አዲስ አበባ የኢትዮጵያ መዲና ከሆነች ከመቶ ዓመት በላይ አስቆጠረች፡፡ በዚህ ዕድሜዋ ከአራቱም አቅጣጫዎች የሚጎርፉት ዜጎች ተጋብተው፣ ጎጆ ቀልሰው ንብረት አፍርተው በማኅበራዊ ተቋሞቻቸው ተሣሥረው ይኖሩባታል፡፡ የዚህችን ከተማ ዕድሜና ታሪክ ከዳግማዊ ምኒልክ ጋር አያይዘው የሚናገሩ የመኖራቸውን ያህል በአንጻሩም በቅድመ ዘመናዊት ኢትዮጵያ የነበሩ ታሪኮች ሊዘነጉ አይገባም ሲሉ የሚከራከሩት ደግሞ አዲስ አበባ በስምና በገጽታ ብትለያይም የተለያዩ ገዢዎች የተፈራረቁባትና ልዩ ልዩ ሕዝቦች በየዘመናቱ ታሪክ እየሠሩባት ከሺህ ዓመታት በላይ ማሳለፏን ጠቅሰው ይሞግታሉ፡፡
የታሪኳና የዕድሜዋ ጉዳይ አከራካሪ የመሆኑ ምክንያት ከወቅታዊ የፖለቲካ ትኩሳቶች የሚነሳ ነው፡፡ በከተማዋ ላይ ለሚነሳው የባለቤትነት ጥያቄ ተሟጋች ወገኖች የራሳቸው እምነት አሸናፊ እንዲሆን ሲጥሩ እንደ መከራከሪያ ግብአት የሚጠቀሙት ታሪክን ነው፡፡ የፖለቲካ ሳይንቲስቶች ደጋግመው እንደሚያረጋገጡት ታሪክ ያለፈን ብቻ ከመተረክ አልፎ ከዛሬ ጋር በመዛመድ ወቅታዊውን ፖለቲካ የሚወስን ትርክት የመፍጠር ሚና አለው፡፡ «ይህም ስለሆነ ታሪክ በመተረክ ውስጥ ታሪክ መሥራት ተደብቆ ይገኛል» ይላሉ ሰሚር ዩሱፍ የተባሉ የታሪክ ምሁር፡፡
ሰሚር ዩሱፍ ታሪክ ያለፈውን ዘመን በዛሬ ቋንቋ፣ መመልከቻ ስነ ዘዴና ፖለቲካዊ ቅኝት የሚጻፍ መሆኑን ከግምት አስገብተው ዘመናዊ የታሪክ ጸሐፊዎች «ዘመናዊ» እንዲሁም «ሳይንሳዊ» በማለት የሚያሞካሹትን የራሳቸውን ትረካ እየበለቱ ክፍተቶቹን ያሳያሉ፡፡ የምሁሩ ተግባር የአንድ አገር ዋና ታሪክ ተብሎ የሚተረከው ሁሉ ሊታወስ የቻለው ብቻ ሳይሆን ሊታወስ የተፈለገው ተመርጦ እየቀረበ ስለሆነ የአንድን ወገን ትረካ ብቻ ከፍ አድርጎ እውነቱ ይህ ብቻ ነው ማለት አደጋ እንደሚያስከትል የባህሩ ዘውዴን ዘመናዊ የታሪክ ሥራ በመፈልቀቅ (Deconstruction) ሥነ ስልት አብነት ነስተው ያሳያሉ፡፡
የአዲስ አበባም ታሪክ ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡ የዋና ከተማ ባለቤትነት ጉዳይ በተለይ ፌዴራላዊ መዋቅር ባላቸው አገሮች ለሙግት የሚጋለጥ ጉዳይ ቢሆንም አዲስ አበባን በተመለከተ ግን የተለያዩ ወገኖች የሚያቀርቡት አስተያየት ታሪክን የተንተራሰና ከተማዋን የራስ ለማድረግ ከመፈለግ የሚመነጭ ነው፡፡
ትረካዎቹ በአስተማማኝ ማስረጃ ተደግፈው የታሪክነት ማዕረግ የተጎናጸፉ ብቻም ሳይሆኑ የቅድመ ታሪክ እውነታዎችንም የሚዳስሱ አፈ ታሪኮችም ናቸው፡፡ ሙግቱን የሚያቀርቡ ሰዎች አፈ ታሪኮቹ ታሪካዊ ሐቅ ናቸው ከሚሉ ክርክሮች ጀምሮ ታሪካዊ መሆናቸው በበቂ ማስረጃ ተደግፎ ባይረጋገጥ እንኳ ሕዝቡ እስካመነበት ድረስ ከታሪክ ያልተናነሠ ዛሬን የመቃኘት አቅም አላቸው እስከሚሉት ድረስ የተለያዩ ጽንፎች ናቸው፡፡
የሁሉንም ወገኖች ክርክር እኩል ለማስተናገድ እስከቻልን ድረስ አዲስ አበባ የተለያዩ ገጽታዎችን በተለያዩ ዘመናት እየተላበሰች ሁሉን ስታስተናግድ የኖረች የወል ቦታ ሆና እናገኛታለን፡፡ «የእኛ፣ የእኛ» የሚያሰኘው አማላይ ገጽታዋም ከተሸከመችው የወል ታሪክና የጋራ አሻራዋ የሚመነጭ ነው፡፡ አንድን ነገር የራስ የማድረግ ፉክክር በወንድማማቾች መካከል የሚፈጠር እንጂ በባእዳን መካከል የሚከሰት አይደለም፡፡ የራስ እንዲሆን የሚጓጉለት ነገርም የራስ ወይም የቅድም አያቶች አሻራ ያረፈበት ውርስ መሆኑ ሲሰማን የሚፈጠር ሥነ ልቡናዊ ዝንባሌ ነው፡፡ ይህንን አብሮ ከመኖር የሚመነጭን ፍላጎት የሚያስጎበኘንን ታሪክን መሠረት ያደረገውን ትርክት በአዲስ አበባ ውስጥ እንጎብኝ፡፡
የአዲስ አበባ አሻራ በጥንታዊት ኢትዮጵያ
በአክሱም ዘመነ መንግሥት ጎልተው ከሚጠቀሱ ነገሥት መካከል ወንድማማቾቹ አብርሃ አጽብሃ የዘመነ አክሱም ምልክቶች ተደርገው ይወሰዳሉ፡፡ ጥንታዊት አዲስ አበባ በዛሬ ስሟ ሳትጠራ በፊት በጥንታዊት ኢትዮጵያ ውስጥ የማን ነበረች? የሚል ጥያቄ ቢነሳ «የአክሱም መንግሥት» እና በአክሱም መንግሥት ሥር ይተዳደሩ የነበሩ ሕዝቦች መሆኗ ሊያወዛግብ አይችልም፡፡ የዚህ ሃሳብ አራማጅ ከሆኑ አጥኚዎች መካከል በላይ ግደይና ተመሳሳይ አሳብ አራማጅ ጸሐፊዎች ምስክር የሚያደርጉት የአክሱም ኢምፓየር የንግድ መሥመሩን በደቡብ አቅጣጫ እስከ ሞቃዲሾ የዘረጋ መሆኑ ነው፡፡ በርግጥም እስከዚያ የደረሰ የንግድ መሥመር አዲስ አበባን ዘሏታል ብሎ ማሰብ አይቻልም፡፡
ወንድማማቾቹ ነገሥታት ለአስተዳደር እንዲመቻቸው ግዛት ተከፋፍለው ነበር የሚሉት እነዚህ ወገኖች የአጽብሃ መናገሻው ኤረር አካባቢ እንደነበረና ቤተ መንግሥቱን በተራራው ተክሎ እንደነበር ይገልጻሉ፡፡ ይህ ተረክ የአዲስ አበባን ከተማነት ብቻ ሳይሆን መናገሻነትም ጥንታዊ ያደርገዋል፡፡ የዚህ ሐሳብ አቀንቃኞች በከተማዋና በዙሪያዋ የተገኙ ጥንታዊ ዋሻዎችንና ቤተ መቅደሶችን ዋቢ ይጠቅሳሉ፡፡
የአክሱም ሥርወ መንግሥት የመጨረሻ ነጋሢ እንደሆነ የሚነገርለት አንበሳ ውድም በዮዲት ጉዲት በተሳደደ ጊዜ መሸሻውን ወደ አሁኗ ሸዋ ማድረጉ፣ ታቦተ ጽዮንም ዝዋይ መጠለሏ የአክሱም መንግሥት በአካባቢው የነበረውን የገዢነት ቦታ አመልካች አድርገውም ይጠቀሳሉ፡፡
የአክሱም ግዛት ማጋደልና መውደቅ በጀመረ ጊዜ የእስልምና ሃይማኖትም መስፋፋት ጀምሮ ነበር፡፡ መነሻውን ሰሜን አድርጎ ወደ ደቡብ ከሚወርደው በበለጠ ፍጥነት በምስራቅ በኩል የገባው እስልምና ጉዞውን አጣድፎ ወደ አሁኑ የአገራችን እምብርት ደርሶ ስለነበር በዚያ «የማግዙማይት ሱልጣኔት» የተሰኘውን እስላማዊ ሥርወ መንግሥት ለመመሥረት እንደበቃ ሥርግው ሀብለ ሥላሴ በታዋቂው የጥንታዊትና ማዕከላዊት ዘመን ታሪክ መጽሐፋቸው ይጠቅሳሉ፡፡
የማግዙማይት ሱልጣኔት ምን ያህል ጊዜ እንደገዛ ባይታወቅም ከአዲስ አበባ በሁለት መቶ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የዛጉዬን አሻራ የሚዘክረው የአዳዲ ማርያም የዐለት ውቁር ቤተ መቅደስ የሒደቱን ተለዋዋጭነት ይመሰክራል፡፡ በላሊበላ አምሳል የተሠራው ያ ቤተ ክርስቲያን በአካባቢው ላይ የአክሱም መንግሥት የነበረው ግዛት በዛግዌም መጠበቁን ጠቋሚ ሆኖ ለክርክር ይቀርባል፡፡ በዚህ መስክ ሙግት የሚያቀርቡት ሌላ መከራከሪያ የሚያነሡት ጥንታዊ አሻራ የዝቋላን ገዳም ነው፡፡ በዘመነ ዛጉዌ እንደተገደመ የሚነገርለት ይህ ገዳም በጥንታውያን ድርሳናት በተጠቀሰበት ቦታ ላይ ስሙ ሳይቀየር እስካሁን መገኘቱ አጋጣሚ ነው ብሎ ማለፍ አይቻልም ይላሉ፡፡
የዛግዌ ሥርወ መንግሥት ዘመኑን አጠናቅቆ በሰሎሞናውያኑ ተተካ፡፡ የመጀመሪያው ንጉሥ ይኩኖ አምላክም መናገሻውን የጁ ስላደረገ ያሁኗ አዲስ አበባ እጁ እስክትገባ ጊዜ ወስዶበታል፡፡ በዚያ ዘመን በአሁኑ ሸዋ ላይ የነበሩ ሌሎች ገዢዎችና ሕዝቦች ነበሩ፡፡ ገድለ ተክለ ሃይማኖትን እንደ ምንጭ ከተጠቀምን የወቅቱ የአካባቢው ገዢ ሞተለሚ የተባለው የወላይታ ንጉሥ (ካኦ) ገንኖበት እናገኛለን፡፡
አዲስ አበባ በመካከለኛው
ዘመነ ኢትዮጵያ
በብዙ የታሪክ ሰነዶች የሚታወቀው «የይፋት ሱልጣኔት» ደግሞ እስካሁን ስሙን ለማስታወሻ በተወበት ሥፍራ መንግሥታዊ አስተዳደርን አስፍኖ አልፏል፡፡ በሃይማኖትም ሆነ በዘር የይፋት ሱልጣኔት ወራስያን የሆኑት አርጎባዎችም ለምስክር ተርፈው በአካባቢው ይገኛሉ፡፡ አብዛኛው የሱልጣኔቱ ባለቤቶች ግን በይኩኖ አምላክ ተሸንፈው ወደ ሐረር በመሸሽ የአዳል ሥርወ መንግሥትን እስከመሠረቱበት ጊዜ ድረስ መቀመጫቸው ሸዋ ውስጥ ልዩ ስሙ አልዩ አምባ ነበር፡፡
በይኩኖ አምላክ የቀናው የሰሎሞናውያኑ መንግሥት መናገሻውን ባያረጋም ከሸዋ ሳይርቅ ጉዞውን ቀጠለ፡፡ አምደ ጽዮንም ዳሞት፣ ፈጠጋር፣ ሐዲያ የተባሉ የአካባቢ መንግሥታትን እያሸነፈ ሕዝቡን ከነቦታው በመንግሥቱ ውስጥ አስገባ፡፡ በዚህ ሁሉ ሂደት የአዲስ አበባ አካባቢ የብዙ ሕዝቦችን መሥተጋብር ፈጥሯል፡፡ የክርስቲያን ሙስሊም ገዢዎች ሲፈራረቁ ሕዝቡም አብሮ በመሸሽ ወይም መሪውን ተከትሎ በመዘዋወር ሌላ ቦታ ሲሰፍር በምትኩም ተተኪውና ቀሪው እየተጋባ ቦታውን በእጅ ያደርጋል፡፡
የሰሎሞናውያን ሥርወ መንግሥት በአህመድ ኢብን ኢብራሂም አልጋህዚ (ግራኝ አህመድ) እስከጠፋ ድረስ በጊዜው ወረብ ተብላ በምትጠራው ሸዋ አማካይ መናገሻ አድርገው በነበሩት ነገሥታት ሥር አዲስ አበባ ጸንታለች፡፡ አዲስ አበባ መናገሻ እስከመሆን ደርሳ የነበረችው ግን በንጉሥ ዳዊት ነበር፡፡ ወረብ በምትባል አውራጃ ሥር ትተዳደር የነበረችው አዲስ አበባ በዚያን ጊዜ የነበረው ስሟ «በረራ» እንደነበር የታሪክ ድርሳናት ያረጋግጣሉ፡፡
የማዕከላዊውን ዘመን ታሪክ ለመረዳት ከሚጠቅሙ ምንጮች መካከል አንዱ አረብ ፈቂህ በመባል የሚታወቀው የግራኝ አህመድን ውሎ እየተከታተለ የዘገበው ጸሀፊ «ፈቱህ አልሀበሽ» ነው፡፡ አረብ ፈቂህ እንደዘገበው የመረብ አውራጃ በተፈጥሮ የበለጸገ፣ ለምለም ከመሆኑም በላይ ታላላቅ አብያተ ክርስቲያናትና የመሳፍንት ቤቶች የነበሩበት ሥፍራ ነው፡፡ አረብ ፈቂህ ጨምሮም በረራን «የሀበሾቹ ምድራዊ ገነት» ሲል ይገልጻታል፡፡ የአረብ ፈቂህንና ሌሎች ጥንታውያን ተጓዦችን ምንጮች መነሻ በማድረግ ሪቻርድ ፓንክረስትን የመሳሰሉ ዘመናውያን የታሪክ አጥኚዎች የበረራን ታሪክ ጽፈዋል፡፡
የዚያ ዘመን ታሪክ በግልጽ ለመረዳት የሚያስችለን ሌላው ምንጭ ጥንታዊው የፍራማውሮ ካርታ ነው፡፡ ይህ ካርታ ትክክለኛ ከመሆኑ የተነሣ የዓለም አሳሾችና ቅኝ ገዢዎች የተገለገሉበት ነው፡፡ በዚህ ካርታ ውስጥ ከተጠቀሱ የኢትዮጵያ ከተሞች መካከል አንዷ በረራ ስትሆን መገኛዋም የአሁኗ አዲስ አበባ በከተመችበት ላይ ነው፡፡ በውስጧና በዙሪያዋ ያሉ ተራሮችንና ወንዞችንም ካርታው አላስቀረም፡፡ ካርታው በተሠራበት ዘመን በረራ የመንግሥት መቀመጫ መሆኗን የሚነግረን ነገር የከተማዪቱ ታሪክ ቀደም ብሎ ለመጀመሩ ማስረጃ ነው ሲሉ የሚሞግቱ አሉ፡፡ ሞጋቾቹ የሚያቀርቡት አመክንዮ ከተማ ተቆርቁሮ፣ አድጎ የመንግሥት መናገሻ እስኪሆን ድረስ ብዙ ዘመናትን ይፈጃልና የነገሥታቱ መናገሻ ሳትሆንም በፊት በረራ ከተማ ነበረች ማለት ነው፡፡ አጼ ዳዊት በጊዜው ለነበረችው መናገሻቸው ጥለው ካለፉት አሻራ መካከል ተጠቃሹ እንጦጦ ተራራ ላይ በጊዜው ነገሥታት ዘንድ ተወዳጅ የሆኑትን የመልአኩ ኡራኤልና ራጉኤል ታቦታት የሚገኙበት ዋሻ ቤተ መቅደስ እስካሁን በቅርስነት የሚጎበኝ መሆኑ ነው፡፡ የፍራማውሮ ካርታ በመሬት ላይ የሚገኙ ተጨባጭ እውነታዎችን መሠረት አድርጎ የተሠራ እንጂ ግምታዊ፣ ምናባዊ ወይም ሃይማኖታዊ መነሻዎችን የሚጠቀም ባለመሆኑ «የመጀመሪያው ሳይንሳዊ ካርታ» ተብሎ የሚጠራ ነው፡፡ ሠሪው ፍራማውሮም ለሳይንስ እድገት ባበረከተው አስተዋጽኦ የጨረቃ የተወሰኑ ክፍሎች በስሙ ተሰይመውለታል፡፡
የግራኝ አህመድ ጦርነት ታላቁን ውጊያ ያካሔደው በዛሬዋ ቢሾፍቱ ሲሆን በጊዜው ስሟ ሽምብራ ኩሬ ትሰኝ እንደነበር የታሪክ ድርሳናት ይነግሩናል፡፡ በአስራ አምስተኛው ክፍለ ዘመን ይህ ቦታ የአማርኛ ስያሜን ይዞ መገኘቱ በሥፍራው የነበረውን ሕዝብ ማንነት አመልካች ሲሆን፣ ውጊያው በዚያ መካሔዱ ደግሞ የማዕከላዊው መንግሥት መቀመጫ የት አካባቢ እንደነበር ጠቋሚ ነው፡፡
የመናዊው አረብ ፈቂህ እንደተረከው ከሽምብራ ኩሬ ቀጥሎ ብርቱ ውጊያ የተካሔደው በበረራ ነበር፡፡ አረብ ፈቂህ ግራኝ አህመድን እግር በእግር ተከትሎ በከተበው የታሪክ ማስታወሻ የተወልን በዘመኑ የነበረውን የቦታ አቀማመጥ፣ የመሳፍንቱንና መኳንንቱን ማንነትና ሌሎች ሶሽዮ ኢኮኖሚያዊ ሁኔታዎችን ስለሆነ ታማኝ የታሪክ ምንጭ ለመሆን በቅቷል፡፡ አረብ ፈቂህ የዐይን እማኝ ከመሆኑም በላይ የአካባቢውን ተወላጆች በመጠየቅ ትክክለኛ መረጃ ለማስፈር ጥሯል፡፡ ጸሐፊው «ምድረ ገነት» ብሎ ባሞካሻት ከተማ ነዋሪዎች የነበሩትም ጋፋቶች፣ አማሮችና ጉራጌዎች መሆናቸውን ጠቁሟል፡፡ ንጉሡ ከጭፍሮቹና ከእጅ ባለሙያዎች ጋር ይኖሩ ከነበረበት ሥፍራ ግራኝ ከአዋሽ ምንጭ ተነሥቶ አሥር ቀናትን በፈጀ ጉዞ በረራ ሲደርስ ንጉሡ ሸሽቶ ወደ ፈጠጋር የሔደ ሲሆን፣ ተከትለው የሔዱት የእጅ ባለሙያዎች ተመልሰው በመምጣት ለሙስሊሞቹ ጦር አቀባበል ማድረጋቸውን ጽፏል፡፡
አረብ ፈቂህ ከበረራ እስከ ደብረ ሊባኖስ የስድስት ቀን መንገድ እንደሆነ ነዋሪዎች የነገሩትን የጻፈ ሲሆን ጀምስ ብሩስም ጉዞውን በእግሩ በማድረግ ስድስት ቀን እንደፈጀበት አረጋግጦ የአረብ ፈቂህን መረጃ እውነታነት ያጸናል፡፡ በዘመናችንም ማርኮ ቪጋኖ፣ ዴቪድ ፊሊፕሰንና ሳሙኤል ዎከር የተባሉ ተመራማሪዎች በሳተላይት ምስል በመታገዝ የፍራማውሮን ካርታን መርምረዋል፡፡ በተጨማሪም የፈራረሱ ግንቦችንና ቤተ መቅደሶችን፣ ቤተ መንግሥቶችንና ምሽጎችን በማጥናት የጥንቷ በረራ የአሁኗ አዲስ አበባ መሆኗን አረጋግጠዋል፡፡
ከግራኝ ጦርነት በኋላ የወደመችው በረራ መነሻውን ባሌ ባደረገው የኦሮሞ ኃይል ስትያዝ ደግሞ የጥቂት ኦሮሞ ጎሣዎች መኖሪያ ሆነች፡፡ በሙስሊም ክርስቲያን ጦርነት ጊዜ ገለልተኛ በመሆን ኃይሉን የቆጠበው የኦሮሞ ሠራዊት በሙሉ ኃይሉ መንቀሳቀስና ከፊቱ የገጠመውን እንቅፋት እየጠረገ መውረስ ጀመረ፡፡ የልብነ ድንግል ወራሽ የሆነው ገላውዴዎስም ግራኝን ካሸነፈ በኋላ እስከ ሐረር ግዛቱን ለመመለስ ያደረገው ሙከራ ስላልተሳካለት የማዕከላዊው መንግሥት መቀመጫ ጎንደር ላይ ስለተሰበሰበ የኦሮሞ ሠራዊት ኹኔታው ምቹ ሆነለት፡፡ የኦሮሞ ሠራዊት ጎንደር ላይ ተሰብስቦ ከተቀመጠው ከነባሩ መንግሥት ጋር በመዋሐድ እስኪቆም ድረስ ግስጋሴውን ማንም አልገታውም፡፡ በረራም የጥንት ሕዝቦቿ መካከል ጥቂቱን እንደያዘች ከከተማነት ወደ ገጠርነት አልፎም ወደ ጫካነት ተቀይራ አዲሶቹን የኦሮሞ ጎሳዎች አቅፋ በተለመደ ተቀባይና አዋሐጅ ጠባይዋ የቀጣይ ምዕራፍ ጉዞዋን ያዘች፡፡
የዘመናዊት አዲስ አበባ ዳግም ውልደት
ከግራኝ አህመድ ጦርነት በኋላ አሻራዋ ደብዝዞ የኖረችው አዲስ አበባ ዳግም የተነቃቃችው በዳግማዊ ምኒልክ ዘመን ነው፡፡ በዚያ ዘመን ጥቂት የኦሮሞ ጎሳዎች ከሚኖሩባቸው ሦስት መንደሮች በቀር መላው አካባቢ ጫካ ለብሶ ነበር፡፡ ለመኖሪያ ምቹ መሆኗ ታውቆ ንጉሡ መናገሻ ሲያደርጓት ግን የተቀረው መኳንንትና መሳፍንትም ንጉሡን እየተከተለ መስፈር ጀመረ፡፡
ይህ አሰፋፈር ከጥንት ጀምሮ በነገሥታቱና በመሳፍንቱ ዘንድ የተለመደ ነበር፡፡ አንድ ንጉሥ መናገሻውን ባደረገበት ቦታ ዙሪያውን ሠራዊቱ ይሰፍራል፡፡ ከዚያም መኳንንቱ ከነጭፍሮቻቸው በዚያው አካባቢ መሥፈር ይቀጥላሉ፡፡ በዳግማዊ ምኒልክ የተቆረቆረችው አዲስ አበባ የመጀመሪያዎቹ የመንደር ስሞች ይህን የታሪክ እውነታ ያመለክታሉ፡፡ ራስ ካሳ ሰፈር፣ ራስ መስፍን ሰፈር፣ ራስ መኮንን ሰፈር፣ ሀብተ ጊዮርጊስ ሰፈር ወዘተ የሚባሉት ስሞች ራሶቹ ንጉሡን ተከትለው ሲሰፍሩ ጭፍሮቹ በሚመሠርቱት ሠፈር የተነሣ ነው፡፡
በዚህ መልክ የተቆረቆረችው ከተማ እንዴት ልትሰፋና የሚሊዮኖች ከተማ ለመሆን በቃች? ስንል ነገሩ ከተለያዩ ምክንያቶች የሚመዘዝ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ የመጀመሪያው ከተሞች ያላቸው ማግኔታዊ የስበት ኃይል ነው፡፡ እንደ ጌታቸው ኃይሌ አስተያየት ከሆነ የከተሞች ማግኔታዊ ኃይላቸው ለመኖሪያ ምቹ መሆናቸውና የሥራ ዕድል መስጠታቸው ነው፡፡ ቦታው ምንም ጫካ ቢወርሰው በመቶዎች ለሚቆጠሩ ዓመታት ሲጋቡና ሲጋጩ የነበሩ ሕዝቦች በዙሪያው ነበሩና የመናገሻ ከተማነቱ ዝና ሲሰማ እየተሳሳቡ በመምጣት ኑሮ ይጀምራሉ፡፡ ቀስ በቀስም ከሩቅ ያሉት መምጣት ይጀምራሉ፡፡ ባህሩ ዘውዴ በኢትዮጵያ ዘመናዊ ታሪክ መጽሐፉ እንደገለጸው በኢጣሊያና በእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ሥር የነበሩት ኤርትራውያንና ሶማሌዎች ሳይቀሩ አምልጠውና ሸሽተው ወደ አዲስ አበባ ይመጡ ነበር፡፡
የአጼ ምንልክ የኢንዱስትሪ ፖሊሲም ሌላው መስሕብ ነበር፡፡ የእጅ ባለሙያዎች እንዲከበሩ አውጀው፣ ሕጉ ባህል እንዲሆንም ራሳቸው ንጉሡ ብረት ቀጥቅጠው በመሥራት «ባለእጅ ብለህ ብትሳደብ እኔን መስደብህ ነው» ሲሉ ካስጠነቀቁ ወዲህ ባለሙያዎች ከጋሞና ከሰሜን ሸዋ መጥተው ሰፍረዋል፡፡ የአዲስ አበባ ሰፈራን ከፍ ካደረጉ ክስተቶች አንዱ የአድዋ ዘመቻ ነው፡፡ የታሪክ ምሁራንም ቅድመ አድዋ ከሆነው የሕዝብ ሰፈራ በላይ ከአድዋ በኋላ የሆነው በብዙ እጥፍ እንደሚበልጥ ይገልጻሉ፡፡ ከዘመቻው መልስ ብዙዎቹ ተዋጊዎች ወደ ትውልድ አገራቸው ከመግባት ይልቅ ምርጫቸው የሆነው በዋና ከተማዋ መቀመጥ ነው፡፡ አንዳንዱ የከተማው ድምቀት አማልሎት ሲሆን አብዛኛው ግን ወዳጅ ዘመዱን ጦርነቱ ስለነጠቀው «ምን ይዤ፣ ማንን ብዬ» እያለ የትውልድ ቀየውን በመተው ከተማ ቀርቷል፡፡
አዲስ አበባ የአገሯን ሰው ብቻ ሳይሆን ባዕዱንም ማስተናገድ ያዘች፡፡ ሁለተኛውን የዓለም ጦርነትን ጨምሮ በልዩ ልዩ የፈተና ጊዜዎች ከአርመን፣ ከግሪክ፣ ከህንድ፣ ከየመንና ሌሎች አረብ አገሮች በየጊዜው የመጡ ሰዎች እስካሁን በቅርስነት የተመዘገቡ ዘመናዊ ቤቶችን በከተማዋ ሠርተዋል፡፡ የአድዋ ድል የዓለም ጥቁር ሕዝቦች ድል ሆኖ ያኮራቸው ጥቁር አሜሪካውያንም ኢትዮጵያን ለማገልገል ወስነው በመምጣት መኖር፣ ማልማትና አገር ማሠልጠን አስበው ብዙ ሠርተዋል፡፡ በዚህ ረገድ ይበልጥ ተጠቃሾች የሆኑት ከአገሬው ጋር ተጋብተው እስከመቅረት የሚደርስ ፍቅር ከኢትዮጵያ ጋር የያዛቸው ጃማይካውያን አይዘነጉም፡፡
በዘመነ ጣሊያን ወረራ እንደ ካዛንቺስና ካዛፖፖላሬን የመሰሉ ሠፈሮች በጣሊያናውያን ባለ ሥልጣኖች ተሰየሙ፡፡ ፒያሳና መርካቶም አራዳንና ሀብተ ጊዮርጊስ ሰፈርን ተክተው ጣሊያንኛ ስያሜያቸውን ተጎናጸፉ፡፡ ጣሊያን ሲወጣም ወረራው ያነሳሳው መስተጋብር ቀጥሏል፡፡ በጦርነቱ፣ በባንዳነቱ፣ በአርበኝነቱ፣ በንግዱና መሸታ ቤቱ ምክንያት ከተማዪቱን አስፍቶ ቢያደምቃትም ጣሊያን መርካቶ ብሎ በሰየማት የሐበሾች ገበያ ነጋዴው በአረቦች የተያዘ በመሆኑ የኃይለ ሥላሴ መንግሥት መላ ዘየደ፡፡ መላውን ያነሳሱትና ያስፈጸሙት አቶ መኮንን ሀብተ ወልድ በንግድ ሥራ ጥሩ ንቃት ያላቸውን ጉራጌዎች መነሻ ካፒታል በመደጎም እያቋቋሙ ንግድ አስጀመሯቸው፡፡ ጉራጌዎቹ ነጋዴዎች ዋጋ በመቀነስና ያገር ልጅ መሆናቸውን እንደ ምቹ አጋጣሚ በመጠቀም ተቀናቃኞቻቸውን አረቦች እያከሰሩ ካገር አስወጡዋቸውና ቦታቸውን በመተካት ተደላደሉ፡፡ ዘመድ ከዘመዱ እየተጠራራ መርካቶን አደመቃት፡፡
የመርካቶ ንግድ መድራትን ያዩ ጎጃሜዎችም እህላቸውን ለመሸጥ ጎራ አሉ፡፡ በጣሊኖች ተይዞ የነበረውን የሜካኒክነት ሙያ የተኩት ትግራዋዮችም ከተክለ ሃይማኖት እስከ ሜክሲኮ አልፎም እስከ ቄራ እየተሳሳቡ በመምጣት ከተማውን አስፋፉ፡፡ የጋሞዎች ጥበብም በሽሮሜዳ አልተወሰነም፡፡ መርካቶ፣ አስኮ፣ ሩፋኤልን አዳረሰ፡፡ ዛሬ ላይ የአንድ ብሔር አባላት በርከት ብለው አንድ ሰፈር ላይ የመገኘታቸው ምስጢር ይህ ነው፡፡
ከተሜነት ለሥነ ጥበብና ለሳይንስ እድገት ትልቅ አስተዋጽኦ የሚያደርግ የኑሮ ዘይቤ ነው፡፡ ንግድና ኢንዱስትሪ ተስፋፍቶ ልማት ሊኖር የሚችለው በከተማ ውስጥ ሲሆን በግልባጩም የንግድና ኢንዱስትሪ መጎልበት ከተሜነትን ያስፋፋል፡፡ ከተሜነት ግን ከዚህም የላቀ ፍልስፍና አለው፡፡ ከተሜነት የነጻነት ጽንሰ ሐሳብ ሥጋ ነስቶ የሚታይበት ሐውልት ነው፡፡ ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ፣ በመገናኛ ብዙኃንን መገልገል፣ ፖለቲካዊ ተቃውሞና ድጋፍ እንዲሁም በብዙ ሰዎች ስብስብ የሚገለጹ ክብረ በዓላትና በአብሮነት የሚከወኑ ኹነቶች የከተሜነት መገለጫዎች ናቸው፡፡
አዲስ አበባም ይህን የከተሜነት ዕሴት ይዛ እያበበች ነው፡፡ ሆኖም አንድ ከተማ ከሌላው የሚለየው ጠባይም አለ፡፡ ፓሪስን ከዱባይ የሚለዩዋት ቀለሞች እንዳሉዋት ሁሉ አዲስስ ምንድነው ልዩ ቀለሟ? ብንል ተከታትለው የሚመጡልን ብዙ መልሶች አሉ፡፡
የአፍሪካ ሕብረት መቀመጫ፣ በዚህም ምክንያት ከዓለም ትልልቅ የዲፕሎማሲ መዳረሻዎች አንዷ መሆኗ፣ አሮጌውና አዲሱ፣ ዘመናዊውና ባህላዊው፣ ሀብታሙና ድሀው ተቀላቅሎ የሚኖርባት መሆኗ እንዲሁም ሌላ ብዙ ምክንያት ሊጠቀስ ይችላል፡፡ በዋና አውራ ጎዳናዋ ላይ ጭነታቸው (ጭድ ሊሆን ይችላል) ገላቸውን የሸፈነባቸው የጋማ ከብቶች የሚታዩባት ብቸኛ ዋና ከተማ ሳትሆንም አትቀርም፡፡
ከዚህ ሁሉ በላይ ግን የብሔር ብሔረሰቦች ሕብር የሚታይባት የኢትዮጵያ ናሙና መሆኗ ይበልጥ የሚወክላት ቀለሟ ነው፡፡
የብሔሮች ስብጥር ሞዛይክ መልክ የሰጣት ከተማ ናት ስንል በብዙ መልኩ የሚታይ ቢሆንም በዋናነት ሁለት ትርጉሞችን የያዘ መሆኑ ነው፡፡ አንደኛው እያንዳንዱ ብሔር የራሱን ቋንቋ፣ ባህልና የአኗኗር ዘይቤ ይዞ በመምጣት ያንን እያንጸባረቀ የሌሎችንም እያከበረ መኖሩ ነው፡፡ በሌላ መልኩ ደግሞ የከተማ ኑሮ መስተጋብር ነውና የራስን ባህልና ቋንቋ ከሌላው ጋር እያዋሐዱ ሰጥቶ የመቀበልና በሒደቱም መለወጥ ግድ ይሆናል፡፡ በዚህ የመለወጥ ሒደት ውስጥ ነባር ዕሴቶች ድራሻቸው ሊጠፋ ይችላል፡፡ ይህ የከተማ ልውጣዊ ጠባይ የማሕበራዊ ሳይንስ ጠበብት የመቅለጫ ማሰሮ (Melting Pot) ብለው የሚጠሩት የአገርን ሚና የሚወክል ሆኖም ደግሞ በከተሞች ጎልቶ የሚታይ አስፈላጊና ሊቀርም የማይችል ክስተት ነው፡፡
አዲስ አበባ ውስጥ ከሁለትና ከሁለት በላይ ብሔረሰቦች የተወለዱ ሰዎች ይበዛሉ፡፡ ከተማ አቅልጦ የሚሠራበት አንድ ዘዴው እንዲህ ባለ የጋብቻና የዘር መቀያየጥ ነው፡፡ ከአንድ ብሔር ብቻ የሚወለደውም ቢሆን የወላጆቹን ቋንቋና ባህል አሟልቶ የመገኘት ዐድሉ የሳሳ ነው፡፡ ከዚያ ይልቅ የወላጆቹንና የጎረቤቶቹን ቀላቅሎ ይይዛል፡፡ ቱባ ማንነቶች ከአራቱም አቅጣጫ በከተማዪቱ መግነጢስ እየተሳቡ ከመጡ በኋላ ማሰሮው ውስጥ የመጀመሪያ መልካቸውን ጠብቀሰው አይቀጥሉም፤ እየቀለጡ ሌላ አዲስ ሆነው ይሠራሉ፡፡ አዲስ ባህልና ማንነት ይፈጥራሉ፡፡
አዲስ አበባን የኢትዮጵያ ናሙና የሚያሰኛት ገጽታም ይህ ነው፡፡ እንደ ኢትዮጵያ የብሔሮች ሙዚየም በሚያሰኛት መልክ ሁሉም ብሔረሰቦች ተጎራብተው ይኖሩባታል፡፡ በሌላ መልኩ ደግሞ ተዋሕደው አዲስ ማንነት እየፈጠሩ በከተማቸው ገጽታ ላይ አሻራቸውን ለትውልድ እየተዉ ያልፋሉ፡፡ አዲስ አበባ በይፋ ከምትታወቅበት ስሟ በተጨማሪ ሕዝቦቿ ፊንፊኔ፣ ሸገር፣ አዱ ገነት በሚሉ ስያሜዎች ያቆላምጧታል፡፡ አገራዊውን ብቻ ሳይሆን ዓለም አቀፍ ዕሴቶችን የምታንጸባርቅ የሁሉም ከተማ ሆናለች፡፡ እንደ ማንኛውም ጥንታዊ ከተማ በታሪክና በአፈ ታሪክ ከተገነባ ሥሯ ጋር አዲስ የሚፈጠረውን አስማምታ መያዝ አልከበዳትም፡፡ የሕዝቦቿ ውሕደትም ቅርብ ጊዜ የጀመረ ሳይሆን በአገሪቱ ጥንታዊ፣ መካከለኛና ዘመናዊ ታሪክ ውስጥ ሳይቆራረጥ የመጣ ስለሆነ በቀላሉ የሚፈታ አይደለም፡፡
ዘመን መፅሄት ህዳር 2011
ዳዊት አብርሃም