ዴሞክራሲ በሰፈነበት አገር ሕዝብ መብቱ መከበሩን የሚያረጋግጥበት ዓይነተኛ ዘዴ ሕጋዊ ምርጫ ነው። ሁነቱም የሕዝብን ፍላጎት መጠየቂያ ነፃ የሆነ የዴሞክራሲ መንገድ እንጂ የመርሃ ግብር ማሟያ አይደለም::
ነፃ፣ ግልፅ እና ፍትሃዊ ምርጫ እንዲካሄድም በውድድሩ መሸነፍና ማሸነፍ እንዳለ የሚገነዘብ ሕጋዊ፣ ለአገርና ለሕዝብ የቆመ መንግሥት ብሎም ተፎካካሪ ፓርቲዎች የግድ ይላል:: ይህ እስካልሆነ ግን ምርጫ ፌዝ፣ ጨዋታና ቀልድ ይሆናል።
የዴሞክራሲያዊ ምርጫ ድምር ውጤት አማራጭ የፖሊሲ አቅጣጫዎች ላይ በመንተራስ ደካማን የማስገደድ፣ ጠንካራን የማስቀጠል ዕድል መስጠት ነው:: ሁነቱም አገራት በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካ ረገድ በቀጣይ የሚራመዱበትን መንገድ የሚያመላክት ብሎም የሚያሳውቅ እንደመሆኑ በርካቶች በጉጉት ይጠብቁታል:: ይሳተፉበታል::
የምጣኔ ሀብት ምሁራን እንደሚገልጹት፣ ምርጫ ለአንድ አገር ሁለንተናዊ እድገት እጅግ ወሳኝ ነው:: ለኢኮኖሚያዊ እድገት በተለይ ኢንቨስትመንት መጎልበት ወሳኝ አስተዋፆኦ አለው:: የኢኮኖሚ እድገት ዋነኛ የጀርባ አጥንት በሆነው ኢንቨስትመንት ከባቢ እና በኢንቨስተሮች ሥነልቦና ላይ ጉልህ ተፅእኖ ብሎም አበርክቶ አለው::
በአንድ አገር ምርጫ ወቅቱን ጠብቆ፣ ሰላማዊ በሆነ መልኩ ሲካሄድ ብሎም ውጤቱን በሰላማዊ መንገድ በሚቀበሉ ዜጎች ሲታጀብ ለኢንቨስተሮች የላቀ ደስታን ይፈጥራል:: በተቃራኒው መካሄድ ካለበት የጊዜ ገደብ ሳይካሄድ ቀርቶ ሲራዘም አሊያም ሰላማዊ በሆነ መልኩ መቋጫውን ካላገኘ ለኢንቨስተሮችም ሆነ ለኢንቨስትመንት መዳከም መንስኤ መሆኑ አይቀሬ ነው::
ይህ እንደመሆኑም በዓለም አቀፍ ደረጃ በተለያዩ አገራት በርካታ ኢንቨስተሮች የምርጫ ቁርጥ እስኪታወቅ ውሳኔአቸውን በይርጋ ያቆያሉ:: ፈጥነው ውሳኔ ለማስተላለፍ ብሎም መዋዕለ ነዋያቸውን ፈሰስ ከማድረግ ይልቅ ስለቀጣዩ ጊዜ እና የሰላም ሁኔታ እርግጠኛ ለመሆን ነገሮችን ቆም ብለው መመልከትን ምርጫቸው ይደርጋሉ::
ኢትዮጵያ በየአምስት ዓመቱ አገራዊ ምርጫ ታካሂዳለች። ከ1983 ዓ.ም ወዲህም እስካሁን ለአምስት ጊዜያት አገራዊ ምርጫ አካሂዳለች። ስድስተኛውን ሁነት ካለፉት በተሻለ ፍትሃዊ ተአማኒና ገለልተኛ በሆነ መልኩ ለማካሄድ ሽር ጉድ ስትል ቆይታለች::
ይሁንና ባሳለፍነው ዓመት በዓለም አቀፍ ደረጃ የተከሰተው የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ሁነቱ በተቀመጠለት የጊዜ ሰሌዳ እንዳታካሂድ አድርጓታል:: ምርጫው በተራዘመ ቁጥር የሚከሰተውን ሁለንተናዊ ቀውስ በማገናዘብ ወረርሽኙን በመከላከልና በመቆጣጠር ሁነቱን ለማስኬድ ወስናለች:: ሁነቱም ግንቦት ወር እንዲካሄድ ቀን ተቆርጦለታል::
የምርጫው ከዴሞክራሲ መገለጫነቱ ባሻገር እንደ አገር ስለሚያሰጠው ሁለንተናዊ በተለይም ስለ ኢኮኖሚ ትሩፋት በርካቶች እየተወያዩበት ይገኛል:: በመንግሥት ደረጃም ምርጫው ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ብልፅግና ትርጉሙ ከፍ ያለ መሆኑን በተደጋጋሚ ሲገለፅ ተሰምቷል::
የምጣኔ ሀብት ምሁራንም ምርጫው በተለይም ለኢንቨስትመንት መጎልበት እንዲሁም ለኢንቨስተሮች ሥነልቦና እጅግ ወሳኝ መሆኑን እየተናገሩ ናቸው:: አዲስ ዘመን ጋዜጣ ያነጋገራቸው የምጣኔ ሀብት ምሁራንም ይህንኑ አረጋግጠዋል::
በሃረማያ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚ መምህር ፍሬዘር ጥላሁን፣ ምርጫና ኢንቨስትመንት ቁርኝት እንዳላቸው ያስረዳሉ:: እንደ ምጣኔ ሀብት ባለሙያው ገለፃ፣ ኢንቨስተሮች በአንድ አገር በተለያዩ ዘርፎች ላይ መዋዕለ ነዋያቸውን ፈሰስ ከማድረጋቸው አስቀድሞ ውጤታማ መሆን የሚያስችላቸውን በርካታ መመዘኛዎን ያስቀምጣሉ::
የገበያ አዋጭነት፣ የደንበኞች ቁጥር፣ የግብአት እንዲሁም የመሠረተ ልማት አቅርቦትን እና ተደራሽነት መጠንን ይቃኛሉ:: ከዚህም በላይ ግን የፖለቲካ መረጋጋት የዴሞክራሲ መረጋገጥ የሰላም እና የፀጥታ ደህንነት መረጋገጥ ያሳስባቸዋል:: ምርጫ ደግሞ የአንድ የዴሞክራሲያዊ አገር መገለጫ እና ማሳያ ነው::
‹‹ሙሉ በሙሉ በሚባል መልኩ የፖለቲካ ምህዳራቸው የሰከነ እና ሰላማዊ አገራት ምርጫን ወቅቱን ጠብቀው ያካሂዳሉ:: ይህም አገራቱ ሰላምና ደህንነታቸው አሳሳቢ እንዳልሆነ ምስክር ይሰጣል›› የሚሉት አቶ ፍሬዘር፣ ኢንቨስትመንትና ኢንቨስተሮች ምርጫን እንደ አንድ የሰላም ዋስትና ብሎም መተማመኛ እንደሚወስዱት ያስረዳሉ::
እንደ ምጣኔ ሀብት ባለሙያው ገለፃ፣ የውጭ ቀጥታም ሆነ የአገር ውስጥ ኢንቨስትመንት በዋነኝነት ሰላም ላይ መሠረቱን ያደረገ ነው:: በአገር አገር እንደልብ ከቦታ ቦታ ተንቀሳቅሶ መስራት መቻል ኢንቨስተሮች ተረጋግተው መዋዕለ ነዋያቸውን ፈሰስ እንዲያደርጉ መተማመኛን ይሠጣል::
አገራት ከሰላምና ፀጥታ እንዲሁም ሌሎች ምክንያቶች ጋር በተገናኘ ምርጫን ማካሄድ ተስኗቸው እንዲራዘም ባደረጉ ቁጥር ምስሉ የተገላቢጦሽ እንደሚሆን የሚያስገነዝቡት የምጣኔ ሀብት ባለሙያው፣ ኢንቨስተሮች ፈጥነው ውሳኔ ከማስተላለፍና መዋዕለ ነዋያቸውን ፈሰስ ከማድረግ ይልቅ ነገሮችን ቆም ብለው እንዲመለከቱ እቅዳቸውን በይርጋ እንዲያቆዩ በር የሚከፍት መሆኑን ያስረዳሉ::
አቶ ፍሬዘር ለዚህ እሳቤአቸውም የዩናይትድ እስቴትስን ምርጫ እና ኢንቨስትመንት ትስስር በዋቢነት ያቀርባሉ:: እንደ እርሳቸው ገለፃም፣ የዩናይትድ እስቴትስ ምርጫ ዋነኛ መሠረቱ ኢኮኖሚ ላይ ነው:: የተለያዩ ኩባንያዎች እና ኢንቨስተሮችም ምርጫውን የሚከታተሉ እና የሚቃኙት እጅግ በአንክሮ ብሎም በጥንቃቄ ነው::
ከእያንዳንዱ እርምጃቸው አስቀድሞም ቀጣይ አራት ዓመት ልዕለ ኃያላን አገር ለማስተዳደር ነጩን ቤተ መንግሥት የሚረከበው ፓርቲ ማነው የሚለው ወሳኝ እና መልስ ማግኘት የሚገባው አንገብጋቢ ጥያቄ ነው:: ምክንያቱ ደግሞ ከራሳቸው እሳቤ እና የቢዝነስ አረማመድ ጋር የሚስማማው ፓርቲ ለመለየት ነው::
ይህን ለማስረዳትም የቀድሞው የዩናይትድ እስቴትስ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ አገራቸው ከሜክሲኮ ጋር በምትዋሰንበት ድንበር ስደተኞችን ለመከላከል በሚል እሳቤ የግንብ አጥር አጥራለሁ፣ ዜጎችንም ወደ መጡበት እመልሳለሁ የሚል ውሳኔ ማቅረብ ይቻላል:: ሰውየው ይህን ዓይነት አቋም እያንፀባረቁ የሜክሲኮ ባለሀብቶች በዩናይትድ እስቴትስ ውስጥ መዋዕለ ነዋያቸውን ፈሰስ ለማድረግ መተማመኛ አይገኙም::
ኢንቨስትመንታቸውን ወደ ሥራ ከማስገባት ይልቅ በምርጫው የሚፎካከሩ ፓርቲዎችን የፖሊሲ አቅጣጫ እንደሚጠባበቁ የሚጠቁሙት የምጣኔ ሀብት ባለሙያው፣ ፓርቲዎቹ አዲስም ሆነ ነባር ኢንቨስተሮችን እና ኢንቨስትመንትን ለማበረታታትም የታክስ አሊያም የወለድ ምጣኔን ከመቀነስ አንስቶ የሚያቀርባቸውን እቅዶች እንዲሁም ከሚያምኑበት እሳቤ ጋር የሚዛመድ አቋም ያለው ፓርቲ የመሪነት ወንበሩን እስኪያረጋግጥ እንደሚጠባበቁም ነው ያስረዱት:: ይህም የትኛው ነው ለእኔ የሚስማማኝ የሚለውን ከመለየት እና ከሚመለከቱበት መንፅር አንፃር የሚቃኝ ነው::
‹‹ለኢንቨስትመንት ወሳኝ የሆኑ ሌሎችም ምክንያቶች እንደጠበቁ ሆነው አገራት ምርጫን በታቀደለት ጊዜ ማካሄዳቸው አዳዲስ እና ተጨማሪ ኢንቨስትመንት በቀላሉ ለመሳብ ከፍተኛ አቅም እንደሚፈጥርላቸው ጠንቅቀው መረዳት ይገባቸዋል›› የሚሉት አቶ ፍሬዘር፣ ለዚህ ደግሞ የፖለቲካውን አየር ጤናማ ማድረግ ግድ እንደሚላቸው አፅእኖት ይሰጡታል::
የአገር ውስጥም ሆነ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ለማጎልበት እና በሚያለሙበት አሊያም ለማሟላት ፍላጎት ባላቸው አገር ላይ እምነት እንዲሰርፅባቸው ለማድረግ ምርጫን በታቀደለት ጊዜ ብቻ ማካሄድም በቂ ነው ብሎ ማሰብ ተገቢ እንዳልሆነ ያሰምሩበታል::
የምርጫው መካሄድ ብቻውን ወሳኝ አይደለም:: ይልቅስ ምርጫው ሰላማዊ፣ ነፃ እና ፍትሃዊ በሆነ መልኩ እንዲካሄድ ማድረግ የግድ እንደሚል አፅእኖት ይሰጡታል:: ምክንያቱ ደግሞ ምርጫው በወቅቱ ቢካሄድም ሂደቱ ግልፅ እና ተአማኝነት የተነፈገው ከሆነ ውጤቱ ያላስደሰታቸው ወገኖች ሰላምን ማደፍረሳቸው አይቀሬ ነው::
ድህረ ምርጫው ለኢንቨስትመንት ጤናማነት እጅግ ወሳኝ ነው:: በአንዳንድ አገራት የምርጫ ድምር ውጤቶችን ተከትሎ ሁነቱ ተጭበርብሯል የሚል አመለካከት ያላቸው ዜጎች በሚፈጥሩት ሁከት ኢንቨስትመንት አደጋ ይደቀንበታል:: በዚህ ረገድ የሚከሰት ቀውስም ነባር ኢንቨስትመንቶች ጉዳት ሲደርስባቸው አዲስ ለመግባት የወሰኑትም እርምጃቸውን እንዲመልሱ ያስገድዳል::
የምጣኔ ሀብት ምሁሩ፣ ኢንቨስትመንት ለማጎልበት ምርጫን በወቅቱ እና ሰላማዊ፣ ግልፅ እና ተአማኝነቱን በጠበቀ መልኩ ማካሄድ ብቻውን ማስተማመኛ እንዳልሆነም ያስረዳሉ:: ከራስ በላይ አገርን የሚያስቀድሙ ባለድርሻ አካላት እና ግለሰቦችን አርቆ አስተዋይነት እንደሚጠይቅም ያሰምሩበታል::
በዚህ ረገድም ገዢውም ሆነ ተፎካካሪ ፓርቲዎችም የሚወዳደሩት አገርን ለመለወጥና ለማልማት እስከሆነም ኢንቨስትመንት ለማጎልበት በምርጫ ሁነት መሸነፍ እና ማሸነፍ እንዳለ ጠንቅቀው በመገንዘብ፣ ውጤቱምን በፀጋ መቀበል እንዳለባቸውም ሳያስገነዝቡ አላለፉም::
ዶክተር ቆስጠንጢኖስ በርኸ እንደሚያስረዱት ከሆነ ደግሞ፣ ኢንቨስተሮች በአንድ አገር መዋዕለ ነዋያቸውን ፈሰስ ከማድረጋቸው አስቀድሞ የሚፈልጉትን አገር የኢኮኖሚ እድገት ፍጥነት እንዲሁም አቅም፣ አገሪቱ ኢንቨስትመንትን ለማጎልበት የሚያስችል ውጤታማ ፖሊሲ ባለቤት ስለመሆኑ ያጤናሉ:: ዓለም አቀፍ እና ግዙፍ የኢኮኖሚ ተቋማት የሚያወጣቸውን መረጃዎች ያገላብጣሉ::
‹‹ከዚህ በላይ ግን የአገሪቱን የፖለቲካ ምህዳር እና የሰላም ሁኔታ ይቃኛሉ፣ ምርጫ ደግሞ የፖለቲካ ምህዳር ከፍታ እና ዴሞክራሲያዊ አገር የመሆኑ አንዱ ምስክር ነው›› የሚሉት የምጣኔ ሀብት ባለሙያው፣ ምርጫ የሚራዘመው አገራት ሁነቱን ለማካሄድ የማያስችል ከባቢ ሲኖራቸው መሆኑን ያወሳሉ::
ባሳለፍነው ዓመት የፖለቲካ ምስቅልቅል ብሎም የኮሮና ቫይረስ በዓለም አቀፍ ደረጃ የተለያዩ አገራት ምርጫ እንዳይካሄድ ምክንያት ሲሆኑ መስተዋሉን የሚጠቁሙት ዶክተር ቆስጠንጢኖስ፣ ወረርሽኙ በኢትዮጵያ ሊካሄድ የነበረውን ምርጫ እንዲራዘም ማስገደዱን ያስታውሳሉ:: ይህ ክስተትም በአገሪቱ ማህበራዊ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ኡደት ላይ የራሱን ጫና አሳድሯል ይላሉ::
ይሁንና አገሪቱ ስድስተኛውን አገራዊ ምርጫ ካካሄደች በኋላ ነገሮች በእጅጉ እንደሚሻሻሉ በተለይ የሰላም እና የፀጥታው ሁኔታ መልክ እየያዘ ሊስተካከል እንደሚችል ያመላከቱት ዶክተሩ፣ ምርጫውም በታቀደለት የጊዜ ሰሌዳ ይካሄዳል የሚል ግምት እንዳላቸውም ነው የጠቆሙት::
ምርጫው ሰላማዊ በሆነ መልኩ ተከናውኖ ከተጠናቀቀም ውጤቱ የውጭ ኢንቨስተሮችን ትኩረት እና እምነት ለመሳብ እንዲሁም የአገር ውስጥ ተዋናዮቹም ይበልጥ በሙሉ አቅም ወደ ሥራ እንዲገቡ የማድረግ አቅሙ ከፍተኛ እንደሚሆን አፅእኖት የሚሰጡት የምጣኔ ሀብት ባለሙያው፣ በተለይም ‹‹ከከተማ ወጥተው በማዕድን እና በእርሻ ኢንቨስትመንት ላይ የተሰማሩትን ከስጋት ያላቅቃልም ነው›› ያሉት::
በአጠቃላይ የምጣኔ ሀብት ምሁራኑ፣ ‹‹ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የተገነባባት፣ ፍትህ የነገሰባት፣ እኩልነት የሰፈነባት እንዲሁም በሁሉ ረገድ የበለፀገች ኢትዮጵያን ለመፍጠር ነፃ ግልፅ እና ፍትሃዊ ምርጫ ማካሄድ ይኖርብናል። ይህን ስናደርግም ኢትዮጵያን በማህበራዊ በኢኮኖሚ እና በፖለቲካ የላቀ ደረጃ ካላቸው አገራት ተርታ ለማሰለፍ የሚያዳግት አይሆንም ነው›› ያሉት::
ታምራት ተስፋዬ
አዲስ ዘመን ሚያዚያ 20/2013