አስመረት ብስራት
ታሪኩ ከተፈፀመ አንድ መቶ ሃምሳ አመታት አልፈዋል። ጊዜው በአፄ ቴዎድሮስ ዘመነ መንግስት በ1830ዎቹ መጀመሪያ ግድም እንደነበር ይነገራል። ይህ ዘመን ህግ እንደ ውሃ የቀጠነበት፤ ተፈጻሚነቱም ኃያልና ጠንካራ የሆነበት ብርቱ ዘመን ነበር። በተለይ በሴቶች ላይ የሚወጡ ባህላዊ ህጎች በወንዶች የበላይነት ብቻ የሚመሩ በመሆናቸው ሴቶች በጭቆና ቀንበር የመውደቃቸው እውነታ ግድ ይል ነበር። ሴቶችን እግር ከወርች ያሰረው ህግም ብዙ ሴቶችን ያንገፈግፍ ነበር።
የዚህ ግፍ መጨረሻ የራቀባት አንድ ሴት ግን ተገኘች። ይች ሴት ቃቄ ወርድወት ትባላለች። የቃቄ ወርድወት የጉራጌ ምድር ያፈራቻት ውብና ጠንካራ ሴት ነበረች። በዘመኑ በሴቶች ላይ የሚደርሰውን የባህል ተፅዕኖና የወንዶች የበላይነትን በመቃወም ከአስር በላይ የመብት ጥያቄዎችን ይዛ የታገለች የለውጥ አርበኛ ስለመሆኗም ታሪኳ ይመሰክራል። ወርድወት አባቷ ቃቄ የኦርቶዶክስ እምነት ተከታይ፤ የወለኔ ቤተ ጉራጌ ተወላጅ፤ እናቷ አጀት አሚና ደግሞ ከሙስሊም የዘር ሀረግ የሚመዘዙ ሴት ናቸው።
የቃቄ ወርድወት የራሷን ህይወት መነሻ በማድረግ ትግልን ከቤቷ ጀምራ አደባባይ በመውጣት «በደል ይብቃ» ስትል ሌሎች አቻዎቿን ጭምር ለለውጥ አነቃንቃለች። ይህ ታሪክ በዛ ዘመን ይፈፀማል ተብሎ በማይታመንበት አጋጣሚ ወርድወት በርካታ ሴቶችን አስከትላ አጉል ባህል፣ የጋብቻ ተፅዕኖና በሴቶች ላይ የሚደርስን ጥቃት ለመታገል ብርሃን ፈንጥቃለች። የሥርዓተ ፆታ በደልን ለማስቆምም የሰላማዊ አመፅ ንቅናቄን መርታለች።
ከአንድ መቶ ሃምሳ አመታት በፊት በጉራጌ ምድር የሆነውን እውነታ ዛሬ በመላው ኢትዮጵያ እየታየ ያለው የሴቶች ወደከፍታ መውጣት መሰረት መሆኑ ይታያል። የቃቄ ወርድወትን አነሳን እንጂ ሁሏም ሴት በተሰማራችበት ዘርፍ የጀግና ጀግና መሆኗ የታየበት ሁሉም ሴት ድርብርብ ክህሎት ተፈጥሮ የለገሰቻቸው መሆኑን ዛሬም በኛ ዘመን ብቅ ብቅ የሚሉ ጀግኖች ምሳሌ ናቸው።
ከእነዚህም መካከል የልጅነት ምኞቷ እውን የሆነላት፤ ፍላጎቷን ገና በአፍላው የወጣትነት እድሜዋ መጀመሪያ በድል እንዲታጀብ ያደረገች ወጣት ናት። ተወልዳ ያደገችው ደቡብ ክልል ሀዋሳ አካባቢ ነው። ሁልጊዜ ከትምህርት ቤት ስትመለስ ወታደራዊ ሰላምታ ለእናቷ በማቅረብ ነበር ወደ ቤት የምትገባው። አስረኛ ክፍል ተፈትና የውትድርናን መንገድ ምርጫዋ ያደረገችው የዛሬዋ እንግዳችን የአስራ ዘጠኝ አመት ወጣት ናት።
ከልጅነቷ ጀምሮ ውትድርና ምኞቷ መሆኑን የምትናገረው ወታደር ገነት ዮሀንስ በሰላም ማስከበር ሂደት ውስጥ ተሳታፊ ነበረች። ወጣትነትና የሀገር ፍቅር በሚያንቀለቅለው ወኔ ውስጥ ሆና ከተሰው ሰዎች ላይ ጥይት በመሰብሰብና በማከፋፈል በተሰለፈችበት ግንባር ጀብዱ የፈፀመች ጀግና ነች።
ሰማንያ ሁለት ሚሊ ሞርተር ተኳሽ የሆነችው ይህች ወጣት በሸክም ሆነ በተኩስ ከማንም የማያንስ አቅም እንዳላት ትናገራለች። በተሰማሩበት የውትድርና ዘርፍ ድል ለማግኘት በቁርጠኝነት የተዋጋች መሆናን ነው የምትናገረው።
ገነትና ጓደኞቿ በሚናገሩበት ወቅት ከድምጿ ጋር የሚደመጠው ወኔና የሀገር ፍቅር ስሜት ልብን ይገዛል። መሰረታዊ ወታደር ገነት በተሰማራችበት አውደ ውጊያ መሳሪያ ለጨረሱ ጓደኞቿ መሳሪያ በማቀበል በማስተባበርና በታላቅ ፅናት የታገለች አፍላ ወጣት ነችና ጀግና መባል ይገባታል በማለት የዘንድሮው የአለም የሴቶች ቀን በሚከበርበት ወቅት እውቅና ተሰጥቷታል።
በዚሁ ላይ ክፍለ ጦሯ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የተፋላሚውን ምሽግ ለመስበር በሚያደርገው ትንቅንቅ ላይ የቀኝ እግሯን ስትመታ ህክምናን ሳይሆን ወደፊት መጓዝን መርጣ የቆሰለ እግሯን አስራ በመፋለም አኩሪ ትግልን ያደረገች ምክትል አስር አለቃ ሂሩት አዲሱን እናገኛለን።
ምክትል አስር አለቃ ሂሩት ምሽግ ለማስለቀቅ በሚደረግ ፍልሚያ ላይ ተራራውን ወደ ላይ እየወጣች በምትፋለምበት ወቅት ነበር እግሯ ላይ ጉዳት የደረሰው። የሴትነት ድካም ብሎም ቁስለኝነት ሳያግዳት ለቆመችለት አላማ ሞትን መርጣ እግሯን በጨርቅ አስራ በመፋለሟ ጀግና መባል ሲያንሳት ነው ተብሎ በዚሁ እለት ለእሷም እውቅና ተሰጥቷታል።
የሴቶቻችን አኩሪ ገድል እየተተረከ ሽልማት ከተበረከተላቸው መካከል አስር አለቃ ኑሪያ አወል ትገኛለች። አስር አለቃ ኑሪያ ሰሜን እዝ ላይ በግዳጅ ላይ እያለች ነበር ለአንድ ተልእኮ ወደ ሌላ ቦታ የተላከችው። እሷ ተመልሳ እንደመጣች ስለሆነው ነገር ምንም አይነት መረጃ ሳይኖራት የመሳሪያ ዲፖ ላይ የጥበቃ ስራዋን እያከናወነች ባለችበት ወቅት መታፈኗንና መሳሪያዋን ማስረከብ እንዳለባት የተነገራት። ከእሷም ጋር የነበሩ ሰራዊት አባላት ሀይላቸውን ለማጠናከር ወደ ኤርትራ መጓዝ እንዳለባቸው ይነገራቸዋል።
“ትጥቅሽን ፍቺ ሲሉ ፈርሜ የተቀበልኩትን መሳሪያ ለማንም አልሰጥም፣ ከሞትኩም ከነመሳሪያዬ እሞታለሁ፤ ለሀገር መሞት ክብር ነው።” በማለት እዛው በፅናት በመጠበቅ ነፃ ከወጣች በኋላ በተለያዩ ግዳጆች ላይ ተሰልፋ በብቃት የተወጣች ጀግና ነች።
በጦር ሜዳ ላይ እያለችም አዛዧ በጥይት ተመትቶ ከፊቷ ሲወድቅ እሱን ከነትጥቁ ተሸክማ ያለምንም ድካም እስከወገን ጦር ድረስ ለማድረስ በጣም ከፍተኛ ፈተናዎችን አሳልፋለች። አዛዧ ህይወቱ ሳይተርፍ ቢቀርም በጥንካሬ በፅናት ወደ ሰራዊቱ ማድረስ በመቻሏ ጀግና ተብላለች።
በተለያዩ ግጥሞች መወድሶች የደመቀው ይህ መርሀ ግብር በሰላም ማስከበር ሂደቱ ቆስለው በህክምና ላይ ያሉ ሴቶችን ያከበረ፤ በጀግንነት ጀብዱ የፈፀሙ ወጣቶችን የተረከ ነበር። ሶስት ቀንና ሶስት ሌሊትን የያዘችውን መሳሪያ ላለማስነጠቅና ላለመማረክ ስትል ራስዋን አፈር ውስጥ ቀብራ ከላይዋ መድፍ እየተተኮሰ የሰነበተች፤ ለቀናት ያለ ምግብና ያለ ውሃ ተራራን አቋርጣ የጀግንነት ተጋድሎ የፈፀመች፤ ሀገሬን አልከዳም በማለት እስከ መጨረሻው የደም ጠብታ የተፋለመች፤ ብቻ የሴትነትን ቆራጥነት በአውደ ውጊያ ላይ ያስመሰከሩ በርካታ ወጣት ሴት ወታደሮች እውቅና ተሰጥቷቸዋል።
በራሷ ተነሳሽነት ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ መሳሪያ በማጓጓዝ፤ ግዳጇን በብቃት በመወጣት፤ ስለሀገር ሲሉ የወደቁትን በመርዳት፤ ውሃ ለምና ውጊያው እንዳይቋረጥ በማጠጣት ጀብዱ የፈፀመችው ደግሞ ጀግናዋ አስር አለቃ ፀጋነሽ ያጎ ናት። ከሷም በተጨማሪ ስርቃ በሚባል ቦታ አንድ ምሽግ ውስጥ ሆኖ የሰራዊቱን እንቅስቃሴ በከባድ ተኩስ ሲያስቆም የነበረን ወታደር አነጣጥራ በመምታት ህይወቷን ለአደጋ አጋልጣ ሌሎችን የታደገች ጀግና መሰረታዊ ወታደር ወይንሸት ነገኦ ናት። በወጣት ሴት ጉልበታቸው በአልበገርነት ስሜት ለፈፀሙት ጀብድ እውቅና የተሰጣቸው እነዚህ ወጣቶች ዛሬም የሀገር ፍቅር ያላቸው ወጣቶች ማሳያ መሆናቸው ተነግሯል።
ሰሞኑን በመከላከያ ሰራዊት የሴቶች ጉዳይ ዳይሬክቶሬት አለም አቀፍ የሴቶችን ቀን (ማርች 8) አስመልክቶ በመኮንኖች ክበብ ያዘጋጀው መርሀ ግብር ገና ከመግቢያው ደማቅ እንደሆነ ያስታውቅ ነበር። መለዯቸውን በአግባቡ የለበሱ የመከላከያ ሰራዊት አባላትና የማርሽ ሙዚቃ አባላት ቦታ ቦታቸውን ይዘዋል። የሰራዊቱን የጀግንነት ውሎ የሚያሳይ የፎቶ ኤግዚቢሽንም እየተጎበኘ ነበር።
̋̋ጀግኖቻችንን እወቁልን አክብሩልን” በሚል መሪ ቃል በሀገራችን ለአርባ አምስተኛ ጊዜ የተከበረው የሴቶች ቀን የመከላከያ ሰራዊት አባላት የሆኑ ሴቶች በተለያዩ ተጋድሎዎች በጀግንነት ላደረጉት ተጋድሎ ምስጋናን አቅርበዋል። ከምስጋናውም ባሻገር የምስክር ወረቀትና የተለያዩ ሽልማቶች ተበርክቶላቸዋል።
የመርሀ ግብሩን በንግግር የከፈቱት ሜጀር ጄነራል ጡርዬ አሰፌ እንደተናገሩት ከጥንት ጀምሮ ሴቶች ሀገር በመምራት የሚታወቁ ሲሆን በአድዋ ታላቅ ገድል የፈፀሙት እቴጌ ጣይቱ ተጠቃሽ ናቸው። ዛሬ የእቴጌ ጣይቱ የልጅ ልጆች በሰላም ማስከበሩ ሂደት ላይም ታላቅ ገድል ፈፅመዋል።
ሴቶች ከወንዶች እኩል በመሰለፍ የሀገርን ዳር ድንበር ለማስከበር መስራት ከመቻላቸውም ባሻገር በተሰለፉበት ቦታ እንደ እናት፣ እንደ እህት የተለያዩ በጎ ተግባራትን መፈፀማቸው ድርብርብ ድል እንደሚያጎናፅፋቸው አስረድተዋል።
የመርሃ ግብሩ አካል የነበረው የፓናል ውይይት ላይ የተናገሩት የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ሴቶች ወጣቶችና ህፃናት ሚኒስቴር ወይዘሮ ፌሰል አብዱላሂ በበኩላቸው ትናንት በጣት የሚቆጠሩ ነገር ግን አመራር ቦታ ላይ የነበሩ እናቶቻችን በጠረጉት መንገድ ላይ ዛሬ በርካታ ሴቶች እስከ ሀገር መሪነት ድረስ በእኩልነት መራመዳቸውን ተናግረው የትናንቱን በማክበር ነገ ለሚከተለው ትውልድ የሚነገር ታሪክ መስራት እንደሚገባ አሳስበዋል።
የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ወይዘሮ መኣዛ አሸናፊ፤ የሴቶች ወጣቶችና ህፃናት ሚኒስቴር ወይዘሮ ፌሰል አብዱላሂ፣ የተለያዩ የመንግስት ባለስልጣናትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በመርሀ ግብሩ ላይ ተገኝተዋል። እያንዳንዱ ከጥንት ጀምሮ የተካሄደው የሴቶች እርምጃ ለሁሉም ሴቶች ዛሬ ላይ ለደረሱበት ስኬት መሰረት ነውና እኛም የግዜያችን ጀግና እንሁን ይላሉ።
ጀግንነት በአውደ ውጊያ ብቻ ሳይሆን በተሰማራንበት በእያንዳንዱ የስራ ዘርፍ ሀላፊነታችንን በብቃት ተወጥተን ለነገው ትውልድ የሚነገር ታሪክ እናኑርላቸው። ትላንት ካልኖረ የለም የፊቱ ነውና ትናንት የቆምንበትን እያከበርን ዛሬ ላይ የቆምንበትን ለልጆቻችንና ለልጅ ልጆቻችን ትናንትን በሚገባ እንፃፍላቸው። ጀግንነት የሚኖሩት ነውና በተፈጥሮ የተሰጠንን የጀግንነት ፀጋ አክብረን እንኑረው የዛሬው መልእክታችን ነው።
አዲስ ዘመን መጋቢት 5 ቀን 2013 ዓ.ም