መርድ ክፍሉ
የኮቪድ 19 ወረርሽኝ መከሰትን ተከትሎ በርካታ ዜጎች ለከፍተኛ የኑሮ ጫና መዳረጋቸው ይታወሳል። ይህ ሁኔታ አሁንም ድረስ የዘለቀ ነገር ነው። የኮቪድ 19 ወረርሽኝ ያደረሰውን ጫና ለመቋቋም እንዲረዳ በወጣቶች አማካኝነት ብዙ ማህበራት ተመስርተዋል። ከነዚህም ውስጥ በደሴ ከተማ የሚገኘው የአርሂቡ ለሰላም የልማትና የመረዳጃ ማህበር አንዱ ነው።
ማህበሩ የአካባቢን ሰላም፣ ልማትና ሰው መርዳትን አንድ ላይ አስተሳስሮ እየሰራ የሚገኝ ነው። በደሴ ከተማ ዙሪያም ሰዎችን ከመደገፍ በተጨማሪ የችግኝ ተከላና የከተማ ፅዳት ላይም ተሳትፎ ያደርጋል። አጠቃላይ ስለማህበሩ እንቅስቃሴ ከሊቀመንበሩ ጣፈጠ ተስፋዬ ጋር ቆይታ አድርገናል።
የማህበሩ አመሰራረትና ያከናወናቸው ተግባራት
ማህበሩ የተመሰረተው መስከረም 21 ቀን 2012 ዓ.ም ላይ ነበር። ለመመስረትም ምክንያት የነበረው በአካባቢው የነበረው የፀጥታ ችግሮች ምክንያት ነበር። የነበሩትን የፀጥታ ችግሮች ለመፍታት በአካባቢው ከሚገኙ ነዋሪዎችና ክፍለከተማው ጋር በጋራ በመሆን 32 ወጣቶች በመደራጀት የአካባቢውን ሰላምና ፀጥታ ለማስጠበቅ ስምምነት ላይ ተደረሰ። ከምሽቱ 12 ሰዓት እስከ ሌሊቱ 6 ሰዓት ድረስ ጥበቃ ይከናወን ነበር።
የክፍለከተማው አመራሮች ባሉበት ስብሰባ ተደርጎ ጠንካራ ማህበር ስለሆነ እውቅና ተሰጥቶት የጥበቃ ስራውን ይሰራ ተብሎ ተወሰነ። በዚህም እያንዳንዱ አባል መታውቂያ አውጥቶ ጥበቃውን ማከናወን ቀጠለ። ይህም ለማህበሩ አጀማመር መሰረት ጣለ።
ማህበሩ በተጠናከረ መንገድ አካባቢውን እየጠበቀ ባለበት ወቅት የኮቪድ 19 ወረርሽኝ ወደ አገሪቱ ገባ። ወረርሽኙ ወደ አገሪቱ እንደገባ ሲነገር ማህበሩ ሙሉ የደሴ ከተማን ያካለለ ንቅናቄ አካሄደ። በንቅናቄውም የእጅ ማስታጠብ ፕሮግራም ለማስጀመር ህዝብን ለመቀስቀስ የከተማ አስተዳደሩን ምክትል ከንቲባና ሌሎች አመራሮችን ይዞ ሰፊ ስራ መሰራት ተጀመረ።
በዚሁ አጋጣሚ በኮቪድ 19 ምክንያት የተጎዱ በርካታ ወገኖች በተለይ በህመም ላይ የነበሩ፣ ከስራ የተፈናቀሉ እንዲሁም ሌሎችን ለመርዳት ከማህበረሰቡ ድጋፎችን በመጠየቅ ለ132 ሰዎች ለእያንዳንዳቸው 25 ኪሎ ዱቄትና ዘይት እንዲሁም አስቸኳይ በሚል ሁለት ሁለት ሳሙና እንዲሰጣቸው ተደርጓል።
በመቀጠል ደግሞ የበሽታው መስፋፋት እያደገ ሲመጣ ተደራሽ ያልተደረገባቸው ቦታዎች በተለይ በከተማው የሚገኘው ማረሚያ ቤት ዋነኛ ትኩረት ተሰጠው። በማረሚያ ቤት ውስጥ የሚገኙ አንድ ሺህ ስድስት መቶ ታራሚዎች ከተማ አስተዳደሩን በማናገር ‹‹አንድ ሳሙና ለአንድ ወገን›› በሚል ነጋዴዎችን በመለመን የተሰበሰቡ ሳሙናዎችን፣ የህፃናት ንፅህና መጠበቂያዎችን እንዲሁም ለሌሎች እቃዎች ተዘጋጅተው እንዲሰጡ ተደርገዋል። በወቅቱም የእጅ ማስታጠብ ስራ ተከናውኖ ግንዛቤ የመስጠት ስራዎች ተከናውነዋል።
በማረሚያ ቤቱ የሚገኘው ቦታ ጠባብ ስለሆነና ካለው የሰው መጨናነቅ ረገድ ታራሚዎች በምን አይነት ሁኔታ መኖር እንዳለባቸው ትምህርት ተሰጥቷል። በተጨማሪም ለእጅ መታጠቢያ የሚሆኑ ትልልቅ ጀሪካኖችም በድጋፍ መልክ ተሰጥቷል። ይህ ስራ ከተሰራ በኋላ በደሴ ከተማ ላይ 18 የኮቪድ ወረርሽኝ ተጠቂዎች አንድ ሆስፒታል ውስጥ እንዲገቡ ተደረገ። በወቅቱ ህብረተሰቡ የተዛባ አመለካከት ስለነበረው የህክምና ባለሙያዎችም ተደናግጠው ነበር።
በስራው ላይ የነበሩ 48 የጤና ባለሙያዎች ከሰው እንዲገለሉ ተደርገውም ነበር። የህክምና ባለሙያዎቹን ለማበረታታትና ህብረተሰቡ ከጎናቸው መሆኑን ለማሳወቅ አራት በጎችንና መፅሀፍቶችን እንዲሁም የታሸጉ ውሃዎችን በመግዛት ለህክምና ባለሙያዎቹ የአስተዳደሩ አካላት በተገኙበት ተሰጥቷል።
በወቅቱ የህክምና ባለሙያዎቹ በተደረገላቸው ድጋፍ ተነቃቅተው ስራቸውን እንደሚያከናውኑና ህብረተሰቡ ከጎናቸው መሆኑን ያዩበት እንደሆነ ተናግረዋል። በዓላትን ምክንያት በማድረግ የተለያዩ ድጋፎች ለህክምና ባለሙያዎቹ ተደርጓል።
በሌላ በኩል በደሴ የሚገኝ የእናቶችና የህፃናት ሆስፒታል ህንፃ የንፅህና ጉድለት ነበረበት። ለሌሎች ሰዎች አርአያ ለመሆን በማሰብ ሁለት ጊዜ ደረቅ ቆሻሻዎችን የማንሳት ስራ ተከናውኗል። በተጨማሪም ሙሉ የሆስፒታሉን ህንፃ ከእሳት አደጋ ውሃ በማስፈቀድ ሁሉም አባላት ባሉበት በግማሽ ቀን እንዲፀዳ ተደርጓል። የማፅዳት ስራው ከተከናወነ በኋላ ሆስፒታሉ አገልግሎት ለመስጠት ምቹ ሆኗል።
ይህ ስራ ሌሎች ማህበራትን የሚያነቃቃና ሊያበረታታ የሚችል ነው። ማህበሩ በሚሰራቸው ማንኛውም ስራዎች የወይዘሮ ስሂን ቴክኒክና ሙያ ተቋም ከፍተኛ ድጋፍ እያደረገ ነው። በየትኛውም ሁኔታ ስፖንሰር ሲፈለግ ተቋሙ ግንባር ቀደም ነበር።
በተቋሙ ውስጥ የሚገኙ ችግኞችን መንከባከብና ሌሎች ስራዎችን የማህበሩ አባላት በተለያዩ ጊዜያት እየሄዱ ይሰራሉ። የማህበሩ ዋና አላማ የሰላምና የልማት ስራዎችን ለማካሄድ ነው። በከተማው የሚገኙ ቦታዎችን በማልማት እንዲሁም የፅዳት ስራዎችን በማከናወን ማህበሩ ግንባር ቀደም ነው።
በቅርቡ የወይዘሮ ስሂን ቴክኒክና ሙያ ተቋም ተማሪዎችን ሲያስመርቅ የማህበሩ አባላት ስነስርዓት ከማስከበር ጀምሮ የኮቪድ 19 ወረርሽኝን ለመከላከል ጥንቃቄ እንዲደረግ ግንዛቤ ሲሰጥ ነበር። በሁሉም ቦታዎች ላይ የሚሰሩ ስራዎች ያሉ ሲሆን በክረምት ወቅት ቤታቸው የፈረሰባቸውን ሰዎች ቤት የመገንባት እንቅስቃሴ ነበር።
የተቸገሩ ሰዎች ወደ ስራ እንዲገቡ የተደረገበት ሁኔታም ነበር። በአካባቢው በሚገኙ የጤና ተቋማቶች በየትምህርት ደረጃቸው ተመዝግበው ስራ እንዲያገኙ የተደረጉ ዜጎች አሉ። በዚህም ብዙ ሰዎችን መደገፍ ተችሏል።
ማህበሩን ያጋጠሙ ችግሮች
ማህበሩ ብዙ ስራዎች ሲያከናውን ከከተማ አስተዳደሩ ምንም አይነት እገዛ አላገኘም ነበር። ነገር ግን በተለያዩ መንገዶች በሚሰጡ መረጃዎች ባህዳር ላይ በተደረገ ስብሰባ ደሴን ከተማ በመወከል ማህበሩ የምስክር ወረቀት አግኝቷል።
በደሴ ከተማ አስተዳደር በኩል ግን ማህበሩን ለመደገፍ ምንም አይነት ስራ እየተከናወነ አይደለም። ማህበሩ በቻለው አቅም የሰራቸውን ስራዎች ሌሎች ማህበራት እንዲስብና እንዲማሩበት እየጣረ ይገኛል።
በአካባቢው የሚታዩ ማንኛውም የፍትህ መጓደል ለምሳሌ በተለያዩ አካባቢዎች የሚታዩ መጥፎ ስራዎች ፊት ለፊት በመሄድ የመጋፈጥ ሁኔታዎች አሉ።
ሁኔታውንም የሚመለከታቸው አካላት በመመልከት እርምጃ እየወሰዱ ይገኛሉ። በክፍለከተማ ደረጃ አስቸጋሪ ሁኔታዎች የነበሩ ሲሆን እንደ በጎ ማህበራት የሚሰሩ በርካታ ስራዎች አሉ። ማህበሩ በአገር አቀፍ ደረጃ ለመስራት የተመዘገበ በመሆኑ በየትኛውም ቦታ ሄዶ የመስራት መብት አለው።
ስራዎች ሲሰሩ የከተማ አስተዳደሩ ድጋፍ የማድረግ ግዴታ አለበት። ማህበሩ አንድ ዓመት ከስድስት ወራት ያክል ሲንቀሳቀስ ምንም አይነት ቢሮና የመሰብሰቢያ አዳራሽ ስለሌለው በትምህርት ቤቶችና በሌሎች ቦታዎች ላይ በማስፈቀድ ስራዎች ይከናወናሉ። ማህበሩን የሚፈልግ አካል ቢሮ ስለሌለ በፈለገው ጊዜ ማናገር አይችልም። ይህ የሆነው ከተማ አስተዳደሩ አስፈላጊውን ትብብር ባለማድረጉ ነው።
ማህበሩን የተለያዩ ድርጅቶች ሊረዱትና በትብብር ለመስራት ሲመጡ ማህበሩ ቢሮ ስለሌለው እክል ተፈጥሮበታል። ከተማ አስተዳደሩ ይህን ችግር በቀጣይ ሊፈታ ይችላል የሚል እምነት አለ። በዋናነት በከተማው የሚገኙ ችግሮች ለመፍታት ጥረት እየተደረገ ሲሆን ቀደም ባለው ስርዓት እና አሁን ያለው ልዩነት አላቸው። ለውጡ በሰፊው በሚቀጥሉት ጊዜያት ይኖራል ተብሎ ይጠበቃል። ማህበሩ ከተመሰረተ ጀምሮ ከባድ የሚባል ችግር አላጋጠመውም።
እንደ ችግር ማህበሩን እየፈተነ ያለው የቢሮ ችግር ለመፍታት ባቀረበው ተደጋጋሚ ጥያቄ ከተማ አስተዳደሩ ለቢሮ የሚሆን ቦታ ፈልጋችሁ ጠቁሙ ባለው መሰረት ከአሥር ዓመት በላይ የተቀመጠ መሬት እንዲሰጣቸው ጥቆማ ሰጥተው ነበር። ነገር ግን ቦታውን እስካሁን ከተማ አስተዳደሩ ለማህበሩ ሊሰጥ አልቻለም።
በሌላ በኩል በከተማ ውስጥ የችግኝ ጣቢያ ባለመኖሩ በጦሳ ተራራ አካባቢ የሚገኝ ቦታን ችግኝ እንዲተከልበት ተደርጎ ነበር። ቦታው ለመንግሥት አገልግሎት መዋል አለበት የሚል ወሬዎች ነበሩ።
ቦታው ለችግኝ ጣቢያ እንዲሆን ማህበሩ በደብዳቤ ከተማ አስተዳደሩን ጠይቋል። ቦታው ለችግረኞች መኖሪያ ቤት ይሰራበታል የሚል ሀሳብ የነበረ ሲሆን ቦታው ለአረንጓዴ ልማት ብቻ መዋል እንዳለበት ማህበሩ አጥብቆ ተከራክሯል።
የደሴ ከተማ ዋናው የውሃ ምንጭ በጦሳ ተራራ የሚገኘው ቦታ ነው። በተራራው አካባቢ ቤት ከተሰራ የውሃው ህልውና አደጋ ውስጥ ሊገባ ስለሚችል መሰራት እንደሌለበት ማህበሩ አሳውቋል። በተጨማሪም ከከተማው ውሃና ፍሳሽ ቢሮ ጋር በመነጋገር ቤቶች እንዳይሰሩ ተደርጓል። ቦታውም ለአረንጓዴ ልማት እንዲውል ለማድረግ ማህበሩ ቦታው እንዲሰጠው ጠይቋል። አስተዳደሩ በቃል ደረጃ ቦታው ለማህበሩ
እንደሚሰጥ ቢናገርም በወረቀት ደረጃ እስካሁን የመጣ ነገር የለም። የከተማ አስተዳደሩ ፈጣን መልስ የሚፈልጉ ጉዳዮች ላይ መልስ መስጠት ደካማ ነው። ህብረተሰቡ ግን ለማህበሩ ጥሩ ድጋፍ እያደረገ ነው።
የማህበሩ ቀጣይ እቅድ
ማህበሩ ችግሮች ቢኖሩበትም በከፍተኛ ሁኔታ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ የሚገኘው ስራ አለ። በመጪው ምርጫ በሰላም እንዲጠናቀቅ ማህበሩ ከወዲሁ ስራዎችን ጀምሯል። በሌላም በኩል ህብረተሰቡ ያለምንም ስጋት ወጥቶ የፈለገውን እንዲመርጥ ጥረት ይደረጋል። ማህበሩ በርካታ ጉዳዮችን አቅዶ ቢንቀሳቀስም ብዙ ስራዎችን አከናወነ ማለት አይቻልም።
ነገር ግን የከተማ አስተዳደሩና የክልሉ መንግሥት ማህበሩን ያውቁታል። በክልል ደረጃ በተዘጋጁ መድረኮች ሰርተፍኬት አግኝቷል። ማህበሩ በደሴ ከተማ ብቻ ሳይሆን በአገር አቀፍ ደረጃ እንዲሰራ እገዛ ሊደረግለት ይገባል።
በቀጣይ ማህበሩ ተለቅ ተለቅ ያሉ እቅዶችን አዘጋጅቷል። ከነዚህ ውስጥ እንደ ደሴ ከተማ ቤት ውስጥ የዋሉ ጧሪ ቀባሪ የሌላቸው ሰዎች እንዲሁም በጣም ከፍተኛ ችግር ያለባቸው ሰዎች ቤት ለቤት በተደረገ አሰሳ ተገኝተዋል። እነዚህን ሰዎች ለመርዳት ተቋም ለመመስረት ማህበሩ አቅዷል።
ተቋሙን ለመገንባት አስተዳደሩ የተጠየቀው መሬት የሚሰጥ ከሆነ በፍጥነት ወደ ስራ ይገባል። በሚገነባው ተቋም ሰዎቹ በየቀኑ ምግብ እንዲያገኙና በፈለጉበት ሰዓት መጥተው ተመጋቢ እንዲሆኑ ሁኔታዎች ለማመቻቸት ታስቧል።
በሌላ በኩል በመንግሥት ታቅደው የተረሱና በአየር ላይ የቀሩ በርካታ ስራዎች ያሉ ሲሆን እነዚህ ስራዎች ለምን እንደቀሩና መች እንደሚሰሩ የሚሉ ጥያቄዎችን ማህበሩ አዘጋጅቷል። የተዘጉና ምንም አይነት አገልግሎት የማይሰጡ ለምሳሌ ለወጣት መዝናኛ ተብለው የተሰሩ አገልግሎቶች በጣም አነስተኛ ናቸው። ከነዚህም ውስጥ አንዱ ለወጣት መዝናኛ የተባለ ቦታ ላይ የተሰራ መጋዘን አለ። የተገነባው መጋዘን ምንም አይነት አገልግሎት እየሰጠ አይደለም።
ይህን ቦታ ለወጣቶች መዝናኛና የወጣት ማዕከል ሆኖ ማገልገል አለበት በሚል ትግል እየተደረገ ነው። ወጣቱ ወደ አንድ አካባቢ ለማምጣት መጋዘኑ ወሳኝ ቦታ በመሆኑ የፌዴራል መንግሥትን ለመጠየቅ ማህበሩ ተዘጋጅቷል።
ይህ ከተሳካ በከተማው የሚገኘው አንድ ወጣት መዓከል ወደ ሁለት ያሳድገዋል። ቦታው የክልሉ መንግሥት የያዘው ቢሆንም ህንፃውን የሰራው የፌዴራል መንግሥት ነው የሚል ውዝግብ አለ። ነገር ግን የፌዴራል መንግሥት ቦታውን ለወጣቱ ይሰጣል የሚል እምነት አለ።
አዲስ ዘመን የካቲት 19/2013