የዚህ ጽሑፍ ርእሰ ጉዳይ ጥምር ትውልድ የነበራቸው የኢትዮጵያ መሪዎች ስለ ኢትዮጵያ ሕዝብ አንድነት የከፈሉት መሥዋዕትነት ለዛሬው ማንነታችን መሠረት ስለሆነ በአድናቆት ልንዘክራቸው የሚገባ መሆኑን ለማሳሰብ፤ ይልቁንም የመንግሥታችን መልክ እንደ ሕዝቦቻችን ሁሉ ኅብረ ብሔር የነበረ መሆኑንና ሕዝቡም ሳይለያይና ሳይነጣጠል አብሮ የኖረ መሆኑን እንድናይ ለማመላከት ነው፡፡
ቅድመ አክሱምና ከአክሱም ዘመን ጀምሮ በኢትዮጵያ አንድነት ታሪክ ሀገራችን ታፍራና ተከብራ ለመኖርና አሁን ከአለንበት ዘመን ላይ ለመድረስ የቻለቺው ነገሥታቱ በሚያወጡት ሕግ፤ደንብና በሕዝቦቿ አስፈጻሚነትና ተጋድሎ ነው፡፡ ይህንኑ በተመለከተ የኢትዮጵያ ታሪክ ተመራማሪ የነበረው ፈረንሳዊው ጆን ዶሪስ ሲጽፍ —
« የኢትዮጵያ ጥንታዊት ከተማ የሆነቺው አክሱም የምትታወቀው ቀዳሚዋ የነገሥታት መዲና (መቀመጫ) በመሆንዋ ወይም የክርስትና እምነት ስለተገኘባት ብቻ ሳይሆን በአክሱም ይዘጋጁ የነበሩት የመንግሥት አዋጆች፤ ትእዛዛትና ሕግጋት ሁሉ በመላ ኢትዮጵያ ለሚኖሩት ሕዝቦች ይተላለፉና ይናኙም ስለነበር ነው » ብሏል፡፡ ስለ መሪዎች ሥራና ስለ ሀገራችን የአንድነት ታሪክ በርካታ ጽሑፎችን ከጻፉ ሰዎች ውስጥ ዶናልድ ሌቪን በበኩሉ“ ግሬተር ኢትዮጵያ” በሚባለው መጽሐፉ (ገጽ401) ላይ
“የኢትዮጵያ ሕዝቦች አንድም የታሪክ ዘመን ተለያይተው አልኖሩም፡፡ እንዲያውም ለሁለት ሺህ ዓመታት ያህል በንግድ፤ በጦርነት፤ በሃይማኖት፤ በባህልና በስደት፤ በጋብቻ፤ በሥራ፤—እርስ በርሳቸው ሲያያዙ የኖሩ ከመሆናቸውም በላይ የአንድነታቸው ዋልታ፤ በሆነው መንግሥታቸው፡ አማካይነት፡የተለያዩ፡ ግንኙነቶችን፡ ከግሪኮች፤ ከዐረቦች፤ ከእንግሊዞች፤ ከፈረንሳዮች፤ ከጣሊያኖች፤ ከፖርቹጋሎች፤—ጋር ከመፍጠራቸውና ስምምነቶችንም ከመፈረማቸው ሌላ ወራሪ ቱርኮችንም ሆነ ሌሎች ጠላቶቻቸውን ይመክቱ የነበሩት በአንድነት ነው” በማለት የአንድነት መሠረት በሚለው ርእስ ሥር ገልጿል፡፡
በኢትዮጵያ ታሪክ ለሀገር አንድነት፤ ሰላምና ሉዓላዊነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ሲያበረክቱ የኖሩና ጥምር ትውልድ የነበራቸው መሪዎችና የጥበብ ሰዎችም ከእገሌ ልወለድ ብለው ሳያስቡ ነው ወደ ምድር የመጡት፡፡ ጥምር ትውልድ ሲባል የተለያየ ቋንቋ ተናጋሪ ከሆኑ ኢትጵያውያን እናትና አባት በአጋጣሚ የተወለዱ ሰዎች ለማለት ነው፡፡ ፕሮፌሰር ፍቅሬ ቶሎሳ የኦሮሞና የአማራ እውነተኛው የዘር ምንጭ 2008 በሚለው መጽሐፉ እንደሚያትተው ብዙ ሰዎች የኢትዮጵያን መንግሥት ሲመሩ የኖሩት ነገሥታት ከሰሎሞናዊውና አግዓዝያን ተብለው ከሚታወቁና ከቀዳማዊ ምኒልክ ጋር ከእስራኤል ወደ ኢትዮጵያ የመጡ የነገደ ይሁዳና የነገደ ዛጉየ ዘሮች እንጂ ከአንድ ወገን ብቻ የመጡ ማለት አማርኛ ተናጋሪ ከሆነው ማኅበረሰብ የተወለዱ የአማራ ነገሥታት አይደለም፡፡ ይህም ማለት የአማራ ገዥ መደብ የሚባል አልነበረም ማለት ነው፡፡ ይልቁንም በታሪክ አጋጣሚ የይሁዳ ነገዶች አልፎ አልፎ ከአማራ ወይንም ከትግሬ፤ ከኦሮሞ ወይንም ከሌላው ሕዝብ —ጋር በመጋባት የወለዱዋቸው ልጆች (ጥምር ትውልድ የነበራቸው ዜጎች ) ሀገር የመሩበት አጋጣሚ ብዙ ነው፡፡በተለይ ከአማሮች ይልቅ ጥምር ትውልድ ያላቸው ኦሮሞዎች ማለት ከሰሎሞናዊው ሥርዎ መንግሥት ነገሥታትና መሳፍንት ጋር በመጋባት ከ16ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ እስከ 18ኛውና የዓፄ ኃይለ ሥላሴ መንግሥት እስከወደቀበትና እስከ አሁኑም ድረስ ነገደ ይሁዳን በማዳከም ሀገሪቱን ሲመሩ ቆይተዋል፡፡
ይልቁንም በተለያዩ የታሪክ ማስረጃዎች ላይ ተጽፎ እንደምናገኘው ከጥንት ዘመን ጀምሮ እስከ አሁኑ ድረስ በኢትዮጵያ መንግሥት መዋቅር ውስጥ የሁሉም ኢትዮጵያዊ ዘር የነበረበትና ያለበት መሆኑ ተመልክቷል፡፡ በተለይ ጥምር ትውልድ ያላቸውና ከተለያየ ዘር የፈለቁ መሪዎች ለሀገር አንድነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ሲያደርጉ ኖረዋል፡፡ በዚህ ጽሑፍ ጥምር ትውልድ ከነበራቸውና በኢትዮጵያ ፖለቲካ ከፍተኛ ሚና ከተጫወቱት መሪዎች ጥቂቶችን ብቻ እንዳስሳለን፡፡
በዳሰሳው ጥምር ትውልድ ከነበራቸው ከጥንት ነገሥታት ውስጥ በአክሱም ዘመነ መንግሥት የነበሩት አብርሃና አጽብሓ ይጠቀሳሉ፡፡ ወንድማማቾቹ ነገሥታት አብርሃና አጽብሓ በዘመነ መንግሥታቸው ማለት በ4ኛው ክፍለ ዘመን የክርስትና ሃይማኖት በኢትዮጵያ እንዲስፋፋና የመንግሥታቸውም ሃይማኖት ሆኖ እንዲታወጅ ያደረጉ፤ በርካታ አብያተ ክርስቲያናትን በሀገሪቱ ውስጥ ያሳነፁና ያስፋፉ፤ ያገሪቱንም ሰላምና አንድነት በደግነት ያስከበሩ በመሆናቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅዱስነት ክብር ከመስጠቷም ባሻገር በስማቸው ጽላት እንዲቀረጽላቸው አድርጋለች፡፡ ዛሬ በምሥራቅ ትግራይ ዞን ሐውዜን አካባቢ በስማቸው የሚጠራው የአብርሃና አጽብሓ ቤተ ክርስቲያን መገኘቱም ከዚሁ የተነሣ ነው፡፡
ወንድማማቾቹና መንትዮቹ ነገሥታት አብርሃና አጽብሓ ጥምር ትውልድ ያላቸው ቅዱሳን አባቶች ናቸው፡፡ አያታቸው ከቀዳማዊ ምኒልክ ጋር ተያይዞ ከመጣው ከአግዓዚው (ሰሎሞናዊው) ሥርዎ መንግሥት የተወለደው፤ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ሆኖ የነገሠውና ዘግዱር ይባል የነበረው ዓፄ ዣን ሰገድ ነው፡፡ ዓፄ ዣን ሰገድ የሚወድዳት ሚስቱ በሞተችበት ጊዜ ባለሟሎቹ ብቸኝነት እንዳያጠቃውና ኀዘኑንም እንዲረሳ በማሰብ እጅግ በጣም የተዋበች ፤ «ማርብላ »የተባለችና በዘርዋ አማራ የሆነች ሴት ከአንዱ ገበሬ ነጥቀው ያመጡለታል፡፡ ንጉሠ ነገሥቱም ያለፈ ታሪኳን ስለማያውቅ ሚስቱ አደረጋትና «ንግሥት ብርሃን ለዓለም » ብሎ አነገሣት፡፡ ይህችም ሴት በኋላ ዓፄ ሰይፈ አርዕድ ተብሎ የነገሠውንና አልአሜዳ የተሰኘውን ወንድ ልጅ ወለደችለት፡፡
ይሁንና ማርብላ የቀድሞ ባለቤቷን ድኃውን ገበሬ እንጂ አዲሱን ባልዋን አትወድደውም ነበር፡፡ ዓፄ ዣን ሰገድ ማርብላ ተገድዳ ወደ እርሱ መምጣቷን ሲረዳ ይቅርታ ጠይቆ ወደ መጀመሪያ ባሏ መለሳት፡፡ በቤተ መንግሥቱ ውስጥም ከነባሉዋ ተቀምጣ ልጃቸውን አልአሜዳን እንድታሳድግ ፈቀደላትና መልካሙን ነገር ሁሉ አደረገላት፡፡ አልአሜዳም ባደገ ጊዜ በአባቷ በኩል ኦሮሞ፤ በእናቷ በከፊል ደግሞ አማራ የሆነችና ኦሃየ ተብላ የምትጠራ ሴት አገባና «ንግሥት አብርሂት ዘኢትዮጵያ » አሰኝቶ አነገሣት፡፡ የኦሃየ አባት የኦሮሞ ተወላጅ ከሆነውና ከታላቁ መጋል የሚወለደው የአዘቦው ንጉሥ ከሀለ ነበር፡፡ መንታ ወንድ ልጆችንም ወለደችለት፡፡ ስማቸውም አብርሃና አጽብሓ ተባለ፡፡ ልጆቹ ገና ለአቅመ ንግሥና ሳይደርሱም አባታቸው ዓፄ ሰይፈ አርዕድ የተሰኘው አልአሜዳ ዐረፈ፡፡ በዚህም የተነሣ እናታቸው «ንግሥት አብርሂት (ኦሃየ) ኢትዮጵያን ለ12 ዓመታት አስተዳድራለች፡፡ ንግሥት አብርሂት ሃይማኖት አክባሪ ጻድቅ ሴት ነበረች፡፡ የክርስትና እምነት የመንግሥት ሃይማኖት ሆኖ እንዲታወጅ ልጆቿን አብርሃንና አጽብሓን ያነሣሣችም እርሷው ናት፡፡ በመሆኑም ዓፄዎቹ አብርሃና አጽብሓ፤ አባታቸው ዓፄ ሰይፈ አርዕድ የተባለው አልአሜዳ፤ እናታቸው ንግሥት አብርሂት የአማራ ደም ቢኖራቸውም የአማራ መንግሥት ግን አልመሠረቱም (ፍቅሬ ቶሎሳ 2008፤173)፡፡
መሪዎቹ በአንድም ሆነ በሌላ የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረ ሰቦች ልጆች ናቸው፡፡ ነፍሱን ይማረውና ታዋቂው ገጣሚ ሰሎሞን ዴሬሳ «በአያቴና በቅድመ አያቴ በር በኩል ማን እንዳለፈ ስለማላውቅ እኔ ንጹሕ ኦሮሞ፤ ንጹሕ ትግሬ፤ ንጹሕ አማራ፤ ወላይታ፤ ጉራጌ፤ ሶማሌ፤ ዐፋር ነኝ ብየ አልናገርም» ይል የነበረው የኢትዮጵያ ሕዝብ በዘሩ የተደበላለቀና የተለያየ ቋንቋ ቢናገርም አንድነቱ ከብረት የፀና እንደሆነ ለማስረዳት ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስም «ኢትዮጵያዊ መልኩን፤ ነብር ዥንጉርጉርነቱን አይለውጥም» ይለናል፡፡
በኢትዮጵያ ታሪክ ጥምር ትውልድ ከነበራቸውና በሰሎሞናዊው ሥርዎ መንግሥት ውስጥ ገብተው ሀገሪቱን ከመሩና ታሪክ ከቀየሩ በርካታ ሰዎች ውስጥ በእናቱ ኦሮሞ፤ በአባቱ ከነገደ ይሁዳና ከንግሥተ ሳባ ዘር የሆነውና የኢትዮጵያን መንግሥት ዙፋን ከላስታው አገው ከዛግዌ ሥርዎ መንግሥት ከነአኵቶ ለአብ እጅ ወስዶ ወደ ሰሎሞናዊው ሥርዎ መንግሥት ወደ ሸዋ ያሸጋገረው በክርስትና ስሙ ተስፋ ኢየሱስ፤በመንግሥት ስሙ ይኵኖ አምላክ (አምላክ ይሁነው፤ ይርዳው ማለት ነው) የተባለው ተጠቃሽ ሲሆን አባቱ እድም አሰግድ ይይኵኖ አምላክን (ተስፋ ኢየሱስን) የወለደው ሐዊ ጊፍቲ ከተባለች የቦረና ኦሮሞ ነው (መሪ ራስ አማን 2009፤141)፡፡
ቀደም ሲል ዮዲት ጉዲት የምትባል የጌዴዎን ልጅ በአክሱም የነበረውን የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት በገለበጠች ጊዜ የቀዳማዊ ምኒልክን ዘሮች ማለት መሳፍንቱንና ካህናቱን ገደለች፡፡ በዚያ ወቀት አንበሳ ውድም የተባለው ንጉሥ በዮዲት ጉዲት ድል ስለሆነ ከአክሱም ወደ ሸዋ ሸሽቶ የዛሬው መራቤቴ በተባለው ሀገር ተቀመጠ፡፡ እዚያም የሰሎሞን ዘር በመሆኑ ከነ ልጅ ልጆቹ ተከብሮና ተፈርቶ ይኖር ነበር፡፡ አንበሳ ውድም ሸዋ ውስጥ በዶባ ሀገር ሳለ ሞተ፡፡ ልጁም ድልነዓድ በአምባ ግሸ ሲኖር የልጅ ልጅ አይቶና ሸምግሎ ሞተ፡፡ በሕይወቱ ሳለ አግባ ጽዮንን ወለደ፡፡ አግባ ጽዮን ጽንፈ አርእድን፤ ጽንፈ አርእድ ነጋሽ ዛሬን፤ ነጋሽ ዛሬ አስፍሓን፤ አስፍሓ ያዕቆብን ፤ያዕቆብ ባሕር አሰግድን፤ባሕር አሰግድ እድም አሰግድን፤ እድም አሰግድ በበኩሉ ከላይ የተጠቀሰቺውን ኦሮሞ ሴት የአዛዥ ጫላን ልጅ ሐዊ ጊፍቲ መንደያን አግብቶ ተስፋ ኢየሱስ የተባለውን ይኵኖ አምላክን ወልዷል (ዝኒ ከማሁ 2009)፡፡
እነዚህ ሰባት ትውልድ ያስቆጠሩት የነገሥታት ዘሮች በአማራ አገር በሽሽግ ሲነግሡና መንግሥታቸውን ከዮዲትም ሆነ ከዛጉየ ነገሥታት ለመመለስ ሠራዊት ሲያደራጁ ቢቆዩም በለስ ስላልቀናቸውና የእግዚአብሔርም ፈቃድ ስለአልተጨመረበት ለ300 ዓመታት ስምንት ትውልድ ከሞላቸው የልጅ ልጆቻቸው—ጋር በከንቱ ታከቱ፡፡ መቼም አባት ለልጁ ተጨናዊ ነውና እድም አሰግድ የወለደው ልጁ ተስፋ ኢየሱስ ቀበጥባጣና ችኩል ስለሆነ የሰሎሞን ዘርም በመሆኑ ሰው ሊገድልብኝ ይችላል ብሎ ስለሠጋ ወደ ሐይቅ አስጢፋኖስ ገዳም ወስዶ ለመምህር አባ ኢየሱስ ሞዓ አደራ ያስተምሩልኝ ብሎ ሰጣቸው፡፡ ተስፋ ኢየሱስ በሐይቅ እስጢፋኖስ ገዳም የቤተ ክርስቲያንንና የመንግሥትን ሥርዓት እየተማረ ባለበት ሰዓት አቡነ ተክለ ሃይማኖት አባ ኢየሱስ ሞዓን ለመጠየቅ ከሸዋ ወደ ሐይቅ እስጢፋኖስ በሄዱበት ሰዓት የሰሎሞናዊው ሥርዎ መንግሥት ወራሽ የሆነውን ተስፋ ኢየሱስን ስለአገኙት በጣም ደስ አላቸው፡፡
የሰሎሞንንም መንግሥት በዚህ ልጅ አማካይነት ላስታ ላይ ከነገሡት ከዛጉየ ነገሥታት እጅ በዘዴ አውጥተው ወደ ሽዋ ለማሸጋገር ቁርጥ ሐሳብ አደረባቸው፡፡ ተስፋ ኢየሱስም ትምህርቱን አቋርጦና ተራ ሰው መስሎ ወደ ላስታ በመሄድ እልመክኑን ለተባለው ለንጉሥ ነአኩቶ ለአብ ሎሌነት አደረ፡፡ ለንጉሡ ዋና ሰይፍ ያዥና ጋሻ ጃግሬው ሆነ፡፡ የቤተ መንግሥቱንም ሥርዓት እዚያው ሆኖ አጥብቆ አጠና፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖትም ወደ ላስታ ቤተ መድኃኔ ዓለም እንደሄዱ ስለ አውራ ዶሮ ጩኸትና ታርዶ ጭንቅላቱን (ራሱን) የበላ ሰው የዳዊትን ዙፋን እንዴት ሊወርስ እንደሚችል በተነገረውና በተተረጎመው ትንቢት መሠረት መንግሥት ከላስታ ከነአኵቶ ለአብ እጅ አፈትልካና በ1262 ዓ ም በይኵኖ አምላክ እጅ ገብታ ወደ ሸዋ ኮብልላለች፡፡ ሰሎሞናዊቱ መንግሥትም እስከ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመን ድረስ ቆይታ ሥርዓተ ቀብሯና ግብዓተ መሬቷ በ1967 ዓ ም ተፈጽሟል፡፡
ጥምር ትውልድ ከአላቸውና ታላላቅ ታሪክ ከፈጸሙ ሰዎች ውስጥ ሌላው ተጠቃሽ ቋረኛው ካሳ (ዓፄ ቴዎድሮስ ) ናቸው፡፡ በአባታቸው በዓፄ ፋሲል በኩል ከሰሎሞን ዘር የሚጋሩትና በእናታቸው ቅማንት የሆኑት ዓፄ ቴዎድሮስ በዘመነ መሳፍንት የተከፋፈለቺውን ሀገራችንን አንድ ለማድረግ ሲታክቱ የኖሩና ከወራሪው የእንግሊዝ ጦር ጋር ገጥመው ለሀገራቸው ክብር ሲሉ መቅደላ ላይ ራሳቸውን የሠው፤ በጀግንነታቸው ለኢትዮጵያዊ ትውልድ ሁሉ አርአያና የአንድነት ተምሳሌት የሆኑ፤ በጭካኔያቸውና በጀግንነታቸው ታሪክ ለዘለዓለም ሲያስታውሳቸው የሚኖሩ ታላቅ ሰው ናቸው፡፡ ልክ እንደ ዓጼ ቴዎድሮስ ሁሉ ለሀገራቸው አንድነት፤ ክብርና ሉዓላዊነት ሲሉ ከውጭ ወራሪዎች (መሐዲስቶች) ጋር ገጥመው ደማቸውን መተማ ላይ ያፈሰሱት ጀግናው ዓፄ ዮሐንስ ዐራተኛ ሳልሣዊ ትውልድ (የሰሎሞናዊነት፤ የትግራዊነትና የአማራነት ዝርያ) ያላቸው ሲሆኑ ልጃቸውን አርአያ ዮሐንስን (የራስ መንገሻን አባት ) የወለዷቸው የባላባት ልጅ ከሆነቺው ከአንዲት የደንከል ወይዘሮ ነው (ተክለ ጻድቅ1982፤42)፡፡
( አቶ ሰይፉ ማኅፈረ የቃል ማስረጃ 1972 መቀሌ መኖሪያ ቤታቸው)
በተመሳሳይ በአባታቸው በንጉሥ ኃይለ መለኮት ሣህለ ሥላሴ በኩል ከሰሎሞናዊው ሥርዎ መንግሥት (ከነገደ ይሁዳ—አግዓዝያን)፤ በእናታቸው ደግሞ በወይዘሮ እጅጋሁ ለማ አዲያሞ በኩል ከላስታ አገው የተወለዱት ዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ በታላላቅ የኦሮሞ ጀግኖች አማካይነት የኢትዮጵያን ዳር ድንበርና ወሰን ፤ ግዛት ያስፋፉ፤ መላ ሕዝባቸውን በፍቅር
አስተባብረው ጣልያንን ዐድዋ ላይ ድባቅ የመቱና የሀገራችንን ነጻነት ያስከበሩ፤ ዘመናዊ የሥልጣኔ ጮራን የፈነጠቁ፤ የአካባቢ የጦር አበጋዞችንና የባላባቶችን የውስጥ አስተዳደር በምክርና በዘዴ፤ በጦርነትም ጭምር ያፀኑ፤ ከደግነታቸውም የተነሣ «እምየ ምኒልክ » እስከ መባል የደረሱና የኢትዮጵያን ዋና ከተማ አዲስ አበባን የመሠረቱ ታላቅና ጥበበኛ መሪ ናቸው፡፡ የኦሮሞና የአማራ ዝርያ ያላቸው ባለቤታቸው እቴጌ ጣይቱ ብጡልም እንዲሁ በሀገር አመራርና በዐድዋ ጦርነት ባሳዩት ብልኅነትና ጀግንነት የሚታወቁ ሳተናና የዓለም ሴቶች ሁሉ ሞዴል ናቸው፡፡ ፍቅሬ ቶሎሳ እንደጻፈው ዓፄ ምኒልክ እንደነ ቢስማርክ፤ እንደነ ናፖሊዮን ቦናፓርት ፤እንደ ቀዳማዊ ጴጥሮስና እንደ ታላቁ እስክንድር የሀገርን አንድነት ለማስጠበቅና ግዛት ለማስፋት በአደረጉት ጥረት ዛሬ ጭምር እንደምናየው የሰው ልጅ እንደሚሞት የታወቀ ቢሆንም ዓፄ ምኒልክ ጡት ቆረጡ የሚል ትክክለኛ ማስረጃ ባልተገኘበት በዚህ የይቅርታና የሰላም ዘመን የበቀል ሐውልት ማቆም ተገቢ አይደለም፡፡ ይልቁንም ልክ እንደ ቻይናውያን ሐውልት በየቦታው ማቆም የነበረብንስ ሀገሪቱን ዳር እስከ ዳር አንድ ለአደረጉትና ለነጻነቷ እንደሻማ ለነደዱት ጀግኖቿ ለነ ዓፄ ቴዎድሮስ ለነ ዓፄ ዮሐንስ፤ ለነ ራስ ጎበና ዳጨ፤ ለነ ፊታውራሪ ገቤሁ ጎራ ፤ ለነ አባተ ቡዋ ያለው፤ ለነ ሀብተ ጊዮርጊስ ዲነግዴ፤ ለነ ባልቻ አባ ነፍሶ፤ ለነ በላይ ዘለቀ፤ ለነ አባ ጅፋር፤ ለነ ራስ አሉላ፤ ለነ ንጉሥ ሚካኤል፤ ለነ ንጉሥ ጦና፤ ለነ ንጉሥ ተክለ ሃይማኖት፤ ለነ ራስ ወሌ ብጡልና አሉላ ብጡልና ለሌሎችም ነበር፡፡
በዚሁ ትውፊት ከሚጠቀሱትና ለሀገር አንድነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ከአበረከቱት መሪዎች ውስጥ በኢትዮጵያ የሰሎሞን ሥርዎ መንግሥት መጨረሻ የሆኑትና በአመራር ድክመታቸው በማይጨው ጦርነት በሕዝብ ላይ በወረደው የኢጣሊያ ግፍ የሚወቀሱት፤ በጦርነቱ ተሸንፈው ወደ ውጭ የተሰደዱትና በአምስቱ የዐርበኝነትና የመከራ ዘመን የኢትዮጵያ ዐርበኞች በዱር በገደሉ ተሰልፈው ጣልያንን በሚወጉበት ሰዓት የእንግሊዝን የቃል ኪዳን ጦር ይዘው በመመለስና ሰሎሞናዊ መንግሥታቸውን በማፅናት ሀገራችንን ለብዙ ዘመናት የመሩት፤ ኤርትራን ከእናት ሀገሯ ኢትዮጵያ ጋር በጥበብ ያዋሐዱት፤ የአፍካ አንድነት ድርጅትን የመሠረቱትና በወሎ ድርቅ ምክንያት በሕዝባዊ ዓመፅ ከሥልጣናቸው የተወገዱት የቀድሞው ንጉሥ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ተጠቃሽ ናቸው፡፡ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ በአባታቸው ትግራዊና ሰሎሞናዊ ሲሆኑ በእናታቸው ደግሞ የወረሂመኑ ኦሮሞና ሥልጤ-ጉራጌ ናቸው፡፡ በእምነት ደረጃም ቅድመ አያታቸው ሼህ ሑሴን ጂብሪል (የሴት አያታቸው የወይዘሮ ወለተ ጊዮርጊስ አባት) እና የእናታቸው የወይዘሮ የሺእመቤት አባት አያታቸው ዐሊ ጋምጮ የእስልምና እምነት ተከታዮች ነበሩ፡፡ እናም ራስ ተፈሪ መኮንን ልጅ ኢያሱን ከሥልጣን ለማውረድ በሸዋ በተደረገው ዐድማ ዋነኛ ተዋናይ ሆነው የታዩት አስልመዋል በሚልና በእስልምና እምነት በመጠርጠር ጭምር፡ ሲሆን፡ የራሳቸውን፡ እስላማዊ፡ዘሮች፡ ግንይደብቁ፡ ነበር (ዝኒ፡ ከማሁፍቅሬ፡2008፤241)፡፡
በዚህ ዓይነት በሰሎሞናዊውም ሆነ በዛጉየ፤ በጎንደር ዘመነ መንግሥት ( በተለይም በዘመነ መሳፍንት ኢትዮጵያን ሲመሩ የነበሩ የሌላ አካባቢና የየጁ ኦሮሞዎች (ጥምር ትውልድ የነበራቸው) መንግሥታዊ ቋንቋቸውም ልክ እንደ ዓፄ ዮሐንስ አማርኛ የነበረ መሆኑን ፍቅሬ ቶሎሳ ከላይ በተጠቀሰው መጽሐፉና ኢትዮጵያን ሪቪው በተሰኘ ጆርናል ( 1992፤28 ) ላይ ጠቅሶታል፡፡
ማጣቀሻዎች
-መሪ ራስ አማን በላይ ( 2009 ) የጥንታዊቷ ኢትዮጵያ ትንሣኤ ታሪክ ኒባደን ፒኤል ሲ አዲስ አበባ፤
-ተክለ ጻድቅ መኩሪያ (1951) የኢትዮጵያ ታሪክ ኑቢያ-አክሱም-ዛጉየ አዲስ አበባ፤
-ተክለ ጻድቅ መኩሪያ (1953) የኢትዮጵያ ታሪክ ከዓፄ ልብነ ድንግል እስከ ዓፄ ቴዎድሮስ አዲስ አበባ፤
-ተክለ ጻድቅ መኩሪያ (1982) ዓፄ ዮሐንስና የኢትዮጵያ አንድነት ኩራዝ አሳታሚ ድርጅት አዲስ አበባ፤
-አሰፋ እንደሻው ( 2004) አክሱም ኢትዮጵያ የሕዝቦች ስብጥርና የአገዛዞች አወቃቀር አጭር ታሪክ ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ቤት አዲስ አበባ፤
-አንደርዜይ ባርትኒስኪና ዮዓና ማንቴል ኒችኮ ትርጉም በዓለማየሁ አበበ (2009) የኢትዮጵያ ታሪክ ከመጀመሪያው እስከ አሁኑ ዘመን አዲስ አበባ፤
-ፍቅሬ ቶሎሳ ጂግሳ (2008 ) የኦሮሞና የአማራ እውነተኛ የዘር ምንጭ ኒባዳን ፒኤል ሲ አዲስ አበባ፤
– Levine, D.(1972) Greater Ethiopia -Sven Rubenson ( 1976) The Survivale of Ethiopian Independence
Ethiopian Review October
1882 p,28
ዘመን መፅሄት ህዳር 2011
ታደለ ገድሌ ጸጋየ ዶ/ር