ሰላማዊት ውቤ
የገና ጨዋታ በኦሎምፒክ ከሚደረጉት ውድድሮች አንዱ ለመሆን በቅቷል። የተለያዩ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ጨዋታው ፈጣን ዕድገት አሳይቷል።ዕድገቱን ስናነሳ በዓሉ ከጌታኢየሱስ ክርስቶስ ውልደት ጋር የተሳሰረ እንደመሆኑ ወደ ኋላ ዞር ብለን አጀማመሩን እንድናይ ግድ ይለናል።
መከበር የጀመረው ክርስቶስ ከተወለደ ጀምሮ መሆኑም አያጠያይቅም።የሐይማኖት ጠበብቶች እንደሚሉት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ከመወለዱ በፊት የነበረውና በመጽሐፍ ቅዱስ ብሉይ ኪዳን የሚጠቀሰው ዘመን ዓመተ ፍዳ ወይም የኩነኔ ነበር የሚባለው።
ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ከተወለደ በኋላ ያለው ዘመን ደግሞ የኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ኣለም በመምጣት በቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም ማህፀን አድሮ እንደ ሰው መወለድ የሰውን ልጅ እኩልነት ያወጀ፣ ኃጢያተኞችን ይቅር በማለት ከሌላው ጋር ያዋሀደ ክስተት እንደመሆኑ ዓመተ ምህረት ተሰኝቷል።
በታካ ነገስት በዓታ ለማርያም ገዳም አገልጋይ የሆኑት መላከ ኃይል አባ ጥላዬ ታደሰ እንደሚሉትም በዚህ ዘመን አቆጣጠር በትክክልም ጌታ እየሱስ ክርስቶስ ከተወለደ የዘንድሮው ታህሳስ 29 ቀን 2013ኛ ዓመቱን ይዟል ማለት ነው። ጨዋታው ለመፈጠሩ የጌታ እየሱስ ክርስቶስ መወለድ ምክንያት በመሆኑ ጨዋታው ከተጀመረ 2013ኛ ዓመቱ ነው ለማለት ይቻላል።
የገና ጨዋታ በሀገራችን ባህላዊና ሀይማኖታዊ ይዘት ያለው ነው። ቀደምት የክርስትና ሐይማኖት አባቶች ለጨዋታው መጀመር ሁለት ምክንያቶችን ይጠቀሳሉ።አንደኛው ጌታ ሲወለድ እረኞች ከመላዕክት ጋር አብረው መዘመራቸውን ተከትሎ የሚነገረው ነው።በወቅቱም አሁን የገና ጨዋታ የምንለውን የተጫወቱበት አጋጣሚ ነበር።እናም ከዚህ በመነሳት ጨዋታው የኋላ ኋላ እየሰፋ መጥቶ በዋናነት ወጣቶች የሚሳተፉበት ሆኖ መነሻው ግን እረኞቹ እንደነበሩ ማየት ይቻላል።
ሁለተኛው ለጨዋታው መነሻ ምክንያት ደግሞ ከእስራኤሉ ንጉስ ሄሮድስና ሰብዓ ሰገል ጋር የተያያዘ ነው። መጽሐፍ እንደሚለው በወቅቱ ጌታ ኢየሱስ የተወለደበት ቤተልሄም መገኛ የነበረችውን እስራኤልን ይገዛ የነበረው ንጉስ ሄሮድስ በእስራኤል ከነበሩ ነብያት አንድ ትንቢት ይሰማል።ትንቢቱ በቤተልሄም አንድ አዲስ ህፃን እንደሚወለድ የሚጠቅስ ነበር።ይሄ ትንቢት በመላኩ ቅዱስ ገብርኤል ‹‹ድንግል በድንግልና ትፀንሳለችና ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ትለዋለች››ተብሎ በመጽሐፍ ቅዱስ በመጠቀስ ተጽፎ ይገኛል።
ታድያ ይሄ አዲስ ይወለዳል የተባለው ህፃን የዳዊትን የአባቱን ዙፋን ይወርሳልና መንግስቱም ለዘለዓለም ይፀናል የመባሉ ትንቢት ሄሮድስን ያሳስበዋል። ሄሮድስ የት እንደሚወለድና ስለ አጠቃላይ ሁኔታው በቅርበት ለማወቅም ጌታ የት እንደተወለደ ለመጠየቅ ወደ እሱ በመጡ ጊዜ ያየውን የሰብዓ ሰገሎች ልብስ ዓይነት አልብሶ አንዱን ሰላይ ወደ ሰብዓሰገሎች ይልከዋል።
ይሄ ሰላይ ከሰብዓ ሰገሎች ጋር ተቀላቅሎ ጌታ ወደሚወለድበትሥፍራ ሲጓዝ ይመራቸው የነበረው የእግዚአብሄር መልአክ ኮከብ ድንገት ቀጥ ይላል። ሰብዓ ሰገሎች ሁኔታውን በመጠራጠር ባደረጉት ፍተሻም ሰላዩ እንደተቀላቀላቸው ይረዳሉ። ሰላዩን ይገድሉና ራሱን ቆርጠው እንደ አሁኑ የገና “እሩር” እየተቀባበሉ ይጫወቱበታል።
አባ ጥላዬ እንደሚሉት ታድያ የገናጨዋታ ከዚህ በመነሳትም ተፈጠረ የሚል አፈ ታሪክ አለ።ያም ሆነ ይህ መጽሐፍ ቅዱስ ላይ ጨዋታው በዚህ ወቅት ተጀመረ የሚል ተጽፎ ባይገኝም መነሻው ከኢየሱስ ክርስቶስ መወለድ ጋር የተያያዘና የጌታን መወለድ ደስታ ማብሰሪያ እንደሆነ በእርግጠኝነት መገንዘብ ይቻላል።
ጨዋታውም አዝመራው ተሰብስቦ፣ጤፍና የብዕር ሰብል ስንዴና ገብስ ሁሉ ታጭዶው በጎተራ በሚከተቱበትና መኽር ተብሎ በሚጠራው በወረሀ ታህሳስ መጨረሻ ነው የሚከበረው። በዚህ ወር ማንኛውም ሰብል ከማሳ ላይ ይነሳል። በእርሻው ላይ ከብት ይሰማራበታል።ለምለም መስኮችና ሰፋፊ ማሳዎች ለገና ጨዋታ ማካሄጃ ይውላሉ። ጨዋታው በሰፋፊ ሜዳዎች መስኮችና ቦታዎች ይካሄዳል።
ቦታዎቹ የሚመረጡት ከሜዳው ወይም ከማሳው ስፋት የተነሳ ተጫዋቾቹ እንደ ልባቸው እየሮጡ ይጫወታሉ በሚል ነው። እሳቸው በ1936 ዓ.ም በተወለዱበት ቀዬ ጨዋታው በእነዚህ ዓይነቶቹ ቦታዎች ይካሄድና እንደ እግር ኳስ ማዶ ለማዶ ግብ የሚገባበት ሥፍራ ያለበት እንደነበር ያስታውሳሉ።
የገና ጨዋታ ከብቶቻችን ሣር በልተው ውሃ ጠጥተው እስኪተኙ ድረስ በጉጉት የሚናፍቁት ጨዋታ ነበር ። ወደ ወጣትነት ዘመን በተሸጋገሩበት ወቅትም ቁጥር አንድ የገና ጨዋታ ተጫዋች እንደነበሩም አጫውተውናል። ለጥምቀት ታቦት ወደ ማደሪያው ከመውረዱ በፊት ገና ድንኳን ሲተከል እንጫወተው ነበር ብለውናል።
ሰርግ ላይ፤ ቅዳሜና እሁድም ሥራ በሌለ ጊዜ ሁሉ ጨዋታው እንደሚካሄድም ነግረውናል።በጥምቀት በዓል ላይ የሚደረግ ፈረስ ግልቢያ ማጀቢያው መሆኑንና ሰርግ በማድመቅ መታወቁንም ይናገራሉ።እርጥብ እንጨት እንደ ጦር ሾሎ ይጠረብና በፈረስ ግልቢያ ወቅት እርስ በእርስ መወራወር ይደረጋል።ጥሩ ጋላቢ ከሆነ ሹል እንጨት ጀርባውን እንደማይወጋው ከነፈረሱ ዝቅ ብሎ ወደ መሬት በመተኛት ጋልቦ እንደሚያመልጠው ለዚህ ጋላቢም በጨዋታው ወቅት ጭምር ‹‹ከፈረሶቹ አሉ በልዩ መሐል አገዳ የሚለያዩ›› ተብሎ ይገጠምለታል።
በተለይ ቀደም ባሉት ዘመናት ደግሞ በገጠሩ ሕብረተሰብ ቤተ ክርስቲያን ተፈቃሪ ስለነበረች ለጥምቀት ታቦት ሲወጣ እቤቱ የሚውል ሕብረተሰብ አልነበረም። ይሄ ሕብረተሰብ በሙሉ ታድያ በየጥምቀተ ባህሩ አካባቢ የሚካሄዱ የገና ጨዋታዎች ታዳሚ ነው።
ዛሬ በኳስ ጨዋታ እከሌ የእከሌ ቡድን ደጋፊ እንደሚባለው ሁሉ ያኔም ሕብረተሰቡ ለገና ጨዋታ ተጨዋች ቡድን በመወገን የጨዋታውን ሜዳ ከብቦ እያጨበጨበ፣ እየጨፈረና እየዘፈነ ድጋፉንና አድናቆቱን ይገልፅ ነበር።ለሚደግፈው ቡድን ሰንጋ ጥሎና ቅርጫ ወስዶ ያበላል።ለዚሁ ጨዋታ ተጫዋቾች ብሎ ቅልጥ ያለ ድግስ ሁሉ የሚደግስ ነበር።የግብዣው ቱሩፋቱ የቡድኑን ደጋፊዎች ሁሉ የሚያጠግብና ታላቅ ማህበራዊ መስተጋብር ያለው ነበር ብለውናል።
እንደ ክርስትና ዕምነት ተከታዮች የገና ጨዋታ የሚጀምርበትና የሚቋጭበት የጊዜ ሰሌዳ አለው።ሌሊት ቅዳሴ ከተቀደሰና ጾም ተፈትቶ ከተገደፈ ቁርስም ከተበላ በኋላ ነው።ከዚህ ጀምሮ አብይ ጾም እስከሚገባ ይካሄዳል። በየዓመቱ በተለይ በገጠሩ ክፍል እረኞች በድምቀት ይጫወቱታል። በተለይ የሰርግ ወቅት በሆነው ወርሃ ጥር ላይ ልክ እንደ ኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ሰሞን በተጧጧፈ መንገድ ይካሄዳል። የጨዋታውን ግብዓቶች ማዘጋጀት ሂደቱም ቀደም ብሎ ይጀመራል።
በእርግጥ መጫወቻ መስኩ አዝመራው ቦታውን ሲለቅ ጨዋታው መተካቱ ስለሚታሰብ ከመኽር ወቅት አዝመራ ስብሰባ ጋር በመያያዙ እንብዛም ዝግጅት አይደረግበትም ። ከእርጥብ የወይራ እንጨት ሩሯን ማዘጋጀት ግድ ነው። እንደ ኳስ የምታገለግለው ሩሯ ጥንክር እስክትል በእሳት ትለበለባለች። አንድና እንደ ኳስ የተድበለበለች ነች።
ሩሯን አዘጋጅተው ሲያበቁ ለመምቻው የሚሆን እጅግ ጠንካራ ከሆነው የወይራ እንጨት ዱላ ይበጃል። በሁለት ጎራ የተሰለፉት የጨዋታው ተጋጣሚዎች ሩሯን የሚመቱበት ይሄ የዱላው ራስ በብዙ ቦታ ገና በመሰኘትም ይጠራል። ዱላው ከወደ ራሱ እንደከዘራ ቆልመም ያለ ቅርጽ አለው።
በገና ጨዋታ ሁለት ቡድኖች ጎራ ለይተው ለጨዋታው በተዘጋጀ ሜዳ የሚጋጠሙትም ከዚህ በኋላ ነው። የግጥሚያዊ ትዕይንት እጅግ ውብ፣ ሳቢና ማራኪ ነው። በግጥሚያው የሚሰለፉት ዕድሚያቸው በወጣትነት ደረጃ ያሉና የሚሰነዘረውን ምት መመከት የሚያስችል ቁመናና ብቃት ያላቸው ናቸው።
ሰልፋቸው ወዲያ ማዶና ወዲህ ማዶ ሲሆን ያንዱ ተጋጣሚ ቁጥር ከሌላው ተጋጣሚ ቁጥር አነስ ያሉ ተጋጣሚዎች መያዙ በተጨዋጮቹም ሆነ በታዳሚው ዘንድ ክርክርና ጥያቄ አያስነሳም። ጨዋታው ከመጀመሩ በፊት በአንድ ወገን የተሰለፈው ከቀኝ ወደ ግራ ያለውን ሥፍራ ይይዛል።
በሌላ ወገን የተሰለፈው ደግሞ ከግራ ወደቀኝ ያለውን ይይዛል። በዚህ መሀል አቅጣጫውን ያልለየ ተጫዋች ከገጠመ በተጨዋቾቹም ሆነ በጨዋታው ደጋፊዎች ‹‹ሚናህን ለይ!›› የሚል ተግፃፅ መሰል ሽንቆጣ ይደርስበታል። ተግሳፁ ቆየት ብሎ ወደ ብሽሽቅ መሰል ቃላት ውርወራ ሊቀየር ይችላል።
ሆኖም ቅርብ ባሉ ታዳሚዎች ወይም ተጋጣሚዎች በዱላ ቸብ ፣ቸብ ተደርጎ ቦታውን እንዲይዝና የጨዋታውን ስነስርዓት እንዲያከብር ይደረጋል። በኋላም ጨዋታው ይጀመራል። ሩሯን እንደተፈለገው በማንሳት አክርሮ መለጋቱ ይጧጧፋል።ሩሯ ከርራ በምትለጋበት ጊዜ በብቃት መከላከል የሚችል ካልገጠማት ቅልጥም ልትሰብርና ያገኘችውን አካል ልትጎዳ ትችላለች።
ሆኖም ዓላማዋ በተቃራኒ በተሰለፉ ተጋጣሚዎች ትይዩ ያሉ ግቦች ላይ ማረፍ ነው።የአንዱ ጎራ በሌላው ጎራ ግብ እሩሯን ሲያሳርፍ ጨዋታው እጅግ ይደምቃል።ተጫዋቾቹ ተጋጣሚዎችም በየፊናቸው እዮሃ … አሲና ገናዬ”… እያሉ በመደጋገም ጨዋታውን ሞቅ ደመቅ በማድረግ ያደሩታል።
ከታዳሚው ወገን የለየ ግልጽ ሙገሳና ወቀሳ ይዥጎደጎዳል። ይሄም የተጨዋቾቹ እርዝመት፣ እጥረት፣ ውፍረትና ቅጥነት የሚሰነዘር ብሽሽቅ መሰል ቃላት ያዘለ ነው። ይሄን ቃላት በመወርወር ሴቶች ቀዳሚ ናቸው።
እነዚህ ሴቶች አንድም ጨዋታውን ለማየትና ለመደገፍ ሁለትም ወዳጆቻቸው፣ የወንድ ጓደኞቻቸውን ለማበረታታት በጨዋታው ስፍራ ዙሪያውን ከበው የማይደግፉትን ወገን ተጫዋች በግጥምና ዜማ ያሞግሳሉ፤ይጎሽማሉ።
‹‹ወንድ ነው ብዬ … ብሰጠው ጋሻ ለእናቱ ሰጣት ላመድ ማፈሻ ፣ወንድ ነው ብዬ ብሰጠው ጦር፣ላባቱ ሰጠው ለቤት ማገር ››ይላሉ የዜማ ቅላፄ ባለው ድምፀት።ሴቶቹ ለሚደግፉት ወገን ተቃራኒ የሆነን ቁመተ አጭር ተጋጣሚ ‹‹ይህን ወዳጅ ብላ ታስከትለዋለች አንድ ቀን ጩልሌ ታስወስደዋለች›› ሲሉ በተቃራኒው ወገን ያሉት አጭሮቹ በተራቸው ይቀበሉና‹‹እረጅም ነህና ሞኝነት አታጣም እቆርጥልሃለሁ አሳጥሬ በጣም ፣ ይኸን ረጅሙን ጎምዶ ጎማምዶ ግማሹን በርጩማ ግማሹን ማገዶ›› እያሉ አፃፋውን ይመልሱ እንደነበርም መላከ ኃይል አባ ጥላዬ ከአራት አስርት ዓመት በላይ ያስቆጠረውን ትዝታቸውን ወደ ኋላ ዞር ብለው አጫውተውናል።
ቀጭኖች ወፍራሞችን ወፍራሞች ደግሞ በፊናቸው ቀጭኖቹን የሚያበሽቁበት ቃላት አስመልክተው ቀጭኖቹ ወፍራሞቹን ‹እየው አካሄዱን አረማመዱን እንደ ቃሪያ ሎሚ ወጥሮ ሆዱን› ሲሏቸው። ወፋፍራሞቹ በበኩላቸው ቀጭኖቹን ‹‹ሲሄድ ቅትር ቅትር ሲበላ እንዳንበጣ ወዘና የሌለው የጨጓራ ቋንጣ ››በሚል የአፃፋ ምላሽ ይሸነቁጧቸዋል ይላሉ የልጅነታቸውን ወቅት አስታውሰው ሲናገሩ።
ነገር ግን “በገና ጨዋታ አይቆጡም ጌታ” እንዲሉት ተረት ብሽሽቁ በጨዋታው የትኛውንም ወገን ቂም አያስቋጥርና በቀል አያሲዝም።ሆኖም አንዳንዴ በዚህ የሚናደድና ዱላ የሚመዙ አይጠፋም።
ቅልጥም እስከ መስበር በሚደርሰው እሩር ከተመታና ከተጎዳ ደግሞ ህመሙ ብቻ ሳይሆን መዋረዱ የሚያበሳጨው ተጋጣሚ አይጠፋም።እናም ተጋፋኝ በሚል ከአንዱ ጋር ፀብ ያነሳል። ፀቡ ሁከትና ግርግር ከመፍጠር ጀምሮ ጎራ የለየ ድብድብ ያስነሳል። ጠና ሲልም እርስ በእርስ መፈነካከት፣ አካል መጉደልና ነፍስ መዋደቅ ያስከትላል።
ሆኖም ድርጊቱን የፈፀመ በወንጀል አይጠየቁም። ጨዋታው ብዙ ሰው ይሞትበትና አካል ጉዳተኛ ይሆንበታል። እርሳቸውም በጨዋታው ተሣታፊ በነበሩበት ዘመን ከአንድም ሁለቴ ተፈንክተዋል። ሁለት የዕድሜ አቻዎቻቸውንም ፈንክተዋል። በዚህ የተቀጣ ወንጀለኛም የሆነ የለም ጨዋታ ነዋ !
ቂም የለም በቀል የለም። ለከርሞ በሰላም ያድርሰን ብሎ መሰነባበት ብቻ አብሮ ይቀራል። መልካም የገና በዓል!
አዲስ ዘመን ታህሳስ 29/2013