መርድ ክፍሉ
በአሁኑ ወቅት ብዙ ወጣቶች በየአካባቢያቸው ከሚመለከቷቸው ችግሮች በመነሳት ለችግሮቹ መፍትሄ መሆን የሚችሉ የፈጠራ ስራዎችን እያከናወኑ ይገኛሉ። ከእነዚህ ወጣቶች መካከል ለዛሬ የሁለቱን የፈጠራ ስራዎች እናስቃኛችኋለን። ለጽሑፉ ግብዓት የሆኑ መረጃዎችን ከፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬትና ከቢቢሲ ተጠቅመናል።
ብስክሌትን በውሃ ላይ ያስኬደ ወጣት
ጌታባለው መኩሪያው ይባላል። በሞከረው የብስክሌት ጀልባ በርካታ አድናቆቶች ተችረውታል። መኖሪያው ደግሞ የጣና በለስ የስኳር ፕሮጀክት በሚገኝበት አዊ ዞን ጃዊ ከተማ ነው። በከተማው መግቢያ አካባቢ ለሚገኘው የስኳር ፋብሪካ ታስቦ የተገነባ ሰፊ የሸንኮራ አገዳ እርሻ በአካባቢው አለ። እርሻው ክረምት ክረምት በአካባቢው ከሚጥለው ዝናብ ውሃ የሚጠቀም ሲሆን በበጋ ወቅት ደግሞ ለዚሁ ሲባል ከተገነባው የመስኖ ግድብ ውሃ ያገኛል። ጌታባለውን ጨምሮ የአካባቢው ልጆች ከአካባቢው ሙቀት ራሳቸውን ለማቀዝቀዝም ሆነ እንደ መዝናኛ ግድቡ ቦታ በመሄድ ይዋኝ ነበር። በዚህ ጊዜ ለምን ጀልባ አልሠራም ብሎ አሰበ። መጀመሪያ ሊሠራ ያሰበው በብዙ ቦታዎች የሚገኘውንና የተለመደውን ባለመቅዘፊያ ጀልባ ነበር። በኋላ ላይ ግን ሐሳቡን በመቀየር የብስክሌት ጀልባ የመሥራት ሃሳቡ መጣለት።
በውሃ ላይ የሚንሳፈፈውን ጀልባ እየሰራ ባለበት ወቅት ፔዳል ያለው ጀልባ የመስራት ሃሳብ መጣለት። ሆኖም የብስክሌት ጀልባውን ሠርቶ ለማጠናቀቅ ዓመታትን መጠበቅ ግድ ሆኖበት ነበር። የብስክሌት ጀልባውን ለመሥራት ብዙ ጊዜ የሚፈጅ ባይሆንም ወጪው ብዙ በመሆኑ ምክንያት ችግር አጋጥሞት ነበር። ይህንን ሁሉ ተቋቁሞ የብስክሌት ጀልባውን እውን ለማድረግ የተነሳው ጌታባለው መጀመሪያ ላይ ሙከራ ያደረገው እጅግ ብዙ ብረት እንዲኖረው አድርጎ ስለነበር ክብደቱ ከፍተኛ መሆኑ ለመንሳፈፍ አስቸጋሪ አደረገበት።
በዚህ ወቅት አገልግሎት ከሰጡ እና ክብደት ከሌላቸው ዕቃዎች ጀልባውን መሥራት ጥሩ መፍትሔ መሆኑን በማመን በዚሁ መሠረት መሥራት ጀመረ። ይህም ጀልባው በቀላሉ እንዲንሳፈፍ ከመርዳቱም በላይ በአነስተኛ ወጪ ሠርቶ ለማጠናቀቅም የሚያስችለው ሆኖ አግኝቶታል። ሙሉ ለመሉ ሠርቶ ያጠናቀቀው በቅርቡ ቢሆንም ስለ ጀልባው ማሰብ የጀመረው ከሁለት ዓመታት በፊት ነው። ቱቦዎች ጀልባው እንዲንሳፈፍ የሚረዱ ናቸው። ብስክሌቱ ደግሞ ለመቀመጫነት የሚያገለግል ሲሆን ጀልባውን ለማንቀሳቀስ እና መሪውን ተጠቅሞ ወደ ተፈለገው አቅጣጫ ለመጓዝ የሚያስችል ነው።
ከብስክሌቱ ፔዳል ጋር የሚገናኘው ተሽከርካሪ ደግሞ ውሃውን ወደኋላ በመግፋት ጀልባው ወደ ፊት እንዲንቀሳቀስ ያግዛል። የብስክሌት ጀልባዎች ከቦታ ቦታ ለመንቀሳቀስ ከመርዳታቸውም በላይ እንደ አንድ የመዝናኛ መንገድ ጥቅም ላይ የሚውሉ እና አካላዊ እንቅስቃሴ ለማድረግም የሚያግዙ ናቸው። ሌሎች የብስክሌት ጀልባ ዓይነቶችን ከተለያዩ ድረ-ገጾች መመለከት ቢችልም የእሱ የብስክሌት ጀልባ በብዙ ምክንያት ይለያል ። ብዙ ዓይነት የብስክሌት ጀልባዎች ቢኖሩም ይሄ በቀላሉ እና አገልግሎት ከሰጡ ዕቃዎች ቤት ውስጥ መሠራቱ ለየት ያደርገዋል።
ከዚህ በተጨማሪም በቀላሉ ተፈትቶ የሚገጣጠም ከመሆኑም በላይ ይዞ ለመንቀሳቀስም የሚያስቸግር አይደለም። የብስክሌት ጀልባውን ሠርቶ ሲያጠናቅቅ ጋራዥ ውስጥ ካገዙት ሰዎች ጋር በመሆን የመሞከር ስራ ሰርተዋል። ሥራውን በሚሠራበት ወቅት ከቤተሰቦቹ ውጭ ድጋፍ ያደረገለት አካል ባይኖርም ጋራዥ ውስጥ የሚሠሩ ጓደኞቹ ያደረጉለት ድጋፍንም ግን ሳያነሳ አያልፍም። ይሁን እንጂ ስለ ብስክሌት ጀልባው በማህበራዊ ሚዲያ ብዙዎች ከተጋሩት በኋላ የባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ባልደረቦች አናግረውት የነበር ቢሆንም ምንም ድጋፍ አላደረጉለትም።
የፈጠራ ሥራው በብዙ መልኩ መሻሻል የሚችል ሲሆን ፈጠራው ተሻሽሎ በሞተር እንዲንቀሳቀስ ማድረግ የሚያስችሉ ሁኔታዎች አሉ። በአካባቢው ያለው ውሃ ለመስኖ አገልግሎት ተብሎ የተሠራ በመሆኑ ለመዋኘትም ሆነ በጀልባ ለመዝናኛነት አይፈቀድም። ጀልባ ለመጠቀም ሴፍቲ ጃኬት መጠቀምም ግዴታ ነው። ይህንን ለማግኘት ባህርዳር ድረስ ሄዶ ቢጠይቅም ሊያገኝ አልቻለም። የግድቡ ውሃ ደግሞ አነስተኛ መሆኑ ሌላው ችግር ነው። ይህንን ከግምት ውስጥ በማስገባትም የብስክሌት ጀልባዋ ጣና ሐይቅ ላይ አገልግሎት እንድትሰጥ ወደ ባህርዳር ለመውሰድም አቅዶ ነበር።
ነገር ግን ባህርዳር ውስጥ የሚያውቀው ሰው ባለመኖሩ ጀልባውን የሚያስቀምጥበት ቦታ የለውም። እነዚህ ችግሮች ግን ተስፋ አላስቆረጡትም። ይህ የመጀመሪያው ፕሮጀክት ቢሆንም ሌሎች የሚያስባቸው ሥራዎችም አሉት። ብቻውን መሥራት አይችልም፤ የሚያግዘው ተቋምም ሆነ ግለሰብ ሲኖር ወደ ተግባር መግባት የሚችለው። የሌሎች ተባባሪ አካላት እርዳታ ያስፈልገዋል። በዚህም ምክንያት እንዳሰበው ሌሎች ዕቅዶቹን ወደ ሥራ ለማስገባት አልቻለም፤ ዋናው ምክንያቱ ደግሞ የኢኮኖሚ ችግር ነው።
የብዙ ፈጠራዎች ባለቤቱ ወጣት
በወልቂጤ ከተማ የሚኖረው ኢዘዲን ካሚል ያደገው የወልቂጤ ክፍለ ከተማ በሆነችው ጉብሬ ውስጥ ነው። ወደ ቴክኖሎጂ ፊቱን ሲያዞር ገና የ14 ዓመት ታዳጊ የነበረ ቢሆንም ለፈጠራዎቹ ከተለያዩ ተቋማት ከሥራዎቹ በቁጥር የማይተናነሱ ሰርቲፊኬቶች ተሰጥተውታል። ያደገበት ከተማ ለቴክኖሎጂ ያላት ቅርበት እንደ አዲስ አበባ ስላልሆነ ለፈጠራ ሥራው የሚያስፈልጉት እንደ ላፕቶፕ፣ ኢንተርኔትና ሌሎች ቁሳቁሶችን እንደልብ አለማግኘቱ ተስፋ አላስቆረጠውም። ለዚህም በአካባቢው ከሚያገኛቸውም ሆነ አንዳንድ ጊዜ አዲስ አበባ ድረስ በመሄድ አገልግለው የተወገዱ ወይም የወዳደቁ ዕቃዎችን ከመርካቶ በትንሽ ዋጋ በመግዛት ያሰባቸውን አዳዲስ ፈጠራዎች እውን እያደረገ ይገኛል።
ከሰላሳ በላይ የፈጠራ ስዎች ያሉት ሲሆን ሰባት አንድሮይድ አፕልኬሽን፣ ለአስራሦስት ፈጠራዎች ‹‹ከሴቭ አይድያ ኢንተርናሽናል›› ምዝገባ አግኝቷል፣ ከኮሮና ቫይረስ ጋር በተያያዘ ሁለት የፈጠራ ስራዎችን የሰራ ሲሆን አጋዥ ቬንትሌተርና ከእጅ እጥበት ጋር በተያያዘ ደግሞ ከንክኪ ነፃ የሆነ በእግር የሚሰራ መታጠቢያ ይገኙበታል።
በተጨማሪም በፀሀይና በኤሌክትሪክ የሚሰራ ባለሦስት እግር ተሽከርካሪ የሰራ ሲሆን አምስት መቶ ኪሎግራም መሸከም የሚችልና ስልሳ ኪሎሜትር በሰዓት መጓዝ ይችላል። ‹‹ኤክስ ፋይል›› የሚባል እሳት አደጋ ሲነሳ ለአምስት የቤተሰብ አባላት ደውሎ የሚያሳውቅና እየጮኸ ጎረቤት የሚጠራ ፈጠራ ነው። በፀሀይና በኤሌክትሪክ ቻርጅ የሚደረግ ሳይክል፣ መልቲ ሎክ ሲስተም ያለው በርና ውጭ አገር ሆኖ በሩን መክፈትና መዝጋት የሚያስችል ቴክኖሎጂም ፈጠራ ማበርከት ችሏል።
በኮሮና ወረርሽኝ ወቅት ለእጅ መታጠቢያ እንዲረዳ የተዘጋጀው ፈጠራ በወልቂጤ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ እገዛ ነው። የዚህ ፈጠራ ሀሳብ የመጣው በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች በመንገዶች ላይ እጅ ያስታጥቡ ነበር። ወጣቶቹ እርቀታቸውን ሳይጠብቁ እንዲሁም የሚታጠቡትም ታጭቀው በመሆኑ ችግሩን ለመፍታት የተሰራ ነው። ፈጠራው ቅድሚያ ታስቦ የነበረው በኤሌክትሪክ ሲሆን መታጠቢያው ፊትን በማየት ብቻ የሚያስታጥብ ነበር ነገር ግን በመንገድ አካባቢ ኤሌክትሪክ ስለሌለ በእግር እንዲሆን ተደርጓል።
ሌላው ታማሚዎች ትንፋሽ በሚያጥራቸው ሰዓት ‹‹የአምቦባግ›› ጥቅም ላይ ይውላል። የኮቪድ 19 ወረርሽኝ ከመጣ በኋላ የመተንፈሻ ቬንትሌተር እጥረት ተከስቷል። ይህንን ችግር ለመፍታት አምቦባግን በመጠቀም የቬንትሌተር ፈጠራ ሰርቷል። ፈጠራው ከንክኪ በፀዳ መልኩ አገልግሎት እንዲሰጥ ተደርጓል። ይህን ፈጠራ በብዛት በግል እንዲሰራላቸው የሚያዙ ሰዎች አሉ። በቀጣይ ከኮሮና ቫይረስ ጋር በተያያዘ ብዙ ፈጠራ ስራዎች እያከናወነ ይገኛል። ለፈጠራ ስራዎቹ ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ቀና ትብብር አድርገውለታል። እንዲሁም የወልቂጤ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ በድጋፍ ብዙ ስራ እንዲሰራ ተባብረውታል።
ሌላው የፈጠራ ስራው መብራትን በብሉቱዝ ማብራትና ማጥፋት ነው። ይህ የፈጠራ የአካል ጉዳተኞች ሊጠቅም ይችላል። ከ20 ሜትር ውስጥ ጥቅም መስጠት ይችላል። በተጨማሪም በየትኛውም አገር ላይ ሆኖ መብራት ማጥፋትና ማብራት የሚያስችልም ፈጠራ የሰራ ሲሆን ፈጠራው ስልክ በመደወል መብራት መቆጣጠር የሚያስችል ቴክኖሎጂ ነው። ሌላው ደግሞ ብቻውን የሚኖር ሰው ምግብ ለማብሰል የሚያግዘው የፈጠራ ቴክኖሎጂ የሰራ ሲሆን ፈጠራው ስቶቭ ወይም ማብሰያው ላይ በተገጠመ መሳሪያ የሚሰራ ነው።
ከፀሐይ ኃይል ማመንጨትንና ባደጉ ሃገራት ውስጥ ጥቅም ላይ የሚውሉ አጠቃላይ የቤት ውስጥ መገልገያ ቴክኖሎጂዎችን አስቦና አስተውሎ መሥራት ያልተሳነው ይህ ወጣት “ማንም ሰው ምንም ነገር ለመፍጠር ሲያስብ ከችግር ተነስቶ ነው ሊፈጥር የሚችለው” በማለት የሥራዎቹን መነሻ ምክንያት ይናገራል።
ብዙውን ጊዜ በቀን ሩጫ የተጠመደ ሰው ማለዳ ስልኩን ሙሉ በሙሉ ቻርጅ አድርጎ ቢወጣም አንዳንድ ጊዜ በቀኑ መጨረሻ ግን የስልኩ ባትሪ ሊያልቅ የሚችልባቸው አጋጣሚዎች አይጠፉም። አንዳንዴ ለአካባቢ ብክለት ታስቦም ይሁን ብዙ ገንዘብ የማያስወጣና የማያደክም የትራንስፖርት አማራጮችን የሚፈልጉም ሰዎች ከመካከላችን ላይጠፉ ይችላሉ። አልፎ አልፎ በችኮላ መካከል ጠዋት ተጥዶ የነበረውን ሻይም ሆነ መጥበሻ እዚያው ከማብሰያው ላይ ተረስቶ የሚወጡባቸውም ቀናት ሊያጋጥሙ ይችላሉ ወይንም የተረሳ ሻማ ቃጠሎ የሚፈጥርበት ጊዜ ይኖራል።
ለእንደዚህ ዓይነት የዕለት ተዕለት ችግሮችና ከባድም ሆነ ቀላል ጉዳትን ሊያስከትሉ ለሚችሉ አደጋዎች መፍትሄ የሚሆኑ ዘዴዎችን ኢዘዲን ሠርቷል። የፀሐይን ኃይል በመጠቀም የእጅ ስልክ ቻርጅ የሚያደርግ ጫማ፣ ተቀምጠው ብቻ የፀሐይን ብርሃን በመጠቀም እንደ ሞተርሳይክል ያለ ፔዳል በእራሱ የሚሄድ ብስክሌት፣ ያልጠፉ የቤት መገልገያ ዕቃዎችን የሚያጠፋ እና የእሳት አደጋን የሚጠቁም መሣሪዎች ከሚጠቀሱት መካከል ናቸው።
አንድ ቀን የእጅ ስልኩን ቻርጅ እንዲያደርግ ቤቱ ትቶት ወደ ሌላ ቦታ ሄዶ ሲመለስ የጠበቀው ክስተት በጄሪካን ለሠራው ፈጠራ ጅማሬ ሆኖታል።
ሲመለስ የጎረቤታቸው ቤት በእሳት ጋይቶ ጠበቀው። መጀመሪያ ላይ ድንጋጤው ውስጥ ሆኖ የነበረ ሲሆን ከዚያ ሰው ሁሉ ሲሯሯጥ እሱም እሳቱን ለማጥፋት ለማገዝ ሞከረ። ኢዘዲን ቻርጀር ላይ ተሰክቶ የነበረው ስልኩን አስታውሶ ለእሳት አደጋው ጥሪ ሰጪ ቢሆን የሚል ሀሳብ መጣለት። ሃሳቡን ወደ ተግባር በመለወጥ ቤት ውስጥ የሚፈጠርን ጭስ በመለየት የእሳት አደጋ ምልክትን በአቅራቢያ ላሉ ሰዎች በድምፅ ይሰጣል። በዚህም በቅርብ ያሉ ሰዎች እርምጃ ካልወሰዱ በመሣሪያው ላይ በተገጠመ ስልክ አማካይነት መዝግቦ ለያዛቸው ሁለት ቁጥሮች ለምሳሌ ለቤቱ ባለቤት እና ለእሳት አደጋ መከላከያ በመደወል የእሳት አደጋ ጥሪ ያስተላልፋል።
ኢዘዲን እስካሁን ለሠራቸው የተለያዩ የቴክኖሎጂ ፈጠራ ሥራዎቹ ብዙ የሚያመሰግናቸው ሰዎች ቢኖሩም፤ በቀዳሚነት የሚማርበትን ዩኒቨርሲቲ ጠቅሶ እንደልቡ የሚመራመርበትን ክፍል ከማዘጋጀት ባሻገር በተለያዩ ጊዜያት ለፈጠራ ሥራዎቹ ያስፈልጉኛል ብሎ የሚጠይቃቸውን መሣሪያዎች እና ቁሳቁሶች እንዲገዙለት አድርገዋል። በተጨማሪም ከካቶሊክ ሚሽን ጋር የተያያዙ ድርጅቶችና ሁለት ጣልያናዊ ሙዚቀኞች ለሦስት ተከታታይ ዓመታት እንደረዱት እንዲሁም 34 ሺህ ብር፣ አርድዊኖ የተባለ ሶፍትዌር እና ሁለት ላፕቶፕ ኮምፒዩተሮችን አበርክተውለታል።
የተለያዩ ውድድሮች ላይ ከመሳተፍ ወደ ኋላ የማይለው ኢዘዲን በቅርቡ በተሳተፈበት ውድድር ላይ የ300 ሺህ ብር ተሸላሚ መሆኑንና ስድስት የተለያዩ የፈጠራ ሥራዎችን ሠርቶ እንዲያቀርብ ተጠይቆም ነበር። በዚህም በጣም ተደስቶ አሁን ስድስት ሥራዎቹን በትክክለኛ ዕቃዎች ሠርቶ ማቅረብ ይችላል። ከተለያዩ ድርጅቶች፣ ማዕከላትና ተቋማት ሰርተፍኬትና ሽልማት ያገኘው ኢዘዲን ከሁሉም በላይ በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ እውቅና ተስጥቶት መሸለሙ ወደፊት ለሃገሩ ብቻ ሳይሆን አህጉሪቱንም ተሻግሮ ለዓለም ብዙ ነገሮችን ሊያበረክት እንደሚችል ተስፋ አለው። ከሁሉም በላይ የወጣትነት ሕልሙ አሁን የውጪ ትምህርት ዕድል አግኝቶ ብዙ ነገሮችን ደግሞ ወደፊት መሥራት ይፈልጋል።
አዲስ ዘመን የካቲት 05/2013