
የምን ጊዜም የቦክስ ስፖርት ንጉሱ መሐመድ አሊ የዓለም የቦክስ ቻምፒዮንና ታላቅ የቡጢ ተፋላሚ ብቻ አልነበረም። የሰብዓዊ መብት ተሟጋች፤ የጥቁር ህዝቦች ሰንደቅ፤ በመላው ዓለም በስፖርትና በታላቅ ስብዕና ተምሳሌትም ጭምር ነው። ብዙዎች ቦክስ ስፖርት ሳይሆን የጥጋበኞች ድብድብ አድርገው ከመሳል አስተሳሰብ አውጥቶ የቦክስን ስፖርት ጥበባዊ ገፅታ በማላበስ ተወዳጅና አሁን ላይ በዓለማችን በአንድ ጊዜ በርካታ ሚሊየን ዶላሮች የሚያሳቅፍ ግንባር ቀደም ስፖርት እንዲሆን ተፅዕኖውን አሳርፏል። ሙዚቀኛም ሆኖ ለሂፕሆፕና ራፕ የሙዚቃ ስልቶች ጉልህ ሚና ተጫውቷል። በቦክስ ስፖርት ታሪክ የምንግዜም ምርጥ ቦክሰኛ የተባለውም በተለያዩ የቡጢ ፍልሚያዎች ዘመን የማይሽራቸው ገድሎችን በማስመዝገብ ነው። መሐመድ አሊ የቦክስ ጓንቱን ሰቅሎ ስፖርቱን በቃኝ ብሎ ከተሰናበተ ከሦስት ዓመታት በኋላ እኤአ በ1984 ከስፖርቱ ልምድ ጋር በተያያዘ ፓርኪንሰንስ በተባለ በሽታ ተይዞ ነበር።ለሰላሳ ሁለት ዓመታት ከዚህ ህመሙ ጋር ሲታገል ቆይቶ ከአምስት ዓመት በፊት በሰባ አራት ዓመቱ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል።ባለፉት ሳምንታት በአሜሪካ ሚኒያፖሊስ ከተማ ነጭ ፖሊስ ያልታጠቀ ጥቁር አሜሪካዊ አንገትን በጉልበቱ እረግጦ ለሞት ማብቃቱን ተከትሎ የዓለም ሕዝብ ትኩረት ከኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ወደ ሟቹ ጆዮርጅ ፍሎይድ ጉዳይ ዞሯል።ይህ ዘግናኝ ክስተት ከዓመታት በፊት በተመሳሳይ ቁጣን የቀሰቀሰውና በነጭ የፖሊስ አባላት ጭካኔ የሞተውን ኤሪክ ጋርነርን ያስታወሰ ሆኗል። ኤሪክ በወቅቱ በፖሊስ አንገቱ ተቆልፎ ‹‹እባካችሁ መተንፈስ አልቻኩም›› እያለ ነበር የሞተው። የጂዮርጅ ፍሎይድ አሰቃቂ ግድያ ዛሬም ድረስ በሞተባት አገሩ አሜሪካና ሌሎች የዓለማችን ክፍሎች ትልቅ ቁጣን ቀስቅሶ ይገኛል።በታላላቅ ከተሞችም‹‹ የጥቁር ሕይወት ዋጋ አለው›› የሚሉ መፈክሮች በተለያዩ ሰላማዊ ሰልፎች ተፅዕኖ ፈጥረዋል።አዲስ ዘመን ስፖርትም በሳምንታዊ የስፖርት ማሕደር አምዱ ‹‹የጥቁር ሕይወት ዋጋ አለው›› ብሎ ለጥቁሮች እኩልነት ስለታገለው የቦክሱ ዓለም የምንጊዜም ኮከብ መሐመድ አሊ ሕይወት ላይ ትኩረቱን ለማድረግ ወደደ።
መሐመድ አሊ ወደ ቦክስ ሕይወት የመጣበት አጋጣሚ አስገራሚ ነው። የአስራ ሁለት ዓመት ልጅ በነበረበት ወቅት ብስክሌቱ ተሰርቆበት በሊውስቪል ኬንታኪ ለሚገኝ ጆ ማርቲን ለተባለ ፖሊስ አመለከተ።«የሰረቀኝን ባገኘው ልክ አገባው ነበር» ብሎም ምሬቱን ይገልፃል።የቦክስ አሰልጣኝ የነበረው ፖሊስ ትንሹን መሐመድ ራሱን እንዴት ከጥቃት መከላከል መማር እንዳለበት መከረው።የተወሰኑ ስልጠናዎችን ሲወስድ ቆይቶም ብስክሌቱ ከተሰረቀች ከስድስት ሳምንታት በኋላ በሰፈሩ በአንድ አማተር የቦክስ ግጥሚያ ላይ ተሳተፈና በነጥብ አሸናፊ መሆን ቻለ።ይህች አጋጣሚም በዓለም በገነነበት ስፖርት የመሰረት ድንጋይ ነች።
መሐመድ የትውልድ ስሙ ካሴስ ክሌይ ቢሆንም በ19ኛው ክፍለ ዘመን ባሮችን ነፃ ለማውጣት በታገሉ ታላቅ ሰው መታሰቢያነት የወጣለት ስም ነበር።ለመጀመርያ ጊዜ የዓለም ከባድ ሚዛን ቻምፒዮን ከሆነ በኋላ በማግስቱ ስሙን ለመቀየር ወሰነ።የነፃነት ታጋዩን ማልኮለም ኤክስ ከጎኑ አድርጎ በሰጠው መግለጫ «ዘ ኔሽን ኦፍ ኢስላም» የተባለውን ተቋም መቀላቀሉን በማሳወቅ የባርያ ስም ይለው የነበረውን ካሴስ ክሌይ በመቀየር በቀድሞ ስሙ ላለመጠራት ወሰነ። በወቅቱ «ኔሽን ኦፍ ኢስላምን» ይመራ የነበረው ኤልጅያህ መሃመድ እኤአ በ1964 ላይ መሐመድ አሊ የሚለውን ስም ካወጣለት በኋላ እሱን በማፅደቅ እስከ ህይወት ዘመኑ መጨረሻ ተጠራበት።
ለሃያ አንድ ዓመታት በፕሮፌሽናል ቦክሰኛነት በርካታ የቡጢ ፍልሚያዎችን ከአሜሪካ እስከ አፍሪካ እንዲሁም ሌሎች ዓለማት ላይ የተፋለመው መሐመድ አሊ ለሦስት ጊዜ የዓለም ከባድ ሚዛን ቻምፒዮን ሆኗል።ለመጀመርያ ጊዜ የዓለም የከባድ ሚዛን ቻምፒዮን ለመሆን የበቃውም የሃያ ሁለት ዓመት ወጣት እያለ ነው። ዓለም አቀፍ ደረጃ ባላቸው ፕሮፌሽናል የቦክስ ግጥሚያዎች ላይ ስልሳ አንድ ጊዜ ተሳትፎ ሃምሳ ስድስቱን ማሸነፍም ችሏል። ከነዚህ ድሎቹም ሰላሳ ሰባት ያህሉን ተጋጣሚዎቹን በበቃኝ በመዘረር ነው። አስገራሚው ነገር በሰላሳ አንድ ተከታታይ የቦክስ ግጥሚያዎች ሳይሸንፍ ለመጀመርያ ጊዜ የተሸነፈው የክፍለ ዘመኑ ምርጥ ፍልሚያ በተባለው ግጥሚያ በጆ ፍሬዘር ነበር።በፕሮፌሽናል የቦክሰኛነት ዘመኑም ሽንፈትን የቀመሰው አምስት ጊዜ ብቻ ነው። የመጨረሻው ፍልሚያም እኤአ በ1981 ከትሬቨር ቤሪቢክ ጋር በማድረግ ስፖርቱን በቃኝ ብሏል።
አሜሪካ በቬትናም በ1970ዎቹ መጀመርያ ያደረገችውን ጦርነት በመቃወሙ ለሦስት ዓመታት ከፕሮፌሽናል ቦክስ ውድድሮች ታግዶ የቆየው መሐመድ አሊ እገዳው በተጣለበት
ወቅት ከአስር የማያንሱ የዓለም ከባድ ሚዛን ቻምፒዮናዎች ባያመልጡት አሁን ካሉት የበለጠ በርካታ ክብሮችን መጎናፀፍ ይችል ነበር። በዚህም ከሰማንያ ሚሊየን ዶላር በላይ ሀብት ማፍራት ችሏል። ለዚህም ሀብቱ ምንጭ ስፖርቱን ከተሰናበተ ወዲህ ግንባር ቀደም ተዋናዮቹ ስሙንና ምስሉን የሚጠቀሙ ከአርባ በላይ ኩባንያዎች ናቸው። ታሪካዊው ኢትዮጵያዊ አትሌት አበበ ቢቂላ በ1960 የሮም ኦሊምፒክ በባዶ እግሩ ሮጦ ለጥቁር ህዝቦች የመጀመሪያውን የማራቶን የወርቅ ሜዳሊያ ሲያስመዘግብ መሐመድ አሊም በቦክስ የወርቅ ሜዳሊያ አጥልቆ ነበር። ሁለቱ ታሪካዊ የጥቁር ህዝቦች ከዋክብት ፊርማቸውን ተለዋውጠውም ነበር። ይሁንና መሐመድ አሊ ይህን የወርቅ ሜዳልያውን ለአገሩ ከማበርከት ይልቅ በሊውስ ቪል ግዛት በሚገኘው የኦሃዮ ወንዝ ጨምሮታል። ሜዳልያውን ለአሜሪካና ለትውልድ ከተማው ሊውስ ቪል ቢቀዳጅም ለጥቁሮች በርገር የመግዛት መብት ባለመኖሩ ተቃውሞውን ለመግለፅ ነበር ይህን ርምጃ የወሰደው። በ1996 አገሩ አሜሪካ ባስተናገደችው የአትላንታ ኦሊምፒክ ችቦውን እንዲለኩስ ከመደረጉ ባሻገር ወንዝ የጨመረው የወርቅ ሜዳልያ ምትክ ሌላ ሜዳሊያ በአንገቱ ተጠልቆለታል። በ1980 በላስቬጋስ በተካሄደ የቡጢ ፍልሚያ በቴክኒካል የበቃኝ ውጤት ቢሸነፍም መሐመድ ትልቁን ክፍያ ስምንት ሚሊየን ዶላር ያፈሰው በዚያ ውድድር ነው።« ራምብል ኢን ዘ ጃንግል» በተባለውና እስካሁንም ከስፖርት ቤተሰቡ አዕምሮ በማይጠፋው በአፍሪካ ምድር በተካሄደው ፍልሚያ መሐመድ አሊ ምን ጊዜም ይታወሳል። እኤአ በ1974 መሐመድ አሊ በሰላሳ ሁለት ዓመቱ ሽንፈትን አይቶ ከማያውቀው ከሃያ አምስት ዓመቱ ጆርጅ ፎርማን ጋር በኮንጎ ኪንሻሳ የቡጢ ፍልሚያ ገጥሞ ነበር። በወቅቱ የኮንጎ ፕሬዝዳንት የነበሩት ሞቡቱ ሴሴኮ ለሁለቱ ቦክሰኞች በኪንሻሳ ከተማ እንዲጫወቱ በነፍስ ወከፍ አምስት
ሚሊዮን ዶላር ከፍሏቸው ነበር።መሐመድ አሊ በውድድሩ ስምንተኛ ዙር ላይ በዝረራ ቢሸነፍም ከወጣት ተፋላሚው ጋር ያደረገው እልህ አስጨራሽ የቡጢ ፍልሚያ እስካሁንም ከህሊና የሚጠፋ አይደለም።
በ1970 የዶክተር ማርቲን ሉተር ኪንግ መታሰቢያ ሽልማት የተቀበለው መሐመድ አሊ፤ የዓለም አቀፋዊ ወዳጅነት ተምሳሌት ሆኖም ያውቃል። የተባበሩት መንግስታት የሰላም መልዕክተኛ ሆኖም ከ1998 እስከ 2008 በታዳጊ አገራት በመዘዋወር አገልግሏል። በህይወቱ ዙርያ በሚያተኩሩ ጥናታዊና የሙሉ ጊዜ ፊልሞች የሰራ ሲሆን በተለይ ለመጀመርያ ጊዜ በተዘጋጀውና ዘ ግሬተስት በተባለ ፊልም ላይ ተውኗል።የህይወት ታሪኩ ላይ በማተኮር ከተሰሩ ፊልሞች የኦስካር ሽልማት በጥናታዊ ፊልም ዘርፍ ያገኘው «ዌን ዊ ዌር ኪንግስ»ና ዝነኛው የሆሊውድ ተዋናይ ዊል ስሚዝ በመሪ ተዋናይነት የተጫወተው «አሊ» የተባሉት ይጠቀሳሉ።
ታላቁን የደቡብ አፍሪካ ነፃነት ታጋይ ኔልሰን ማንዴላ ከእስር እንደተፈቱ በአካል ተገኝቶ ደስታውን ለመግለፅ መሐመድን የቀደመው የለም። በአካል ካገኛቸው ታላላቅ መሪዎች የእንግሊዟ ንግስት ኤልሳቤት፤ የሮማው ሊቃነ ጳጳስ ፖፕ ጆን ፖል፤ የኩባው መሪ ፊደል ካስትሮ እንዲሁም የኢራቁ ሳዳም ሁሴን ይገኙበታል።አይም ዘ ግሬተስትና ስታንድ ባይ ሚ ከዘፈን ስራዎቹ መካከል የሚጠቀሱት ናቸው።በንግግር ችሎታው፤ በልዩ የግጥም ስንኞቹም ተወዳጅነት ያተረፈ መሐመድ አሊ ነው።«በማይሞት እምነትና ፍቅር ዓለም የተሻለ ዓለም መፍጠር እንደሚቻል አሳይቶናል።ሁሌም ቻምፒዮን ነው»።በማለት የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማን ጨምሮ በርካታ የዓለማችን ተፅዕኖ ፈጣሪና ታላላቅ ሰዎች በቀብር ስነስርዓቱ ላይ ተገኝተው መሐመድን ወደማይመለስበት ሸኝተውታል። እሱ ቢያልፍም ጥቁሮች ዛሬም ድረስ ‹‹የጥቁር ሕይወት ዋጋ አለው›› ብሎ ከዘመናት በፊት ትግሉን የጀመረውን ጀግና ያስቡታል።
አዲስ ዘመን ሰኔ 14/2012
ቦጋለ አበበ