብሊክ ዲፕሎማሲ›› ለአገር ኢኮኖሚ ዕድገት ሚናው እስከምን ድረስ ነው ብለው ያምናሉ?
አቶ ፈይሣ፡– ‹‹ፐብሊክ ዲፕሎማሲ›› ሲባል አንዱ አገር ከሌላ አገር ጋር የሚደረግ ትስስርና ወዳጅነት ብቻ ተደርጎ መወሰድ የለበትም :: በአገር ውስጥ ያሉ ብሔሮች አንዱ ከሌላኛው ጋር በሚገባ መግባባት አለባቸው :: አንድነታቸው የሚጠናከሩባቸው ሥራዎች መከናወን አለባቸው :: ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ብሔሮች መተሳሰብ፣ በጋራ መሥራትና መከባበሩ በሚገባ መሰረት ከያዘ ለኢኮኖሚው ዕድገት ትልቅ ፋይዳ አለው :: የአንድ አገር ዕድገት የሚጀምረው ማህበራዊ መስተጋብሮች ጤናማ ሲሆኑና አንደኛው ለሌላኛው የስኬት መደላድል እየፈጠረ ሲሄድ ነው :: በዚህ ረገድ በሚገባ ከተሠራ ኢትዮጵያ ጥሩ ደረጃ ትደርሳለች :: አሁን የሚስተዋሉ ጅምሮች ተስፋ የሚሰጡ ናቸው :: ግን በጣም በጥልቀትና በስፋት መሥራት ያለባቸው በርካታ ጉዳዮች አሉ :: ይህ ደግሞ በሁሉም ዘርፍ ላይ በተቀናጀ እና በተናበበ መንገድ መሆን አለበት :: በመሆኑም ፐብሊክ ዲፕሎማሲ የሚኖረው ትርጉም ከአገር ውጭ ብቻ የሚከናወን ሁነት ወይንም ተግባር ብቻ ተደርጎ መወሰድ የለበትም :: በተጨማሪም ለኢኮኖሚ ዕድገት የሚኖረው ፋይዳውም በቀላሉ መታየት የለበትም::
አዲስ ዘመን፡- የኢትዮጵያን ሠላምና አንድነት በማስቀጠል ረገድ የትምህርት ተቋማት እንዴት መሥራት አለባቸው?
አቶ ፈይሣ፡- የትምህርት ተቋም ሲባል ለብዙ ሴክተር ዋነኛ መሠረት ነው :: ለፖለቲካው፣ ማህበራዊ ጉዳይ፣ ኢኮኖሚው፣ ለሣይንስ፣ ቴክኖሎጂ ሆነ ዓለም አቀፍ ግንኙነት የሁሉ ነገር መሰረቱ ትምህርት ነው :: ትምህርት በሌለበትና የትምህርት አድማስ ባልተስፋፋበት ሁኔታ ስለ እድገት ማውራት አስቸጋሪ ነው :: ትምህርት በዘመነበትና ትምህርት ወደ ኋላ በቀረባት የዓለማችን ክፍል ብናይ የምናስተውለው ልዩነት የሰማይና የምድር ያክል የተራራቀ ነው :: ስለአገር አንድነትም ስናወራ ዋንኛ መሰረቱ ትምህርት እና ትምህርት ቤት ነው::
ስለትምህርት ሲወራ ምሁራንና ወጣቶች ያሉት በዚሁ አውድ ውስጥ መሆኑን መዘንጋት የለብንም:: በተለይም በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ ወጣቶች አገራቸውን እንዲወዱ፣ የአገር አንድነት ምን ያክል ጠቃሚ እንደሆነ፣ የአገር ጉዳይ የጋራ መሆኑና የአገር አንድነትን ከሚሸረሽሩ ጉዳዮች መራቅ እንደሚገባና በሚገባ መሠራት አለበት :: ትምህርትና ወጣት የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ናቸው :: መነጣጣል የማይችሉ በአገር እድገትና ስልጣኔ ደግሞ እጅግ ትልቅ ትርጉም ያላቸው ወሳኝ ጉዳዮች ናቸው ::
በእርግጥ ለኢትዮጵያን አንድነት ጠንቅ ከሆኑ ጋር የሚተባበሩ አሉ ይህ በጣም ያሳዝናል :: ለአገር ጠንቅ ሆነው የሚሰሩት ልቦና ይስጣቸው :: ግን በትምህርት ሥራ መምህራን ስለ አገር ተቆርቋሪነትና በወጣቶች ላይ በሚገባ መሠራት አለበት :: መቻቻል እና መተባበር ብሎም የአገር አንድነትን ጠብቆ ለመሄድ በትምህርት ዘርፍ ላይ መሥራት ያስፈልጋል:: በመማር ማስተማር ላይ በመደረብ ለወጣቶች ስለአገር አንድነትና ሉዓላዊነት በሚገባ ማስተማር ይገባል:: የትምህርት ተቋማት ስለአገራቸው በደንብ እንዲያውቁ መሥራት አለባቸው:: አንድ ሰው በሌላ አገር ሄዶ ሊሠራ እና ሀብታም ሊሆን ይችላል፤ ግን በአገሩ ያለውን ክብርና ሥም ሊያገኝ አይችልም:: ስለዚህ በአገሩ የሚኮራ፣ ለአገሩ የሚሠራ ሰው ኃላፊነቱን እንደተወጣ ይቆጠራል :: በአጠቃላይ የትምህርት ተቋማት ለአንድ አገር ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ወሳኝ መሆናቸውን በሚገባ ተረድተው መሥራት ይጠበቅባቸዋል::
አዲስ ዘመን፡– የኢትዮጵያ ዕድገት ወሳኝ ከሆኑት መካከል አንዱ የህዳሴ ግድብ ነው :: ከዚህ ጋር በተያያዘ የትምህርት ተቋማት ሚና ምን መሆን አለበት?
አቶ ፈይሣ፡– ሰዎች ስለአገራቸው ሃብት፤ ቅርስ እና መሰረታዊ ጉዳዮች ማወቅ አለባቸው:: የታላቁ ኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብም ከእነዚህ ውስጥ አንዱ ነው:: የኢትዮጵያ ወንዞች እና ተፋሰሶች ከራሳችን አልፈው ለሌላው የሚተርፉ ናቸው:: ግን ብዙ ባለመሠራቱ የቅኝ ግዛትን ተጠቅመው እኛ ላይ ጫና ለማሳደር የሚሮጡ ብዙ ናቸው :: ግድቡ ግብጽ እና ሱዳንን እንደማይጎዳቸው እውነታውን መቀበል የከበዳቸው እኛ ከጥንት ጀምረን በዓባይ ወንዝና ትውልዱ ላይ ባለመስራታችን ነው::
ግብፅ ላይ በጣም ተሰርቷል :: የግብጽ ዜጎች ዓባይን ከሕይወታቸው ነጥለው እንዳያዩ ተደርጓል :: ስለ ዓባይ ያላቸው አመለካከት እጅግ ከፍ ያለ ነው :: እኛ ኢትዮጵያውያን አንድ ቀን ውሃውን እንደምናቋርጥባቸው ነው የተነገራቸው:: የአገራቸው ሚዲያም ለበርካታ ዓመታት ለሕዝቡ ያስታጠቀው ነገር ጥሩ አይደለም :: ብዙ የምርምር ሥራዎቻቸው፣ ሚዲያዎቻቸው፣ ፊልሞቻቸው፣ ድራማዎች እና በአጠቃላይ የጥበብ ሥራዎቻቸው በሙሉ ዓባይ ላይ ያተኮሩና ሕዝብ ልብ ውስጥ የገቡ ናቸው ::
እውነታው ግን ማወቅ አለብን :: ከታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ውጭ ሌሎች ግድቦች ነገ ይመጣሉ:: በዚህ ጊዜ የኤሌክትሪክ ኃይል ወደ ውጭ ሸጠን ብዙ ጥቅም እንደምናገኝ ለዜጎች ጥሩ ግንዛቤ መፍጠርና ዜጋን ማንቃት ይገባል:: በዚህ ረገድ ደግሞ የትምህርት ተቋማት የሚኖራቸው ሚና እጅግ ትልቅ መሆኑ ከግንዛቤ ማስገባት ይኖርብናል:: የግድቡን መገንባት ጥቅም ሳይንሳዊ በሆኑ መረጃዎችና ኢትዮጵያ የምታገኘውን ዘርፈ ብዙ ጥቅም በጥናትና በመረጃ በማስደገፍ ተንትኖ ማሳየት ይገባል :: ግንዛቤ መፍጠርና ተፈጥሮ የለገሰንን ሃብት መጠቀም መብት እንዳለንም በሚገባ በማህበረሰቡ ውስጥ እንዲታወቅ መሥራት ይገባል::
አዲስ ዘመን፡– የውስጥ ችግሮች በታላቁ ህዳሴ ግድብ ላይ የሚኖረው አሉታዊ ሚና እንዴት ይረዱታል?
አቶ ፈይሣ፡– የውስጥ ችግር በውስጥ ይፈታል፤ የውስጥ ችግርን ግን ወደ ውጭ ወስዶ የጠላት አጀንዳ ማድረግ አሳፋሪ ነው:: አሁን የተጀመሩ ጅምሮች በተለይ ከግድቡ ጋር በተያያዘ የማይደግፍ ኢትዮጵያዊ ሁሌ አንገቱን ደፍቶ እያፈረ የሚኖር ይመስለኛል :: ሰው አገር ከሌለው ትርጉም የለውም:: ከሥም በላይ ቀድሞ የሚመጣው አገር ነው:: ምንም ዓይነት ችግር ቢኖርም ለሀገር አንድነት፣ ኢኮኖሚው ዕድገትና ለሚመጣው ትውልድ የሚጠቅም ሥራ የማይደግፍ ሰው መኖር የለበትም::
በየትኛውም የዓለም ክፍል የሚኖር ኢትዮጵያዊ በህዳሴ ግድብ ላይ በጋራ መቆምና የተዛባ አመለካከት የማስተካከል ኃላፊነት አለበት :: ወጣቶች፣ ማህበረሰቡ፣ ምሁራን እና ተቋማት በህዳሴው ግድብ ላይ ከመንግሥት ያላነሰ ትልቅ ኃላፊነት አለባቸው:: ልዩነቶችንም በሚፈቱበት መንገድ መፍታት እንጂ የግድቡን መገንባት ከዚህ ጋር ማያያዝ ተገቢ አይሆንም:: ግድቡ ለሚቀጥሉት በርካታ ትውልዶች የሚገነባ እንጂ የተወሰኑ ቡድኖች የሚጠቀሙት እንዳልሆነ መታወቅ አለበት:: ይህ ግድብ የኢትዮጵያን ህልውና በጥሩ ጎኑ የሚቀይርና በዓለም አቀፍ ደረጃም የሚኖረንን ተፅዕኖ ፈጣሪነት ምስል ከፍ አድርጎ የሚያሳይ ነው::
አዲስ ዘመን፡– የግል ትምህርት ተቋማት ህዳሴን ግድብ ጨምሮ ለአገር ኢኮኖሚ ማበርከት የሚጠበቅባቸውን ያክል እያበረከቱ ነው?
አቶ ፈይሣ፡– እስካሁን የነበረው አካሄድ ትምህርትን ለዜጎች የማዳረስ አዝማሚያ ነበር :: በተለይም የትምህርት ዕድል ያላገኙ ዜጎች ላይ ያተኮረ ነበር :: ከአሁን በኋላ ቀደም ሲል የነበረው አሠራር ሙሉ ለሙሉ የሚቀጥል አይሆንም :: ወደፊት በጥራት ላይ ያኮረ ነው :: ከአሁኑ በኋላ አግባብነት ጥራት ላይ አጥብቆ የመሄድ ዝንባሌ አለ:: በአሁኑ ወቅት ያሉ የትምህርት ተቋማት በጥራት በቂ ናቸው ባይባልም ለዜጎች ትምህርትን በማዳረሱ ረገድ ላይ የጎላ ችግር አለ ማለት አይቻልም :: አካሄዱ የሚያሳየው ተዳራሽ ከማድረግ ወደ ጥራትና አግባብነት እየሄደ ነው ::
ቀደም ሲል በነበራቸው አካሄድም በቂ ነው ባይባልም ለአገሪቱ ኢኮኖሚ ዕድገት ራሳቸውን ሚና ቀላል ግምት የሚሰጠው አይደለም :: ነገሮች በሂደት እየተለወጡ እንደሚሄዱ መገንዘብ ያስፈልጋል :: የትምህርት ተቋማት የግል ወይንም የመንግሥት ብሎ ስያሜ ይሰጣቸው እንጂ ድምር ውጤታቸው አገርን ወደተሻለ መንገድ መውሰድ ነው:: በዚህ ላይ ትልቅ ሚና እንደሚኖራቸው ጥርጥር የለኝም::
አዲስ ዘመን፡– ዘርፉ ላይ እንደቆየ ሰው በአገር ኢኮኖሚ ላይ የትምህርት ሚና በምን ደረጃ ይገለፃል?
አቶ ፈይሣ፡– የትኛውም ኢኮኖሚና የየትኛውም አገር የእድገት መሠረቱ ትምህርትና ስልጠና ነው:: ትምህርትና ስልጠና ደግሞ ዕውቀት እና ክህሎትን አካቶ ብቃት ያለው የሰው ኃይል ማፍራት የሚቻልበት መንገድ ነው:: ይህ ኃይል የትኛውም አገር ኢኮኖሚ ዕድገት ከተፈለገ በትምህርት ጥራቱ፣ ለሳይንስና ቴክኖሎጂ ዕድገት፣ ሳይንስና ፈጠራ ላይ በትኩረት መሥራት ይገባል:: አንድ አገር አደገ የሚባለው የሰው ኃይል ብቃት፣ ምርታማነት፣ ሳይንስና ቴክኖሎጂ አደገ ማለት ነው:: ይህ የሚሆነው ደግሞ የትምህርት ጥራትና አግባብነት ተጠብቆ በአግባቡ ሲሠራ ነው:: በመሆኑም የአገር ኢኮኖሚ መሰረቱን ይዞ የሚያድገው በትምህርት ነው:: በመሆኑም ጥራትና ብቃትን መሰረት አድርጎ የሚሄድ የትምህርት አሰጣጥ ሥርዓት ኢኮኖሚን በመለወጡ ላይ የማይተካ ሚና አለው::
አዲስ ዘመን፡– የትምህርት ጥራት ቀጣይ ፈተናዎች ምን ሊሆኑ ይችላሉ?
አቶ ፈይሣ፡– ዘርፉን የሚፈታተኑ ችግሮች ብዙ ናቸው:: አንዳንዶቹ በአጭር ጊዜ የሚፈቱ ሲሆኑ ሌሎቹ ጊዜ ሊወስዱ ይችላሉ :: በአሁኑ ወቅት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፈተና የሆነው ብቁ መምህራን እጥረት ነው :: በተለይም የሦስተኛ ዲግሪ መምህራን እጥረት አለ :: ሌላው እንደ አገር ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ለመጠቀም የኢንተርኔት እጥረትና ተደራሽነት ይስተዋላል :: ለዲጂታላይዜሽን እና ለመማር ማስተማር ሥራው ኢንተርኔት በሚገባ አለመኖር ትልቅ ፈተና ነው:: በተለይም በኢትዮጵያ ብቸኛው ሆኖ የኢንተርኔት ድርጅት አቅራቢው ኢትዮ- ቴሌኮም ብቻ መሆኑ በቂ አይደለም::
አሁን ባለው ሁኔታ ኢንተርኔት ዋጋ ለትምህርት የሚሆን አይደለም :: ዋጋው ሁሉም መማር እና ማስተማር የሚፈልግ አካል ከፍሎ መጠቀም ይከብደዋል :: ስለዚህ እነዚህ ፈተናዎች ናቸው:: በመሆኑም ኢንተርኔት እና ቴክኖሎጂ መስፋፋት ብሎም ዋጋው መቀነስ አለበት :: አገልግሎቱ ኖሮም ክፍያው ከፍ ያለ ከሆነ አሁንም ችግር ሆኖ መቀጠሉ አይቀርም::
አዲስ ዘመን፡– በአሁኑ ወቅት ኢትዮ–ቴሌኮም የጀመራቸው አዳዲስ ሥራዎችና አሠራሮች ተስፋ አይሰጥም?
አቶ ፈይሣ፡– በጣም ትልቅ ተስፋ አለው:: ጎረቤታችን ኬንያ ከእኛ የተሻሉ ቴሌኮም አቅራቢዎች አሏት:: በሕዝብ ብዛትና ተጠቃሚዎች ቁጥር ከእኛ ያነሱ ሀገራት ብዙ ቴሌ ፕሮቫይደር አላቸው:: ታዲያ ከ110 ሚሊዮን በላይ ያላት ኢትዮጵያ በርከት ያሉ ፕሮቫይደሮች ወደ ልማቱ መግባት አለባቸው:: ልምድና ብቃታቸው የተመሰከረላቸው ቴሌ ወደ ልማቱ ማስገባት ተገቢ ነው:: እነዚህ አካላት ወደ ልማቱ ከገቡና በዚህ ላይ በስፋት ከተሠራ እንደ ሀገር ኢኮኖሚውን በማነቃቃት ትልቅ ድርሻ አለው:: ይህም ብቻ ሳይሆን የቴሌኮም ዘርፍ እያደገ ከሄደ ሌላኛውን ይዞ የመሄድና የማሳደግ ዕድሉ ሰፊ ነው ::
አዲስ ዘመን፡- በሥራ አጋጣሚ ጎብኝተው በኢኮኖሚያቸው እድገት በእጅጉ የተገረሙባቸውና ኢትዮጵያ ፈለጋቸውን ብትከተል የሚሏቸው አገራት አሉ?
አቶ ፈይሣ፡- ሲንጋፖር በጣም አስገራሚ አገር ናት:: በአጭር ጊዜ ውስጥ ትልቅ ለውጥ ከተመዘገበባቸው የዓለማችን ክፍሎችም አንዷ ናት:: ስማርት ከተማ ናት:: ሌላው ቀርቶ መንገድ ላይ ትራፊክ የለም:: አሜሪካ ውስጥ ናሳን ጨምሮ ብዙ ተቋሞቻቸው ዘመናዊ እና በጣም ብዙ እውቀት የሚጠይቁ ቴክኖሎጂዎችን ይጠቀማሉ :: የሲንጋፖር ግን የተለየ ነው :: ሌላኛዋ አስገራሚ ከተማ ሲዖል የደቡብ ኮሪያ ዋና ከተማ ናት :: ኮሪያውያኑ ሀገራቸውን በጣም ይወዳሉ :: 10 ሚሊዮን ሕዝብ በሚኖርባት ከተማ በጣም ተለውጣለች :: ያላቸው ሥነ ምግባርና የሥራ ተነሳሽት በጣም የሚደነቅ ነው :: ከዛሬ 40 ዓመት በፊት በዓለም ላይ ድሃ የነበሩ ሀገራት ዓለምን በቴክኖሎጂና በእውቀት ሲመሩ በጣም ያስቀናል ::
በኢትዮጵያም መሰረታዊ ለውጦች መምጣት አለባቸው:: ትምህርት፣ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ለማሳደግ ትኩረት መስጠት ይገባል:: ሁሉም በችሎታውና በአቅሙ በትጋት ቢሠራ ለውጥ ይመጣል:: እያንዳንዱ ግለሰብ ራሱን ከለወጠ አገር ትለወጣለች:: ሰው ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይል ማንበብ አለበት :: ልምድና እውቀትን ለማዳበር ወደ ኋላ ማለት አይገባም :: በሕይወታችን ዘመን በሙሉ መማር አለብን :: ዓለም እየተለወጠች እና ነገሮች እየተቀያየሩ ነው :: እኛ ኢትዮጵያውያንም በዚህ መንገድ ማሰብና መዘጋጀት አለብን :: በትጋት ከሠራን ሀገራችንን በአጭር ጊዜ ማበልፀግ እንችላለን :: በድህነታችን ማንንም መውቀስ የለብንም :: ጠንክሮ ከተሠራ የማይለወጥ ነገር የለም::
የአንድ አገር ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገቶች በአንድ ሌሊት የሚመጡ ባለመሆናቸውና እድገት በባህሪው ሁሌም አዳዲስ ነገሮችን የሚፈልግ በመሆኑ ሁሌም አዲስ ፈጠራዎች እና ቴክኖሎጂዎች የታከሉበት አስተሳሰብ መኖር አለበት :: በአጠቃላይ በጋራ ከሠራን ብዙ ነገሮች እንደሚለወጡ አምናለሁ:: ከምን በላይ የኢትዮጵያን ጥቅም እናስቀድም :: ሀገር ከሁሉም በላይ መሆኗን አምነን መሥራት የዜግነት ኃላፊነታችን ነው:: ትምህርት ደግሞ በትውልድ አዕምሮ ላይ የሚሠራ ወሳኝ ጉዳይ በመሆኑ በጣም በጥንቃቄ እና በጥራት መሠራት አለበት:: እኛም ይህንን አስበን እየሰራን ነው::
አዲስ ዘመን፡– ከዝግጅት ክፍላችን ጋር የእርስዎን ተሞክሮ እና አጠቃላይ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ በመወያየታችን እናመሰግናለን::
አቶ ፈይሳ፡– እኔም እንግዳ ስለሆንኩኝና ሐሳቤን እንዳካፍል ስለጋበዛችሁኝ አመሰግናለሁ::
ክፍለዮሐንስ አንበርብር
አዲስ ዘመን ሰኔ 3/2013