ብርሃን ፈይሣ
ጀግንነት፣ እናትነት፣ ደግነት፣ ሰው አክባሪነት፣ አዛኝነትና ተጫዋችነት አንድ ላይ ሲገኙ አንድ ሥም አላቸው፤ ይኸውም ደራርቱ ቱሉ ይሠኛል። የኢትዮጵያዊነት ባህሪ በትከክል ህያው ሆኖ የሚታየው በእርሷ መሆኑንም ብዙዎች ይስማማሉ። በስፖርቱ መንደር በተለይም በሴት የእርሷን ያህል ተጽዕኖ አሣዳሪና በክብር የተንቆጠቆጠች አትሌት አለች ለማለት አያስደፍርም። ከአትሌትነት እስከ ብሄራዊ ፌዴሬሽን አመራርነት፣ የአህጉር አቀፍ ማህበራት ሥራ አስፈጻሚ አባልነት እንዲሁም ከዓለም ተጽዕኖ አሣዳሪ ሴቶች መካከል በመካተት ሃገሯን በማስጠራት ላይ ትገኛለች። በመላው ዓለም ዛሬ እየተከበረ ያለውን ‹‹የሴቶች ቀንን›› አስመልክቶም ፍልቅልቋን አትሌት ኮሎኔል ደራርቱ ቱሉን መዘከርና ምሣሌነቷን ማጉላትም የግድ ይሆናል።
አፍሪካ በተለይም የምሥራቅ አፍሪካዎቹ ጎረቤት ሃገራት ኢትዮጵያ እና ኬንያ ከአትሌቲክስ ስፖርትና ድል ጋር ከመወዳጀታቸው አስቀድሞ የበላይነቱ በአውሮፕያዊያን አትሌቶች ቁጥጥር ሥር ነበር። በባርሴሎናው ኦሊምፒክ ግን ዓለም ያላየው አዲስ ታሪክ ተጻፈ፤ የ10 ሺህ ሜትር የሴቶች ድል እጁን ለአፍሪካ ሰጠ። በእርግጥ አፍሪካዊያን አትሌቶች በዓለም ቻፒዮናዎችና ኦሊምፒኮች ተሣታፊ ሲሆኑ፤ የመጀመሪያቸው ባይሆንም ከዚያ ቀደም አሸናፊነት ወደ እነርሱ አምርቶ ስለማያውቅ ቅድመ ግምቱን ያገኙት አውሮፓዊያኑ ነበሩ። ከሩጫው መጀመር አስቀድሞ የአትሌቶች ሥም ሲጠራ በውብ ፈገግታ ታጅባ ለተመልካቾች ሠላምታ ያቀረበችው ጠይሟን ወጣት አትሌት በተለየ ዓይን የተመለከታትም አልነበረም። ከሩጫው በኋላ ግን ‹‹ይቺ አትሌት ማን ናት፣ ከወዴትስ ናት?›› የሚለው የዓለም መነጋገሪያ አርዕስት ሆነ።
የደማቋ ኮከብ ትውልድ ሥፍራ፣ ዓለም ሚስጥሩን ለማወቅ የሚጓጓለት፣ ባለሙያዎች ጥናትና ምርምር የሚያደርጉበት፣ የፊልም ባለሙያዎች ዘጋቢ ፊልሞችን የሠሩለት፣ የሌላ ሃገር አትሌቶች በምኞት አሻግረው በሚመለከቷት የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ልብ በሆነችው በቆጂ ነው። አፈሩ፣ አየሩ፣ መልከ ዓምድሩ፣ ምግቡ፣ የአኗኗር ሁኔታው ሁሉ ለአትሌቶች ተመጥኖ የተዘጋጀ በሚመስልበት በዚህ የአትሌቶች ምንጭ በሆነ ሥፍራ ከልጅነቷ ጀምሮ ሩጫን ታዘወትር ነበር። እርግጥ ነው ከኑሮው ሁኔታ ጋር ተያይዞ ወደ ትምህርት ቤትም ይሁን ሌላ ሥፍራ ለማቅናት የእግር ጉዞና ሩጫ የመጀመሪያው አማራጭ ቢሆንም የደራርቱ ግን የተለየ ነበር። በሯጭነቷና በፍጥነቷ የተነሳም ከጓደኞቿ ‹‹ጥንቸሏ›› የሚል ቅጽል ሥምን አትርፋለች።
የስድስተኛ ክፍል ተማሪ ሣለችም በትምህርት ቤቶች መካከል በሚካሄደው ዓመታዊ የሩጫ ውድድር እንድትሣተፍ ተመረጠች። አሁንም ድረስ በዓለም አቀፍ ደረጃ ዝነኛ የሆኑ አትሌቶችን በመለየትና ለክብር በማብቃት ላይ የሚገኙት የሠውነት ማጎልመሻ መምህርና አሠልጣኝ የሆኑት ሥንታየሁ እሸቱ የያኔዋ የስድስተኛ ክፍል ተማሪ በሩጫ ያላትን ችሎታ አጢነው ነበር። ተሥፋ እንዳደረጉትም ጥንቸሏ ደራርቱ አሸናፊ ለመሆን በቃች። ይህ አሸናፊነት በየደረጃው እያደገ መጥቶ ብቃቷ በክለቦች ፍላጎት በማሣደሩ የማረሚያ ቤቶች ስፖርት ክለብ ትንሿን አትሌት በ1980 ዓ.ም የግሉ ለማድረግ ቻለ። በሃገር ውስጥ በሚካሄዱ ውድድሮች ተሣትፎዋ ለብሄራዊ ቡድን አባልነት ሲያሣጫት ከአንድ ዓመት በኋላ በዓለም አቀፍ ውድድር ላይ ተሣታፊ ለመሆን ቻለች። ከዚያም አልፋ ተሥተካካይ በሌለው የምድሪቷ ታላቅ የስፖርት ውድድር ኦሊምፒክ ላይ ሃገሯን እንድትወክል ተደረገ።
በተከታታይ በተካሄዱት የሎስአንጀለስ እና ሴኡል ኦሊምፒኮች ኢትዮጵያ ባለመሣተፏ በስፖርቱ የነበረው ሁኔታ መቀዛቀዝ አሣይቶ ነበር። በዚህ ወቅት የተካሄደው የባርሴሎና ኦሊምፒክም በወንዶች ሃገሪቷ ውጤታማ በሆነችበት 10 ሺህ ሜትር ሴቶችን ወክላ ደራርቱ ተሣታፊ ነበረች። በመድረኩ ልምድ የሌላት አትሌት በመሆኗም የሌላው ዓለም ቀርቶ ኢትዮጵያውያን የስፖርቱ ቤተሠቦችም የተለየ ግምት አልሰጧትም ነበር። ውድድሩ ከተጀመረ በኋላ ግን ታሪክ ተለወጠ፤ በአዲሲቷ አትሌት አሸናፊነት ማንቀላፋት የጀመረው ስፖርት ዳግም ንቃቱን አገኘ። የመጀመሪያውን የኦሊምፒክ ወርቅ ሜዳሊያ በማጥለቅም ከሃገሯ አልፋ ለአህጉሯ ሴቶችም ጭምር የይቻላል ተምሣሌት ሆነች።
በባርሴሎናው ድል ከፍተኛ ሞራል የተሠማት ደራርቱ በቀጣዩ ጊዜ ከባድ ልምምድ በመሥራትና በተደጋጋሚ ውድድር ማድረጓን ተከትሎ ጉዳት አስተናገደች። ከጉዳት መልስም ለአትላንታው ኦሊምፒክ የግል ውድድሮቿን በመግታት ጭምር ልዩ ዝግጅት በማድረግ ወደ ውድድሩ ሥፍራ አቀናች። ይሁን እንጂ ፈጣኗ አትሌት እንደለመደችው አሸናፊ ሣትሆን ቀረች። ይህንን ቁጭት በውስጧ እንደያዘች ከአራት ዓመታት በኋላ ለደራርቱ ሁለተኛ ለኢትዮጵያውያን ደግሞ በተገኘው ውጤት ቀዳሚ በመሆን ሁሌም ከዓይነ ህሊና የማይሠረዘው የሲድኒ ኦሊምፒክ ተካሄደ። ከአትላንታ ኦሊምፒክ ማግሥት የልጅ እናት ለመሆን የበቃችው ደራርቱ ከወሊድ መልስ ወደ ኦሊምፒክ ዝግጅት ነበር የገባቸው። አራት የወርቅ፣ አንድ የብር እና ሦስት የነሃስ በጥቅሉ ስምንት ሜዳሊያዎችን በማስመዝገብ በኢትዮጵያ የኦሊምፒክ ታሪክ ቀዳሚ በሆነው በዚህ ኦሊምፒክ ፍልቅልቋ ደራርቱ ውድድሩን ካደመቁት መካከል ነበረች። ከዓመታት በኋላም ወርቃማ ታሪክ በጻፈችበት ርቀት በድጋሚ የወርቅ ሜዳሊያ አጠለቀች፤ በወቅቱ የኢትዮጵያ ሕዝብ ብሄራዊ መዝሙር ሲዘመርም ማንባቷ እስካሁንም የማይረሣ ጉዳይ ነው።
ፍልቅልቋ ኮከብ ከተሣተፈችባቸው አራት ኦሊምፒኮች በሦስቱ ሁለት ወርቅ እና አንድ ነሃስ ስታጠልቅ፣ በኤድመንተን እና ጉተንበርግ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች ላይ ደግሞ የወርቅና ብር ሜዳሊያዎችን የግሏ አድርጋለች። ከዚህ ባሻገር በወጣቶች ቻምፒዮና፣ በሃገር አቋራጭ፣ በማራቶን እንዲሁም በአጫጭር ርቀት የጎዳና ላይ ውድድሮችም ተካፋይ በመሆን በርካታ አኩሪ ገድሎችን ፈጽማለች፣ ሜዳሊያዎችን እንዲሁም ሌሎች ሽልማቶችንም ሠብስባለች። በምታስመዘግበው ውጤት ከክለቧ ማረሚያ ቤቶች በየጊዜው የማዕረግ ዕድገት በማግኘትም የኮሎኔልነት ማዕረግ ላይ ደርሣለች። ከሩጫ ሕይወቷ ከተለየች በኋላም ከአትሌቲክሱ ያልተለየችው ደራርቱ በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት በመሆን ሥራ አስፈጻሚውን በመቀላቀል ስፖርቱን በመምራት ላይ ት ገኛለች።
ሰባት አሥርት ዓመታትን በተሻገረው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ እድሜ አትሌቶች ወደ ሥራ አስፈጻሚነት ሲመጡ ሁለት የሥልጣን ዘመኖች ተቆጥረዋል። ይህ ጊዜ ሲገመገመም ብዙዎች በሙሉ ድምጽ ድጋፋቸውን የሚሰጧት ደራርቱ ወደ ፌዴሬሽኑ መቀላቀሏን ተከትሎ የአትሌቶች ዋስ ጠበቃ መሆንዋ በእርግጥም የታየበት ነው ለማለት ያሥደፍራል። በስፖርቱ አመራርነት ከአስተዳደር ሥራዎች ባለፈ አትሌቶችን በማበረታታትና ከጎናቸው መገኘቷ እናትነቷን የሚያጎላ ነው። አትሌቶችና አሠልጣኞች በተመሣሣይ የአንድነት ሥሜት እንዲሠሩ በመካከላቸው መግባባትን ከመፍጠር ባለፈ ለአትሌቶች እጅግ ቅርብ በመሆን በደስታቸውና በሐዘናቸው ተካፋይ መሆኗ ይስተዋላል። በውድድሮች ላይ ተገኝታም ሆነ ከውድድር መልስ ለአትሌቶች አቀባበል በማድረግ እንዲሁም በውድድር ወቅት በግሏ ከፍተኛ ወጪ በማውጣት አትሌቶችን የምትደግፍበትና የምታበረታታበት መንገድም ከስፖርቱ የቅርብ ሰዎች በተደጋጋሚ የሚነሣና ደራርቱን ለየት የሚያደርጋት ነው።
በተለይ ስፖርቱን በሚመለከት የትኛውም ጉዳይ ላይ በቀናነት የምታበረክተው አስተዋጽኦም የሚያስመሰግናት ነው። ጥቂት ጊዜያትን ቀደም ብሎ አንዲት አትሌት ወደ ውድድር ለማቅናት በገጠማት የጉዞ መስተጓጎል ምንም እንኳን እኩለ ሌሊት ቢሆንም ደራርቱ በቦታው ተገኝታ ስህተቱ እንዲታረም ያደረገችበት መንገድ የሚያስመሰግናት ነው። በረጅሙ የአትሌቲክስ ስፖርት ታላላቅ ታሪክ ጽፈው ያለፉ አትሌቶችንና የስፖርቱን ቤተሠቦች በማስታወስ ያደረገችው ተግባርም እስካሁን ስፖርቱን ከመሩት ባለሙያዎች በልዩነት የሚያሥጠራት ይሆናል። ‹‹የባዶ እግር ትሩፋቶች›› በሚል ርዕስ በተካሄደው በዚህ ሥነሥርዓት ላይ ከሜልቦርን እስከ ሪዮ ዴጄኔሮ ኦሊምፒክ ድረስ ሃገራቸውን ለማሥጠራት የተጉ አትሌቶችን፣ አሠልጣኞችን፣ የቡድን መሪዎችን፣ የሕክምና ቡድኖችን፣ የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎችን ጨምሮ በብሄራዊ ቡድኖች ውስጥ የተካተቱ ልዑካንን በታላቅ ክብር ምሥጋና እና ሽልማት እንዲያገኙ ማድረጓ የቅርብ ጊዜ ትውስታ ነው። ከዕውቅና አሠጣጡም በተጓዳኝ የተዘነጉና የሚገባቸውን ክብር ሣያገኙ የቆዩ እንዲሁም በሕይወት ያለፉ ባለሙያዎችንና ቤተሠቦቻቸውን ካሉበት በማፈፈላለግ ለዚህ ደረጃ በማብቃቷም የስፖርቱ ባለውለታና በስፖርት ቤተሠብም ሁሌም ስትዘከር የምትኖርጭምር ያደርጋታል።
ከደራርቱ መልካም ምግባሮች መካከል አንዱ በግሏ የምታደርገው ለጋሥነት ሲሆን፤ የተቸገረን አይታ ማለፍ አይሆንላትም። የማይነጥፉት እጆቿ የተዘረጋላቸው በርካቶች ሲሆኑ፤ ጥቂቱን ለማስታወስ ያህልም ከቅርብ ጊዜው መነሣት ይቻላል። በኮሮና ቫይረስ ምክንያት ከወራት በፊት ብዙዎች ለከፋ ችግር በተጋለጡበት ወቅት ደራርቱ አሰላ ከተማ ከሚገኘው ሆቴሏ ለአንድ ወር ያህል ለችግርተኛ ወገኖቿ ማዕድ ሥታጋራ ቆይታለች። በአንድ ክለብ መርሃ ግብር ላይ በክብር እንግድነት ለመገኘት በመጓዝ ላይ ሣለችም በመንገድ ላይ ያጋጠማትን የክለቡ ደጋፊ የሆነ አካል ጉዳተኛ በተሽከርካሪዋ ወደ ሥፍራው በማድረስ ትተባበረዋለች። በመንገዳቸው ላይ በነበራቸው ጭውውትም ችግሩን አዳምጣ ማለፍን ሣይሆን ከጊዜያት በኋላ አስታውሳ ባለ ሦስት እግር የአካል ጉዳተኞች ተሸከርካሪ በማበርከት ደግነቷን አሣይታለች።
እአአ 2017 የቢቢሲ የዓለም 100 ተጽዕኖ ፈጣሪ ሴቶች ዝርዝር ውስጥም ደራርቱን አካቷታል። የዓለም አትሌቲክስ የምንጊዜም ምርጥ አትሌት በሚል በዓመታዊው ታላቅ የሽልማት ሥነ ሥርዓቱ ላይ የዕድሜ ልክ ሽልማት ያበረከተላት አትሌትም ናት ደራርቱ። ይህ ሽልማት በስፖርቱ የተለየ አስተዋጽኦ ላበረከቱ የስፖርቱ ሰዎች የሚሰጥ ሲሆን፤ በኢትዮጵያም ክብሩን ካገኙ ጥቂት ግለሰቦች መካከል አንዷ ከሴቶች ደግሞ ብቸኛው ናት ደራርቱ።
ኢትዮጵያ በስፖርቱ በአህጉር ዓቀፍ ደረጃ የማህበራት አመራርነት የነበራትን ሥፍራ ቀስ በቀስ በመልቀቋ ብዙዎች ይቆጫሉ። እንደ ቀደምት የስፖርት ጀማሪነትና የማህበራት መሥራችነቷ በሥራ አስፈጻሚ ደረጃ የነበራት ድርሻ እየተሸረሸረ ነው ይባል እንጂ ኮሎኔል ደራርቱ ግን በዚህ ረገድ የተሥፋ ጭላንጭል አሣይታለች። ይኸውም የአፍሪካ አትሌቲክስ ኮንፌዴሬሽን የቦርድ አባል ከመሆኗ ባሻገር በምሥራቅ አፍሪካ ቀጠና የአትሌቲክስ ማህበሩ ምክትል ፕሬዚዳንት በመሆን እያገለገለችም ትገኛለች።
አዲስ ዘመን የካቲት 29/2013