መልካምስራ አፈወርቅ
ባልና ሚስት ለአመታት በትዳር ጸንተው ቆይተዋል። ጊዜያትን ያስቆጠረው ጥምረት አንዳንዴ ንፋስ ሲገባው፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ ሰላም ሲሰፍንበት ኖሯል። ጥንዶቹ በመሀላቸው ችግር በተፈጠረ ጊዜ ሲላቸው በራሳቸው አቅም፣ አንዳንዴም በቅርብ ዘመዶች ጥረት መፍትሄ ሲሰጡት ቆይተዋል።
ወይዘሮ ራኒያ አህመድ ከባለቤታቸው ዶክተር ኢብራሂም መሀመድ ጋር ባላቸው የትዳር ቆይታ የጋራ ሀብት ንብረት አፍርተዋል። ብዙ ጊዜ ባለመግባባት የዘለቀው ትዳር ጠብና ችግር ያገኘዋል። ኩርፊያና ዝምታ ይጎበኘዋል። ያም ሆኖ ፍቺ ከሚሉት ጥግ ደርሶ አያውቅም። ሁሌም በእርቅ ይታከማል። በይቅርታ ይመለሳል። ከቅያሜ በኋላ የቤቱ ሰላም ተመልሶ ህይወት እንደቀድሞው ይሆናል።
አሁን ባልና ሚስቱ በአንድ ጉዳይ ከስምምነት ደርሰዋል። ሚስት በቅርቡ ለሚያደርጉት የውጭ አገር ጉዞ መዘጋጀት አለባቸው። ይህን እውነት የሚያውቁት ባለቤታቸውም ለመንገዳቸው የሚያስፈልገውን ለመሙላት ከጎናቸው ሆነዋል። ወይዘሮ ራኒያ ከቀናት በኋላ ጥቂት ጊዜያትን በእረፍት ለማሳለፍ ወደ አሜሪካ ይጓዛሉ። ባለቤታቸው ዶክተር ኢብራሂም በጉዞው ቅሬታና ተቃውሞ የላቸውም። በቅርቡ ደርሰው የመመለሳቸውን እውነት ያውቁታልና የሚሆነውን ሁሉ እያደረጉ ነው።
ጉዞና ሽኝት
እንደታሰበው ሆኖ የጉዞ ቀኑ ደረሰ። ወይዘሮዋ አገር ቤት ያሉ ወዳጅ ዘመዶቻቸውን ተሰናብተው ሻንጣና ጓዛቸውን አነሱ። ባለቤታቸው ከአየር መንገዱ አድርሰው ጉንጮቻቸውን ለስንብት ሳሙ። ሸኚና መንገደኞች በበዙበት ስፍራ እጆች በርቀት ተውለበለቡ። የቸር መንገድን የተመኙ ሁሉ ሰዎቻቸውን በርቀት አሰናበቱ። አውሮፕላኑ የሰማይ መንገዱን ሊያቀና ከመሬት በከፍታ ርቀት አኮብክቦ ፤በአፍታ ቆይታም ከጉሙ ገብቶ ከዓይን ተሰወረ።
ዶክተር ኢብራሂም ባለቤታቸውን ሸኝተው ወደቤት ተመለሱ። ወይዘሮ ራኒያ የእረፍት ዓላማውን ሊጀምሩ አገረ አሜሪካ አቀኑ። ባልና ሚስቱ የሰው አገር ሰማይ ሊጋርዳቸው፣ መለያየት ሊያራርቃቸው ቀናት መቆጠር ያዙ። አገር ቤትና ውጭ አገር ፣ህይወት በየፈርጁ ቀጠለ።
ህዳር 16 ቀን 2006 ዓ.ም
ዶክተር ኢብራሂም በዚህ ቀን ሊከውኑ ያሰቡትን ጉዳይ ለመጀመር ማልደው ተነስተዋል። በጽሁፍና በሰነድ ማስረጃዎች የተዘጋጁና በጥንቃቄ የተያዙ ዶሴዎችን አጥብቀው ወደ ፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ሸሪዓ ፍርድ ቤት ዘልቀዋል።
በእጃቸው ያለውን የጽሁፍ ማመልከቻ ለፍርድ ቤቱ ያቀረቡት ዶክተር ኢብራሂም ጉዳዩ የፍቺ ጥያቄ መሆኑ ታውቆላቸዋል። ተከታዩ ሂደት ይከወን ዘንድም ማመልከቻው ወደሚመከለተው ክፍል ተመርቷል።
በማመልከቻው መሰረት ጉዳዩን የተመለከተው ፍርድ ቤት ህጉ በሚፈቅደው አግባብ ባለቤታቸው በጋዜጣ ጥሪ እንዲደረግላቸውና በተባለው ቀንና ስፍራ እንዲቀርቡ ሲል አዟል። አመልካቹ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ ተቀበሉ። የተባለው እንዲፈጸም ጋዜጣውን ለማሳተም ሂደቱን ጀመሩ።
ህዳር 20 ቀን 2006 ዓ.ም ለህትመት የበቃው አዲስ ዘመን ጋዜጣ ተጠሪ ወይዘሮ ራኒያ አህመድ ለታህሳስ 2 ቀን 2006 ዓ.ም በፍርድ ቤቱ እንዲቀርቡ ሲል የጥሪ ማስታወቂያ አወጣ።
ማስታወቂያው ለንባብ ደርሶ ቀናት ተጠበቁ። በቅርብ የሌሉት ወይዘሮ ራኒያ ጋዜጣው በእጃቸው ደርሶ በተባለው ቀንና ቦታ አልተገኙም። ፍርድ ቤቱ ተጠሪዋ በጊዜው አለመገኘታቸውን ተረዳ። የአመልካቹን ሀሳብ ዳግመኛ መርምሮም ጥያቄያቸውን አዳመጠ።
ዶክተር ኢብራሂም እስካሁን በጋብቻ ታስሮ የቆየው ትዳር በፍቺ እንዲቋጭ ይፈልጋሉ። ይህን እውነትም ለፍርድ ቤቱ አስረድተው አድማጭ ጆሮ አግኝተዋል። ባለቤታቸው በጥሪው መሰረት ያለመገኘታቸው ለጥያቄው ምላሽን እንደማያዘገይ በማስረዳትም ፍቺው በአስቸኳይ እንዲፈጸምላቸው እየጠየቁ ነው።
ፍርድ ቤቱ የአመልካቹን ጥያቄና ሃሳብ ከተረዳ በኋላ ውሳኔውን አሳለፈ። አመልካች ፍቺ በመጠየቃቸውና ተጠሪዋ በጋዜጣው መሰረት ባለመቅረባቸው ከታህሳስ 10 ቀን 2006 ዓ.ም ጀምሮ በሁለቱ ሰዎች መሀል የነበረው ጋብቻ በፍቺ እንዲቋጭ ሲል ትዕዛዙን ሰጠ።
ይህ ትዕዛዝ ተፈጻሚ ከሆነ ጥቂት ጊዚያት በኋላ ወይዘሮ ራኒያ የዕረፍት ቆይታቸውን አጠናቀው ከአሜሪካ ወደ አገር ቤት ተመለሱ። እግራቸው መሬት ከመድረሱም የትዳራቸውን መፍረስ አወቁ። ጉዳዩን ለማጣራት ሲሞክሩ ፍቺው በሸሪዓ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ መፈጸሙን ሰሙ።
ወይዘሮዋ ጊዜ አልፈጁም። ጉዳዬ ይታይልኝ፣ ፍትህና ህግ ይዳኘኝ ሲሉ ከፍርድ ቤቱ ደጃፍ ተመላለሱ። መጋቢት 8 ቀን 2007ዓ.ም ለኢፌዲሪ የሕገመንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ ማመልከቻ ጽፈው አስገቡ።
አቤቱታ…
ወይዘሮዋ የቀድሞ ባለቤታቸው የእሳቸውን ከሀገር መውጣት ጠብቀው ለፍርድ ቤቱ የፍቺ ጥያቄ ማቅረባቸውን ይጠቅሳሉ። ፍርድ ቤቱም የእሳቸውን አለመኖር አውቆ በጋዜጣ ጥሪ አቅርቧል። በቅርብ ያልነበሩት ሴት ጆሯቸው አልሰማምና በጊዜ መቅረብ ሳይቻላቸው ይቀራል። ይህ እንዲሆንም የተንኮሉን ስራ ግለሰቡ እንደፈጸሙት በክሳቸው ላይ አመላከቱ።
ወይዘሮዋ በማመልከቻቸው ሌላም ሀሳብ አከሉበት። በኢፌዲሪ ሕገመንግስት አንቀጽ 34/5 መሰረት በሃይማኖታዊ ፍርድ ቤት ለመዳኘት ፈቃዴ ሳይጠየቅና ይሁንታዬን ሳልሰጥ እንዲሁም መጥሪያው በእጄ መግባቱ ሳይረጋገጥ ውሳኔ መሰጠቱ አግባብ አይደለም ሲሉ ተቃወሙ።
ወይዘሮዋ የፌዴራል ሸሪዓ ፍርድ ቤት የፍትሀብሄር ስነስርአት ህጉን አለአግባብ በመጠቀም ታህሳስ 10 ቀን 2006ዓ.ም የፍቺ ውሳኔ ማሳለፉ አግባብነት እንደሌለው በአቤቱታቸው ጠቀሱ። በፍቺው ውጤት ላይ በተጠቀሰው የንብረት ክርክር በተጠሪው ለቀረበው ማመልከቻ ተቃውሞ ማቅረባቸውን አውስተውም ለተቃውሞው ትኩረት ሳይኖር ክርክሩ እንዲቀጥል ተደርጓል ሲሉ አመለከቱ።
ግለሰቧ መስከረም 19 ቀን 2007 ዓ.ም በተጻፈ ማመልከቻ ጉዳዩ ለሕገመንግስታዊ ትርጉም ፣ለሕገመንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ እንዲላክላቸው ሲጠይቁ ቆይተዋል። አቤቱታቸው ላይ ግን ትዕዛዝ ሳይሰጥ ጉዳዩ እንደነበረ እንዲቀጥል ሆኗል። ይህን የተረዱት ወይዘሮ ራኒያ የሕገመንግስቱ አንቀጽ 34/5 አንቀጽ 35 / 7 እና (9) በፍርድ ቤቱ ውሳኔ የተጣሱ በመሆኑ የሕገመንግስት ትርጉም ይሰጥልኝ ሲሉ ቅሬታቸውን አመለከቱ።
ጉዳዩ በሸሪዓ ፍርድ ቤት
የወይዘሮዋ የቅሬታ ማመልከቻ አስቀድሞ የቀረበለት የፌዴራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ሸሪዓ ፍርድ ቤት ታህሳስ 10 ቀን 2006 ዓ.ም በሰጠው ውሳኔ ተጠሪ ህዳር 10 ቀን 2006 ዓ.ም ከአመልካች ጋር የነበራቸውን አለመግባባት ለመፍታት ጥረት ቢያደርጉም አለመሳካቱን መግለጻቸውን ያረጋግጣል።
ከዚሁ ጋር ተያይዞም ለወይዘሮዋ በጋዜጣ ጥሪ ቀርቦ በወቅቱ አለመቅረባቸውን ያመለክታል። በፍቺው ጥያቄ መሰረትም ግለሰቧ በሌሉበት የፍቺ ውሳኔ መሰጠቱን በመግለጽ አመልካቿ ለሕገ መንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ ይቅረብልኝ ሲሉ ያቀረቡትን ጥያቄ ፍርድ ቤቱ እንደማይቀበለው በመግለጽ ጉዳዩን እንደነበረ ለማየት መወሰኑን ያረጋግጣል።
ፍርድ ቤቱ በውሳኔው እንዳመለከተው በአመልካችና በተጠሪ መካከል ባለው ክርከር የካቲት 18 ቀን 2007 ዓ.ም ትዕዛዝ ሰጥቷል። ትዕዛዙም በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 08 አስተዳደር በቤት ቁጥር 427 የሚገኙ የቤት ቁሳቁሶችን በመቁጠር እኩል መካፈል እንዲችሉ ሲል ውሳኔ አሳልፏል።
በዚህም መሰረት አመልካች ለተጠሪ የሚያስረክቧቸውን የንብረት ዝርዝር በመጥቀስና ትዕዛዙ ተፈጻሚ እንዲሆን በመግለጽ ለውጤቱ መጋቢት 8 ቀን 2007 ዓ.ም ቀነ ቀጠሮ ሰጥቷል።
የፍርድ አካሄድ በጉባኤው መነጽር…
እስካሁን ከቀረቡት ማስረጃዎች ለማወቅ እንደተቻለው የፌዴራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ሸሪዓ ፍርድ ቤት ቀደም ሲል በሰጠው የፍቺ ውሳኔ የተከተለው የህግ አግባብ የሸሪዓ ፍርድ ቤቶችን አቋም ለማጠናከር የወጣውን አዋጅ ቁጥር 188/92 አንቀጽ 5/1 እና 2 የተጠቀሱትን ድንጋጌዎች መሰረት ያደረገ ነው።
የአዋጁ አንቀጽ 5/1 እንደሚጠቁመው ከተከራካሪ ወገን አንደኛው በሸሪያ ፍርድ ቤት ለመዳኘት አቤቱታ ሲያቀርብ ፍርድ ቤቱ ሌላው ወገን በዚህ አግባብ ለመዳኘት ፍቃደኛ መሆኑ አለመሆኑን ለማረጋገጥ መጥሪያ እንዲደርሰው ማድረግ ግዴታው ይሆናል። መጥሪያው በአግባቡ እንዲደርሰው የተደረገው ተከራካሪም ተቃውሞና ፈቃደኝነቱን ለማሳወቅ በፍርድ ቤቱ ሬጂስትራር ቀርቦ ማረጋገጥ ይኖርበታል። እንዲህ ካልሆነ ግን ተቃራኒው ወገን ተቃውሞ ማድረግ እንዳልፈለገ ተደርጎ ይቆጠራል።
በፍርድ ቤቱ አካሄድ ፍቺ እንዲፈጸም ሲወስን ወይዘሮዋ በአዲስ ዘመን ጋዜጣ በተደረገላቸው ጥሪ ቀርበው መልስ እንዲሰጡ መጠቆሙን ያሳያል። ተጠሪዋ በወቅቱ ለጥሪው ምላሽ ባለመስጠታቸውም በፍርድ ቤቱ ለመዳኘት ፈቃደኛ እንደሆኑ ተቆጥሮ ውሳኔውን ማሰለፍ እንደተቻለ ተገልጿል።
በኢፌዲሪ ህገመንግስት አንቀጽ 34/5 መሰረት በተከራካሪዎች ፈቃድ በሃይማኖት ወይም በባህሎች ህጎች መሰረት መዳኘትን አይከለክልም። ይህም ዝርዝሩ በህግ ይወሰናል ሲል ያስቀምጠዋል። በፍርድ ቤቱ ለመዳኘት ፈቃዱን ሰጥቷል ተብሎ የሚገመተው ወገንም በአግባቡ መጥሪያው ሊደርሰው እንደሚገባ ያስረዳል።
ከተቀመጠው ህግ አኳያም የውሳኔው አግባብነት ሲመረመር መጥሪያው ከአዋጁ ተያይዞ ከሚገኘው ቅጽ ጋር ለተጠሪው ደርሶ ፈቃደኛ መሆን ያለመሆኑ ሊገልጽ እንደሚገባ ያስቀምጣል።
ይህ እውነት ባለበት አግባብም መጥሪያው ለወይዘሮዋ በአግባቡ ደርሷል ለማለት የሚያስችል አይሆንም። አግባብነቱ ከፍትሐብሄር ሥነስርአት ህጉ አንጻር ቢፈተሽ እንኳን ተጠሪው ህዳር 16 ቀን 2006 ዓ.ም የፍቺ አቤቱታቸውን አቅርበው ህዳር 20 ቀን 2006 ዓ.ም በጋዜጣ ጥሪ ማስታወቂያ እንዲወጣ መደረጉ አግባብ ሆኖ አልተገኘም።
ለዚህም የተቀመ ጠው ምክንያት አመልካ ችዋ በውጭ አገር ከመኖ ራቸው ጋር በቂ ጊዜ የተሰጠ ባለመሆኑ አስፈላጊው ጥረት ተደርጓል ለማለት እንደማያስችል ነው። ተከራካሪዎች በሃይማኖት ፍርድ ቤት የመዳኘት ፍላጎት መረጋገጥ እንዳለበት ከመግለጹ አኳያም የመጥሪያ አላላኩ እንደመደበኛው የፍትሐብሄር ክርክር መብትን ለማስከበር ብቻ ሳይሆን የተከራካሪ ወገኖችን ፍላጎት ጭምር ማክበር ሊሆን እንደሚገባ ማወቅ ተገቢ ነው።
የውሳኔው ውሳኔ…
የሸሪዓ ፍርድ ቤቱ አንደኛው ወገን በሃይማኖት ህግ ለመዳኘት ፍላጎት እንዳለው ሳያረጋግጥ ያሳለፈው ውሳኔ ህገ መንግስታዊ ጥሰትን መፈጸሙን እንደሚያሳይ ተረጋግጧል። በመሆኑም ጉባኤው በጉዳዩ ላይ የህገመንግስት ትርጉም ሊሰጥበት ይገባል ሲል በሙሉ ድምጽ ተስማምቶ ለመጨረሻው ብይን ለፌዴሬሽን ምክር ቤት እንዲተላለፍ ወስኗል።
ምክር ቤቱም የአጣሪ ጉባኤውን የውሳኔ ሀሳብ መሰረት በማድረግ የህገ መንግስት ትርጉምና የማንነት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ያቀረበውን የውሳኔ ሀሳብን ተመልክቷል። በምክር ቤቱ ግንዛቤም የሸሪዓ ፍርድ ቤቱ በቀረበለት የጋብቻ ፍቺ አቤቱታ ወይዘሮዋ ባልተገኙበት ጉዳዩን በማየት የሰጠው ውሳኔ በህገመንግስቱ ይህን ጉዳይ አስመልክቶ በተቀመጡ አንቀጾች ድንጋጌ መሰረት ህጉን ያከበረ ውሳኔ እንዳልሆነ አረጋግጧል።
በመጨረሻም…
የፌዴራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ሸሪያ ፍርድ ቤት የአመልካችንና የተጠሪን ጉዳይ በተመለከተ ያሳለፈው ውሳኔ በሕገመንግስቱ አንቀጽ 34 እና 35 የተቀመጡትን የጋብቻ፣ የግል፣ የቤተሰብና የሴቶች መብት ድንጋጌዎችን የሚቃረን ሆኖ ተገኝቷል። ውሳኔው ሕገመንግስታዊ ጥሰት ያለው በመሆኑም በሕገመንግስቱ አንቀጽ 9/1/ ድንጋጌ መሰረት ተፈጻሚነት ሊኖረው አይገባም፣ ሲል የፌዴሬሽን ምክር ቤት የመጨረሻውን ውሳኔ በሙሉ ድምጽ አሳልፏል።
አዲስ ዘመን የካቲት 27/2013