መርድ ክፍሉ
በገና በዓል ዙሪያ በተደረጉ ጥናቶች መሠረት ድሮ ሰዎች ፀሐይ አምላክ ናት ብለው ያምኑና ያመልኳት ነበር። ክረምት የሚመጣውም ፀሐይ ስትታመም ወይም ስትደክም ነው ብለው ያምኑም ነበር። በምድር በሰሜን ንፍቀ ክበብ አካባቢ አጭር የሚባለው ቀን የሚውለው እ.ኤ.አ. በታኅሣስ 21 ወይም 22 ነው።
ይህንንም ጊዜ ፀሐይ የድካሟ የመጨረሻ ደረጃ ላይ የምትደርስበት ይሏታል። ፀሐይ ከመጨረሻ ድካሟ በኋላ ወደ ቀድሞ ጥንካሬዋ ስለምትመለስ ይህ ወቅት በልዩ ሁኔታ ይከበር ነበር። ይህ በዓል በተለያዩ አገሮች በተለያየ ሁኔታ ይከበርም ነበር። ለምሳሌ ግብፃውያን ‹‹ራ››› ብለው የሚጠሩት ፀሐይን እንደ ኮፍያ ያጠለቀ አምላካቸውን የሚያስቡበትና የሚያከብሩበት በዓል ሲሆን፣ የጥንት ሮማውያን ደግሞ ሳተርን የሚሉትን የእርሻ አምላክ ለማክበር በዓሉን ሳቱርናሊያ ብለው ያከብሩ ነበር። ቀጥሎ የሚመጣውን አረንጓዴነት በማሰብም ቤተ መቅደሳቸውንና ቤታቸውን በአረንጓዴ እፀዋት ያስጌጡታል።
ለዛሬው የፈረንጆች ገና አከባበር ዋና መሠረቱ የሮማ አረማውያን ሳቱርናልያ የሚባለው ታኅሣሥ 17 እስከ 25 የሚቆይው የአንድ ሳምንት ሕግ አልባ ክብረ በዓል ነው። በዚህ ሳምንት የሮማ ፍርድ ቤቶች በሙሉ ይዘጉ ነበር። የሮማ ሕግም በዚህ ሳምንት ውስጥ ንብረት ያጠፋም ሆነ ሰው ያቆሰለ እንደማይቀጣ ይደነግጋል።
ሳምንት የሚቆየው በዓል የሚጀምረው የሮማ ባለሥልጣኖች የሮማውያን ጠላት ብለው የሚሰይሙትና የመጥፎ መንግሥት ጌታን የሚወክለውን ሰው/ሰዎች ከመረጡ በኋላ ነው። እነዚህ የሚመረጡት ሰዎች ምንም ጥፋት ያላጠፉ ንፁኃን ሰዎች ነበሩ።
እያንዳንዱ የሮማ ማኅበረሰብ የየራሱን የሮማውያን ጠላት ይመርጥና ሳምንቱን ሙሉ እነዚህን ንፁኃን ሰዎች ከመጠን በላይ እንዲበሉ፣ እንዲጠጡና እንዲዳሩ ያስገድዷቸዋል። ሮማውያኑም በዓሉን የሚያከብሩት ከመጠን በላይ በመብላት፣ በመጠጣት፣ በመዳራትና በመዋጋት ነበር።
በበዓሉ የመጨረሻ ቀንም ማለትም ዛሬ የክርስቶስ የልደት ቀን ነው ተብሎ በሚታመንበት ታህሳስ 25 እነዚህን ሳምንቱን ሙሉ የተሰቃዩ ንፁኃን ወንዶችና ሴቶች በመግደል ሮማውያን ጠላቶቻቸውን እንዳጠፉ በመቁጠር ይኩራሩ ነበር።
የገና በዓል ከስሙ ስንጀምር ገና የሚለው ስም መሰረቱ የግሪክ ቃል ነው። በግሪክ ቋንቋ ገና ማለት ልደት ማለት ነው። ምዕራባውያን ሜሪ ክሪስማርስ ሲሉት ኢትዮጵያውያን ደግሞ መልካም የገና በዓል ይላሉ። ስለዚህ ገና የሚለው ቃል ልደትንም ነው የሚወክለው። የአዲስ ኪዳን ውስጥ ከአራቱ ወንጌል ሦስቱ ከግሪክ ቋንቋ ነው የተተረጎመው።
ይህንነ ትውፊት በመጠበቅ ገና የሚለውን ቃል ኢትዮጵያውያን ወስደውታል። ስለ ገና በዓል ኃይማኖታዊ መሰረትና አከባበር በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን በመንበረ ፓትርያሪክ በውጭ ጉዳይ መምሪያና በብፁ ወቅዱስ ፓትርያሪክ ልዩ ጽህፈት ቤት ውስጥ ከሚሰሩት መምህር ዳንኤል ሰይፈሚካኤል ጋር ያደረግውን ቆይታ እንደሚከተለው አቅርበነዋል።
የበዓሉ ኃይማኖታዊ መሠረትየገና በዓል ኃይማኖታዊ መሠረቱ ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ልጅ ለማዳን ከሰማያት ሰማት ወርዶ ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ ሰው ሆኖ ሰው ከገባበትና ከተፈረደበት እንዲሁም ከተያዘበት መከራ፣ ሞትና እሥር ነፃ ሊያወጣ ሰው ሆኖ የተወለደበትን ቀን መሰረት ተደርጎ የሚከበር ነው።
በዓሉ ሲከበር በነቢያት፣ በአበውና በካህናተ ኦሪት የነበሩ ትንቢቶች፣ ተስፋዎችና ሥርዓቶች ነው። ይህም ሲባል ለአበው የሰጠውን ተስፋና በነቢያት ላይ አድሮ በተናገረው ትንቢት እናም በብሉይ ካህናት የሠራውን ሥርዓት መሠረት ተደርጎ ከሰዓቱም ከጊዜውም ሳያዛንፍ በገባው ቃል ኪዳን መሰረት አምስት ሺህ 500 ዘመን ሲፈፀም ሰው ሆኗል። ይህንን ቅዱስ ጳውሎስ የቀጠሮ ቀን ወይም የዘመኑ ፍፃሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት ተወለደ ብሎ ተናግሮታል።
ይህ የሚያሳየው እግዚአብሔር ለአዳም የሰጠው ተስፋ ወይም ቀጠሮ ነበር። ይህ ቀጠሮ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ ሰው ሆኜ ሞትን ተቀብዬ አድንሃለው የሚል ነው። ይህ የድህነትና የምህረት ተስፋ ነበር። እንዲሁም አዳምን ወደቀደመው ማዕረጉ የሚመልስ ተስፋ ስለነበር ይህንን ለመፈፀም ሰው ሆኗል።
ይሄ ቤተክርስቲያን ከምታስተምረው በተጨማሪ በብሉይ ኪዳን ውስጥ በቀጥታ የተቀመጠ ሲሆን በብሉይ ኪዳንና በዘፍጥረት አዳም ከተሳሳተ በኋላ ሁለት ነገሮች መጽሐፉ ላይ ተቀምጠዋል። መጀመሪያ ሴት ብሎ ያወጣላትን ስም የሄዋን ብሎ የቀየረው ከተሳሳተ በኋላ ነው።
አዳም ከገነት ከተባረረ በኋላ ማለት ነው። ሁለተኛው አዳም እራቁቴን ሆኛለው፣ ፈጣሪን አስቀይሚያለው፣ አታድርግ የተባልኩትን አድርጊያለው ብሎ መፀፀቱንና ንስሀ መግባቱን እግዚአብሔር ከተመለከተ በኋላ ‹እንግዲህ አዳም ከኛ እንደ አንዱ ሆነ› ብሏል። እነዚህ የሚያሳዩት እግዚአብሔር ሰው እንደሚሆን ቅድመ ትንቢት ወይም ተስፋ ነው።
በመለኮት አዳም እንደ አንዳችን ሆነ የተባለው ከሦስቱ ሥላሴዎች አንዱ የሆነው ቃል የተባለው ወልደ እግዚአብሔር ሥጋ መልበሱንና ሰው መሆኑን ወይም ሰው እንደሚሆንና ሥጋ እንደሚለብስ አስቀድሞ የተነገረ ተስፋ ነው። ሌላው ሄዋን እፀበለሱን በልታና አዳምን አብልታ ያሳተች በመሆኑ ለሞት፣ ከገነት ለመባረርና ከፈጣሪው ለመባረር ምክንያት የሆነችውን ሄዋንን ሂወቴ አላት።
አበው ይህንን ሲያብራሩት አዳም ከድንግል ማርያም አምላክ ሰው ሆኖ እንደሚያድነው ስላወቀ፣ እንደገናም ይሄ የሚፈፀመው በሄዋን መሆኑን ስለተረዳ እንዲሁም አዳም የሚድነው ከሄዋን በሚገኝ ትውልድ ወይም ከሴት ብቻ ያለወንድ ዘር እግዚአብሔር ተወልዶ ሰው እንደሚሆን አስቀድሞ ስለነገረው ሄዋንን ሂወቴ አላት። ሄዋን ማለት በግብር ትርጉም እመ ሄዋን ማለት ነው። በቋንቋ ትርጉሙ ደግሞ ሂወት ማለት ነው።
ይህ ትንቢት ሳይቋረጥ አበው በሚባሉት 22 አባቶች ከአዳም ጀምሮ እስከ አብርሃም፣ ይስሃቅና ያዕቆብ ድረስ። ከዚያ በኋላ መሳፍንት በሚባሉት ከሙሴ ጀምሮ ሳሙኤልና ኤሊ በሚባሉ መሳፍንት። በነገሥታት በእነ ዳዊትና ሰለሞን። በነቢያት ደግሞ በኢሳያስ፣ በህዝቅኤል፣ ኤርሚያስና ዳንኤል ጀምሮ እስከ ደቂቅ ነቢያት ሁሉ እግዚአብሔር ሰው እንደሚሆን ተነግሯል።
ገና ማለት ነቢያት የተነበዩለት፣ አበው ተስፋ ሲያደርጉበት የነበረውና በነገሥታትና በመሳፍንት የተደረገው እንዲሁም ካህናተ ኦሪት በምሳሌ ሲሰሩት የነበረው ሁሉ የተፈፀመበት ነው። እግዚአብሔር ዘመን ከማይቆጠርለት አንድ ሁለት እየተባለ ዘመን የተቆጠረለት እና ሌሎች ነገሮች የተከናወኑበት ቀን ነው ገና የሚባለው። ስለዚህ ገና ከኃይማኖት ውጭ ምንም አይነት መሰረት የለውም።
የገና በዓል የሚከበረው የክርስቶስን ልደት ለማክበር ብቻ ነው። በዘመናት ሂደት ውስጥ እግዚአብሔር ዓለምን ከፈጠረበት ጊዜ አንስቶ እጅግ በጣም በረቀቀ በማይደረስበት ጥበብ ዓለምን ለማዳን ሰው የሆነበት ጥበብ የታየበትና የተገለጠበት ነው። ስለዚህ የኃይማት መሰረቱ የአምላክ ሰው መሆን ነው።
በዓሉ ሲከበር የተከናወኑ ተግባራትም አብረው ይነሳሉ። ከዚህም ውስጥ ክርስቶስ ሊወለድ ሲል አስቀድሞ በመላዕክት ብሥራቱ ተነግሯል። ልደቱ በተፈፀመ ጊዜ ደግሞ የሰብዓ ሰገል ወይም ጠቢባን ነገሥታት የሚባሉት ከሩቅ አገር በኮከብ ተመርተው ወደ ቤተልሄም መድረሳቸውና ለተወለደው ጌታም እጅ መንሻ ማቅረባቸው በወንጌላውያን ተገልጿል።
ስለዚህ ይህን ክንውን በበዓሉ ወቅት አብሮ ይዘከራል። እንደገና እረኞች ሜዳ ላይ ሆነው ሳለ መላዕክት ተገልጠው የጌታን ልደት አብስረዋቸው፤ ወደ ቤተልሄም ሄደው ከተኛበት ወይም ከተወለደበት በረት ክብር መስጠታቸውና መስገዳቸው ተገልጿል። ይሄም ሌላ ክንውን ነው።
እነዚህን ክንውኖች ማወቁ የሚጠቅመው በወቅቱ የተደረገው ነገር ማንኛውም ሰው እንደሚወለደው አይነት ቢሆንም አምላክ ነውና ለተለየ ዓላማ የመጣ የእግዚአብሔር ልጅ ሰውን ለማዳን የመጣ በመሆኑ እንዲሁም በታሪክ አጋጣሚ እግዚአብሔር የሰውን ሥጋ ለብሶ የመጣበትና የማይደገም በመሆኑ ክስተቶቹን በሚገባ ማጥናቱ የልደቱን ኃይማታዊ መሠረት በደንብ እንዲታወቅ ያደርገዋል።
የበዓሉ አከባበር
የገና በዓል አከባበር በተመለከተ በየዘመኑ የተከፋፈሉ አከባበሮች አሉት። መጽሐፍ ቅዱስ ተርጓሚዎች እንደሚናሩት የገና በዓል አከባበር ሄሮድስ ከሁለት ዓመት በፊት ኮከቡን እንዳዩት ሰብዓሰገል ከነገሩት በኋላ ምን አደረገ የሚል ምርምር ተካሂዶ ነበር። ምርምር ያደረጉት አባት ኮከቡ ጌታ በተወለደበት ጊዜ ነበር የታየው፣ ነገር ግን ሰብዓሰገል ቤተልሄም እስኪደርሱ ሁለት ዓመት ፈጅተዋል።
ቅድስት ድንግል ማርያም በየዓመቱ ጌታ በተወለደበት ቦታ ላይ ልደቱን ታከብር ነበር። ሄሮድስ የሁለት ዓመት ህፃናትን ለማስገደል ምክንያት የሆነው ጌታ ከተወለደ ሁለት ዓመት ሆኖታል የሚል ሀሳብ ስለነበረ ነው።
ከዚህ ውጭ አብዛኛው በክርስትና ኢየሱስ ክርስቶስ ከተወለደ በኋላ ሦስት ዓመት ከስድስት ወር በግብፅ ስደት ላይ ነበር። ከዛም አገሩ ቤተልሄምም ብዙ ሳይቆይ በዮሴፍ አገር ናዝሬትና ገሊላ ኖሯል። ከዛም በኋላ በዮርዳኖስ ተጠምቆ ወንጌልን መሰረተ። ከዚያም ሞቶና ተነስቶ ክርስትናን ከመሰረተ በኋላ መንፈስ ቅዱስን ልኮ ሐዋርያትን ሲያሰማራ በአብዛኛው ትኩረት የተሰጠው ከልደቱ ይልቅ ለትንሳኤው ነበር። ሐዋርያት በሰፊው ይህን እንዳከበሩት የምናውቀው በየዓመቱ ያለማቋረጥ ህማሙን፣ ሞቱንና ትንሳኤውን አክብረዋል።
በሮማውያን ዘመን ክርስትና ነፃነት አልነበራትም። አሁን እንደሚከበረው የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት፣ ጥምቀቱ፣ ግዝረቱ፣ ያደረጋቸው ታአምራት እና ሌሎች ነገሮችን ማክበር አይቻልም ነበር። በዚህ አይነት ሁኔታ ተከብሯል ብሎ ለመናገር ብዙ ጥናቶች እየተደረጉ ናቸው። ነገር ግን በነፃነት ውስጥ የነበሩት ኢትዮጵያ፣ አርመኒያና ፋርስ ቤተክርስቲያናት ልደቱን ያስቡት እንደነበር ብዙ መረጃዎች አሉ።
በዓሉን በሥርዓተ አምልኮ፣ በቅዳሴ፣ በስብከተ ወንጌልና በማህሌት ያከብሩት ነበር። የልደት በዓል በሰፊው እንዲከበር መሰረት የጣለው የንቂያ ጉባኤ ነበር። ከክርስቶስ ልደት ከ325 በኋላ የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት በዓል ከአበይት በዓላት አንዱ ሆኖ እንዲከበር ማለትም ፅንሰቱም ልደቱም እንዲከበር ተወሰነ።
የአከባበሩ ሥርዓት ነፃነት ስለበር እያደገ ከህዝብ ትውፊት ጋር፣ ከአኗኗር ባህል ጋር፣ ከማህበራዊ እሴቶች ጋር እየዳበረ መጥቷል። ለምሳሌ የገና ጨዋታ የሚባል አለ። በልደት በዓል ወቅት ከሚደረጉ ጨዋታዎች መካከል አንዱ ነው። ምስጢሩ ከጌታችን ሰው መሆን ጋር አብሮ የሚሄድ በመሆኑ ‹‹በገና ጨዋታ አይቆጡም ጌታ›› እየተባለ ልዩነት ሳይኖር የሚደረግ ጨዋታ ነው።
ይሄ ከማህበራዊ እሴት ጋር ሰው ከሰው ጋር እየተጠያየቀ፣ ታናናሾች ታላላቆችን እያከበሩ፣ ታላላቆች ታናናሾቻቸውን እየጠሩ በአንድነት በጋራ አምላክ ሰው የሆነበት እየተባለ ጠንካራ የሆነ ማህበራዊ ትስስር፣ ፍቅር በሰው ልጆች ውስጥ መከባበርና እርስበርስ መዋደድ፣ የኃይማኖታዊ እሴቱ ባህላዊ ዋጋ እንዲኖረው እየተደረገ በብዙ ቦታዎች ስጦታ እየተበረከተ እየተከበረ ይገኛል። ይህ ሁኔታ ሰዎች ክብር እንዲሰማቸው፣ አንዱ ለአንዱ ወገንተኝነት እንዲሰማው መከባበር እንዲኖር አድርጎታል።
የበዓሉ አከባበር በኢትዮጵያ
በኢትዮጵያ የገና በዓል ሲከበር ልዩ የሆነ ነገር አለው። ከዚህም ውስጥ ኢትዮጵያውያን በነፃነት ውስጥ የነበሩ ህዝቦች በመሆናቸው ቤተክርስቲያን ህብረተሰቡ በማህበራዊ፣ በኢኮኖሚያዊ፣ ባህላዊ፣ ሥነጥበባዊ ሁለንተና ውስጥ ትልቅ ተቋም እንደመሆንዋ ብዙ የሚያምሩ አከባበሮች አሉት። ከነዚህም ውስጥ የቅዱስ ላሊበላ አከባበር ይጠቀሳል። የልደት በዓል በቅዱስ ላሊበላ ልክ ቤተልሄም እንደተከናወነው ታሪካዊ ነገሩ እንዳይለወጥ ቤተልሄምን የሚወክል ቦታ ተዘጋጅቶ፣ በልዩ ሁኔታ የመላዕክቱና የእረኞቹ ዝማሬ፣ የሰብዓ ሰገል ስጦታ አጠቃላይ የተደረገውን በሚዘክር ሁኔታ የተለየ ሥነጥበባዊ ሥራ ተሠርቶ ይከበራል።
ይሄ በመላው ዓለም ከሚከበረው በተለየ መልኩ ቅዱስ መጽሐፍት በሚያዙት መንገድ መሰረት አድርጎ የሚከበር ነው። ቅዱስ ላሊበላ ላሊበላን የሰራበት የአስተሳሰብ ምንጭ ቅዱሳን መጽሐፍቶች ናቸው። በዋናነት የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ላሊበላን እንዲሠራ ምክንያት ሆኖታል። የቅዱስ ላሊበላ ቤተክርስቲያን አሠራር የጌታን ልደትና ከልደት በኋላ የሠራቸውን ሥራዎች ለማሰብ ነው።
ኢትዮጵያውያን እየሩሳሌም ሳይሄዱ ላሊበላ በመሄድ የጌታን ልደት ማክበር እንዲቻል ተደርጎ ተሠርቷል። ለዚህም ቅዱስ ላሊበላ ቃልኪዳን ተቀብሎበታል። ላሊበላ መጥቶ ልደቱን ያከበረ፣ ቤተልሄም ሄዶ እንደ ሰብዓሰገል እጅ መንሻ እንዳቀረበ፣ እንደ እረኞቹ ደስታውን እንደገለፀ እና እንደ መላዕክት እንደዘመረ ይቆጠርለታል። በኢትዮጵያ መሰረቱን ሳይለቅ በልዩ እሴት አባቶች ተራቀውበት በእግዚአብሔር እገዛ ያከብሩታል።
አዲስ ዘመን ታህሳስ 29/2013