አስመረት ብስራት
ወቅቱ እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር 1908 ነበር። በኒውዮርክ ከተማ ነዋሪ የሆኑ 15 ሺ ሴቶች የተሻሻለ የሥራ ሰዓትና የደመወዝ ክፍያን እንዲሁም የመምረጥ መመረጥ መብታቸው እንዲከበር አደባባይ ወጡ። ከአንድ ዓመት በኋላም የአሜሪካ ማኅበራዊ ፓርቲ ዕለቱን የሴቶች ብሔራዊ ቀን በማለት አወጀ። እ.ኤ.አ በ 1910 ላይ በዴንማርክ ዋና ከተማ ኮፐንሀገን በተካሔደው ዓለምአቀፋዊ የሴቶች ሠራተኞች ኮንፍረስ ላይ ክላራ ዚክተን በተባለች ሴት አማካኝነት ቀኑ ዓለምአቀፋዊ ቅርፅን እንዲይዝ ሐሳብ ቀረበ።
ኮንፈረንሱን ለመሳተፍ ከአስራ ሰባት ሀገራት የተውጣጡ ቁጥራቸው መቶ የሚሆን ሴቶችም ሀሳቡን በጄ አሉት። ይህንንም ተከትሎ ኦስትርያ፣ ዴንማርክ፣ ጀርመንና ስዊዘርላንድ እአአ በ1911 በዓሉን በማክበር ፈር ቀዳጅ ሆኑ። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሴቶች ቀንን እአአ በ 1975 በይፋ ሲያከብር በዓሉ ዓለምአቀፋዊ ይዘት ሊኖረው ቻለ። ከዚሁ ጋር ተያይዞም እአአ በ 1996 የተባበሩት መንግስታት ድርጅት “ያለፈውን በማሰብ የወደፊቱን እናቅድ “ የሚል መሪ ሀሳብ አክብሮትም ነበር።
በአሉ የፈረንጆቹ መጋቢት ወር በስምንተኛው ቀን የሚከበር ይሁን እንጂ ክላራ በተባለችው ሴት አማካኝነት ሐሳቡ ሲጠነሰስም የተቀመጠለት ቋሚ ቀን አልነበረም። የሴቶች ቀን ግን ሩሲያውያን ሴቶች እአአ በ1917 “ዳቦና ሰላም” በማለት ያነሱት የተቃውሞ እንቅስቃሴ የበለጠ ቅርፅ እንዲይዝ አድርጎታል።
ለአራት ቀናት የዘለቀው የተቃውሞ እንቅስቃሴና አመፅ በጁላዊያኑ የዘመን አቆጣጠር እሑድ የካቲት 23 የሩሲያውን ቄሳር የሴቶችን የመምረጥ መብት እንዲፈቅድ ያስገደደ ሲሆን በመንግሥት አስተዳደር ደግሞ እውቅና እንዲሰጥ ሆኗል። ይህ እንግዲህ በጎርጎሳውያኑ የዘመን አቆጣጠር መጋቢት 8 መሆኑ ነው።
የአለም አቀፍ የሴቶች ቀን ስለመከበሩ እንደመግቢያ ያነሳነው ያለ ምክንያት አይደልም። የቀኑን መከበር አስመልክቶ በኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት በሚታተምው አዲስ ዘመን ጋዜጣ ላይ በሚዘጋጀው ልዩ እትም ላይ የህይወት ተሞክሯቸውን እንዲያካፍሉን ለወጣቱ ትውልድ አርአያ እንዲሆኑን ከመረጥናቸው እንስቶች መካከል አንዷን ልናስተዋውቃችሁ በመሆኑ ነው።
ቀይ ደልደል ያለች ፍልቅልቅ ሴት ናት። ወደ ብዝሃ ህይወት ኢንስቲትዩት የእንስሳት ምርምር ዳይሬክቶሬት ቢሮ ጎራ ስንል በፍፁም ኢትዮዽያዊ አክብሮት ነበር የተቀበለችን። ወይዘሮ ሰብለ ስንቄ ተሰማ ትባላለች። በብዝሀ ህይወት ኢንስትቲዩት የእንስሳት ሳይንስ ባለሙያ ናት።
በምንጃር ሸንኮራ አካባቢ የተወለደችው ወይዘሮ ሰብለ አባቷ በቢሾፍቱ ከተማ በሚገኘው አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ደብረዘይት እንስሳት ህክምና ማዕከል ውስጥ የላብራቶሪ ባለሙያ ነበሩ። በዚህም እድገቷም እስካሁን ድረስ መኖሪያዋም ቢሾፍቱ ከተማ እንዲሆን አድርጎታል። ያደገችበት አካባቢ ግብርና ምርምርና የእንስሳት ክትባት ማምረቻ መካከል ሲሆን የአባቷን እግር እየተከተለች ምን አንደሚሰሩ ለመረዳት መሞከር የልጅነት ጊዜ ተግባሯ እንደነበር ትናገራለች።
ይች ልጅ ያልገባትን መጠየቅ ያገኘችውን ፅሁፎች ማንበብ ትጀምራለች። በዚህ ልቧ በመሳቡ የተነሳ የምርመር ስራን ለመስራት የሚያስችላት የትምህርት ደረጃ ላይ ለመድረስ የአስራ ሁለተኛ ክፍል ላይ የሚሰጠውን ሀገር አቀፍ ፈተና በጥሩ ውጤት ለማለፍ ትተጋ ነበር። ምንም እንኳን በተቻላት መጠን ከህልሟ ለመድረስ ብትታትርም ሀሳቧ ሳይሰካ ይቀርና በወቅቱ ማትሪክ እንዳልመጣላቸው በርካቶቹ ቤት ውስጥ መዋል እጣፈንታዋ ይሆናል።
ለቤተሰቦቿ አምስተኛ ልጅ የሆነችው ወይዘሮ ሰብለ በትምህርቷ ጎበዝ የደረጃ ተማሪ ከሚባሉት ተርታ ተሰልፋ የአባቷን ፈለግ ተከትላ በምርምር ስራው ትገፋለች ተብላ ተስፋ የተጣለባት ነበረች። ሀሳቧ ሳይሳካ ቢቀርም ቤት ውስጥ ሆና ስለመትወደው ነገረ ማጥናትን ምርጫዋ ታደርጋለች። ገና ትምህርታቸውን ያልጨረሱ ጓደኞች ስለነበራት እነሱን ለመሸኘት በሚል ሰበብ ከቤት ወጣ ብላ ንፋስ ትቀበላለች።
በዚህ አገጣሚ ነው እንግዲህ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የእንስሳት ህክምና ትምህርት ክፍል የፅዳት ሰራተኛ የሚፈልግ መሆኑን የሚገለፅ ማስታወቂያ በሩ ላይ ተለጥፎ የተመለከተችው። ሰው ተሰልፎ ስታይ ሄዳ ከተሰለፉት ሰዎች ፊት ትገባለች። ማንም ሳይቃወማት ወደ ውስጥ የገባችው ይቺ ልጅ የተሰጣትን ፈተና ታልፍና በፅዳት ሰራተኝነት ትቀጠራለች።
እሷ በተቀጠረችበት አጋጣሚ ደግሞ ፓቶሎጂ ላብራቶሪ ውስጥ የሚያፀዱት ሴት ለአንድ ወር እረፍት በመውሰዳቸው እሷ ቦታቸውን እንድትተካ ትመደባለች ። ይህ አጋጣሚ ከነፍሷ ጥሪ ጋር ያስተዋወቃት ሆኖ ይገኛል። ከልጅነቷ ጀምሮ ስታየው ያደገችውን ሙያ ልትማር እድል ተከፈተላት ።
ወይዘሮ ሰብለ ስራዋን እየሰራች በተጓዳኝ ደግሞ ላቦራቶሪ ውስጥ የሚሰራውን ነገር በሙሉ በአይነ ቁራኛ ትከታተላለች። የምታየውን ነገር ደግሞ ምን እንደሆነ ለማዋቅ መፃህፍትን ታገላብጣለች። ለተማሪዎቹ ማስተማሪያነት የሚሰሩ እያንዳንዱ የላቦራቶሪ ስራዎችን ፅሁፎች በማንበብ እራሷን ለማብቃት ከፍተኛ ሙከራንም አድርጋለች። ይህንን ጥረቷንና ጉብዝናዋን የተረዱ በምርምር ስራው ላይ ያሉ ዶክተር በጣም በመገረም ይህች ልጅ የላቦራቶሪ ረዳት ሆና እዚሁ መቅረት ይኖርባታል ብለው ሀሳብ ያቀርባሉ፤በወቅቱም ሀሳባቸው ተቀባይነት በማግኘቱ እርሷም በክፍሉ በረዳትነት እንድትሰራ ይደረጋል ።
ያኔ ባላት አቅም በአራት ኪሎ ዩኒቨርስቲ በዲፕሎማ የባዮሎጂ የትምህርት ክፍል ገብታ ፍላጎቷን ለመኖር አንድ ብላ ጀመረች። በዩኒቨርስቲ ውስጥ ቋሚ ሰራተኛ በመሆኗ የመማር እድል ማግኘቷን የምትናገረው ወይዘሮ ሰብለ፤ በዚህም ደስታ ሳይሰማት አሁንም ወደተሻለ ከፍታ ለመድረስ ጥረት ማድረጓንም ቀጥላለች። በአድቫንሰ ዲፕሎማው የትምህርት መረጃነት የመጀመሪያ ዲግሪዋን ለመማር አመልክታ በባይሎጂ እየሰራች ከተማረች በኋላም እዛው ከነበረችበት የስራ መደብ ሳትነሳ የተለያዩ ከፍ ያሉ ስራዎች እየሰራች እንድትቆይ ትደረጋለች። ‹‹ስራዬን ይወዱታል ክፍት የተባለ ቦታ በሙሉ እየመደቡ ያሰሩኛል፤ ነገር ግን ለስራዬ የሚመጥን ክፍያ ለመክፈል ወደኋላ ይሉ ነበር ›› የምትለው ወይዘሮ ሰብለ ሀላፊነት ወስዳ የምትመራው በብዙ ሚለዮኖች የሚገመቱ የሳይንሰ መሳሪያዎች መካከል እየዋለች ባገኘችው የትምህርት ደረጃ ያህል እንኳን አለመቀጠሯ ያስከፋታል።
ይህም ቢሆን እየተማርኩ ከሆነ ምንም ችግር የለም ብላ ባለችበት ዝቅተኛ ስራ ላይ ሆና ማሰተርስ ዲግሪዋን ለመማር ጥያቄ ታቀርባለች። በወቅቱ ከፍተኛ የመማር ፍላጎት ቢኖራትም ለግቢው ሰራተኛ ከመጀመሪያ ዲግሪ በላይ መማር አይፈቀደም ይባላል ። ነገር ግን እርሷ “ እኔ ተቋሙን እያገለገልኩ የተሻለ ቦታ እና ክፍያ አልያም የትምህርት እድል የማይሰጠኝ ከሆነ ›› በማለት ሌላ ስራ ማፈላለግ ጀመረች።
ምንም አይነት የላብራቶሪ ስራ ላይ ተመድባ ለመስራት የሚያቅታት ነገር እንዳልነበረ የምትናገረው ወይዘሮ ሰብለ ማንም ሰው ይሄንን እሰራለሁ እችላለሁ ካለ ያሰበው ደረጃ ለመድረስ በበቂ ሁኔታ ጥረት ማድረግ ነው እንጂ የሚያቅተው ነገር አይኖርም ትላለች። .ወይዘሮ ሰብለ በጥረቷ ያገኘችውን የላብራቶሪ ስራ ከፍ ባለ ደረጃና በተሻለ ደመወዝ ለመስራት በማሰብ ላይ እያለች የብዝሃ ህይወት ኢንስትቲዩት በእሷ ሙያና የትምህርት ደረጃ ማስታወቂያን አወጣ። ማስታወቂያውን እንዳየችም ጊዜ ሳታጠፋ በመመዝገብ የፈተናውን ቀን መጠባበቅ ጀመረች። የፈተናው ቀንም ከብዙ ሰዎች ጋር ተፈትናና ተወዳድራ አንደኛ በመውጣት በማይክሮ ዌብ የስራ ዘርፈ የመቀጠር እድልን አገኘች። በስራውም ውጤታማ ለመሆንና ላቅ ወዳለው ህልሟ ለመሸጋገርም የተለያዩ የምርምር ውጤቶችን በማንበብ በመስራት ብቃቷን አረጋገጠች። በብዝሃ ህይወት ኢንስቲትዩት በተቀጠረች በስድስተኛው ወርም የመጀመሪያ ዲግሪዋን ያዘች።
ከዚህ በኋላም በተቋሙ የእንስሳት ዳይሬክቶሬት ክፍል ውስጥ እንድታገለግል ተዘዋወረች። በክፍሉ ከሚገኙት ሶስት ማለትም የውሃ ውስጥ እንስሳት፤ የዱር እንስሳትና የቤት እንስሳት ላይ ተከፋፍሎ በሚደረግ ዝርያን መመርመርና ሊጠፉ የደረሱትንም ድጋሚ አራብቶ ወደ ማህበረሰቡ የማሰራጨት ስራ ይሰራል ።በሌላ በኩል ደግሞ መስክ በመውጣት በአንድ አከባቢ የብዝሃ ህይወት አይነት መረጃ መሰብሰብ መረጃውን ይዞ በመምጣት ለምርምር ምቹ ሁኔታዎች መፍጠርም ይሰራል። ለምሳሌ የሀገራችን ዶሮዎች እርሻ ውስጥ ሲጭሩ ውለው የማይታመሙ ፣የሚሰጡት እንቁላል ራሱ ጣፋጭ ሆኖ እያለ የውጭ ሀገር ዶሮዎች በብዛት ወደ ሀገሪቱ በመግባታቸው ምክንያት የአበሻ ዶሮዎች ዝርያ እየተመናመነ ነው። ይህ እንዳይጠፋ ብዝሃ ህይወት ዘር የመሰብሰብ፣ በማባዛትና በማኖር ስራ ውስጥ ደግሞ ወይዘሮ ሰብለ ተሳታፊ ናት።
ህብረተሰቡ ከጥንት ይዞት የመጣውን የራሱን ተፈጥሮን የመንከባከብ አሰራር እያሳደገ እንዲሄድ ለአርሶ አደሮች የተለያዩ ስልጠናዎችና ትምህርትም ይሰጣል። በመሆኑም አሁን ላይ ወይዘሮ ሰብለ በኢንስትቲዩቱ የምርምር ሰራተኛ ሆና እየሰራች ትገኛለች። ኢንስቲትዩቱ በሰጣት የትምህርት እድል “አኒማል ፊዝዮሎጂ” የትምህርት ክፍልን ተቀላቀለች። አሁን የማስትሬት ዲግሪ ትምህርት ላይ ብትሆንም ገና ያልበረደ፣ ያልረካ የመማር ፈላጎት በውስጧ ይንቦገቦጋል።
‹‹የፅዳት ሰራተኛ ሆኜ መነሳቴን እናገራለሁ ብዬ የማስበው ፒኤች ዲግሪዬን ሲይዝ ነበር። በመሃል አንቺ መጣሽና ሚስጥሬን አስወጣሽኝ›› የምትለው ወይዘሮ ሰብለ፤ የሰው ልጅ ምንም ነገር ቢሆን ለማወቅ ፈልጎ የሚሳነው ነገር አለመኖሩን ትናገራለች። በጥረት ስኬት ላይ መድረስ የሚቻል መሆኑን ሯሷን እንደምሳሌ እያቀረበች ታስረዳለች።
ባለትዳርና የሁለት ልጆች እናት መሆኗን የምትናገረው ወይዘሮ ሰብለ፤ ከመኖሪያዋ ቢሾፍቱ አዲስ አበባ እየተመላለሰች መስራቱ የእለት ከእለት ጉዞ አድካሚ ከመሆኑ ባሻገር፤ ልጆቿን ለማሳደግ የሳላፈችውን ፈተና ትጠቅሳለች።
ከቢሾፍቱ አዲስ አበባ ድረስ መጥታ ስትሰራ ለልጆቿ ከሌሊቱ አስር ሰዓት ተነስታ ምግብ አዘጋጅታ የተለያዩ የቤት ውስጥ ሀላፊነቶችን ተወጥታ በትራንስፖርት አዲስ አበባ ገበታ ደግሞ በምሽት ወደ ቢሾፍቱ መመላለስ ለመስራትና ለማደግ ከምትከፈላቸው ፈተናዎች ጥቂቶቹ ናቸው። አሁን ልጆቿ የሰባተኛና የስድስተኛ ክፍል ተማሪ ሆነው እናታቸውን በመረዳት ላይ ያገኛሉ። ለስምንት አመታት የቀጠለው ምልልስ በተለይ ደግሞ ቤት ውስጥ የሚረዳት ሰው ሲጠፋ ፈታኝ ከመሆኑ ባሻገር ልጆቿ ተኝተው ስለምታገኛቸው ናፈቆቱም ከሚፈትኗት ነገሮች አንዱ መሆኑን ትገልፃለች።
‹‹ባለቤቴ ስራ ለማገዝ የተቻለውን ቢሞከርም መቼም የሀገራችን ባህል ሆነና ሴቷ የግድ የቤተሰብ ሀላፊነቱን መወጣት ስለሚኖርባት በጣም ይከበዳል።›› ትላለች። በጣም የሚገርመው ሴቶች ስራን ከሰሩ ከልባቸው እንደሚሰሩ ይታወቃል። ነገር ግን እድሉ በእጃቸው ላይ ሆኖ ባለማስተዋል የሚያልፉ መሆናቸው በጣም ይገርማል። ዩኒቨርሲቲ ውስጥ እየሰሩ የመማር እድሉ በእጃቸው ላይ ሆኖ በትንሽ ስራ ላይ እድሜ ልካቸውን የሚያሳልፉ ሴቶችን ስትመለከት እንደምታዝን ትናገራለች።
አዲስ ዘመን የካቲት 29/2013