መርድ ክፍሉ
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከሚያወጣቸው መረጃዎች መገንዘብ እንደሚቻለው ዓለማችን በየቀኑ ለመኖር የማትመች እያደረጓት ያሉ ፈተናዎቿ በቁጥር እየጨመሩ ነው። እነዚህም ችግሮች መፍትሔ እንዲያገኙ ደግሞ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ከሚያደርጓቸው ድጋፎች በተጨማሪ የእያንዳንዱን የምድር ነዋሪ የበጎ ፈቃደኝነት አገልግሎት የሚሹ ሆነዋል።
በጎ ፍቃድ አገልግሎት ማለት በፍቃደኝነት ላይ የተመሰረተ ተሳትፎ በማድረግ ውስጣቸው ከሚሰማቸው ሰብዓዊ አመለካከት ተነስተው ለሚኖሩበት ማህበረሰብ ሰፊ የልማት አውታሮችን በመዘርጋት የዜግነት ኃላፊነትን የሚገነዘቡ ሃገራዊና ብሔራዊ ግዴታዎችን የሚያውቁበት በማህበራዊ ሚናዎች ስር ግንባር ቀደም የሚሆኑና የሃገርና የወገን ፍቅርን የሚያዳብሩበት ትልቅ ሚና ያለው ተግባር ነዉ።
እነዚህ ወጣቶችም ባላቸው የእረፍት ጊዜያቸውን መስዋዕት አድርገው ልማትን ለማምጣትና ለአካባቢ ደህንነት ነጻ ጊዜያቸውን፣ ገንዘባቸውን፣ ጉልበታቸው እና እውቀታቸውን በተጨማሪም በጎ አመለካከትን የሚያውሉበት ስራ ሲሆን ሌሎችን ከመርዳት አኳያም በጎ ምኞትን ተላብሰው ከማህበረሰባቸው ጎን ሁነው የሚያውቁትን የሚያስተምሩበትና ከሌሎች አካላትም የህይወት ክህሎት የሚቀስሙበት ዋነኛ መንገድ ነው።
የኮቪድ 19 ወረርሽን ወደ ኢትዮጵያ ከገባ በኋላ አቅም የሌላቸውን ሰዎች ለመርዳትና ለመደገፍ ብዙ በጎ አድራጎት ማህበራት ተመስርተዋል። ማህበራቱ የእለት የምግብ ድጋፍ ከማቅረብ በተጨማሪ በየወሩ የገንዘብ ድጋፍ እስከማድረስ ተሻግረዋል። ማህበራቱ በወጣቶች የተደራጀ በመሆኑ የደም ልገሳ፣ የከተማ ፅዳት እንዲሁም ቤት ለቤት በመሄድ አቅመ ደካሞችን በስራ እያገዙ ይገኛሉ።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በዓላትን ጠብቆ ቤት የማደስ፣ ማዕድ ማጋራት እንዲሁም በዘላቂነት ድጋፍ የሚፈልጉትን በመደገፍ ባለፉት ሁለት ዓመታት ውጤታማ ስራ ሰርቷል። ይህም ስራ ብዙ ወጣቶችን አበረታቶ በአሁን ወቅት ብዛት ያላቸው ማህበራት ፈቃድ አውጥተው እንዲንቀሳቀሱ መንገድ ከፍቶላቸዋል።
በአዲስ አበባ በተለያዩ አካባቢዎች የተቋቋሙት የበጎ አድራጎት ማህበራት ድጋፍ የሚፈልጉ ሰዎችን ባላቸው አቅም እርዳታ ቢያደርጉም ከህብረተሰቡ ግን የሚፈለገውን ያክል ተቀባይነት እያገኙ አይደሉም። ህብረተሰቡ ያለውን በአቅሙ እንዲያዋጣ ሲጠየቅ ከመሳደብ እስከ መማታት የደረሰ ሁኔታ እንደሚፈጠር ብዙ ማህበራት እንደ ችግር ያቀርባሉ።
ህብረተሰቡም አጭበርባሪዎች በመብዛታቸው ሕጋዊውን ማህበር ለመለየት ተቸግረናል የሚል መማረር ያሰማል። ለዚህ ደግሞ መፍትሄው የበጎ አድራጎት ማህበራትና ህብረተሰቡ ተጋግዞ የሚሰራበት ሁኔታ መፈጠር አለበት።
የመረዳዳትም ሆነ በልክ የመኖር ባህሎች ዛሬም እንዳሉ የሚያሳዩ ተግባራት እንዳልጠፉ በርካታ ማሳያዎችን ማንሳት ይቻላል። በተለይ በቅርቡ የኮቪድ 19 ወረርሽኝ መከሰትን ተከትሎ በርካታ ዜጎች ለከፍተኛ የኑሮ ጫና መዳረጋቸው ይታወሳል።
ይህንን ክፉ ጊዜ ለማለፍ ደግሞ የደጋግና ቅን ልቦች መኖር ትልቅ አስተዋፅኦ ማድረጉን ስንመለከት የመረዳዳት ባህላችን ዛሬም ጠንካራ መሆኑን እንገነዘባለን። ዛሬ በአዲስ አበባ የሚገኘው ነገን ናፋቂዎች በጎ አድራጎት ማህበር ጋር ቆይታ አድርገናል።
የማህበሩ ሥራ አስኪያጅ ወጣት ራውል ፒዳ እንደሚናገረው፤ ማህበሩ የተመሰረተው በ2012 ዓ.ም ላይ ሲሆን የተቸገሩ ሰዎች ድጋፍ ማድረግ የመጀመሪያው አላማ አድርጎ የተመሰረተ ነው።
ከዚህ ባሻገር የበጎ ፈቃድ ስራን በማበረታታት ወጣት በጎ ፈቃደኞችን ለማበራከት ነው። በጎ የሚያደርጉ ወጣቶች በበዙ ቁጥር ደጋፊ የሌላቸው፣ ጧሪ ቀባሪ ያጡ እንዲሁም ሰው የማያያቸውን ድጋፍ ለማድረግ ይረዳል።
ማህበረሰቡ አካባቢ የበጎ አድራጎት ሥራ ሲሰራ ተቀባይነቱ ብዙ አጥጋቢ አለመሆኑን ይናገራል። የማህበሩ አባላት ወጣቶች ስለሆኑ ከአመኔታ ጋር እንዲሁም ብዙ ጊዜ ህብረተሰቡ በብዙ መንገድ ድጋፍ እንዲያደርግ ስለሚጠየቅ የመሰላቸው ሁኔታዎች እንደሚኖሩ ይናገራል። ከማህበሩ እቅድ አንፃር ብዙ ሰዎችን ለመደገፍ አስቸጋሪ እንደሆነባቸው ይጠቅሳል።
ማህበሩ በተቻለው አቅም ሥራዎችን እያከናወነ ውጤት ሲያመጣ ህብረተሰቡ በራሱ ተነሳሽነት የተወሰነ ድጋፍ እያደረገ መሆኑንም ያመለክታል። ማህበሩ የተደራጀ ተቋም ባይኖረውም ከተለያዩ ሰዎች የሚገኙ ድጋፎችን ለሚገባቸው ሰዎች የማድረስ ስራ እንደሚያከናውን ይጠቁማል። በአካባቢው የሚገኙ አቅመ ደካሞችን ቤት ለቤት በመሄድ አስቤዛዎችንና የንፅህና መጠበቂያ ቁሳቁሶችን ድጋፍ እንደተደረጉ ይናገራል።
ህብረተሰቡ ስለበጎ ፈቃድ አገልግሎት ያለው አመለካከት በደንብ ባለመዳበሩ ምክንያት ተቀባይነት ለማግኘት መቸገራቸውን ይናገራል። ለዚህ ደግሞ ህብረተሰቡ እውቅና ያለው ሰው ሲጠይቀው እንጂ ወጣቱን ለማገዝ ምንም ፍላጎት አያሳይም።
ታዋቂና ተፅዕኖ የሚፈጥሩ ሰዎች ከህብረተሰቡ በቀላሉ የሚፈልጉትን ነገር ማግኘት ይችላሉ። በወጣቶች የበጎ አድራት ማህበር ሲመሰርቱ ህብረተሰቡ ሰለማያውቃቸው ግብዓት ለማግኘት እንደሚቸገሩ ይጠቅሳል።
መንግስትም ምንም አይነት ድጋፍ እንደማያደርግላቸው የሚጠቁመው ወጣት ራውል፤ በዓመት አንድ ጊዜ ለሪፖርት ወይም ለኦዲት ከመንግስት አካላት ጋር ግንኙነት እንደሚደረግ ይጠቁማል።
በነዚህ ምክንያቶች አባል የነበሩ ሰዎች እንደሚለቁም ይጠቅሳል። ቢሮ ለማግኘት መቸገርና ድጋፍ ማጣት ብዙ ስራዎች ለመስራት የተቋቋመን ማህበር እንቅፋት እንደሚፈጥርበት ይናገራል።
በዚህም የሚረዱ ሰዎች እንደሚቸገሩ ይጠቁማል። የማህበሩን ስራ ለማስተዋወቅና አላማውን ህብረተሰቡ እንዲያውቀው ለማድረግ እንቅስቃሴዎች ያሉ ሲሆን ገቢ ማሰባሰብ ላይ ብዙም ትኩረት አለመሰጠቱን ያመለክታል። ነገር ግን ትኬቶችን በማዘጋጀትና በመሸጥ በሚገኘው ገንዘብ አስቤዛ በመግዛት ለችግረኞች እንደሚሰጥ ይገልፃል።
በቀጣይ ግን ማህበሩን የማቋቋም ስራ ለማከናወን ታዋቂ ግለሰቦች ስለ ማህበሩ እንዲያውቁ በማድረግና አሁን ያጋጠሙ ችግሮች ሲቀረፉ የገቢ ማስገኛ መንገዶችን በመፍጠር የሚደረጉትን ድጋፎች ለማሳደግ ታስቧል። በአሁን ወቅት የሚገኙ ድጋፎች በቀጥታ ለተቸገሩት የሚውል ነው። በሌላም በኩል ትኬቶችን በመሸጥ የሚደረጉትን ድጋፎች አጠናክሮ ለመቀጠል ሀሳብ እንዳለም ይናገራል።
ወጣት ራውል እንደሚገልፀው፤ ማህበሩ ከተመሰረተ ዓመት የተቆጠረ ሲሆን በርካታ ሰዎች ስለማህበሩ በተወሰነ መልኩ እያወቁ መጥተዋል። ማህበሩ ፈረንሳይ ለጋሲዮን በሚገኝ ወጣት ማዕከል ውስጥ ቢሮ ተሰጥቷቸው እየተንቀሳቀሱ ነው። የአካባቢው ህብረተሰብ ሊረዱ የሚገባቸው ሰዎችን ይዘው ቢሯቸው ይመጣሉ።
የህብረተሰቡ አመኔታ በተወሰነ መንገድ እያደገ መምጣት ማህበሩን የሚያጠናክረው ነው። በማህበራዊ ሚዲያ ላይ ማህበሩ በከፈታቸው ገፆች ከተለያዩ አካባቢዎች ሰዎች ድጋፍ እያደረጉ ይገኛሉ። በዚህም ማህበረተሰቡ ከጎናቸው መሆኑን እያዩበትም ነው።
ማህበሩ በሌሎች በጎ አድራጎት ማህበራት በመሄድ የቁሳቁስ ድጋፍ እንደሚያደርጉ የሚናገረው ወጣት ራውል፤ ጌርጌስዮንና ሙዳይ በጎ አድራት ማህበር በመሄድ ድጋፍ እንደተደረገ ይጠቅሳል።
ማህበሩ በቀጣይ የህብረተሰቡን ችግር በጥናት በመለየት ድጋፍ የሚያስፈልጋቸውን መርዳት ትልቁ እቅድ ነው። ነገር ግን ድጋፍ የሚፈልጉ ሰዎች ሁሌም በእርዳታ እንዳይቆዩ ከባለሀብቱ ጋር በመነጋገር ዘላቂ የሆነ ነገር በመፍጠር የገቢ ምንጭ እንዲፈጥሩ ሀሳቦች አሉ።
በቀጣይ ዓመት ማህበሩ ትልቅ ፕሮጀክቶችን ያሰበ ሲሆን ፕሮግራሙ ድጋፍ ሲደረግላቸው የነበሩ ሰዎች የስራ እድል ተፈጥሮላቸው እራሳቸውን የሚችሉበትን ሁኔታ ይፈጥራል ተብሎ ይታሰባል። ከማህበሩ አቅም በላይ ስራዎች ሲመጡ ታዋቂ ሰዎችን እንዲደግፉ ይደረጋል። በበዓላት ወቅት ደግሞ በርካታ ሰዎችን ለመደገፍ የሚያስችል ስራ ለማከናወን እቅድ መያዙን ያመለክታል።
ሌላው የማህበሩ አባል ወጣት ዮናስ ተገኑ እንደሚናገረው፤ የበጎ አድራጎት ማህበር መስርቶ መንቀሳቀስ በራሱ ብዙ ችግሮች አሉት። እነሱ ድጋፍ በሚያደርጉበት ወቅት አንድ በዊልቸር የሚንቀሳቀሱ ሴት አግኝተው ነበር።
ሴትየዋ በማህበሩ ተደጋጋሚ ድጋፍ ተደርጎላቸውም ነበር። ሴትየዋን በቋሚነት የሚደግፍ ሰው በአጋጣሚ ተገኝቶ ጥሩ እንክብካቤ ማግኘት ጀመሩ። በአንድ ወቅት የገቢ ማሰባሰቢያ ትኬት እየተሸጠ በነበረበት ወቅት ሴትዮዋ እኔም ገዝቼ ድጋፍ ማድረግ አለብኝ ብለው አስተዋፅኦ ማድረጋቸውን ያስታውሳል።
እንደዚህ አይነት ተመሳሳይ ሁኔታዎች እንደሚ ያጋጥሙ የሚናገረው ወጣት ዮናስ፤ ከዚህ ሁኔታ መማር የሚቻለው ትንሽም ሲኖራቸው መርዳት የሚፈልግ ብዙ ሰው እንዳለ ነው። ድጋፍ በሚደረግበት ወቅት የሰዎችን ደስታ ማየት እራሱን የቻለ የአዕምሮ እርካታ እንደሚሰጥ ይናገራል። የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረግ ቢችሉ ውጤታማ ስራ መስራት እንደሚቻል ይጠቁማል።
ድጋፍ ለሚደረግላቸው ሰዎች ገንዘብ ለመሰብሰብ የትኬት ሽያጭ ይከናወናል። በሲ.ኤም.ሲ አካባቢ የማህበሩ አባላት ትኬት እየሸጡ በነበረበት ወቅት አንድ ሰው ‹‹ሌቦች ናችሁ›› ብሎ ችግር ተፈጥሮ እንደነበረ ያስታውሳል።
ገቢ ማሰባሰቢያው አብዛኛው ቤት ለቤት በመሄድ በሚደረግ ትኬት ሽያጭ በመሆኑ ህብረተሰቡ ለመተባበር እንደሚቸገር ይናገራል። ማህበሩ እውቅና አግኝቶ የሚንቀሳቀስ በመሆኑ ለሚሸጣቸው ትኬቶች ሙሉ እውቅና አግኝቶ መሆኑን ያስረዳል። ከዚህ ቀደም የተሰሩ ስራዎችን እንደ ማስረጃዎች በማቅረብ ለማሳመን እንደሚሞከር ያመለክታል።
ማህበሩን ለመደገፍ መንግስትም ይሁን ሌሎች ለጋሽ ሰዎች በቻሉት አቅም ድጋፍ ሊያደርጉ እንደሚገባ የሚናገረው ወጣት ዮናስ፤ የተሻለ ስራን ለማከናወን ሁሉም መተባበር እንደሚገባም ያስረዳል። ድጋፍ የሚፈልጉ ሰዎችን ለመርዳትና ካሉበት ችግር ለማውጣት ድጋፍ እንደሚያስልጋቸው ያብራራል።
የማህበሩ አባል የሆነው ወጣት ንጉስ ከበደ፤ ወጣት ሲኮን ብዙ ችግሮች እንደሚጋጥሙ ያመለክታል። በተመሳሳይም ብዙ ኃላፊነቶች እንደሚደራረቡም ይናገራል። ነገር ግን የሚያጋጥሙ ችግሮችን በመቋቋም የተቸገሩ የማህበረሰብ ክፍሎችን ማገዝ ትልቅ ስራ እንደሚጠይቅ ይጠቁማል።
ህብረተሰቡ በጎ እናደርጋለን በሚሉ ሰዎች የተታለለበት ሁኔታዎች ስለነበሩ ከልባቸው የሚሰሩ ወጣቶች ድጋፍ ሲያሰባስቡ ችግሮች እንዲያጋጥማቸው ምክንያት መሆኑን ይናገራል።
ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን ህብረተሰቡ ሲመለከት ድጋፍ እየተገኘ መሆኑን ያመለክታል። ለህብረተሰቡ ማህበሩ ግልፅ የሆነ አሰራር እየተከተለ እንዲሁም ማህበረሰቡ እራሱ መርጦ የሚያመጣቸው ሰዎች እየተደገፉ መሆናቸውን ሲመለከት ለውጦች እንዳሉ ያስረዳል። ማህበሩ በቀጣይ ብዙ ስራዎችን ለመስራት እንቅስቃሴ እያደረገ መሆኑን በመጥቀስ፣ ድጋፍ የሚደረግላቸው ሰዎች ቋሚ የሆነ ድጋፍ የሚያገኙበት መንገድ ለመፍጠር መታሰቡን ያብራራል።
ድጋፍ የሚደረግላቸው ሰዎች በማህበሩ ላይ ጥገኛ እንዳይሆኑና በዘላቂነት እራሳቸውን እንዲችሉ ለማድረግ ማህበሩ ፕሮጀክቶችን ቀርፆ በመንቀሳቀስ ላይ እንደሚገኝ ይጠቅሳል። ማህበሩ የተሻሉ ነገሮችን ፈጥሮ ድጋፍ የሚደረግላቸው ሰዎች እራሳቸውን ችለው ሌሎችን እንዲደግፉ ታስቧል። ሌላው ማህበሩ ከፈረንሳይ ለጋሲዮን ወጣ ብሎ በሌሎች አካባቢዎች ላይም ድጋፍ ለማድረግ ማሰቡን ወጣት ንጉስ ያመለክታል።
ማህበሩ የተመሰረተበት የራሱ የሆነ አላማ ያለው ሲሆን የተመሰረተበትን አላማ ከግብ ለማድረስ የሕዝብ ድጋፍ እንደሚያስፈልገው ተናግሯል። በወረዳ፣ በክፍለከተማ እንዲሁም በከተማ ደረጃ ድጋፎች ቢደረጉ የተሻለ ስራ መስራት እንደሚቻል ይጠቁማል። በማህበሩ ትንሽ ነገር ሰርቶ ማለፍ ሳይሆን ትልልቅ ነገሮችን በመስራት ህብረተሰቡ የሚደሰትበት ሁኔታ እየፈጠረ እንደሚገኝ ያመለክታል።
አዲስ ዘመን ጥር 28/2013