ኃይለማርያም ወንድሙ
የገና በአል በአውሮፓውያንና በአሜሪካውያን ዘንድ በደማቅ ስነ ስርዓት ይከበራል። የዚህ በዓል ድምቀት ከሆኑት መካከል የገና ዛፍ ይጠቀሳል።በእነዚህ ሀገሮች የገና ዛፍን በመጠቀም በአሉ መከበር የጀመረው ጥንት ነው።
የገናን በአል በገና ዛፍ የማድመቅ ስነስርአት ግብፅና ሮም ሁሌም ልምላሜን እንደ ተምሳሌታዊነት ሲጠቀሙበት ከነበረው ጥንታዊ ባህል የመጣ ነው።ይህም ወደ ጀርመን ተሻግሮ በትውፊት በገና ዛፎችና በሻማ ብርሃን ታጅቦ ማክበሩ ቀጥሎ ቀስ በቀስ በ18ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጀመሪያ አካባቢ ወደ አሜሪካ ተሸጋገረ።
የገና ዛፍ በዓል አከባባር በጣም መድመቅ የጀመረው ግን ንግሥት ቪክቶሪያ በፈረንጆቹ ክረምት መባቻ ገናን ስታከብር ከጀመረችው የማስዋብ ልምድ እና ኒውዮርክ ከተማ ሮክፌለር ማዕከል ከሚገኝ ዛፍን በመብራት ከማስጌጥ ተሞክሮ ጋር ተያይዞ ነው ይባላል።
ቀደም ሲል እንደጠቀስነው የገና ዛፎችን የማስዋብ ትውፊት በ16ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የጀመረችው ጀርመን ስትሆን በወቅቱ ለእግዚአብሔር ያደሩ ክርስቲያኖች በበዓሉ ሰሞን በቤታቸው የተጌጡ የዛፍ አምሳያዎችን ያስቀምጡ ነበር።ከዚያም በማርቲን ሉተር በዛፎቹ ሥር የተለኮሱ ሻማዎች እንዲታከሉበት ተደረገ።
በ19ኛው ክፍለ ዘመን የገና ዛፍ አከባበር ለየት ያለ እንግዳ ነገር ይዞ ብቅ አለ። ለመጀመሪያ ጊዜ በአሜሪካ የገና ዛፍ በዓል አከባበር የተመዘገበው በ1830ዎቹ ወደ ፔንሲልቬንያ በመጡ የጀርመን ሠፋሪዎች ነበር።
በአሜሪካ ከዚህ ጊዜ አንስቶ የገና ዛፍ የታወቀ ቢሆንም፣ በአሜሪካ በሚገኙ በብዙ ጀርመን ቤቶች የገና ዛፎች ትውፊትና ባህል ግን አስቀድሞም ይተገበር ነበር።በአሜሪካ እስከ 1840ዎቹ ድረስ ግን የገና ዛፍ የኢአማንያን መለያ ተድርጎ ይቆጠር ስለነበረ በብዙ አሜሪካውያን ዘንድ ተቀባይነት ሳያገኝ ቆይቷል።
በዚህ ዘመን ምዕራባውያን ገናን ሲያከብሩ ቤታቸውን ለበዐሉ ሰሞን ያጋጊጣሉ፤ለዚህም ጽድን የመሳሰሉ የተጌጡ ልዩ ልዩ ዛፎችን በግቢያቸውም ሆነ በቤታቸው እንዲሁም በመንገዶች ማየቱ የተለመደ ነው።
በርካታ ምዕራባውያን ሀገሮች ለገና ቤቶቻቸውንና ግቢያቸውን በአረንጓዴ በዛፎች ያስውቡ የነበረው ራሳቸውን ከህመም፣ ጣዕረሞትና ዕኩይ መንፈስ ለመጠበቅ ብለው ነው ይባላል።
ይህ የምእራባውያኑ የገና በአል አከባበር ተጽእኖ በአፍሪካ እና በምስራቁ አለም ጭምር ዘልቋል። ከግብፃውያን 15 በመቶ የሆኑት የኮፕት ኦቶዶክስ ክርስቲያኖች የገና በአላቸውን ሲያከብሩ መንገዶች ሁሉ እንዲያሸበርቁ ይደረጋል።
በኮፕት ኦርቶዶክስ የልደት በዓል የሚከብረው በደመቀ ሁኔታ ነው።በዋዜማው በአብያተ ክርስቲያናቱ የመቅደሱ ሥርዓት ከምሽቱ አራት ሰዓት ተኩል ይጀምርና ሌሊት አሥር ሰዓት ይፈጸማል።
ምእመናን ወደየቤታቸው በመሔድ ‹በትልቁ የልደት ገበታ› ከቤተሰባቸው ጋር ተሰይመው ጾማቸውን ይፈታሉ። ‹‹የኦርቶዶክስ የገና ዕለት›› ተብሎ በሚታወቀው በቀጣዩ ቀን፣ ማለትም በታኅሣሥ ፳፱ ምእመናን በየቤቱ እየሔዱ በመጠያየቅ በዓሉን በደስታ ያከብራሉ። ብዙ ጊዜ ከአንዱ ቤት ወደ ሌላው ሲሔዱም ‹‹ካህክ (Kahk)›› የተባለ ልዩ ጣፋጭ ብስኩት በስጦታነት ይወስዳሉ።
በዓሉ በሚከበርበት ወቅት ብዙ የገበያ እንቅስቃሴ ይኖራል፤ መንገዶች በዓሉን በሚገልጹ ጌጣጌጦች እንዲዋቡ ይደረጋል። የግብፅ ሕፃናት እነርሱ ‹‹ባባ ኖኤል (Baba Noel)›› የሚሉት የገና አባት በበዓሉ ዕለት ስጦታ እንዲሰጣቸው ይናፍቃሉ። ከጣፋጭ ብስኩቶችም ‹‹ለባባ ኖኤል›› ብለው ያስቀምጣሉ።
እንደ ሆንግ ኮንግ ባሉ ክርስቲያን ባልሆኑ ሀገሮች በቅኝ ግዥዎቻቸው ዘመን የተዋወቁትን የአከባበር ስልት ይተገብራሉ።በሌሎችም ንዑሳን ክርስቲያኖች ባሉባቸው ሀገሮች ወይም የባህል ተጽዕኖው ህዝቡ በአሉን እንዲያስተውል የሚያደርጉ ናቸው።
የገና ትውፊቶች በብዙ ሀገሮች የገና ዛፎችን በመትከልና ወይም የተተከሉ የጥድ ዛፎች በማሸብረቅ በዛፎቹ ቅርንጫፍች ላይ ከረሜላ ߹ ጥጥ የተለያየ ቀለም ያላቸውን አፉፋ (ፊኛ) የአበባ ጉንጉን ቀይ ቀለም የበዛባቸው ብልጭልጭ ነገሮችን ያንጠለጥሉበታል።
በመንገዶችም ህፃናቱ ኩኪስና ወተት ይዘው አዳዲስ ዕይታዎችን በመጨመር የእየሱስ ክርስቶስን ልደት ያከብሩታል።ስለ ጌታ ልደት፣ ቅዱስ ኒኮላስና ሳንታ ክላውስ (ፈረንጆቹ የገና አባት የሚሉት) ዓይነት ስዕሎችም የሚወክሉ ስዕሎችን ሰቅለው በመዘመር ታሪክ እየተነገራቸው ያከብሩታል።የገና ካርድ ስጦታም መሰጠት የተለመደ ነው።
ከኢትዮጵያውያን ቀደም ብለው በዓለ ልደት የሚቀበሉት ምዕራባውያን የገና በአልን ከአዲሱ ዓመታቸው መባቻ ጋር የተቀራረበ ስለሆነ ልዩ በሆነ መልኩ ያከብሩታል።ሳንታ ክላውስ ወይም የገና አባት የሚሉት ቀይ ልብስ ለብሶ በነጭ ፂም ቀይ ኮፍያ አድርጎ ለህፃናቱ ስጦታ ይሰጣል።
የገና ዛፍ ብለውም በየቤቱና በየግቢው ብሎም በየመንገዱ በብልጭልጭ ነገሮችና በቀያይ ቀለሞች ያስውቡታል። ይህንንም ህፃናት ልጆቻቸው ትውፊቱን እንዲያውቁትና ይዘውት እንዲዘልቁ ይጠቀሙበታል። በገና አባት የገና ስጦታ ለህጻናት የመስጠቱ ነገር የጥበብ ሰዎች በጌታ ልደት ተገኝተው ያበረከቱትን ወርቅ እጣንና ከርቤ ሊያመለክት ይችላል።
በኢትዮጵያ የክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድም የእየሱስ ክርስቶስ የልደት በአል /ገና/ በደማቅ ስነስርአት ይከበራል።በአሉ በተለያዩ የክርስትና እምነት ተቋማት ዘንድ በየአስተምህሮቹ ላይ ተመስርቶ ይከበራል። ከዚሁ ጋር ተያይዞም የእምነቱ ተከታዮች በአሉን በደስታ ለማሳለፍ ዝግጀቶችን ያደርጋሉ።
የገና በዓል አከባበር በኛም ሀገር ቄጠማ በመጎዝጎዝ፣ልዩ ልዩ ባህላዊ ምግቦችንና መጠጦችን በማዘጋጀት ይከበራል።ወቅቱ የአዝመራ ወቅት እንደመሆኑ ጥጋብ ነው፤በዚህ የተነሳም አርሶ አደሩ በደማቅ ስነስርአት ያከብረዋል። በአልባሳት መዋብ፣ መረዳዳት፣የገና ጨዋታ መጫወት የዚህ የበዓል ወቅት ትውፊቶች ናቸው።
ኢትዮጵያውያን የክርስትና እምነት ተከታዮች በዛሬው እለት የገና በዓልን እያከበሩ ናቸው።የልደት በዓል ገና በመባልም ይታወቃል፤የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ገና ከግሪክ የተወረሰ ቃል ነው ይላል።የገና በዓል ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ በምስራቅ አውሮፓ ታኅሳስ 29 የሚከበር ሲሆን፣ በምዕራባውያን ግን ታኅሳስ 15 ቀን ይከበራል።
ስለ ገና በዓል ካነሳን ዘንዳ ስለገና ጨዋታ ጨረፍ አልጎ ማረፉ ተገቢ ነው።አንዳንድ ሰዎች በዓሉ ራሱ ገና የተባለው ለገና ጨዋታ ሲጫወቱበት ከነበረው ዘንግ ወይም በትር በመነሳት ነው ይላሉ። በትሩ ከጠንካራ ዛፍ የሚሠራ እና ግማሽ ሜትር የሚደርስ ቁመና ሲኖረው ጫፉ ላይ ቆልመም ያለ ነው።‹‹ገ›› የመሰለ ቅርጽ ያለው በትሩን ሩር ወይም ጥንግ ሲመቱበት ሲያዞሩት ደግሞ የዞረ ‹‹ገ›› (፫) አልያም ‹‹ና›› ይመስላል። በዛ ምክንያት ገና ተባለ የሚሉ አሉ።
የገና ጨዋታ ሲጀመር ከእረኞች ቀስ በቀስ ወደ ሌሎቹ የተሸጋገረ መሆኑም ይገለጻል። ሌላው በገና ጨዋታ አይቆጡም ጌታ እንደሚባለው የሀገራችን ተረት ደግሞ ከሄድን በነገሥታቱ ዘመን በገና ጨዋታ ባላባቱም ጭሰኛውም ዳኛውም እረኛውም እግረኛውም አንድ ላይ እንደ እግር ኳስ ጨዋታ በቡድን 12 ለ12 ሆነው ይጫወታሉ።
በጨዋታው ንጉሡ ወይም ባላባቱ ቢጎዱ (ቢቆስሉ) በጨዋታውም ቢሸነፉ አምነው መቀበል ነው ያለባቸው፤ መቆጣት ክልክል ነበር። አሸናፊውም ተሸናፊውን አይጥ አበላው ተብሎ ይዘፈንለታል ሲሉ መረጃዎች ያስረዳሉ።
በመላው ዓለም ምዕራባውያን ከሚያከብሩት በዓላት ገና በልጆች በመወደድ ቀዳሚው ነው።እኛም የራሳችን የአከባበር ስልት እያለን የልጆቻቸውን አለባበስ እያየን አከባበራቸውን እየተከተልን ነው።ርግጥ ነው የባህል ወረራ በተስፋፋበት በዚህ ዘመን የኛው የቴሌቪዥን ማሠራጫዎች ሳይቀሩ በአሉን ሲያከብሩና የበአል እንግዳ ሲያናግሩ የገና አባት ምስል እንዲሁም በመብራት የተሽቆጠቆጠና የሚያረብቀርቅ የገና ዛፍ ከጀርባቸው አልያም ከጎናቸው እያሳዩን ነው።
ትልልቅ የንግድ ድርጅቶችም በዓሉን አስታከው ምርቶቻቸውን ሲያስተዋውቁ የገና ዛፍ እና የገና ሽማግሌ/ሳንታ ክላውስ/ ምስሎች አይቀሩም። በምግብ ቤቶች በቡና ቤቶች መስተንግዶ ቤቶቹ በሁለት አቅጣጫ ብቻ ግራ ቀኝ ነጭ ፀጉራቸው ሹሩባ የተሠራ የፈረንጆቹን ቀይ ኮፍያ አድርገው ሲያስተናግዱ ማየት የተለመደ ነው። ወንዶቹም ቀይ ኮፍያ ራሳቸው ላይ ጣል አድርገው ያስተናግዳሉ። በብልጭልጭ መብራት፣ የተጌጠ የገና ዛፍ፣ በየሆቴል ቤቶቹ ኬክ ቤቶቹ ተልምዷል።
ደግነቱ አሁን አሁን ፕላስቲክ ሰው ሠራሽ ጥድ ሆነልን እንጂ እየተመናመነ የመጣው ደናችን አደጋ ውስጥ ወድቆ ነበር።በተለይ የጽድ ዛፍ ለጭፍጨፋ ተጋልጦ ቆይቷል።
በአንዳንድ የግል አጸደ ህፃናት ትምህርት ቤቶች ህፃናትን የገና በዓል የምታከብሩበት ገንዘብ አዋጡ በማለት ህጻናቱ በአውሮፓውያኑ መንገድ በአሉን እንዲያከብሩ ሲደረግ ይታያል። ለህፃናቱ እንደ ፈረንጆቹ ገና ቀያይ ኮፍያ አድርገው የገና አባት የተባለው ግለሰብ የገና ቀይ ከፍያውን ከነጭ ፂሙ ጋር አድርጎ ለተማሪዎቹ ኬክና ከረሜላ እየሰጠ የገና በአል ሲከበር ያስተዋሉ ይገልጻሉ።
የገና በዓል አከባበሩን ለምን ኮረጅን? ምነው ሌሎቹን መኮረጅ ተሳነን? ለኔ ጠንካራ የሥራ ባላቸውን ቴክኖሎጂዎቻቸውን የማንበብና የትምህርት ስልታቸውን ብንኮርጅ ይሻለን ነበር።እኛ ሁሌ ጭፈራና ዳንኪራ ልቅ ፊልም በማየትና በመኮረጅ ለማደግ አንችልም።
የሀገራችን የክርስትና እምነት ተከታዮች የራሳቸው የሆነ የገና በዓል አከባበር ስርዓትና ትውፊት እንዳላቸው ይታወቃል።ይህን ስርአት እና ትውፊት በመጠበቅ በአሉ ቢከበር ትሩፋቱ ብዙ ነው።ጎብኚዎች ይህን የማያውቁትን ስርዓትና ትውፊት ፍለጋ በብዛት ሊመጡ ይችላሉ።በአላችንን ልናደምቅባቸው የምንችላቸውን ቀጤማ፣ድፎ ዳቦ ፣የተለያዩ ባህላዊ መጠጦቻችንን ወዘተ ልንጠብቃቸው ይገባል። የበአል አከባበራችንን ማድመቅ የሚገባን ቢሆንም የራሳችንን ትውፊት ጥለን የአውሮፓውያኑን አንጠልጥለን መሆን የለበትም።
አዲስ ዘመን ታህሳስ 29/2013