ለምለም መንግሥቱ
በተመሳሳይ ዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ የአንድ አካባቢ እናቶች ናቸው፡፡ በህብረት ሆነው ሀር ሲያዳውሩ ነበር በሥፍራው የደረስኩት፡፡ ሥራቸውን የሚከውኑት እየተቀባበሉ በሚዘፍኑት ዘፈን አጅበው ነው፡፡ ስራው በዚህም መልኩ መሰራቱ ደግሞ ፍጥነት እንዲኖረው ከማድረጉም በላይ ሳይደክማቸው በተነቃቃ መንፈስ ብዙ እንዲያመርቱም የሚያስችላቸው ይመስላል፡፡ ግን ሴቶቹ በወላይትኛ ቋንቋ የዘፈኑት ዘፈን እኔ እንደገመትኩት አልነበረም፡፡ በጤና መታወክ በጋራ ሆነው ከሚሰሩት የሀር ትል ልማት ሥራና ከእነርሱም ለአንድ አመት ተለይተው ቆይተው በቅርብ ጤናቸው ተመልሶ ለተቀላቀሏቸው የሥራ ባልደረባቸውና የማህበራቸው መሪ ለሆኑት ወይዘሮ ሙሉነሽ ኤና የተሰማቸውን ደስታ እየገለጹላቸው ጎን ለጎንም ስራቸውን እያቀላጠፉ ነበር፡፡
‹‹ፍቅር›› የሚል ስያሜ ያለው ማህበር መሥርተው ወይዘሮ ሙሉነሽ ጋር ከአምስት አመት በላይ በጋራ የሀር ልማቱን ሲያከናውኑ ቆይተዋል፡፡ እኝህ አጋራቸው በጤና መታወክ ምክንያት በመለየታቸው አዝነው ነበር፡፡ ሀዘናቸው በደስታ በመለወጡ ነበር ወደ ሥራ የመመለሳቸውን ምክንያት በማድረግ ደስታቸውን በዘፈን ማቅረብ የወደዱት፡፡ በሀር ልማት ላይ የተሰማሩት የፍቅር ማህበር አባላት በጋሞ ዞን ምዕራብ አበያ ኡጋዩ ቀበሌ ነዋሪዎች ናቸው፡፡
የማህበሩ ሰብሳቢ ወይዘሮ ሙሉነሽ ኤና ከማህበሩ አባላት ጋር ሥለ ሥራቸው በቃላት ከመግለጽ ይልቅ በተግባር እንዳይላቸውና ምስክር እንድሆናቸው ነበር የመረጡት፡፡ ለሀገር ልማት የሚውለውን ትል ከማርባት ጀምሮ ያለውን በየተራ ባስጎበኙኝ ጊዜ ‹‹ሃምሳ ሎሚ ለአንድ ሰው ሸክሙ፣ለብዙ ሰው ጌጡ ነው›› እንደሚባለው አይነት ሆኖ ነበር ያገኘሁት ፡፡ ትሉ የሚፈለፈለው ቢራቢሮ ከሚባለው ነፍሳት ሲሆን፣ ከቢራቢሮው ትል እስኪገኝ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል ፡፡ የተፈለፈሉት ትሎች ከቀርከሃ እና ከእንጨት ውጤቶች በተሰራ ዝርግ ዕቃ ላይ ተደርገው ምግባቸው የጉሎ ቅጠል ይቀርብላቸዋል፡፡ በሙቀትና በቅዝቃዜ ለጉዳት ተጋልጠው የሀር ልማት ሥራው እንዳይስተጓጎል፣ የሚመገቡት የጉሎ ቅጠል እንደ እድሜያቸው እየተመጠነ ይሰጣቸዋል። ዕድገታቸውን እየተከታተሉ መጠኑን በመጨመርና ቢያንስ በቀን ሶስት ጊዜ በማቅረብም እንክብካቤ ይደረግላቸዋል፡ የሀር ልማት ሥራቸውን አንዲት ሴት ከፀነሰችበት ጊዜ ጀምሮ ወልዳ የልጇን ወግ ማዕረግ እስክታይ ድረስ ካለው ድካምና ትልቅ ኃላፊነት ጋር ያመሳስሉታል፡፡
ትሎቹ አምስት አይነት የዕድገት ደረጃ አልፈው ከ 45 እስከ 55 ቀናት እንክብካቤ በኃላ ነው ምርት የሚሰጡት፡፡ ሥራው በዚህ አያበቃም፡፡ ወደ ሀርነት ከተቀየረ በኃላ በደረቅና በፈሳሽ ሳሙና ይቀቀላል፡፡ በንጹህ ውሃ በደንብ ከፀዳ በኃላ ተጨምቆ በቤት ውስጥ በማስጫ ገመድ ላይ እንዲደርቅ ይደረጋል፡፡ ልክ እንደ ጥጥፍሬ ሆኖ በሀር ውስጥ የተደብለበለው በእነርሱ አጠራር “ፑፓው “ በቀላሉ ይላቀቃል፡፡ ሀሩም ተዳውሮ ወደክርነት ይቀየራል፡፡ ከዛም ለልብስ ዝግጁ ይሆናል፡፡ ይሄን ሁሉ ሂደት አልፎ ነው እንግዲህ ገቢ የሚያስገኘው፡፡
ወይዘሮ ሙሉነሽ እንደነገሩኝ ሀሩን አዳውረው ልቃቂት ገበያ ማቅረብ የጀመሩት በቅርብ ጊዜ ነው፡፡ ቀደም ሲል ያልተዳወረውን ነበር በኪሎ የሚሸጡት፡፡ተዳውሮና ሳይዳወር ለገበያ በሚቀርበው መካከል ያለውን የዋጋ ልዩነትና የትኛው አዋጭ እንደሆነ ያረጋገጡት አዳውረው ልቃቂቱን ለገበያ ማቅረብ ከጀመሩ በኋላ ነው፡፡ የተዳወረው በኪሎ እስከ 1ሺ 200 ብር ዋጋ ሲያወጣ ያልተዳወረው ደግሞ ግማሹን ያህል እንኳን ዋጋ አያወጣም፡፡ ምንም እንኳን አዳውረው በመሸጣቸው የተሻለ ተጠቃሚ ቢሆኑም አርባምንጭ ከተማ ላይ የሚገኘው ምርት ተቀባያቸው ብቸኛ በመሆኑ ከፍ ያለ ምርትን አምርተው የበለጠ ማግኘት አልቻሉም ፡ ፡ በመሆኑም ተቀባያቸው ከእነርሱ ሰብስቦ አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ለሚያስረክበው ለአልባሳት አምራች ድርጅት ቀጥታ ለማቅረብ፣ በረጅም ጊዜ ደግሞ በአካባቢያቸው ኢንደስትሪ በማቋቋም ሙሉውን የማምረት ሥራ በማከናወን ዕውቅና ለማትረፍ ነው ዕቅዳቸው፡፡
“የፍቅር” ማህበር አባላት 104 ሲሆኑ፣ ወይዘሮ ሙሉነሽ ከአካባቢያቸው በልማቱ ላይ እንዲሳተፉ ተመርጠው ስልጠና ወስደው የሀር ልማት ትሎቹን ዘር ተቀብለው ወደ ቤታቸው ሲመለሱ በጎረቤቶቻቸው ብዙ ትችት ደርሶባቸው እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡ ‹‹አንቺ ዘዋሪ፡፡ ትል ለቅመሽ መጣሽ፡፡›› የሚሉና ሌሎችን ነቀፌታዎች አስተናግደዋል፡፡ እርሳቸውም በወቅቱ ለሥራው ጀማሪ በመሆናቸው ምቾት ከማጣታቸውም በላይ እለወጥበታለሁ ብለው እንዳላሰቡ አልሸሸጉም፡፡ ነገር ግን ለሚደርስባቸው ትችት ጆሮ ሳይሰጡ ስራውን ለመሞከር ደፈሩ፤ ይህ ድፍረታቸው ገንጥሎ አልጣላቸውም እንደውም ዛሬ ላይ ተጠቃሚ ከመሆን ባለፈ ለሌሎችም አርአያ ለመሆን አብቅቷቸዋል፡፡ በወቅቱ ዳር ሆነው ሲነቅፏቸው የነበሩትም ዛሬ ማህበራቸውን ተቀላቅለው የጥቅሙ ተጋሪ ሆነዋል፡፡
“በመጀመሪያው የሀር ልማት ምርት ሰባት መቶ ብር ነበር ከሽያጩ ያገኘሁት፡፡ በወቅቱ ኪሎው 35 ብር ሂሳብ ነበር የሚሸጠው ፡፡ ይህን ያህል ብር ሲቆጥሩ የመጀመሪያቸው ስለነበር የብሩ መጠን አስደንግጦኝም ነበር ፡፡ በመቀጠል ግን ሶስት ሺ ብርና ከዚያ በላይ ሲገኝ ብዙ ሰርቶ በደንብ ተጠቃሚ ለመሆን ጥረት ማድረግ ጀመርኩ” ይላሉ ፡፡
ወይዘሮ ሙሉነሽ ጥቅሙን ስለተገነዘቡ በግላቸውም በቤት ውስጥ እያመረቱ ለገበያ ያቀርባሉ፡፡ ከልማቱ ሽያጭ የሚያገኙትን አጠራቅመው ይኖሩበት ከነበረው ጠባብ ቤት ወጥተው በሰፊ ቤት ለመኖር ችለዋል ፡፡ የሸቀጣሸቀጦች መሸጫ ሱቅም ከፍተዋል፡፡ ለልጆቻቸው በቂ ምግብ፣ የትምህርት ቤት ወጭና የሚፈልጉትን ሁሉ ለማሟላት አልተቸገሩም፡፡ የባለቤታቸውን እጅም አይጠብቁም፡፡ የሀር ልማቱ መተዳደሪያቸው ከሆነው የሙዝ ልማትና የበቆሎ ምርት ተጨማሪ መሆኑ ኑሮአቸው እንዲሻሻል እግዟቸዋል፡፡ በተለይ አምና አባያ ሐይቅ ሞልቶ የሙዝና የበቆሎ ምርታቸውን ሲበላሽ እርሳቸው የሀር ልማቱ በመኖሩ ችግርን ተቋቁመው እንዲያልፉም አግዟቸዋል፡፡
እንደ ወይዘሮ ሙሉነሽ ገለጻ ማህበራቸው በባንክ የቁጠባ ሂሳብ በመክፈቱ እስካሁን 120ሺ ብር ተቀማጭ ማፍራት ችሏል፡፡ ወደፊት የሀር ልማቱን በሚያከናውኑበት ቦታ መዝናኛ ክበብ በማቋቋምና ሌሎችንም ንግዶች ጎን ለጎን በማካሄድ ገቢያቸውን የማሳደግ ዕቅድ እንዳላቸውም ይናገራሉ፡፡
የሴቶቹን ጥረትና ውጤታማነት በማድነቅ ሀሳባቸውን የሰጡት በጋሞ ዞን ምዕራብ አባያ ወረዳ የእንስሳትና አሣ ሀብት ልማት ጽህፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሮ አስማማው አዋሽ ፤ የአካባቢው ሴቶች በተለያዩ ባህላዊና ወንዳዊ ተጽኖዎች ውስጥ ይገኛሉ፡፡ በየጓሯቸው ያለው የሙዝ߹ የበቆሎ ልማት የባልና ሚስት የጋራ ሀብት ሆኖ ሳለ ሴቷ ግን ምንም መብት የላትም፡፡ ድርብ ጋብቻ፣ ያለዕድሜ ጋብቻም የአካባቢው መገለጫ ነው፡፡ ሴቶቹ በሀር ልማት ላይ መሳተፋቸው ከሚደርስባቸው ተጽዕኖ ለመላቀቅ ከፍተኛ እገዛ እንዳደረገላቸው በሥራቸው በሚያደርጉት ድጋፍ ማረጋገጣቸወንም ይናገራሉ፡፡
አንዳንዶች መኖሪያ ቤት በመገንባት፣ የእርባታ እንስሳት በመግዛት የኢኮኖሚ አቅም መፍጠር ከመቻላቸው በተጨማሪ የትዳር አጋሮቻቸው ጥረታቸውን በማየት በሥራ እያገዟቸው እንደሆነም ተናግረዋል፡፡ በዚህ ከቀጠለ የተሻለ ለውጥ እንደሚመጣ ይገልጻሉ፡፡ ተቋማቸው ይሄን ለማስቀጠል አስፈላጊውን ክትትልና ድጋፍ እንደሚያደርግም ተናግረዋል፡፡
የፍቅር ሀር ልማት ማህበር አባላት የሚኖሩበት የኡጋዩ ቀበሌ የሥራ ቦታ በመሥጠቱ ፣የእነርሱን ማህበር ጨምሮ በጋሞ ዞን ውስጥ በማህበር ተደራጅተው በተመሳሳይ የሀር ልማት ሥራ ላይ ለተሰማሩ ሥራ ፈላጊ ወጣቶች ሙያዊ ሥልጠና በመሥጠትና ለሥራው አስፈላጊ የሆኑ ነገሮችን በማሟላት ደግሞ ከመንግሥት ጋር አጋር ሆኖ የሚሰራው የዓለምአቀፍ ሥነ ነፍስና ሥነምህዳር ምርምር (አይ ሲ አይ ፒ ኢ) ማዕከል እገዛ ማድረጉ ለውጤት አብቅቷቸዋል፡፡
ማዕከሉ ቀበሌው ባመቻቸው ቦታ ላይ ቤት በመገንባት፣ ለትሎቹ ማርቢያ የሚውለውን ከእንጨትና ከቀርከሃ የሚዘጋጀውን ግብአት በማቅረብና ሌሎች ድጋፎችንም በማሟላት ያልተቋረጠ ሙያዊ ድጋፍ እያደረገላቸው ይገኛል፡፡ ለሀር ልማት ሥራ የሚያገለግሉ ቁሳቁሶች በሀገር ውስጥ እንዲቀርቡ በአካባቢው በእንጨት ውጤቶች ሥራ ላይ የተሰማሩ ግለሰቦችን በማሳተፍ የቴክኖሎጂ ሽግግርን በማጎልበትም ማዕከሉ የሀር ልማት ሥራው እንዲጠናከር በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡ የማህበራቱን ሥራ ለማቃለልም በማዕከል አገልግሎት የሚሰጥ በኤሌክትሪክ ኃይል የሚሰራ የማድረቂያ ማሽንም ተክሎ አዘጋጅቷል፡፡
በደቡብ ክልል ጋሞ ዞን ምዕራብ አባያ ውስጥ የሽ በተባለው የሀር ልማት ፕሮጀክት ማዕከሉ እያከናወነው ሥላለው ተግባር በማዕከሉ የሀር እርሻ ሥራአስኪያጅ ዶክተር ሽፋ ባሎ እንዲህ ያስረዳሉ፡፡ በሀር ልማት ፕሮጀክት ውስጥ በመሳተፍ ላይ የሚገኙት 70 በመቶ ሴቶች ሲሆኑ፤ ወጣቶች ተሳታፊ ናቸው ፡፡ይህ የሆነው በብዙ ምክንያት ነው ያሉት ስራ እስኪያጁ የሴቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ ምቹ የሆነ ሥራ ለመፍጠር ፣የቤታቸው ሥራ ሳይስተጓጎል ከቤታቸውና ከመንደራቸው ሳይርቁ አልምተው ተጠቃሚ ለመሆን እንዳስቻላቸውም ይናገራሉ፡፡
እንደ ዶክተር ሽፋ በአመት እስከ ሰባት ዙር በማምረት ገቢ ማግኘት ስለሚያስችል የሴቷን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ከፍ በማድረግ በኩል ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ያስረዳሉ ፡፡ በተለይም የገጠሯ ሴት የአባወራዋን እጅ ከመጠበቅ የሚያላቅቃትና የውሳኔ አቅሟን ከፍ በማድረግ ልማቱ የጎላ ሚና አለው፡፡ ማዕከሉ በዚህ መልኩ በአካባቢው ሲንቀሳቀስ ስድስተኛ አመቱን ይዟል። ፕሮጀክቱ የሽና ሞይሽ በሚባል በደቡብና በአማራ ክልሎች የሚከናወን ሲሆን፣ ለ 12ሺ 500 ሥራ አጥ ወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር የተቀረጸ ነው፡፡
ከእነዚህ ውስጥ 2 ሺ አምስት መቶዎቹ በደቡብ ክልል በሀር ልማት፣ የተቀሩት በአማራ ክልል በማር ልማት የሚሳተፉ ናቸው፡፡ በሁለቱም ልማት ላይ ለሚሳፉት የሚሰጠው ግብአት በሥልጠና ማብቃት፣የሥራ መነሻና ለሥራ የሚሆን ቁሳቁስ ማሟላት፣ የገበያ ትስስር መፍጠር፣ ከሀር ልማቱ ጎን ለጎን በጓሮ አትክልትና በእንስሳት ልማት በማከናወን ተጨማሪ ገቢ እንዲያገኙም የዘር አቅርቦትና የተለያዩ ድጋፎችን ማድረግ ይጠቀሳል፡፡ እንዲህ ያለው ድጋፍ በቂ የሆነ መተዳደሪያ የእርሻ መሬት ለሌላቸው ኑሮአቸውን ለመለወጥ እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡ በተለይም ለሴቶች፡፡ ለሀር ልማት የሚውለውን የትል ዝርያ ከማዕከሉ በተጨማሪ መልካሳ ከሚገኘው የምርምር ማዕከል ጋር በመሆን የሚያቀርብ ሲሆን፣ ሀር በማልማት ላይ የተሰማሩት እንቅላል የማምረት ክህሎቱን በሥልጠና በማግኘታቸው ችግር አይገጥማቸውም፡፡
ደቡብ ክልል ውስጥ እየተከናወነ ያለው የሀር ልማት በሀገር ደረጃ ውጤታማ እንደሚሆንና ቀድመው የሀር ልማት ሥራ ውስጥ እንደገቡት ቻይና፣ ኮሪያ፣ ህንድና ሌሎችም ኢትዮጵያ በልማቱ ስሟ እንደሚጠራ ተስፋ አሳድሯል፡፡
አዲስ ዘመን የካቲት 29/2013