የ“ቀዳማዊ አራጌ ትዝታ!”
ትዝታዬ የሚያርፈው ከሦስት አሠርት ተኩል ዓመታት በፊት በተፈጸመ አንድ ገጠመኝ ላይ ነው። ታሪኩ በአራት ኪሎ አካባቢ ቤተኛ የሆነ የአንድ የአእምሮ ህመምተኛን ይመለከታል። ብዙዎቹ የሚጠሩት “እብዱ” እያሉ ነበር። በግሌ ከህመሙ ውጭ እንደሌሎቹ “እብድ” ብዬ ከምጠራው ይልቅ አስተዋይና ጠቢብ ፈላስፋ ነበር ማለቱ ይቀለኛል። ስሙንና ከየት መጣ የሚለውን ማንም ሰው ለይቶ የሚያውቅ አልነበረም። ብቻ አንድ ሰሞን በአራት ኪሎ አካባቢ መታየት ጀመረ። እንቅስቃሴው በአራት ኪሎና በፒያሳ አካባቢ የተወሰነ ነበር። ለበርካታ ወራት ያህል የእነዚህን ሁለት አካባቢዎች ጎዳናዎችና አደባባዮች ቤቱ አድርጎ ኖሮ በመጨረሻ የት እንደደረሰና ምን እንደነካው ባልታወቀ ሁኔታ ፍጻሜው ተደመደመ።
የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ ይህንን ምስኪን ግለሰብ የወዳጅ ያህል ቀርቦት ነበር። ቀርቦት ነበር ከማለት ይልቅ ተቀራርበው ነበር ማለቱ ይቀላል። ያ ምስኪን ወንድማችን ህመምተኛ ብቻ ሳይሆን ኑሮና መከራ ከጤንነቱ ጋር ያላተሙት ምስኪን ኢትዮጵያዊ ነበር። ኢትዮጵያዊነቱ እንዳለ ሆኖ ኢትዮጵያዊ ክብር እንዳልነበረው ግን ልብ ይሏል። ጸሐፊውና ይህ ሰው ማለዳ ላይ እና በምሳ ሰዓት ይገናኙ የነበረው ቢሮው ይገኝበት ከነበረው የብርሃንና ሰላም ማተሚያ ቤት ደጃፍ ላይ ነበር። አልፎ አልፎም በፒያሳ አካባቢ ይገጣጠሙ ነበር።
ማለዳ ቡቱቱ ልብሱን ለብሶና ከሰል የመሰለ ፀጉሩን አንጨብርሮ በብርሃንና ሰላም ደጃፍ ላይ ቆሞ የቁርሱን ዳረጎት ለማግኘት ጸሐፊውን ይጠብቀው ነበር። አልፎ አልፎም በምሳ ሰዓት ብቅ ይል ነበር። ሣንቲሙን ከተቀበለ በኋላ በአክብሮት አመስግኖ “ወደ እንጉርጉሮ ጉዳዩ” ይመለሳል። ብዙዎች ሲያዩት ደንግጠው ይሸሻሉ።
አንዳንዶች ይህንን ምስኪን ግለሰብ “ሳያብድ ያበደ የመንግሥት ሰላይ” እንደሆነ ሲያሙት ሰምቻለሁ። ሃሜታው ለዚህ ጸሐፊ እውነትነት የሌለው ብቻ ሳይሆን በራሱ ይሄንን ማሰብ የእብዶች ሃሳብ ነበር ማለቱ ይቀላል።
ንግግሩ ቅብጥርጥር ያለ ቢሆንም አልፎ አልፎ ስለ ትምህርት ይጠቅስ ነበር። አንዳንዴም የእንግሊዘኛ ቃላት ወርወር ያደርጋል። ምናልባትም የተማረ ሳይሆን እንደማይቀር ጸሐፊው ይጠረጥር ነበር።
ይህንን ምስኪን የጎዳና ላይ ህመምተኛ (በጊዜው ማኅበረሰቡ እብድ እያለ ይጠራው እንደነበር ከላይ ጠቅሻለሁ) ይህ ጸሐፊ ቀርቦት መወዳጀት ብቻ ሳይሆን “መንትዮች” በሚል ርዕስ በወቅቱ ባሳተመው የልቦለድ መጽሐፍ ውስጥ ማኅበረሰቡ “እብዱ አራጌ” የሚለውን ስም ተውሶ የአንድ ገፀባህርይ ስም በማድረግ የህሊናችን ተምሳሌት አድርጎ እንደሳለው መጽሐፉን ያነበቡ ሰዎች ሳያስታውሱ የሚቀሩ አይመስለኝም።
“አራጌ” በአራት ኪሎ ጎዳናዎችና አደባባዮች ላይ ቆሞ በማዘውተር ከሚያንጎራጉራቸው ዜማዎች መካከል ሦስት ያህሎቹ ግጥሞች የነፍሰ ሄር ጥላሁን ገሠሠ፣ የድምጻዊ አያሌው መስፍንና የዛሬ ስድስት አሠርት ዓመታት ግድም ወደ ኮሪያ ለዘመቱ ዘማቾች የተዜሙ ዜማዎች መሆናቸው የገባኝ ደጋግሞ ሲያዜማቸው ቀረብ ብዬ ካዳመጥኩት በኋላ ነበር። ግጥሞቹን ለራሱ ዐውድ እንደሚስማማ አድርጎ በማሻሻል ያንጎራጉር እንደነበርም ትዝ ይለኛል።
ጥያቄ አቅርቤያለሁ መልስ ብትሰጡኝ፣
ኑሮ ምን ዓይነት ነው ሰዎች አስረዱኝ።
ጥቁር ነው ወይ ጠይም ወይንስ የቀይ ዳማ፣
ዘርዝሮ የሚያስረዳኝ በእውነት ካለማ።
ዜማው እንዳልተቃኘ የሙዚቃ መሳሪያ ስሜትን ቢጎረብጥም አዚያዚያሙ ግን አንጀት ያላውሳል።
አንድ ዕለት ጠዋት በማለዳ “አራጌ” እንደለመደው በዋናው የአራት ኪሎ አደባባይ ላይ ቆሞ ብዙዎች ሰምተው የሰለቻቸውን የወትሮውን ግጥሙን እያንጎራጎረ ሳለ ሁለት እናቶች ከቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን አስቀድሰው ያልፉ ነበር። ሴቶቹ ጠና ያሉ እናቶች ናቸው። የአራት ኪሎ ነዋሪዎች መሆናቸው ያስታውቃል። ከላይ የቀረበውን “የአራጌን” “ጥያቄ አቅርቤያለሁ” እንጉርጉሮ ልክ እንደሰሙ አንዷ ሴት በሣቅ በታጀበ ፌዝ “ኑሯችን ምን እንደሚመስል ሂድና መንግሥቱ ኃይለ ማርያምን ጠይቀው?” በማለት ጮክ በማለት ተናገሩት። ሌላኛዋም ሴት ቀበል አድርገው “እብድና ብርድ ያስቃል በግድ” ብለው ከተረቱ በኋላ “እብድና ዘመናይ የልቡን ይናገራል” በማለት አክለውበት “መንግሥቱ ኃይለ ማርያምን ስለ ኑሯችን ዓይነት ስትጠይቀው እግረ መንገድህን የዘጋብንን የእግዚአብሄር ደጃፍ ክፈትልን!” ብለህ መልዕክት አድርስልን በማለት እየተሳሳቁ “አራጌን” ትተውት እብስ አሉ።” በወቅቱ በፓርላማው በኩል ያለው የቅድስት ሥላሴ መግቢያ በር በደርግ መንግስት ትዕዛዝ ተዘግቶ እንደነበር ይታወሳል።
ይህ ታሪክ ከተፈጸመ የአንድ ጎልማሳ ሰው ዕድሜ ያህል ማስቆጠሩን ከላይ ጠቅሻለሁ። ትዕይነቱና ትዝታው ግን ዛሬም ድረስ ከውስጤ አልደበዘዘም። ታሪኩም ብቻ ሳይሆን “የአራጌ” መልክ ራሱ ከህሊናዬ አልሟሸሸም። የዘመድ ያህል ቅርቤ ነው። ደግሜ እላለሁ የ“አራጌን” ስዕል በሚገባ ለመተዋወቅ የፈለገ ሰው ምንም እንኳ ገበያ ላይ ባይገኝም “መንትዮች” የሚለው መጽሐፌን አንባቢያን ፈልገው እንዲያነቡ ደግሜ እጠቁማለሁ። “አራጌን” ባሰብኩት ቁጥር “የእብደቱ” ምክንያት ምን እንደሆነ ያለማወቅ ብቻ ሳይሆን ለምን የኑሮ ጣጣ ላይ ብቻ አትኩሮ ያንጎራጉር አንደነበረ አይገባኝም። አንድ ያንጎራጎረውን ግጥም ላክል። ሰዎችን ጠይቄ እንደተረዳሁት ይህ የዜማ ግጥም የተደረሰው የኮሪያ ዘማቾችን ለማስታወስ አንደሆነ የሚያወቁ አስረድተውኛል።
አራት ኪሎ ቤቴ ፒያሳ ነው ቤቴ፣
ይብላኝ ለወለዱኝ አናትና አባቴ፤
ርሃብና ጥማት ሆኗል ጎረቤቴ።
አራጌ ስለ እናት ያንጎራጉር የነበረውን የድምጻዊ አያሌው መስፍንን የዜማ ግጥም አስታወሼ ፋይሉን ልዝጋ።
“ወልደሽ ያሳደግሽን እናቴ ናፈቅሽኝ፣
ልጠይቅሽ ልምጣ ይቅርታ አድርጊልኝ።
የምልሽ መሰለሽ ወይ!”
ማጠቃለያው “አራጌ”የወቅቱን ማኅበረሰብ ችግሮች የሄሰ ጥሩ ልበ ብርሃን ነበር። እርሱ አደባባይ መሃል ቆሞ በድፍረት እየጮኸ አቤቱታውን ቢሰሙትም ባይሰሙትም እየለፈለፈ አስታወቀ። ያውም በዜማ ከሽኖ። እርሱ የማኅበረሰቡን ችግር በይፋ ስለተናገረ “እብድ” የሚባል ቅጽል አተረፈ። ለእርሱ ደግሞ ማኅበረሰቡ ራሱ ጨርቁንና ህሊናውን የጣለ እብድ እንደነበር ሳይጠረጥር አልቀረም። “አራጌ” ለማኅበረሰቡ አንደጮኸ “ጥልቅ ይግባ ስምጥ” ሳይታወቅ እንደ ወጣ ቀርቷል። ያ የጮኸለት የኑሮ እንቆቅልሽ ግን ዛሬም ብሶበት አልተቃለለም። ዛሬም ስለ ኑሯችን የሚጮኹልን ብዙ “አራጌዎች”ን ብናገኝ አንጠላም። እንደ እብድ እየጮኹ ለመፍትሄ የሚቆሙልን ወኪሎች ያስፈልጉናል። ከጊዜ ወደ ጊዜ እየናረ የሚሄደው ኑሮ ራሱ ለማሳበድ ከበቂ በላይ አቅም አለው። እንደ “አራጌ” አደባባይ ላይ ቆሜ ባልለፈልፍም በብዕሬ መጮኽ ከጀመርኩ እነሆ ሦስት ዐሠርት ተኩል ዓመታት ተቆጥረዋል። የእኔም ብእር “ከአራጌ” የተዋሰውን ጥያቄ ዛሬም ደግሞ ይጠይቃል።
“የብዕሬ ዳግማዊ አራጌነት”
ሰሞኑን የኑሮን አቀበት ሕዝቡ መውጣት ተስኖት “ኤሎሄ! ኤሎሄ! መንግሥት ሆይ ለምን ተውከን!” እያለ በጓዳው ብቻ ሳይሆን በአደባባይም ጭምር በማንባት ላይ ይገኛል። ገበያውም እንደ ሕዝቡ በግራና በቀኝ በወልጋዳ ፖሊሲዎች ሰበብና በኤክሳይዝ ታክስ ዳፋ ስለተከሰቱት የወቅቱ ችግሮች “በመስቀል ላይ እንደተቸነከረ ላማ ሰበቅታኒ” እያለ በመጮኽ ላይ ነው።
የኤክሳይዝ ቀረጥ ትግበራ ከተጀመረ ጊዜ አንስቶ “እንኳንስ ዘንቦብሽ እንዲያውም ጤዛ ነሽ” እንዲሉ ገበያውን አሳብዶ ጨርቁን አስጥሎታል። ብራችን ጋሽቦ ዋጋው እንደ ቅጠል ቀሏል። “ላምጭው ያስገድዳል!” በሚለው ሞኒተሪያዊ የሀገሪቱ ሕግ መሠረት “ከእጅ ወደ አፍ አላደርስ ያለንን ገንዘብ ከኪሳችን አራግፈን ለመንግሥት ሰብስበን በመስጠት አንድዬ እንዳደረገን ብንሆን ይሻል ይመስለኛል። የብእር እብደት የሚጀምረው እንዲህ እንዲህ እያለ ነው። አባባሉስ ቢሆን የሚመስለው “በመስከረም የሚያብድ ሰኔ ላይ ሱሪውን ከፍ ከፍ ማድረግ ይጀመራል” እያለም አይደል።
በመመሪያ ከተዘረዘሩት የኤክሳይዝ ቀረጥ ታክስ ከተጣለባቸው “የቅንጦትና የምንትስ” ሸቀጦች በተጨማ ሪነት መንግሥት በእለታዊ የፍጆታ ራሽናችን ላይ በስውር ገደብ ጥሎ ከሆነ ቢያሳውቀን ቁርጣችንን አውቀን እንቀመጣለን እንጂ ሳንጃ መዘን ለፍልሚያ ለመጋበዝ ምን አቅም አለን። ሽንኩርትና ጤፍ በደሃው ቤት እንዳይገቡ ይሙት በቃ ከተፈረደባቸው ሰንብቷል። ከተሜውም ሆነ ገጠሬው እየኖረ ያለው በፈጣሪ ተራዳዒነት ነው ቢባል አያስቆጣም።
በግል እምነቴ “የብልፅግና መንግሥታችን” ገበያውን ለማረጋጋት ወይ አቅም አጥቷል ወይ ግዴለሽ ሆኗል። አቅም አጥቶ ከሆነ ለሕጉ ብርታትን እንዲሰጥ ወደ ፈጣሪ እንማጠናለን። ግዴለሽ ሆኖም ከሆነ ልክ እንደ አብዮታዊው የነገሌ ቦረና የንጉሠ ነገሥቱ ጦር አመጸኛ አባላት ሹማምንቱን ወደ አንድ “ግብዣ እንጋብዛለን።”
የነገሌ ቦረናን ጦር ስም ጠቅሻለሁና ጥቂት ማብራሪያ ላክልበት። የንጉሠ ነገሥቱን ሥልጣን አዳክመው ለአብዮታዊ ለውጡ ምክንያት ከሆኑት ሀገራዊ ጉዳዮች መካከል አንዱ የነገሌ ጦር አመፅ እንደሆነ ታሪክ ይነግረናል። ጦሩ በግዳጅ ቀጣናው እንዳለ ለንጉሡ ብሶቱን ያሰማል። ንጉሡም የጦሩ ጥያቄ ምን እንደሆነ አጣርቶው እንዲመጡ በከፍተኛ ወታደራዊ መኮንኖች የሚመራ አንድ ቡድን ወደ ነጌሌ ይልካሉ። ቡድኑ ነጌሌ እንደደረሰ ሠራዊቱ ምንም መተናኮል ሳያደርግ የቁም እስረኛ አድርጓቸው ወደ ሜንስ ቤታቸው (ምግብ ቤት) በማስገባት ለቀናት ያህል ጦሩ የሚበላውን እህል ቅጠል የማይል ምግብ እንዲመገቡና የሚጠጡትን ድፍርስ ውሃ እንዲጎነጩ አቀረቡላቸው። እነዚያ ከፍተኛ ወታደራዊ መኮንኖች በታገቱባቸው ቀናት እውነቱን ከተረዱ በኋላ ነፃ ተለቀው ያዩትን ለንገሡ እንዲያስረዱ ትምህርት ሰጥተው በድርድር ሊለቋቸው ችለዋል።
ዛሬም ከሕዝቡ አናት ላይ ቁጭ ብለው ያልጠራና ያልሰከነ ፖሊሲ በመንደፍና በማፀደቅ እንዲተገበርም ግፊት በማድረግ በየሚዲያው ላይ የሚፎክሩትን ሹማምንት አስቤዛቸውን ከሚገዙባቸው ታላላቅ የምግብ ግሮሰሪዎች ፊታቸውን እንዲመልሱ ተደርጎ የመርካቶን ያበደ ገበያ እንዲያዩ፣ ሰማይ ሰማያት ከተጠጋው የሾላና የመሪ ገበያ እንዲሸምቱ ዘዴ ብንቀይስ አይከፋም። ያኔ የኑሮ ውድነት ማለት ምን ማለት አንደሆነ ይገባቸዋል። እንደ “እብዱ አራጌ” ኑሮ ያወፈፈውን ሕዝብ ኑሮም ሊረዱት ይችላሉ።
ለጨሰው ሀገራዊ የኢኮኖሚ ድቀት መንግሥት አንድ መፍትሔ መስጠት ካልቻለ ነገሮች ሁሉ ወዴት አንደሚያመሩ ለመተንበይ ያዳግታል። ድንጋይ እየተሸከመ የሚውለው ወዝአደር የሚከፈለው የቀን ደመወዝና የሚገዛው የምግብ ሸቀጥ ዋጋ የሰማይና የምድር ያህል ተራርቋል። ብዙ ወላጆች ልጆቻቸውን ትምህርት ቤት መላክ እስከማይችሉ ድረስ ኑሮ አስጨንቋቸዋል። የትራንስፖርቱና የመድኃኒት አቅርቦቱ እንደ ሮኬት መተኮሱን የቪ ኤይት ተጓዥ ሹማምንቶቻችን አልሰሙ ከሆነ እነሆ ኡኡታችን ይድረሳቸው።
በጠራራ ፀሐይ የተጧጧፈው የመኪና ዘረፋና የንብረት ቅሚያ ወዴት እየሄድን እንደሆነ ለመተንበይ ያዳግታል። ስርቆትና ዘረፋዎች ከኢኮኖሚው መላሸቅ ጋር የሚስተዋሉ ማኅበራዊ ነቀርሳዎች መሆናቸውን ለመናገር ከኑሯችን ይልቅ የምሁራን ጥናት አይቀርብም። የ“እብዱን አራጌን” የእብደት ጥያቄ ዛሬም የምንጠይቀው የኑሯችንን አቀበት መቋቋም ተስኖን አቅማችን ስለተሟጠጠ ነው። ወዳጄ “እብዱ አራጌ” ዛሬ በሕይወት ኖሮ እንደ ቀድሟችን ብንገናኝ ኖሮ ይህንን ግጥም እንዲያንጎራጉረው አስጠናው ነበር።
“እባካችሁ ሰዎች ውሰዱኝ ስትሄዱ፣
ኑሮ ዘንድ መድረሻ በየት ነው መንገዱ።
እሩቅ ነወይ በቅርብ መኖሪያ መንደሩ፣
ግድ የለኝም እኔ ውሎ ለማደሩ።
ጥያቄ እስቲ ላቅርብ እንዲያው ለነገሩ፣
በየት በኩል ይሆን የኑሮ ሀገሩ።
ኑሮን ተመልክቼ ከልቤ ላድንቀው፣
በዝርዝር አስረዱኝ መንገዱን ልወቀው።
እንደ “እብዱ አራጌ” ኑሮ ያስመረረው ብእሬ፤ የሕዝቤን ጨኸት እንዲህ እያለ ጮኾ ያስጮኻል። ሰላም ይሁን!!
አዲስ ዘመን ቅዳሜ የካቲት 28/2012
(ጌታቸው በለጠ – ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com