ወርቅነሽ ደምሰው
በሀገራችን በዓላት አካባበር ለየት ያለ ድባብ ያለው ነው፡፡ በዓልን በዓል ለማስመሰል ሁሉም ባለው አቅም የሚታትርበት፤ የገበያ ግርግሩ ሸመታ የሚጧጧፍበት ነው፡፡ በዓል መድረሱን የሚናገሩት የበዓል ድምቀቶች በቀላሉ የሚታይ አይደለም፡፡ የበዓል ሽርጉድ ከዋዜማው ጀምሮ እስከዕለቱ በተለያዩ ሁኔታዎች የሚከወኑበት ነው፡፡
በበዓሉ ዕለትም ዘመድ ከአዝማዱ፤ ጎረቤት ከጎረቤቱ፤ ሰፈር ከመንደሩ ሁሉም ተሰባሰቦ በጋራ አብሮ በመብላትና በመጠጣት በዓልን በጋራ ማሳለፍ ከጥንት ጀምሮ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ የኢትዮጵያዊ ባህላችን ነው፡፡
በተለይ በዓልን ኢትዮጵያውያን ከሌሎች ለየት የሚያደርገው የተለያዩ የበዓል መገለጫዎች አሉት፡፡ ከእነዚህም የበዓል ወቅት እርስ በእርስ ከመረዳዳትና በዓልን በጋራ ከማክበር ባሻገር በሙስሊም ሆነ ከክርስቲያኑ ዘንድ በዓልን በጋራ አብሮ ማሳለፍ የተለመደ መሆኑ ነው፡፡
ታዲያ በበዓላት ወቅት ሃይማኖታዊ አስተምሮትም የሚፈቅደውና ኢትዮጵያዊ ባህላችን የሆኑት እሴቶቻችን ያለው ሰው ለሌለው የማካፈልና አቅመ ደካሞች የመረዳትና እርስ በእርስ መደጋገፍ ሳይረሳ ማለት ነው፡፡ በኢትዮጵያ በበዓላት ወቅት ያለው መረዳዳትና በዓል በጋራ የማክበር ሁኔታ ምን ይመስላል ስንል ከሃይማኖት አባቶች ጋር ቆይታ አድርገናል፡፡
የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ጠቅላይ ጸሐፊ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ታጋይ ታደለ እንደሚናገሩት፤ በሀገራችን በበዓላት በተለይ ከችግረኞች፣ ከድሆችና አቅም ከሌላቸው ሰዎች ጋር አብሮ በመሆን ለዘመናት በጋራ በመረዳዳት በመካፈል አብሮ በመብላትና በመጠጣት ሲከበር ኖሯል፡፡
ይህ በኦርቶዶክስ እምነት ብቻ ሳይሆን በሁሉም ቤተ እምነቶች ያለ ሲሆን፤ በሙስሊሙ ማህበረሰብ ዘንድ በዓል ሲከበር ከሌሎች ክርስቲያኖች ጋር አብሮ ተካፍሎ በዓልን ማክበር የተለመደ የኢትዮጵያዊነት መገለጫ ነው፡፡
አሁን ላይ አብሮነቱ ጠፋ ባይባልም፤ ነገር ግን እየተሸረሸረ መምጣቱ ብዙ ጥናቶች ያሳያሉ ያሉት ሊቀ ትጉሃን ፤ የኢትዮጵያዊ ባህላችን ሰው ከሰው ጋር አብሮ መብላትና መጠጣት ብቻ ሳይሆን ለእንስሳት ሳይቀር የሚራራ እንደነበር የሚታወቅ ቢሆንም፤ አሁን ላይ ግን ከዚህ የአብሮነት ባህል ያፈነገጡ ድርጊቶችን መመልከት የተለመደ ሆኗል፡፡
አሁን ላይ አንዱ ኢትዮጵያዊ ሌላውን እየገደለ እና እያፈናቀለ ለበርካታ ውስብስብ ችግሮች መዳረግ በስፋት እየተመለከትን ነው፡፡ ይህ አሁን ያለው አብሮነቱ ሙሉ ለሙሉ ባይጠፋም፤ እየላለና እየሻከረ መምጣቱን የሚያሳይ ሲሆን፤ ይህንን በማውገዝ የጥንቱን አብሮነት በመመለሰ በመረዳዳትና በመደጋገፍ ያለንን አብሮ በማካፈል፤ አብሮ በመብላትና በመጠጣት ደስታን ሆነ ኀዘንን በጋራ መካፈል እንደሚገባም መክረዋል፡፡
ሊቀ ትጉሃን እንደሚሉት፤ ልክ አድዋ የመጣውን የጋራ ወራሪ ጠላት በጋራ መክተን እንደተሻገርን ድህነት፤ ችግርንና የተለያዩ ውጣ ውረዶችን በጋራ መመከት ይገባል፡፡ ኮቪድ ወረርሽኝ ሀገራችን በገባ ወቅት የታየው ጠንካራ የመረዳዳት ባህል የመረዳዳት ባህላችን አለመሸርሸሩን ማሳያ በመሆኑ አሁንም በዓላት ሲከበሩ አቅመ ደካማዎች በማሰብ ያለው ለሌላው በማካፈል በዓሉን በጋራ ማሳለፍ እንደሚገባ ጠቁመዋል፡፡ በተመሳሳይ የታሰሩት በመጎብኘት፤ ለችግር የተጋለጡትን በማገዝና በህመም አልጋ ላይ ያሉት ወገኖቻችንን በመጎብኘት ማሳለፍ አለብን፡፡
ለመረዳዳት ሆነ አብሮ በጋራ ተካፎሎ ለመብላት ደግሞ ኢትዮጵያዊ መሆኑ ብቻ በቂ መሆኑን ጠቁመው፤ እነዚህ እሴቶቻችን ከሃይማኖታዊ ፋይዳቸው ባሻገር ማህበራዊ ፋይዳው የጎላ ስለሆነ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ሊፈጽሟቸው የሚገባቸው ተግባራት በመሆናቸው ማንም ከማንም ሳይለይ በጋራ በዓላት ማሳለፍ ይጠበቅበናል ሲሉ መልዕክታቸውን ያስተላለፋሉ፡፡
የኢትዮጵያ ሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ምክትል ዋና ኃላፊ ሐጅ መስዑድ አደም በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያዊ መረዳዳትና እርስ በእርስ መደጋገፉ እሴታችን ዘመናትን የተሻገረ ነው፡፡ ለእነዚህም ማህበራዊ መገለጫዎች በበዓላት፣ ሠርግ፣ የግብርና ሥራ፣ በጉልበት የማገዝ፣ በእድርና፣ እቁብን በመሳሰሉት የሚገለጽ ነው፡፡ በዚህም ሰዎች ችግራቸውን በጋራ በመተጋገዝና በመረዳዳት ያልፉበታል፡፡
በተለይ በበዓላት ጊዜ ኢትዮጵያውያን የምንታወቅበት እንደ ቡና ጠጡ ያሉ ባህሎቻችን የአብሮነታችን ማሳያዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ባህሎቻችን ብዙ ትርጉም አላቸው፡፡ ጉዳዩ የአንድ ሲኒ ቡና የመጠጣት ሳይሆን፤ አብሮነት የሚገለጥባቸው ኢትዮጵያዊ ባህሎች ናቸው፡፡
ኢትዮጵያውያን ከሌላው ዓለም በተለየ መልኩ ሕይወታችን ማህበራዊነት ላይ የተመሰረተ ነው የሚሉት ሐጅ መስዑድ ፤ በሙስሊሞችና ክርስቲያኖች መካከል እርስ በእርስ የመተሳሰብና በአንዱ በዓል አንዱ የእንኳን አደረሳችሁ ከመባባል ባሻገር አብሮ መብላቱና መጠጣቱ የተለመደ የአብሮና የትስስር ጠንካራ መገለጫ ነው፡፡ ለዚህም ነው አሁን ላይ እየተሰራ ከሚገኘው ክፋት አንጻር ትስስሩ ሳይበጠስ እሴቶቻችን በጠንካራ መሠረት ላይ ዘልቀው መቆየት የቻሉት፡፡
እናቶች ወደ ገበያ ሲሄዱ የሚጠባ ልጅ አደራ ብለው የሚሄዱት ጎረቤት ላይ ነው፡፤ የጎረቤት እናት ደግሞ የአደራ ልጇን አጥብታ ታሳድጋለች፡፡ ኢትዮጵያዊነት ትስስሩ በዚህ ልክ የሚገለጽ ነው፡፡ እኛ ያለን ማህበራዊ እሴቶታችን ጠንካራ ስለሆነ ይህንን አጠናክረን መቀጠል ይገባናል፡፡
እንደ ሐጅ መስዑድ ገለጻ፤ የመረዳዳትና በዓል በጋራ ማሳለፍ በተመለከተ አሁን ላይ በከተሞች የሚታዩ ሁለት ዓይነት ነገሮች አሉ፡፡ አንዳንድ ቦታ ላይ ያለው ሁኔታ ለማህበራዊ ትስስር አመቺ ሆኖም ትስስሩ ላልቶ ይታያል፡፡
ለምሳሌ የጋራ መኖሪያ ቤቶች የመረዳዳትና በዓልን በጋራ የማሳለፍ ሁኔታ ላልተው የሚታዩባቸው ናቸው፡፡ ሌሎች አንዳንድ ቦታ ደግሞ የመደጋገፍና በዓልን በጋራ መረዳዳት ከማሳለፍ በላይ አለፍ ብለው ቤተሰባዊነት ትስስር የሚመሰረቱበት ሁኔታ መኖሩን ያስረዳሉ፡፡
አሁን ላይ ማህበራዊ ትስስሩ የሚያጋጥሟቸው ፈተናዎችን በርካታ ናቸው የሚሉት ሐጅ መስዑድ፤ አንደኛው በሥራ ምክንያት ጠዋት ወጥቶ ማታ የሚገቡ ሰዎች ከጎረቤቶቻቸው ጋር ያለው ማህበራዊ ትስስር የላለ መሆኑ ሲሆን፤ ሁለተኛው ማህበራዊ እሴቶታችንን በመናቅና የምዕራባውያንን ግላዊ እሳቤ በማንጸባረቅ ለመውረስ ጥረት የሚያደርጉ አካላት መኖራቸው ነው፡፡ ይህን ባህላችንን ሊሸረሽር የሚችል ተግባር በመሆኑ ትክክል ያልሆነ ተግባር መሆኑን ማስተማር ይገባል፡፡
አሁን ባለው ሁኔታ የኢኮኖሚያዊ ችግር ከሌለ በስተቀር መረዳዳትና መደጋገፍ በዓልን በጋራ ማሳለፍ የማይፈልግ ሰው አለ ለማለት አያስደፍርም፡፡ ለዚህም የኮቪድ ወረርሽኝ መከሰትን ተከትሎ ኢትዮጵያውያን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባቀረቡት የማዕድ ማጋራት ላይ የሰጡት ምላሽ ፈጣን ምላሽ አንዱ ማሳያ ነው፡፡ ይህ የሚያሳየው እሴቶቻችን ተሸርሽረው ያላለቁ በጠንካራ መሠረት ላይ የተገነቡ መሆናቸውን ነው፡፡
ማህበራዊ ትስስሮቻችንን በማጠናከርና በማሳደግ የበለጠ የሥራ ባህላችንን በማሻሻል፤ ልጆችን በሥነምግባር በማሳደግ፤ በአካባቢ ሰላም ላይ በጋራ በመነጋገር ቀድሞ ኢትዮጵያዊ ባህላችን ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ የሚናገሩት ሐጅ መስዑድ፤ ከእስልምና አስተምሮ አንጻር ሲታይ ነብዩ እንደሚሉት ከቤታችሁ ግራና ቀኝ አርባ በር ድረስ ያሉት ጎረቤቶታችሁ ናቸው፡፡
በዚያ ውስጥ የተለያዩ እምነቶች ሊኖሩ ይችላሉ፤ የግድ ከሙስሊሞች ጋር ተጎራበቱ አይደለም ያሉት፤ ይህ ማለት ደግሞ የግድ በብሔር፤ በእምነትና በቋንቋ እኛን ከሚመስል ጋር ብቻ መጎዳኘት ሳይሆን ሰው በመሆኑ ብቻ ነው መቀራረብን መፍጠር የሚገባን ፡፡ ማህበራዊ እሴቶቻችን ደግሞ ችግርን ለመሻገር፣ አብሮነትን ለማጠናከር፣ የሀገርን ሰላም ለመገንባት፣ ትውልድን ለማፍራት እና ቅርስን ጠብቆ ለማስተላለፍ የሚያስችል እንዲሆኑ የሁላችን ኃላፊነት መሆን አለበት ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
በተመሳሳይ ኢትዮጵያ ወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት የቀድሞ የቦርድ ሰብሳቢ መጋቢ ዘሪሁን ደጉ በበኩላቸው፤ በዓላት ሲከበሩ ሁለት ዓላማ አላቸው፡፡ አንደኛ ለፈጣሪ ምስጋና ማቅረቢያ ሲሆን፤ ሁለተኛው በዓሉ ሲከበር እርስ በእርሳችን በቋንቋ፣ በብሔርና በኑሮ ደረጃ ስንለያይ አብረን የምንቆምበት እርስ በርስ የምንቀራረብበት መድረክ ነው፡፡ በሃይማኖት ከምናከብረው የበለጠና በዓል ምክንያት ከምንደግሰው ድግስ የበለጠ እግዚአብሔር የሚያስደስተው ለሰው ልጆች ነፍስ የምንሰጠው ቦታና ርህራሄ ነው ይላሉ፡፡
በተለይ በአሁኑ ወቅት በዓላትን ስናከብር በርካታ ሰዎች ከቀያቸው በተፈናቀሉበትና በርካታ ንጹህን ዜጎች በግፍ በተገደሉበት ወቅት የምናከበር በመሆኑ ሁለት ነገር ላይ ትኩረት ማድረግ አለብን፡፡ የመጀመሪያው በግጭቱ በተለያየ ምክንያት ቤተሰብ ላጡ፤ በሃዘን ውስጥ ላሉ፤ ልባቸው ለቆሰለ ወገኖች እግዚአብሔር መጽናናትን እንዲሰጣቸው መጸለይና ባለን ነገር እነሱን በማሰብ በመደገፍ ማሳለፍ ይገባል፡፡
ሁለተኛው ለራሳችንን እንደሀገርም ቃልኪዳን በመግባት እንደሃይማኖት ተከታይ እያንዳንዳችን ማድረግ ከሌለብን ነገር ላይ እጃችንን አንስተን ሀገርን በሚታደግ በአብሮነት ጉዳይ ላይ በጋራ መቆም አለብን የሚለውን ምክር አስተላልፈዋል፡፡
‹‹በዓላት ሕዝብ ከሕዝብ ጋር እርስ በእርስ የሚያስተሳስሩ ገመዶች ናቸው›› የሚሉት መጋቢ ዘሪሁን፤ ‹‹በበዓላት ቀን ብቻ ሳይሆን በዘወትር ኑሮአችንም ያለው ከሌለው ጋር ተካፍሎ እንዲኖር ስለሚያደርግ ሃይማኖታዊ እሴቱን ብቻ ሳይሆን ማህበራዊ ትስስሩን እየጠነከረ እንዲሄድ ያደርገዋል›› ብለዋል፡፡
እንደ መጋቢ ገለጻ፤ በተለይ የገና በዓልን በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ያከበሩታል፤ ይህ ሁሉ አማኝ ባለበት ሀገራችን ለምንድነው አንዳችን ለአንዳችን ጠላት የምንሆነው? እንደዚህ ዓይነቱን ድርጊት የሚፈጸሙት ደግሞ በሃይማኖታዊ አስተምሮት በማነጽ ከድርጊታቸቸው እንዲቆጠቡ ማድረግ ይገባል፡፡
መንግሥት፣ ሌሎች ተቃዋሚ ፓርቲዎና አክቲቪስቶችም ቢሆን እያንዳንዱን ዜጋ በዚህ መንገድ እየመከርና እየገሰጸን የሀገራችንን ሰላምና አብሮነት ልናጠናክር ይገባል፡፡
ሌላው በበዓል ወቅት ቅርታ መደራረግ ዋነኛው የበዓሉ አካል መሆን አለበት፡፡ አንዳችን ሌላችን ይቅርታ ሳንባባልና ጥላቻ ቂም ይዘን ለበቀል እየተዘጋጀን ባለንበት ሁኔታ ሃይማኖታዊ በዓል ማክበር ትርጉም አይኖረውም፡፡ ሃይማኖት ትርጉም የሚኖረው ይቅርታና ፍቅር ሲኖር ነው እንጂ፤ በጥላቻ የተሞላ ልብ ይዘን ሃይማኖት ሃይማኖት ሊሆን አይችልም፡፡
ከጥላቻ ከበቀል ተላቀን ይቅርታ በመስጠትና በመቀበል መተሳሰብና ፍቅር እንዲኖረንና በፍቅር እንድንኖር እግዚአብሔር ይረዳን ዘንድ መጸለይ ይገባል የሚሉት መጋቢ ዘሪሁን፤ እያንዳንዱ ሰው በዓሉን በሚያከብርበት ጊዜ የተቸገሩና መንፈሳቸው ለተጎዱ ሰዎች በመጸለይና በማፀናናት እንዲሁም ያለው ሰው ለሌለው በማካፍል በሀገራችን ዕጣፈንታ ላይ አብረን ቆመን በጋራ ይቺ ሀገር ታስፈልገኛለች በማለት ለሀገራችን ሰላምና አብሮነት ሁላችንም እንድንሰራ ይገባል ሲሉ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡
አዲስ ዘመን ታህሳስ 29/2013