መልካምሥራ አፈወርቅ
ልዩ ማንነት ተመሣሣይ ዓላማና ግብ ከያሉበት አገናኛቸው። ሁሉም ከቤት ሲወጡ መድረሻቸውን ያውቁታል። በእናት አባት ምርቃት፣ በወዳጅ ዘመድ አጀብ ተሸኝተዋል። በልቦናቸው ደምቆ የተጻፈውን ውጥን ከግብ ማድረስ የልጅነት ህልማቸው ነበር።
ሦስት ናቸው። ሦስት ወጣት ሴቶች። በአንድ የዕውቀት ማዕድ እስኪገናኙ በመልክ ተያይተው አያውቁም። ሁሉም ከቤታቸው ርቀው ከወላጆቻቸው ተሠናብተው መንገድ ጀምረዋል። ውስጣቸው ነገን ያልማል። ነጋቸው በሌላ ነገ እየተተካ ያስባሉ። ጉዟቸው ወደጅማ ዩኒቨርሰቲ ያቀናል። በዚህ ሥፍራ ዕውቀት ይሸመታል። አቅም ይፈተናል፣ ምርትን ከግርዱ እንደመለየት ጊዜው ሲደርስ ጎበዝ ከሠነፉ ይነጠላል።
ከቤት ሲርቁ ሆድ መባሱ አይቀሬ ነው። አያውቁት አገር ሲሄዱ ጭንቅ ጥብብ ይላል። የእናት ጓዳ፣ የቤት እንጀራ ቢናፍቅ አይገርምም። እንዲህ ሲያጋጥም ‹‹ይሁን›› ብሎ መቻል ግድ ነው። ለምን? ካሉ በዚህ ቦታ የሩቅ ዓላማ አለ፤ ግቡ ሩቅ፣ ፍሬው ወርቃማ የሆነ ድንቅ ዓላማ።
ቀጋ ለቃሚዋ
ሐብታም አበባው የደብረታቦር ልጅ ነች። ‹‹ልዑል ሚካኤል›› ከሚባል አነስተኛ ቀበሌ ተወልዳ አድጋለች። ሐብታም አምስተኛ ክፍል እስክትደርሰ ሠነፍ ከሚባሉ ተማሪዎች ትመደብ ነበር። በፀባይዋም ቢሆን በረባሽነቷ የሚለይዋት ብዙ ናቸው። የዚያኔ በትምህርት ሰዓት አቋርጣ ትወጣና የዱር ፍሬ ትለቅማለች። አጋምና ቀጋ እየበላችም በሜዳ ስትሮጥ ትውላለች።
ሐብታም ስድስተኛ ክፍል ስትደርሰ ነባር አመሏ ተቀየረ። የጣለችውን ደብተር አነሣች። ጠዋት ማታም ለጥናት ጊዜ ሰጠች። የዓመቱ መጨረሻ ላይ ከክፍሉ ተማሪዎች በውጤት በልጣ አንደኛ ሆና አለፈች። አስተማሪዎቿ አደነቋት። ወላጆቿ ተደሰቱ። እሷም ልቦና ገዛች። እንዲህ በሆነ በዓመቱ ውጤቷ ተመሣሣይ ሆነ። ቀጣዮቹን ጊዜያት ተመሣሣይ ታሪኮችን ደገመች።
ይህን ያዩ አባት በወላጆች ስብሰባ ሲታደሙ የልጃቸውን ጉብዝና ተረዱ። በየጊዜውም ሐብታምን አሥር ብር መሸለም አስለመዱ። ሐብታም በሽልማቱና በትምህርት ውጤቷ ደስታ ተሠማት። ብሯን በጉያዋ እያኖረች የቀጣይ ዓመታት ጉብዝናን አለመች።
ሐብታም አሥረኛ ክፍል ስትገባ ትምህርት ቤት ልትቀይር ግድ ሆነ። ማልዶ መነሣት፣ ርቆ መሄድ፣ በእግር መጓዝ አልቀረላትም። እንዲህ በሆነ ጊዜ ከቤት ሣትደርስ ይመሻል። ጨለማው ድካሙ ይፈትናል። ተምሮ ውሎ መግባቱ ጉልበት ያዝላል።
አንድ ቀን ሐብታምና ጓደኞቿ ከቤት ሣይደርሱ በከባድ ዝናብ ተያዙ። ዝናቡ በዋዛ አላባራም። በረዶ አስከትሎ መድረሻ አሣጣቸው። ከመንገድ መቅረታቸው ያሠጋቸው ወላጆች በልጆቻው ማምሸት ተጨነቁ። ቆይቶ እነ ሐብታም ቤታቸው ደረሱ። ዝናቡ እንዳይሆን አድርጓቸው ነበር።
ይህ አጋጣሚ ለሐብታም የተሻለ ዕድል አመጣ። ወላጇቿ ትምህርተ ቤቱ ካለበት ከተማ ቤት ተከራይታ እንድትማር ፈቀዱ። ሐብታም ተረጋግታ ትምህርቷን ቀጠለች። በዓመቱ መጨረሻም የተለመደውን ውጤት አገኘች። እስከ አሥራ አንደኛ ክፍል የአንደኝነት ደረጃዋን የነጠቃት አልተገኘም።
የማትሪክ ፈተና የወሠደቸው ወጣት ጊዜው ሲደርስ ውጤቷን ናፈቀች። ከትምህርት ቤት ደርሣም ውጤቷን ወሠደች። በእጇ የገባውን እውነት ዓይኗ አለመነም። ውጤቷ እንዳሠበችው አልሆነም። ደነገጠች። ተከዘች፣ ውጤቱ ለምትፈልገው የትምህርት መሥክ እንደማያበቃት አወቀች።
ሐብታም ውጤቷ ለምትፈልገው የአካውንቲግ ትምህርት ባያደርሣትም ዩኒቨርስቲ ከመግባት ግን አላገዳትም። ያም ቢሆን ዕድሉን አሣልፋ በግሏ ለመማር ወሠነች። ከራሷ መክራም ‹‹ይሁንብኝ›› አለች። መልሣ ደግሞ የግቢን ሕይወት ማየት ናፈቀች። ይህ ሥሜት አውሎ አላሣደራትም። ‹‹ጨርቄን፣ማቄን›› ሣትል ጓዟን ሸክፋ ተነሣች።
ሐብታም በ2010 ዓ.ም ጅማ ዩኒቨርስቲ ባየችው ሕይወት ተማረከች። ግቢ ስትደርስ የትምህርት ምርጫዋ በረከተ። የደረሣት ዕጣ ቋንቋዎችና ሥነጽሁፍ ዲፓርትመንት ሆነ። በትምህርት መስኩ ምርጫ አልተከፋችም። ውሎ አድሮ በሙያው ከተመረቁ የቀድሞ ተማሪዎች የሚማርክ ተሞክሮን ተጋራች። ሽልማታቸውን ሥታይ በውስጧ ሕይወት ተዘራ። በመንገዳቸው ልታልፍ፣ በጥረታቸው ልትጓዝ ተመኘች። ከዚያን በኋላ ለትምህርቱ እጅ ሰጠች። የገባችበትን መሥክም ከልብ ወደደችው።
ሐብታም የትናንት ማንነቷ ዳግም ከጉብዝናዋ አገናኛት። በየሴሚስቴሩ ሽልማት በመውሰድ ታወቀች። ዝናዋ አድናቆት ደርቦ ሲመጣ ጥንካሬዋን አጎላው።
በግቢው ጓደኞች የሏትም። የልብ የምትላት ወዳጅዋ አንዲት ብቻ ሆነች። ከባልንጀራዋ በሀይማኖት ቢለያዩም መከባበር፣ መወደድን አወቁበት። ይህ አብሮነት በጥንካሬ አዘለቃቸው። አንዳንዴ የትምህርት ውጤት ዝቅ ሊል ይችላል። እንዲህ በሆነ ጊዜ ሐብታም በብርታቷ ትገፋለች፤ ሠበብ ይሉትን ንቃም ከማንነቷ ትመለሣለች። ይህ ዓይነቱ እውነት ደግሞ እስከ መጨረሻው አዝልቆ ለደማቅ ውጤት አብቅቷታል።
ዛሬ ላይ የትናንቷ ረባሽ፣ ተማሪ ታሪኳ ፍጹም ተቀይሯል። ቀድሞ ከትምህርቱ አጋምና ቀጋን የምትመርጠው ጉብል አሁን የአንፀባራቂ ድል ባለቤት ሆናለች። ዘንድሮ በከፍተኛ ማዕረግ ከተመረቁ የጅማ ዩኒቨርስቲ ሴት ተማሪዎች መካከል ሐብታም አበባው የወርቅ ሜዳሊያውን በማጥለቅ ቀዳሚዋ ነች። 3 ነጥብ 89 አጠቃላይ ውጤት በማስመዝገብም ለድል ምዕራፍ በቅታለች።
ሐብታም ዛሬ ላይ ሆና ትናንት የሸሸችውን የማስተማር ሙያ ታስበዋለች። አሁን ደንቡ በሚፈቅደው አግባብ በዩኒቨርስቲው ቀርታ ማስተማር ፍላጎቷ ነው። ይሁን እንጂ ዘንድሮ የፀደቀው ‹‹የዲግሪ ተማሪን የዲግሪ ምሩቅ አያስተምርም›› ይሉት መመሪያ ይህን ታደርግ ዘንድ አልፈቀደም።
እሷ ግን አሁንም ወደ ቤቷ፣ ወደቤተሠቦቿ አልሄደችም። ዕውቀቷን ለተተኪዎች ለማካፈል በተጠንቀቅ ሆና ምላሽ ትጠብቃለች። ሐብታም ትናንት ከታላቅ እህቷ ጥንካሬን ተምራለች። እሷም በተራዋ ለታናናሾቿ አርአያ ሆና እንደወርቅ ሜዳሊያዋ የደመቀ፣ የከበረ ምልክት ማኖርን ትሻለች።
አሁንም ጅማ ዩኒቨርስቲ ግቢ እንገኛለን። ልዩ ማንነት፣ ተመሣሣይ ዓላማና ግብ ካገናኛቸው ሦስት ሴት ተማሪዎች መሀል። ዛሬ እነዚህ ተማሪዎች ከሩቅ እንደመምጣታቸው አልሆኑም። ቤተሠባዊ ሥሜትን ተጋርተዋል። ከዕውቀት ማዕድ ተካፍለው፣ ከአንድ መሥመር ገብተዋል።
አርሴማ የገጠሯ ጉብል
አርሴማ ጌታነህ ውልደትና ዕድገቷ ከምዕራብ ጎጃም፣ መራዊ ከተማ ወጣ ብላ ከምትገኝ ‹‹አኖራይታ›› ቀበሌ ነው። ጥሎባት በትምህርት ፍቅር የወደቀቸው ነብሥ እንዳወቀች ነበር። ወላጆቿ ፍላጎቷን ሲያውቁ ያሻትን ትሆን ዘንድ አልፈቀዱም።
ለቤቱ ስድሥተኛ ልጅ የሆነችው ጉብል የቤቶቿን ፊት መንሣት ሥታይ ተከፋች። ደጋግማም ትምህርት ቤት እንዲልኳት ወተወተች። ወላጆቿ ከእሷ በላይ ያሉትን አምስት ልጆች አላስተማሩም። ሌሎች ሁለት ሕጻናትም የትምህርት ቤቱን ደጃፍ አያውቁትም።
አርሴማ ይህን ጠንቅቃ ታውቃለች። ልቧ እያወቀ አይሞከሬ ጥያቄዋን ቀጠለች። ያለፈው ታሪክ በእሷ እንዲደገም አትሻም። ውትወታዋ አላባራም። ሙከራዋ አልቆመም። እናት አባት ተሠላቹ። ውሎ አድሮ ግን ጆሮ ሠጧት። ደብተርና መጻፊያው ተገዛላት። እሱን ይዛ ትምህርት ቤት ሄደች። ቀለም ስትለይ ውሎዋን ወደደቸው። አስተማሪዎቿ አያያዟን አይተው ከልብ አገዟት። አርሴማ ከሌሎች እኩዮቿ ልቃ መታየት፣ መጎበዝ ያዘች።
ውላ ሥትገባ እናት ከማጀት ዘልቃ ጉድ ጉድ እንድትል ይሻሉ። ታላላቆቿም ቢሆኑ እንደ ታናሽቷ ብትታዘዝ ይወዳሉ። አርሴማ ግን ደብተሯን ካነሳች ማንንም አትሠማም። ጧት ማታ እያጠናች በጥንካሬዋ ዘለቀች፤ የደረጃ ተማሪ ሆናም ለዩኒቨርስቲ ደረሠች።
ገጠር ተወልዳ ያደገችው አርሴማ ከወላጆችዋ ተነጥላ ልትሄድ ሆነ። አሁን የልጅነት ሥሜት ይፈታተናት ያሳስባት ያዘ። ከማታውቀው አገር ከማያውቋት መሀል መገኘት ጭንቅ ሆነባት።
ጅማ ዩኒቨርስቲ ስትደርስ ብቻዋን አልሆነችም። የአገሯ ልጆች ከጎኗ ነበሩ። መጀመሪያ ሠሞን አካባቢውን መልመድ ቸገራት። ቆይታ ግን እያንዳንዱን አወቀች። በትምህርቷም አተኮረች። አርሴማ በጥናት አትጨነቅም። እንደ ሌሎቹም በውጤት የመፎካከር ልምድ የላትም። ሰዓቷን በአግባቡ ተጠቅማም ለራሷ ጊዜ ሠጥታለች።
ከፈተና በኋላ በሚኖረው ጊዜ ብዙዎች ጉብዝናዋን ያውቃሉ። እሷ ግን ከራሷ በቀር የባልንጀሮቿን ውጤት አይታ አታውቅም። ያገኘችውን አረጋግጣ ለነገው ትዘጋጃለች። አርሴማ አሁን ጅማ ዩኒቨርስቲን ‹‹ቤቴ›› ብላ ይዛለች። ሕይወት እንደ ትናንቱ ቀጥሏል። ትምህርት፣ ጥረትና ፈተና በመልካም ውጤት ታጅበው እየተጓዙ ነው። የገጠሯ ተማሪ ሁሉን እንደየመልኩ ተቀብላለች። ነገን እያሠበች ዛሬን እየተጋች ነው።
አርሴማ ከዕለታት በአንዱ ቀን ውጥን ሕይወቷን ከመንገድ ያስቀረ የመሠላትን ክፉ ዜና ሠማች። በዓለም ላይ የተከሠተው የኮሮና ቫይረስ የእሷን ጨምሮ የባልንጀሮቿን ትምህርት ሊያቋርጥ ከበር ቆሟል። አሁን ትምህርት ሊቋረጥ ዩኒቨርስቲው ሊዘጋ ነው። ችግሩ የመላው ዓለም ቢሆንም አርሴማ በእሷ ላይ ብቻ እንደመጣ አድርጋ ተከፋች። ምርጫ አልነበራትም።፡ ቤቴ፣ ሕይወቴ ያለችውን ሥፍራ የኋሊት አየችው። ሥንብቱ አልቀረላትም። ጓዟን ሸክፋ ወደ አገር ቤት ተመለሠች።
እንዲህ በሆነ ጥቂት ጊዚያት በኋላ አርሴማና የጅማ ዩኒቨርሰቲ ዳግም ተገናኙ። ወጣቷ በአዲስ መንፈሥና ብርታት ከትምህርቷ ተወዳጀች፤ በባከኑት ወራት ቁጭት ቢገባት በቀድሞ ብርታቷ ጀገነች። ያሠበችውን አላጣችም። በጥንካሬዋ ለብዙዎች ምሣሌ ሆና በመልካም ውጤቶች መታጀብ ያዘች።
አሁን በአርሴማ ዘንድ የባከኑ ጊዜያት የሉም። ያለፉት ወራት በድል ታጅበው ለፍሬ በቅተዋል። የትምህርት ዓመቱ እንደተቋጨ አርሴማ የልፋቷ ፍሬ ከእጇ ደረሠ። በግቢው ከሚገኙ ሴት ተማሪዎች ተወዳዳሪ ሆና በ3 ነጥብ 67 በከፍተኛ ማዕረግ ተመረቀች።
አርሴማ በተመረቀችበት ዘርፍ በጋዜጠኝነት ሙያ ብትሠማራ ትወዳለች። ወደፊት በትምህርቷ መቀጠል የምትሻው ወጣት ማንኛዋም ሴት ተሥፋ በመቁረጥ ከዓላማዋ መደናቀፍ የለባትም ባይ ነች። ያለፈችበት የሕይወት ሐዲድ ለበርካቶች ተሞክሮ ይሆናል። ከፊት ለፊቷ እንዳየቻቸው ብርቱ ሴቶች ሁሉ ከእሷ ጀርባም ሌሎች ጠንካሮች እንዲከተሏት ምክንያት መሆን ትሻለች።
ለምለም ራሷን የማረከች ተዋናይ
ለምለም በየነ ጎንደር ከተማ ተወልዳ ስታድግ ሕይወቷ ከቤተክርስቲያን ሥርዓት አልራቀም። በልጅነቷ መካከለኛ ከሚባሉት ተማሪዎች መሀል ነበረች። አሥራ ሁለተኛ ክፍል ስትገባ ግን ጥንካሬ ተላብሳ ከጎበዞች መንደር ተገኘች። ለቤቱ የመጀመሪያ ልጅ ነችና ወላጆቿ ያተኩሩባታል። ያለችበት የትምህርት ደረጃና የዕድሜዋ ብስለት አግዟት በጥናት ስትበረታ ውጤቷ አማረ። ያሠበቸው ዕውን ሆኖም ለዩኒቨርስቲ ታጨች።
አጋጣሚ ሆኖ እሷ ዩኒቨርስቲ ባለፈችበት ጊዜ በአካባቢው ሠላም ይሉት ጠፋ። ይህ ያስከተለው መዘዝም የመግቢያ ጊዜዋን አዘገየው። ይኼኔ ለምለም የጋለው ሞራሏ ቀዘቀዘ። ሐሳብ ዓላማዋ የተደናቀፈ መሠላት።
ውሎ አድሮ ለምለም ወደ ጅማ ዩኒቨርስቲ ለመሄድ ዕድሉን አገኘች። ያለፉት ወራት በዋዛ ቢባክኑም በአዲስ ዓላማና ወኔ ራሷን አዘጋጀች። ጅማ ዩኒቨርስቲ እጁን ዘርግቶ ተቀበላት። ባየቸው፣ ባገኘችው ሁሉ ተደሠተች፣ እፎይታና ሠላም ተሠማት። ግቢውን አካባቢውን ወደደች፤ ከትምህርቱ፤ ከባልንጀሮቿ ተላመደች።
የተማረችበትን የቲያትር ትምህርት መጀመሪያ አልወደደችውም። ፍላጎቷ ለሥራ አመራርና የሕግ ትምህርት አመዘነ። ያም ሆኖ ትምህርቱን ስትይዘው በእጅጉ በረታች። ያለፈችበት የቤተክርስቲያን ሕይወት አግዟትም በመስኩ ውጤት ማስመዝገብ ያዘች። ይኼኔ ሙያውን ወደደችው። ለመድረክና ለትወና የተሰጠች መሆኑ ሲገባት መስኩን ባለመቀየሯ ኮራች።
ለምለም ከመጀመሪያው ዓመት ጀምሮ በምታስመዘግበው ከፍተኛ ውጤት ከዩኒቨርስቲው የገንዘብ ሽልማት ስታገኝ ቆይታለች። በየጊዜው በትምህርት ክፍሏ በምታስመዘግበው ውጤትም ከመምህራኖቿ ማበረታቻዎች ሲቸራት ነበር።
አሁን በደም ሥሯ የሚዘዋወረውን የትወና ሕይወት በተግባር ማግኘት ትሻለች። አስቀድማ ያልወደደቸው መስክ ዛሬ ላይ ውስጧን ማርኮ እጅ አሰጥቷታል። ራሷን በሰጠችለት ዓለም በእጅጉ ተሸንፋለች። ከዚህ በኋላ ለእሷ ከተማረችበት ሙያ በላይ ሌላ ሕይወት የለም።
ለምለም ትናንት ላይ ቆማ ዛሬን ስትቃኝ በትምህርት ምርጫዋ ያለመደሰቷን ታሪክ ታስታውሳለች። ቤተሠቦቿም ቢሆኑ በሙያው ባትሠማራ ይወዱ ነበር። ዛሬ ግን ትጠላው የነበረው መስክ ታላቅነት አላብሷታል። ዘንድሮ በመስኩ ከተመረቁ ተማሪዎች መካከል ከፍተኛ ውጤት በማግኘቷ በማዕረግ ለመመረቅ በቅታለች።
በ3 ነጥብ 54 አጠቃላይ ውጤት በከፍተኛ ውጤት ማለፏን ስታስብ ለዚህ ያበቃት ቆራጥ ውሣኔዋ እንደነበር ውስጧ ያምናል። በእርግጥም የራሷን ዓላማ በራሷ ሐሳብ ማጽደቋ ከሌሎች ተጽዕኖ እንድትወጣ አስችሏል። ለምለም አሁንም ቢሆን ያለአንዳች ተጽዕኖ መራመድን ትሻለች። ይህ ዕውን ይሆን ዘንድም በእጇ ባለው ታላቅ ሙያ መግለጥን ትሻለች።
ዛሬ ለምለም ወደትውልድ አገሯ ጎንደር ተመልሣለች። ቤተሰቦቿ እሷን ሲያስመርቁ የነበራቸውን ደስታ ስታስብ ደግሞ ውስጧ በተለየ ሐሴት ይሞላል። በወላጆቿ ዓለም የራሷን ማንነት የምትለካው ወጣት ልክ እንደሷ ሁሉ እኩዮቿና ታናናሾቿ ባለፈችበት የጥንካሬ መንገድ እንዲጓዙ ትመክራለች።
ልዩ ማንነት ተመሣሣይ ዓላማና ግብ ያገናኛቸው ሦስቱ ተማሪዎች ‹‹ሴትነት›› ይሉት ወግ ሣያግዳቸውና በተጽዕኖ ሠንሠለት ሣይታሠሩ ለአንፀባራቂ ውጤት ደርሠዋል። እነዚህ ሴት ተማሪዎች ዛሬ ላይ የበተኑት ወርቃማ ፍሬ ነገ ለሌሎች በቅቶ ውጤቱ የጎመራ እንደሚሆን ዕሙን ነው። ጥንካሬ፣ ብርታትና ቆራጥነት ካለ አይደርሱበት ጫፍ የለምና።
አዲስ ዘመን የካቲት 29/2013