መርድ ክፍሉ
በኢ.ፌ.ዴ.ሪ ህገመንግሥት ትኩረት ተሰጥቷቸው ከተከበሩ መብቶች መካከል የዜጎች የመደራጀት መብት በዋነኝነት ይጠቀሳል ።የአገሪቱ ህገመንግሥት አንቀጽ 31 የሚከተለውን ይደነግጋል ።‹‹ማንኛውም ሰው ለማንኛውም ዓላማ በማህበር የመደራጀት መብት አለው ።
ሆኖም አግባብ ያለውን ህግ በመጣስ ወይም ህገመንግሥታዊ ስርዓቱን በህገወጥ መንገድ ለማፍረስ የተመሰረቱ ወይም የተጠቀሱትን ተግባራት የሚያራምዱ ድርጅቶች የተከለከሉ ይሆናሉ፡፡›› በመሆኑም ዜጎች ህገመንግሥቱ ያጎናፀፋቸውን የመደራጀት መብት በመጠቀም በበጎ አድራጎት ወይም በማህበር ሊደራጁ ይችላሉ፡፡
በአዲስ አበባም ይሁን በሌሎች ክልሎች ወጣቱ እየተደራጀ በጎ ሥራዎችን በማከናወን ላይ ይገኛል ። ለዚህ ደግሞ በአገሪቱ ያለው ሲወርድ ሲዋረድ የመጣው የመረዳዳት ባህል መሰረት ሆኗቸዋል ።መንግሥት ወጣቱ ለሥራ ብቻ ሳይሆን ለበጎ ተግባራትም ተደራጅቶ እንዲሰራ መመሪዎችንና አዋጆችን እያሻሻለ ይገኛል ።
በተጨማሪም አቅም በፈቀደ መልኩ ድጋፍም ያደርጋል ።እዚህ ጋር ሊስተዋል የሚገባው ነገር በአንዳንድ አካባቢዎች የበጎ አድራጎት ማህበራትን ሥራ ለማዳከም የሚንቀሳቀሱ የመንግሥት መዋቅሮች እንዳሉ መረሳት የለበትም ።
የመረዳዳትም ሆነ በስልክ የመኖር ባህሎች ዛሬም እንዳሉ የሚያሳዩ ተግባራት እንዳልጠፉ በርካታ ማሳያዎችን ማንሳት ይቻላል። በተለይ በቅርቡ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ መከሰትን ተከትሎ በርካታ ዜጎች ለከፍተኛ የኑሮ ጫና መዳረጋቸው ይታወሳል። ይህንን ክፉ ጊዜ ለማለፍ ደግሞ የደጋግና ቅን ልቦች መኖር ትልቅ አስተዋፅኦ ማድረጉን ስንመለከት የመረዳዳት ባህላችን ዛሬም ጠንካራ መሆኑን እንገነዘባለን።
ዛሬ በአዲስ አበባ የሚገኘውና በጎዳና የሚገኙ ልጆችን የሚደግፈው ራ-ብርሃን የህፃናት መርጃ በጎ አድራጎት ማህበርን እንቃኛለን ።
ራ-ብርሃን የህፃናት መርጃ የበጎ አድራጎት ማህበር በፊደላት ትርጓሜ ራ- ማለት ብርሃን ፀሐይ ኃይል መድኃኒት ማለት ሲሆን ራ ፊደል ነው:: የፊደል ማስቆጠሪያው ደሞ ትምህርት ቤት ነው:: እሱን መስራት አላማቸው ነው ።
ብርሃን ደግሞ በውስጡ ስሜት፣ አስተሳሰብ፣ ተስፋ፣ ተነሳሽነት እንዲሁም ትልቅ አቅም ያለበት የብዙዎችን ሀሳብ መያዝ የሚችል ግልፅ ሆኖ ረቀቅ ያለ ሀሳብ ያለው ቃል ነው ።ብርሃን በደንብ ህፃናትን መግለፅ የሚችል አቅም ያለው ቃል ነው፡፡
ምስል መሳል የሚችል ቃል ነው ።ዓላማውን እና ራዕዩን በደንብ መግለፅ ይችላል ሁሉም ሰዎች በቀላሉ ሊረዱት ይችላሉ ።
ይህ ህብረት የተቋቋመው በጎዳና ላይ ለወደቁ፣ እናትና አባት ለሞቱባቸው፣ በየሆስፒታሉ ተወልደው በወሊድ ምክንያት እናቶቻቸው ለሞቱ ባቸው፣ አሳዳጊ አጥተው የሚገኙ ህፃናትን ቁሳዊ እና መንፈሳዊ ድጋፍ በማድረግ ህፃናቱን የተሻለ የስኬት ማማ ላይ እንዲወጡ ለማስቻል የተመሠረተ ማህበር ነው::
የራ-ብርሃን ልጆች በመልካም ምግባር የታነፁ የመልካም ስብዕና ባለቤቶች እንዲሆኑ ሀገራቸውን የሚወዱ እና የሀገራቸውን ታሪክ ጠንቅቀው የሚያውቁ በአስኳላ እውቀታቸው የተሻሉና በአካላዊ ደህንነታቸው የተሻሉ ልጆች፣ በመንፈሳዊ እውቀት እና ህይወት የተሻሉ ጠንካራ ሰራተኞች ሀገር ተረካቢ ልጆችን መፍጠር ዓላማው አድሮጎ የተነሳ ማህበር ነው።
ማህበሩ የራሱ የሆነ ቤተሰቦች መጽሐፍት፣ ቤተ ሙከራ፣ ትምህርት ቤት፣ መኝታ ክፍል፣ ለህፃናት እና ታዳጊዎች የሚሆን ምቹ መዝናኛ ሥራ፣ የመመገቢያ አዳራሽ፣ ማዕድ ቤት፣ ግምጃ ቤት፣ የአስተዳደር ቢሮ መዝናኛ ክፍል፣ ስፖርት ቤት፣ ሥራ የሚሰሩበት ክፍል፣ ሽንት ቤት፣ መታጠቢያ ክፍል፣ የፀሎት ቤት ለሁሉም ሃይማኖት አማኞች እንደየእምነታቸው፣ የስብሰባ አዳራሽ መለስተኛ ክሊኒክ ያሉት ትልቅ ግቢ ለመገንባት ያቀደ ማህበር ነው፡፡
ማህበሩ በሴት አባላት የተመሰረተ ይሁን እንጂ ከተለያዩ ለጋሽ ድርጅቶች ጋር በመተባበር የተለያዩ ሥራዎችን ይሰራል ።በተጨማሪም የጎዳና ልጆችን በማብላት፣ በማልበስና በማጠብ ሰፊ ሥራዎችን አከናውኗል ራ-ብርሃን የህፃናት መርጃ የበጎ አድራጎት ማህበር ።ከማህበሩ መስራቾች ጋር ቆይታ አድርገናል ። ተከታተሉት ።
የማህበሩ አመሰራረትና ሥራዎች
የማህበሩ መስራች የሆነችው ብሩክታይት ስጦታው፤ ማህበሩ ተመስርቶ ሥራ የጀመረው ሚያዝያ ወር 2012 ዓ.ም ላይ መሆኑን ትናገራለች ።ማህበሩን ለመመስረት ምክንያት የነበረው በጎንደር ዩኒቨርሲቲ የነበረው ‹‹ካለን እናካፍል›› የተባለው ማህበር አባላት ወደ አዲስ አበባ መጡ ።ማህበሩ በቴሌግራም በነበረው እንቅስቃሴ እነሱም መካተታቸውን ትገልፃለች ።በአዲስ አበባ የሚገኙት አባላት እርስ በርስ ለመተዋወቅ መገናኘታቸውን ትጠቁማለች፡፡
አባላቱ ቅድሚያ ሲገናኙ ያደረጉት ነገር በጎዳና ላይ የሚገኙ ህፃናትን መመገብና የማልበስ ሥራ ነበር ። በተጨማሪም ገላቸውን የማጠብ ሥራ መከናወኑንም ታመለክታለች ።በወቅቱ ‹‹ዮዝ ኢምፓክት›› የሚባል የበጎ አድራጎት ድርጅት ጋር በትብብር መሰራቱን ትጠቅሳለች ።የማህበሩ አባላት እርስ በርስ እየተዋወቁ ሲሄዱ አዳዲሰ ሀሳቦች እየመጡ ወደ ተግባር መገባቱን ታስታውሳለች፡፡
በጎዳና የሚገኙ ህፃናትን የማብላት ሥራው ከተከናወነ በኋላ በየካ ክፍለ ከተማ ውስጥ የሚገኝ በጣም ያረጀ፣ ዝናብና ብርድ የሚያስገባ የካንሰር ታማሚ አረጋዊ ቤት ማደሳቸውን ትጠቁማለች ።ቤቱ በታደሰበት ወቅት የክረምት ወራት የገባበት ወቅት ስለነበር ከአገር ውስጥና በውጭ ከሚገኙ ሰዎች ገንዘብ በመሰብሰብ ቤቱ እንደ አዲስ እንዲሰራ መደረጉን ትናገራለች ።
ቤቱ በታደሰበት ወቅት የማህበሩ አባላት እርስበርስ መግባባት መቻላቸውን ትጠቁማለች ።በመቀጠልም በጎዳና ላይ መንታ የወለደችን አንድ ሴት የሚመለከተውን በማነጋገር ቤት በመቀበል ቤቱን በማደስ እንድትገባ መደረጉን ትገልፃለች ።በተጨማሪም ሥራ እንድትጀምር ሁኔታዎች እንደተመቻቹላትም ታመለክታለች ።ሌላው ደግሞ ቦንጋ በመሄድ የመማርያ ደብተር መግዛት ለማይችሉ ህፃናት፣ አካል ጉዳተኞችና የአርሷደር ልጆች መማርያ ደብተር በማሰባሰብ 450 እሽግ ደብተር መሰጠቱን ትጠቅሳለች ።
በቋሚነት እሁድ እሁድ የጎዳና ልጆች የማብላት ሥራ ነበር ።በጎዳና የሚገኙ ህፃናት፣ ሴቶችና ወጣቶች ምግብ እንዲበሉ፣ ልብሳቸውን እንዲያጥቡ እንዲሁም ገላቸውን እንዲታጠቡ ይደረግ ነበር ።ማህበሩ እውቅና አውጥቶ በራሱ እንስኪንቀሳቀስ ድረስ ሥራው ቆሞ እንደነበር ትናገራለች ።በቀጣይ ሥራውን ለማስቀጠል መታሰቡንም ታመለክታለች ።
ሌላው ማህበሩ ያከናወነው የካንሰር ህሙማንን ያቀፈው አዲስ ተስፋ ማህበርን የመደገፍ ሥራ ነው ።
በማዕከሉ ውስጥ የሚገኙት ህፃናት የተሰባሰቡት ከክፍለ አገራት ሲሆን ለህክምና ምቹ እንዲሆንላቸው ሰባ ደረጃ አካባቢ በሚገኝ ማዕከል ውስጥ እንደተቀመጡ ትናገራለች ።እረጅም ቀጠሮ ሲኖርባቸው ደግሞ ወደ መጡበት አካባቢ እንደሚመለሱ ትጠቅሳለች ።በማዕከል ውስጥ የሚገኙ ህፃናትን የመጎብኘት ሥራ መከናወኑን በመጥቀስ የገና በዓልን ከእነሱ ጋር ማህበሩ ማክበሩን ትናገራለች ።
በቦንጋ የደብተር መስጠት ሥራ በተከናወነበት ወቅት በአካባቢው የቤተ መጽሐፍ ችግር እንዳለ መመልከታቸውን ትገልፃለች። በአካባቢው ቤተ መጽሐፍት ተብሎ አገልግሎት እየሰጠ የሚገኘው ሁሉንም ማስተናገድ የማይችል መሆኑን ታስረዳለች ።የቤተመጽሐፉን ፕሮጀክት በእቅድ ደረጃ ተይዞ እንቅስቃሴ መጀመሩን ትጠቁማለች፡፡
ሌላው የማህበሩ መስራች የሆነችው ትዕግስት ሀጎስ እንደምትናገረው፤ ማህበሩ የተመሰረተው የኮቪድ ወረርሽኝ በተከሰተበት ወቅት ነው ።በወቅቱ በጎንደር ዩኒቨርሲቲ የሚገኘው ‹‹ካለን እናካፍል›› በጎ አድራጎት ድርጅት ውስጥ የሚገኙ ተማሪዎች ወደ አዲስ አበባ ሲመጡ ሀሳቡን አመጡት ።ከዛም ከተለያየ ቦታ በመሰባሰብ ማህበሩ እንዲመሰረት ተደረገ፡፡
ማህበሩ እንደተመሰረተ የመጀመሪያው ሥራ የነበረው በጎዳና ላይ የሚገኙ ህፃናትና እናቶች እንዲሁም ወጣቶችን የማብላት ሥራ በማከናወን መሆኑን ትገልፃለች ።በቦሌ ድልድይ አካባቢ የሚገኙ የጎዳና ልጆችን በመሰብሰብ የማብላት ሥራ እንደተሰራም ትጠቁማለች ።በተጨማሪም ገላቸውን የማጠብ ሥራ ተሰርቷል ።በመቀጠል ደግሞ የአንድ አረጋዊ ቤት ሙሉ ለሙሉ በማፍረስ እንዲታደስ መደረጉን ትገልፃለች ።
በዓላትን በተለያዩ ማዕከላት ውስጥ እንደሚያከብሩ የጠቀሰችው ትዕግስት፣ ጌርጌስዮን የአዕምሮ ህሙማን ማዕከል ለመስቀል በዓል ማሳለፋቸውን ትናገራለች ።በመስከረም ወር 2013 ዓ.ም መንገድ ላይ ለተገላገለች አራስ ሴት ከነበረችበት የላስቲክ ቤት ለማስወጣት የሚመለከተውን በማስፈቀድ ቤት እንደተሰራላት ታመለክታለች ።በሌላም በኩል ከጎዳና ልጆች ጋር በየሳምንቱ አብረው እንደሚያሳልፉ ትጠቁማለች ።የዚህን ዓመት የገና በዓል ከካንሰር ህሙማን ጋር አብረው ማሳለፋቸውን ታስታውሳለች ።
የህብረተሰቡ አቀባበል
የማህበሩ አባላት ሴቶች ሲሆኑ በህብረተሰቡ ዘንድ ያለው አቀባበል አበረታች መሆኑን ትዕግስት ትናገራለች ።ማህበሩ ሥራውን የጀመረ አካባቢ ሁኔታዎች አስቸጋሪ እንደነበሩ ታስታውሳለች ።ነገር ግን ሴት በመሆናቸው ብቻ በህብረተሰቡ ዘንድ የነበራቸው ተቀባይነት ጥሩም እንደነበር ታመለክታለች ።
ማህበሩን ያጋጠሙት ችግሮች
ማህበሩ ሲመሰረት ወንዶች የነበሩ ቢሆንም በሥራ ምክንያት በማህበሩ እንቅስቃሴ ላይ መሳተፍ አለመቻላቸውን ብሩክታይት ትናገራለች ።የመማሪያ ድብተሮቹ በሚሰበሰቡበት ወቅት የጫማ ጠረጋ ሥራ በማከናወን እንደነበር ታስውሳለች ።በዚህ ወቅት ሁሉም ጫማውን ሰው እንዲያስጠርግ የነበረው ልመና አስቸጋሪ እንደነበር ታስታውሳለች ።
እንደ ትዕግስት አባባል፤ በከፋ ዞን ቦንጋ ከተማ 450 ለሚሆኑ ተማሪዎች የመማርያ ደብተር ተሰጥቶ ነበር ።በዚህ ወቅት የተለያዩ ችግሮች አጋጥመው ነበር ።የደብተር መግዣ ለመሰብሰብ ጫማ ጠረጋ ተከናውኖ ነበር ።ይህ ሥራ አስቸጋሪ ነገር እንደነበረው ታስታውሳለች፡፡
የማይረሳ ክስተት
የካንሰር ታማሚ ህፃናት ጋር በዓል የተከበረበት ወቅት አባላቱ የህፃናቱን ሁኔታና ህመም ሲመለከቱ ማዘናቸውን ትጠቅሳለች ።በካንሰር የተጠቁት ዓይናቸውን፣ አጥንታቸውን፣ የደም እንዲሁም የማህፀን ካንሰር የያዛቸው ህፃናት እንደሚገኙ ትናገራለች ።ህፃናቱን ማየት በጣም አሳዛኝ ሁኔታ እንደፈጠረም ታስታውሳለች ።ህፃናቱ ለኬሞ ቴራፒ በኮንትራት መኪና የሚሄዱ ሲሆን ለሚንቀሳቀሱበት ብዙ ወጪ እንደሚወጣ ታመለክታለች ።አጠቃላይ የነበረው ሁኔታ ልብ የሚነካ እንደነበር ትጠቁማለች ።
የማህበሩ ቀጣይ እቅድ
በቀጣይ ማህበሩ ጎዳና ላይ የወደቁ ህፃናትን በዘላቂነት ለማንሳት አላማ አለው ።ለዚህም የሚሆን ማዕከል ለመክፈት እቅድ እንዳላቸው ብሩክታይት ታመለክታለች ።በዋናነት አዲስ አበባ ውስጥ ማዕከል በመክፈት በጎዳና የሚገኙ ህፃናትና ሴቶችን ለማንሳት ታስቧል ።በየጎዳናው ማስቲሽ የሚስቡ ህፃናትና ወጣቶች ሁሉም ሰው አልፏቸው እንደሚሄድና እንዳይሰርቁን በማለት እንደሚሸሿቸው ትጠቁማለች ።ነገር ግን እነዚህን ህፃናትና ወጣቶች ከጎዳና የሚያነሳ ሰው እንደሚያስፈልግም ትጠቅሳለች ።ማህበራቸውም በቀጣይ ይህን ሥራ ለመስራት ዝግጅት እያደረገ እንደሚገኝም ታመለክታለች ።
ትዕግስት እንደምትናገረው፤ የመማርያ ቁሳ ቁስ የተሰበሰበላቸው ተማሪዎች በቂ የሆነ ቤተ መጽሐፍት የላቸውም ።ለዚህም ማህበሩ በአካባቢው ቤተመጽሐፍት ለመገንባት እቅድ ይዞ መንቀሳቀስ ጀምሯል ።በቀጣይነት በጎዳና የሚገኙ ልጆችን በዘላቂነት የሚደገፉበት ሁኔታ ለማመቻቸት ማህበሩ ሀሳብ አለው ።ከዚህ ባለፈ የሚረዳ ድርጅት ከተገኘ በጎዳና የሚገኙ ወጣቶች ሙያ ተምረው ወደ ሥራ የሚገቡበት ሁኔታ ለማመቻቸትም ታስቧል።
አዲስ ዘመን ጥር 21/2013