ዲሞክራሲያዊ አመራር ወይም አስተዳደር የበቀለበትን እና የበለጸገበትን ዘመን ስናስብ ከክርስቶስ ልደት በፊት በአምስተኛው ምዕተ ዓመት ውስጥ መሆኑን ታሪክ ይነግረናል፡፡ የዚህ ታሪክ ባለቤት ሆና የምትጠቀሰው ግሪክ ለዓለም አስተዋጽኦ ባደረገችው የአመራር ዘይቤ ክብር ይሰማታል፡፡
ግሪክ በቀል የሆነው ዲሞክራሲ በግሪክ የከተማ መንግሥታት በተለይም የአቴናውያን ባህል መሆኑ ይዘከራል፡፡ ከአቴንስ የከተማ አስተዳደር ናሙናው እየተወሰደ ወደ ሌሎች የግሪክ የከተማ መንግሥታት የተስፋፋው የመጀመሪያው የዲሞክራሲያዊ ሥርዓተ መንግሥት ባህል ዛሬ ላይ የብዙዎችን የዓለማችን ሀገራት የአስተዳደር ዘይቤ ቅኝት ተቆጣጥሮታል፡፡
አቴናውያን የዲሞክራሲ ባህል በቀጥተኛ ምርጫ የሕግ ወሳኞቻቸውን እና አስፈጻሚዎቻቸውን የሚሰይሙበት ሥርዓት ድንቅ መሆኑ ይተረካል፡፡ በዚያን ዘመን ይሄንን ባህል /ፍልስፍና/ ማፍለቅ እጅግ አኩሪ ነው፡፡ አሳታፊ እንደሆነ በሚነገርለት የግሪክ ዲሞክራሲ ግን በዕድሜ ከበሰሉ ወንዶች በስተቀር ሌሎች የሚሳተፉበት ዕድል አልነበረውም፤ በመሆኑም በዘመናት ሽግግር በተለያዩ መንግሥታትና ሕዝቦች ዘንድ በብዙ ፖለቲካዊ ትግሎች የዳበረ መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡
የሚያስደንቀው ጉዳይ ግን ‹‹ እንዲህ ያለ ሥልጡን የፖለቲካ እና የአስተዳደር ሥርዓት በአፍሪካ አህጉር እንኳንስ በዚያ ረጅም ዘመን አሁንም የለም›› ብለው ለሚያስቡ የፖለቲካ ሊቃውንት ከወደ ኢትዮጵያ የሚሰሙትን ዜና ማመን ቢከብዳቸው የሚገርም አይሆንም፡፡ ከብዙ ምዕተ ዓመታት በፊት እዚሁ ተፈጥሮ የዳበረ እና ሲሠራበት የነበረ፣ አሁንም በሥራ ላይ ያለ እጅግ አሳታፊ አመራር እና የአስተዳደር ዘዴ በኢትዮጵያ ባለው የኦሮሞ ማኅበረሰብ ውስጥ መኖሩን ሲሰሙ ምን እንደሚሰማቸው መገመት አይከብድም፡፡
ከዲሞክራሲ ሥርዓት አንጻር ሲታይ ብዙ ያልተነገረለት፤ ግን ብዙ ሊነገርለት የሚገባው የኦሮሞ ማኅበረሰብ የገዳ ሥርዓት ከጥንታዊው የግሪክ የከተሞች ዲሞክራሲያዊ ባህል ይልቅ እጅግ በተሻለ አሳታፊነቱ የሚደነቅ ነው፡፡ የሚገባውን ክብር ገና አላገኘም እንጂ፤ ‹‹ጨለማው አህጉር›› ብለው አውሮፓውያን በሚጠሩት አፍሪካ ውስጥ በኦሮሞ ማኅበረሰብ ዘንድ ሲያበራ የኖረ ሀገር በቀል የዲሞክራሲያዊ አመራር ሻማ አለ-የገዳ ሥርዓት፡፡
ዶክተር ታደሰ በሪሶ ‹‹The Oromo Gada System: Why Considered Democratic?›› በሚል በጻፉት ጥናት የገዳ ሥርዓት በኢትዮጵያ ውስጥ በኦሮሞዎች ዘንድ የነበረ ጥንታዊ ማኅበራዊና ፖለቲካዊ አደረጃጀት መሆኑን ያብራራሉ፡፡ እንደ ምሁሩ ማብራሪያ ከሆነ በባህሪው ዲሞክራሲዊ መሆኑ የሚነገርለት የገዳ ሥርዓት የኦሮሞ ማኅበረሰብ ፈጥሮ እሱው ያበለጸገው ተደናቂ ዕሴት ሲሆን፤ እስከ አሁን ድረስ ለማኅበረሰቡ ጥቅም እየሰጠ ያለ አደረጃጀት ነው፡፡ የገዳ ሥርዓት በሀገሪቱ ከነበረው መንግሥታዊ አስተዳደር በተሻለ ዲሞክራሲያዊነቱ ሊጠቀስ የሚችል ሥርዓት ነው፡፡
ገዳ በኢትዮጵያ ውስጥ የኦሮሞ ማኅበረሰብ የነበረውን ጥንታዊ ጥበብ እና መንግሥታዊ አሠራር አፍሪካውያን ሳይቀሩ ሳያውቁት መኖራቸው አስገራሚ ነው፡፡ ከሁሉም በላይ ለሁሉም ወገን አስደማሚ የሚያደርገው ግን ዘውዳዊ እና አምባገነናዊ መንግሥታት በሞሉበት አህጉር ውስጥ ገዳን የመሰለ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ከረጅም ዘመናት በፊት በልጽጎ መገኘቱ ነው፡፡
‹‹አስመሮም ለገሰ›› የተባሉ አጥኚ እንዳስረዱት የኦሮሞ ማኅበረሰብ ሦስት ዋነኛ እና መሠረታዊ ተቋማት አሉት፡፡ ከሃይማኖት አንጻር ‹‹ቃሉ››፣ ከፖለቲካ አመራር አንጻር ‹‹ገዳ›› እና ጠቅላላ ጉባኤውን በተመለከተ ‹‹ጉሚ›› የሚባሉ ተቋማት አሉት፡፡ እነዚህ ተቋማት ተዛማጅ እና አንዱ ከአንዱ ጋር በመገናዘብ የሚሠሩ ናቸው፡፡ የገዳ ሥርዓት በተደራጀበት ሥርዓት መሠረት በውስጡ የሃይማኖት መልክ ያላቸው ክዋኔዎች፣ ሕግ የማውጣት እና ሕግ የመተርጎም እንዲሁም ግጭት የሚፈታባቸው ጥልቅ እና ተዛማጅ አሠራሮችን በውስጡ ያዘለ ነው፡፡
ዶክተር ታደሰ በሪሶ እንደሚያብራሩት ደግሞ ‹‹የገዳ ሥርዓት ዲሞክራሲያዊ ተቋም ነው›› ተብሎ የሚደነቅበት የራሱ ባህርያት አሉት፡፡
ሰላማዊ የሥልጣን ሽግግር፤
ገዳ በትውልድ መደቦች መካከል ላለ ልዩነት እውቅና ይሰጣል፡፡ ትውልዶችም በገዳ ሥርዓት ውስጥ የያዙትን ሥልጣን በየስምንት ዓመቱ በማስረከብ ለቀጣይ ትውልድ አመራር እውቅና እየሰጡ ያልፋሉ፡፡ ይህ ለስምንት ዓመታት በሥልጣን ላይ የሚቆየው የአመራር ትውልድም በፖለቲካ፣ በወታደራዊ፣ በኢኮኖሚያዊ፣ በሕግ ማውጣት እና በእምነት ክዋኔዎች ውስጥ ዋነኛ መሪ ሆኖ ለስምንት ዓመታት ብቻ የሚሰየም ነው፡፡
የኦሮሞ ማኅበረሰብ በረጅም ታሪካዊ ጉዞው የየዕለት ሕይወቱን የሚመራው በዚህ አካሄድ ነው፡፡ ትውልዶች ያለምንም አድልዎ እና ልዩነት በሥርዓቱ ለመታቀፍ የተጋበዙ ናቸው፡፡ ሁሉም ሰው ለሥርዓቱ የተገባ ነው፡፡ ዘውዳዊም ሆነ ሌላ ሥርዓት ተቀባይነት የለውም፤ የፖለቲካ ሥልጣን በትውልዶች መካከል በእኩልነት ይሸጋጋራል፡፡
ሥርዓተ ገዳ ሲካሄድ እድምተኞች (ወልገኢ)
የኦሮሞ ወንድ ልጆች የገዳ ሥርዓት በሆኑት በአምስቱ የገዳ ሥርዓታት (ሥርነገዳ) ውስጥ በየእድሜ ደረጃቸው ይሳተፋሉ፡፡ ዕድሜ ሲባልም የሥነ-ሕይወታዊ ዕድሜን ሳይሆን በወላጅ እና በልጆች መካከል በሚበየን ማኅበረሰባዊ ብያኔ መሠረት የሚሰጥ ዕድሜ ሆኖ በዚህ ውስጥ ስምንት፣ ስምንት ዓመታት የሚያሳልፍ አንድ ኦሮሞ ወንድ በአርባ ዓመታት ውስጥ በአምስቱ ምሴንሶተ ተሳትፎ ያደርጋል ማለት ነው፡፡
አንድ ኦሮሞ በየጊዜው የሚያገኘው ዕውቀት፣ በየሚሴንሳው የሚገበየው ጥበብ ከጊዜ ወደ ጊዜ ከፍ ወዳለ ኃላፊነት እንዲደርስ ያደርገዋል፡፡
በእነዚህ መማሪያዎች ውስጥ መግባት አንድን ኦሮሞ በጦር ልምድና በአመራር ሥልጡን ሆኖ ለማኅበረሰቡ የተዘጋጀ ተመራጭ እንዲሆን ያደርገዋል፡፡ ከ41 እስከ 48 ዓመት ዕድሜ ያለው ደግሞ የገዳ እድሜ ነው፡፡ በዚህ ደረጃ /ዕድሜ/ ሲደረስ የፖለቲካ፣ የጦር፣ የማህበራዊ ጉዳዮች መሪ ለመሆን የሚበቃበት ዘመን ነው፡፡ ስለዚህ የገዳው መሪ የሚመረጠውም በገዳ የእድሜ እርከን ወይም ትውልድ ውስጥ ካሉ ኦሮሞ ወንዶች መካከል ሲሆን ምርጫው ዲሞክራሲያዊ ነው፤ ማእረጉም ‹‹አባ ገዳ›› ይባላል፡፡
ከዚያ በኋላ ለስምንት ዓመታት የጉባኤው ቃል አቀባይም፣ መሪም ሆኖ ያገለግላል ማለት ነው፡፡ በገዳ ሥርዓት ውስጥ ሌሎች ሹማምንትም አሉ፡፡ አንዱ አባ ዱላ ሲሆን የጦር መሪ ነው፤ ሌላው ‹‹አባ ሴራ›› የሚባል ሲሆን በኦሮሞ ትውፊታዊ ሕግ መሠረትዳኝነት የሚሰጥ ነው፡፡ እነዚህ እና ሌሎችም የገዳው ተመራጮች የሚያገለግሉት ለስምንት ዓመታት ብቻ ነው፤ በሥልጣን መቆያ ጊዜያቸው (ገደብ) ሲያልቅ ለሌላው የገዳ መደብ (ባለ ተራ) ያስረክባሉ ማለት ነው፡፡ ለቀጣዮቹ ስምንት ዓመታት የሚመረጡት አዲሶቹ ተመራጮችም በዚያው ነባር ስርዓት መሠረት ይመራሉ፡፡
የሥልጣን ሽግግሩ ያለ ጭቅጭቅና ያለ አንዳች ፍትጊያ የሚከናወን ነው፡፡ አዲሶቹ ለነባሮቹ ክብር ሰጥተው፣ ነባሮቹም ለአዲሶቹ መልካም ዘመን ተመኝተው የሚረካከቡ ሲሆን፣ ነባሮቹ አዲሶቹን የማማከር ሥራ ሊሠሩ ይችላሉ፤ ይጠበቅባቸዋልም፡፡
ባሊ፤
በገዳ ሥርዓት ውስጥ የሥልጣን ርክክብ ክዋኔ ነው፡፡ የሥልጣን ርክክቡ ከመካሄዱ በፊት ሥልጣን የሚሰጡ፣ የሚቀበሉት እና ከስምንት ዓመት በኋላ ተከትለው የሚረከቡት አባ ገዳዎች ለሃያ ሰምንት ቀናት ጠዋትና ከሰአት ኦዳ ዛፍ ስር ይሰበሰባሉ፡፡
በተለይ የባሊ ርክክብ ሊካሄድ አንድ ሳምንት ሲቀረው ደግሞ እነዚህ አባ ገዳዎች ጎጆ ቤት ይዘጋጅላቸዋል። ሴቶች ምግብ ያበስሉላቸዋል። የአከባቢው ህብረተሰብም በተለይ ስልጣን ለሚሰጡት እና ለሚቀበሉት እንደየአቅማቸው ስጦታ/ጉማተ / ይሰጧቸዋል።
የባሊ ርክክብ ቀን እስኪደርስ ጠዋት ጠዋት መጀመሪያ ስልጣን የሚሰጡ አባ ገዳዎች በሰልፍ ባህላዊ ልብሳቸውን ለብሰው እንዲሁም ጦር ወይም ቦኩ/ዱላ/ ይዘው የተለያዩ ህጎችን እያወጁ ከጎጀአቸው ወጥተው ኦዳ ዘፍ ስር ይሰበሰባሉ። በተመሳሳይ መልኩ ስልጣን የሚረከቡ እና ከስምንት ዓመታት በኋላ የሚተኩት አባ ገዳዎች በዚያው ሥፍራ ይሰበሰባሉ።
የተቀደሰ ቦታ በመሆኑ የተሰበሰቡት አባገዳዎች ጫማቸውን አድርገው አይገቡም። ይዘው የመጡትን ጦር ከሥፍራው ራቅ አድርገው በረድፍ ይደረድራሉ።
አባ ገዳዎች ስልፋቸውን ጠብቀው በተባለው መሰረት ወደ መሰብሰቢያ ቦታቸው ሲሄዱ የሰልፉን መሪ /ከለቻ/ ማቋረጥ የተከለከለ ነው። ይህም ለአባ ገዳዎች የሚሰጠውን ክብር ያሳያል። እንደዚሁም አባ ገዳዎች ከኦዳው ዛፍ ስር ተሰብስበው ሲነሡ እና ወደ ጎጆ ለመሄድ በተነሡ ቁጥር በተቀመጡበት ሥፍራ መፋቂያዎቻቸውን ሰክተው ይነሣሉ፤ በአንድ በኩል ለመገኘታቸው/ለመሳተፋቸው/ በሌላም በኩል ለተቀመጡበት ሥፍራ ምልክት /ምስክር/ እንዲሆናቸው ነው፡፡
ሕጉን ለማወጅ ግን የሚመረጡት በገዳ ሥልጣን ውስጥ ያለፉ ቀደምት አባቶች /ዩበ/ ናቸው፡፡
አስፈላጊ የሆኑት ማኅበራዊ፣ ባህላዊ፣ አካባቢዊ ወዘተ የሆኑ ሕግጋት ይታወጃሉ፡፡
ካወጁም በኋላ ጫማቸውን አድርገው ጦር ወይም ቦኩአቸውን ይዘው ወጥተው በሃላዊ ዘፈናቸውን ይዘፍናሉ። ከዚያም በኋላ እንደ አመጣጣቸው በሰልፍ የታወጁ ህጎችን ለሕዝቡ እያሳወቁ ወደ ጎጆአቸው ይመለሳሉ። የአከባቢው ነዎሪዎችም እንደየ ጎሳቸው ስጦታ አምጥተው ምርቃት ተቀብለው ይሄዳሉ። ከሰአት በኋላም በተመሳሳይ መልኩ ህጎች ይታወጃሉ።
ስልጣን የሚረከቡ አባገዳዎች ከጎጆዋቸው ወጥተው ስልጣን ወደሚያስረክቡ አባገዳዎች ጎጆ በመሄድ ተመራርቀው፣ ምግብ በልተው እና ጠጥተው ፣ ባሊ ወስደው ፈረስ እየጋለቡ ወደ ጎጆአቸው ይመለሳሉ። ‹‹ባሊ ወሰዱ›› የሚባለው የዶሮ ላባ የሚመስል ላባ በጥንቅላታቸው ላይ በጠመጠሙት የባህል አልባስ ውስጥ ሲሰካ ነው። ከዚያ ሰአት ጀምሮ ስልጣን በእጃቸው ነው ማለት ነው።
አሳታፊ ዲሞክራሲ፤
የገዳ ሥርዓት የሥልጣን ክፍፍልን በየትውልድ ደረጃ የሚሰጥ ሥርዓት አለው፡፡ የገዳ ሥርዓት የሰውን የእድሜ እርከን ተከትሎ ከልጅነት እስከ አረጋዊነት ያለውን ዕድሜ ለተከታታይ ሥርዓታዊ ደረጃዎች ይመድባል፤ በዕድሜ ከ1-8 ደበሌ፣ ከ8-16 ጋሜ፣ ከ16-24 ኩሳ፣ ከ24-32 ራባ፣ ከ32-40 ዶሪ እና ከ40-48 ገዳ ይባላሉ። ከአንዱ ወደ ሌላው ደረጃ ለመሄድ ደግሞ ራሱን የቻለ ክዋኔያዊ ሥርዓት ተዘጋጅቶለት የሚከናወን ነው፡፡
በየአንዳንዱ ደረጃ ውስጥ የሚፈጸሙ ‹‹መብት›› እና ‹‹ኃላፊነቶች››፤ ‹‹የተፈቀዱ›› እና ‹‹የተከለከሉ›› ጉዳዮች በውል ተለይተው ተቀምጠዋል፡፡ ዕድሜን መሠረት አድርገው የሚሰጡት አገልግሎቶች ልዩ ልዩ ናቸው፡፡ ከከብት ጥበቃ ጀምሮ በጦር ሠራዊት አባልነት ተሰልፎ እስከ መዋጋት የሚደርሱ የኃላፊነት ቦታዎች እና ግዴታዎች አሉ፤ ከማስተዳደር እስከ ማማከር ያሉ የአገልግሎት ደረጃዎቹ ተለይተው ይሰጣሉ፡፡ በእድሜ ደረጃ አባቶች፣ ልጆችና የልጅ ልጆች የሚሳተፉበት ሥርዓት ነው፤ ገዳ ፍትሐዊ ተሳትፎ ተግባራዊ የሚደረግበት ሥርዓት ነው፡፡
በአመራሩ በአምስቱ ምሴንሶተ የገዳ ፓርቲዎች/ ሙዳና፣ ሐልቺሳ፣ ደለና፣ ሃርሙፋ እና ሮበሌ/ እና ተከታታይ የእድሜ እርከኖች መካከል የጎንዮሽም ሆነ የላዕላይ-ታህታይ ፉክክር የለም፡፡ በምዕራቡ ዓለም ሲደረጉ የነበሩ እና እየተደረጉም ያሉ በዕድሜ ምክንያት የሚደርሱ ኢ-ፍትሐዊ የተሳትፎ ዕድል አሰጣጥ በገዳ ሥርዓት ውስጥ ከጥንትም ጀምሮ ችግር አልነበረም፤ አሁንም የለም፡፡
የማኅበረሰቡ የሰመረ ግንኙነት፤
ይህ በየዕድሜ እርከኑ ያለ የተሳትፎ ዕድል የኦሮሞ ማህበረሰብ ትውልዶችን አንዱ ከአንዱ ተማምኖ፣ ተከባብሮና ተዋሕዶ እንዲኖር ዕድል ሰጥቶታል፡፡ ግጭት የሚፈታበት፣ የእያንዳንዱ መብት የሚከበርበት፣ ማንነት እና እሴቶች የሚጠበቁበት ሥርዓት ስለሆነ ገዳ ለኦሮሞ ማኅበረሰብ ሰላም እና የማኅበረሰብ ግንኙነት ስምረት የማይተካ ሚና አለው፡፡
የኦሮሞ ሕዝብ ‹‹የጦር ስምሪት ልምድ ያለው ንቁ ሕዝብ ነው›› ሲባል የሰላማዊ ኑሮ እና አኗኗር ሥርዓትንም በገዳ ስርዓቱ በኩል ሚዛን ጠብቆ እንዲሄድ የሚያደርግ ነው ማለት ነው፡፡ ጦር መስበቅ በድንገት የሚመጣ አይደለም፤ የኦሮሞ ማኅበረሰብ ጦር ለመስበቅ የገዳ ስርዓቱን ፈቃድ፣ ምክር እና አመራር ይጠብቃል፡፡ ይህ ደግሞ ጊዜ ወስዶ የሚመከርበት ሥርዓት ነው፤ ለኦሮሞዎች ጦርነት የችግሮች የመጨረሻው የመፍትሔ አማራጭ ነው፡፡
ኦሮሞዎች በራሳቸው ማኅበረሰብ መካከል ብቻ ሳይሆን ከሌላው ነገድ /ማኅበረሰብ ጋር የሚጣጣሙባቸውና የሚዋሐዱባቸው ማኅበረሰባዊ ሥርዓታት አሏቸው፡፡ ሥርዓታቱ አንዱን ከሌላው ነገድ /ጎሳ/ አባል፣ በኦሮሞ ማኅበረሰብ ውስጥ ሲኖር ደግሞ ከሌላው ኦሮሞ ጋር እኩል መብቱ ተጠብቆና ተከብሮ የሚኖርበት ይፈጥሩለታል፤ እነዚያ ድንቅ ሥርዓታት ‹‹ጉዲፈቻ›› እና ‹‹ሞጋሳ›› ይባላሉ፡፡ ‹‹ጉዲፈቻ›› አንድን ልጅ ተረክቦ በሙሉ ኃላፊነት ልክ ከአብራክ እንደተገኙ ልጆች አድርጎ በጥንቃቄ ማሳደግ ሲሆን ‹‹ሞጋሳ›› ደግሞ ፍጹም ልጅ አድርጎ በቃልኪዳን መቀበል ነው፡፡ በዚህ ምክንያት ገዳ የኦሮሞን ማኅበረሰብ ከሌላው ጋር በማዋሐድ ብዙህነትን የሚያጎናጽፍ በመሆኑ ኦሮሞን በኢትዮጵያ ውስጥ ሰፊ ማኅበረሰባዊ መሠረት እንዲኖረው አድርጎታል፡፡
. ገዳ ሌላውን ማኅበረሰብ የሚያቅፍበት ብቻ ሳይሆን ግጭት ሲኖር የሚፈታበት አኩሪ ስርዓቱም በምሳሌነት የሚጠቀስ ነው፤ የጉማ/ካሳ/ እና አራረ/እርቅ/ ባህላዊ የግጭት አፈታት ሥርዓቱም ሰላማዊና ችግር ሲከሰትም ወደ መደበኛ ፍርድ ቤት ከመሄድና ከመጉላላት የሚድንበት ሥር የሰደደ አኩሪ ባህሉ በመሆኑ ተደናቂ ያደርገዋል፡፡
‹‹ገዳ ዲሞክራሲዊ ሥርዓት ነው›› ሲባል ለሴቶችም የሚሰጠው ዕድል ስላለ ነው፡፡ እንደ ገዳ ሁሉ ‹‹ሲንቄ›› እና ‹‹አቴቴ›› የሚባሉ ባህላዊ ስሪቶች የሴቶች የአመራር ተቋማት አይነት መገለጫ ሆነው ያገለግላሉ፤ በእነዚህም የኦሮሞ ሴቶች መብት ይከበራል፡፡
የትምህርት እና ልምምድ ጊዜ
በገዳ ሥርዓት ካሉት ድንቅ ባህላዊ ክንዋኔዎች ውስጥ አንዱ ለአባ ገዳነት የሚበቃበት ሥርዓት ሊጠቀስ የሚገባው ነው፤ አንድ ኦሮሞ በገዳ ሥርዓት አባገዳ ሆኖ ሥልጣን ለመያዝ የሙከራ ጊዜዎች ይኖሩታል፡፡ አንድ ሰው ከመሾሙ በፊት ለሁለት የገዳ የሹመት ወቅቶች /አስራ ስድስት ዓመታት ያህል/ ልምድ የሚቀስምበት ዕድል ይኖረዋል፡፡ በዚህ ጊዜ ስለሕግ እና ልማድ፣ ማኅበረሰቡ ስለሚመራበት የአመራር ጥበብ ከታላላቆቹ ልምድን ይቀስማል፡፡ ይህ በሌሎች ዓለማት ባሉ ዲሞክራሲን ባዳበሩ ባህሎች ውስጥ እንኳን ያልነበረ በመሆኑ የገዳ ስርዓትን ልዩ ያደርገዋል፡፡ ይህ አካሄድ ለኦሮሞ ማኅበረሰብ አመራር የሚመጥን፣ ክህሎትንና ዕውቀትን የያዘ አስተማማኝ አባገዳ ለማግኘት የሚያስችል ነው፤ ይህ አሠራር አባ ገዳ ከመሆን በፊት የሚፈጸም አስፈላጊ ቅድመ ሁኔታ ነው፡፡
ቃሉ እና ሞይቲ፤
‹‹ቃሉ›› የኦሮሞ ማኅበረሰብ የሃይማኖት ተቋም መጠሪያ ነው፡፡ ቃሉ ‹‹ዋቄፈና›› ለሚባለው የኦሮሞ እምነት መሪ ነው፡፡ የዚህ መሪ ሚና ለገዳ ሥርዓት መሠረትም ነው ተብሎ ይታመናል፡፡ በመሆኑም ሁሉንም የምርጫ እና ሃማኖታዊ ክዋኔ ያስፈጽማል፡፡ የአባገዳውን ሹመት በመሃላ ያጸናል፤ ይመርቃል፤ የሥልጣን ሽግግሩን ያበስራል፤ በአባገዳዎች መካከል ልዩነት/ችግር/ ሲኖርም ይፈታል፡፡ ያም ሆኖ በአባገዳዎቹ አሠራር ጣልቃ አይገባም፡፡ ምክንያቱም ምንም እንኳ እምነቱ እና የገዳ ሥርዓቱ ቢደጋገፉም የተለያዩ ተቋማት ናቸው፤ ቃሉ በፈጣሪ/ዋቃ/ እና በሰዎች መካከል አገናኝ ነው፡፡
በቃሉ እና በቃሊቲ የሚመሩት የኢሬቻ እና አቴቴ የበዓላት ሥርዓቶችም የገዳ ሥርዓት መድመቂያዎችና መገለጫዎች ናቸው፡፡ ኢሬቻ? በወንዶች፣ በሴቶቹ ዘንድ ደግሞ አቴቴ የኦሮሞ የምስጋና ሥርዓት ነው፡፡ ዓለማየሁ ኃይሌ የተባሉ አጥኚ ‹‹የኢሬቻ በዓል እንደ ታሪክ ባህልና ሃይማኖታዊ ቅርስ›› በሚል ጽሑፋቸው እንዳስረዱት ኢሬቻ ለምለም ሣርና ቄጠማ እንዲሁም አበባ ይዞ የምስጋና ጸሎት ለማድረግ መሰለፍ ነው፤ በዋቄፈታ እምነት ውስጥ ከፍተኛ ቦታ ያላቸው ቃሉዎች እና አባ መልካዎች በዚህ ሥርዓት ውስጥ የክዋኔው መሪዎች ይሆናሉ፡፡ የኢሬቻና አቴቴ ሥርዓቶች በተራሮች ወይም በጅረቶች አካባቢ ሲፈጸሙ አባገዳዎች በክብር ይሰየማሉ፡፡ በተለይም ክረምቱ አልፎ መስከረም ወር ሲጀምር ከዓመት ወደ ሌላ ዓመት ስለተሸጋገሩ ወንዞቹን ሞልቶ ልምላሜን ለግሶ አዲስ ዘመን ስላስጀመራቸው ዋቃን (ፈጣሪን) በዝማሬ ያመሰግኑታል፡፡
እያንዳንዱ የኦሮሞ ጎሳ ያለ አድልዎ በገዳ የሥልጣን ሽግግር ውስጥ ድርሻ ይኖረዋል፤ ሥልጣን የያዘው በአግባቡ ሥልጣኑን እንዲወጣም ሌሎቹ እንደ ሞጋች ሆነው (ለቼክ እና ባላንስ) ይጠቅማሉ፡፡ በዘመናዊው ፖለቲካ ‹‹ተፎካካሪ›› የምንለው ዓይነት ሚና ይጫወታሉ፡፡
ጉሚ
የገዳ ሥርዓት ሕግ አውጪ አካል /ጠቅላላ ጉባኤ/ አለው፤ እሱም ‹‹ጉሚ›› በመባል የሚታወቅ ሲሆን አንድ የኦሮሞ ማኅበረሰብ መማክርት ስብስብ ነው፡፡ ጉባኤው በስምንት ዓመት አንድ ጊዜ ለአንድ ሳምንት ያህል ይሰበሰባል፤ እያንዳንዱ ሰው የዚህ ጉባኤ አባል እንደሆነ ይታሰባል፡፡
በዚህ ጉባኤ ለመሳተፍ ዕድሜ፣ ጾታ፣ ወይም የፖለቲካ አመለካከት ልዩነት ገደብ የለም፡፡ በጉባኤው የማኅበረሰቡ ሕግጋት መጠበቃቸው ይረጋገጣል፤ ይገመገማል፡፡፡ አስፈላጊ ሲሆን አዲስ ሕግ በጉባኤው ይረቃል፤ ይታወጃል፡፡
ጉባኤተኛው ያጠፉትን ይመክራል፤ ከባሰም አባገዳውን ጨምሮ የገዳውን አባላት ይሽራል፤ ችግሮች ካሉም መክሮ ይፈታል፡፡
ሊቃውንትን ያስደመመ የአመራር ሥርዓት
በ19ኛው ምዕተ ዓመት በምስራቅ አፍሪካ ቅኝት ያደረገው ‹‹ፕላውዴን›› የተባለው የእንግሊዝ መንግሥት ወኪል የገዳን ስርዓት አጥንቶ ‹‹ሪፐብሊካን ከሚባሉ ከሁሉም መንግስታዊ ስርዓቶች በተሻለ የገዳ ሥርዓት እጅግ የበለጸገ ነው›› ብሎ ነበር፡፡
አሜሪካዊው የማኅበረሰብ ጥናት ባለሙያ (ሶሲዮሎጂስት) ዶናልድ ኤን ሌቪን ደግሞ የገዳን ሥርዓት ‹‹እጅግ የረቀቀ እና ስልጡን ሥርዓት ነው›› ብሎ ማድነቁ ይጠቀሳል፡፡
የጂኦግራፊው ሊቅ ጆርጅ ኤፍ.ካርተር ደግሞ የገዳ ሥርዓትን ‹‹ልዩ የመንግሥት ሥርዓት›› ሲል ማሞካሸቱም ይነገራል፡፡
ማጠቃለያ
ኢትዮጵያ የምትኮራባቸውና ለዓለም ልታበረክታቸው የሚገቡ በርካታ ማኅበራዊ እሴቶች ያሏት ጥንታዊት ሀገር ናት፤ ከድንቅ ማኅበራዊ ዕሴቶቿ አንዱም የገዳ ሥርዓት ነው፤ የኦሮሞ ማኅበረሰብ ያመነጨው የገዳ ስርዓት ባዕዳን ስለዲሞክራሲ የሚነግሩን ሳይሆን ቁጭ አድርገን ልናስተምራቸው የሚገባን መሆናችንን የሚያሳይ የቀዳሚ ሥልጣኔያችን እማኝ ነው፡፡
ገዳ በሀገራችን የነበረውን አሳታፊ የአመራር ፈሊጥ፣ የፍትሕ ሥርዓት፣ የአስተዳደር ዘይቤ፣ የማኅበራዊ ትስስር ጥበብ በማሳየት በኩል የሚደነቅ ሥርዓት ነው፡፡ ሀገራችን ለዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ምቹ ማኅበራዊ ምህዳር እንደነበራትና እንዳላትም የሚያመላክት ነው፡፡ የዘመናዊው ፖለቲካ ልሂቃን ዲሞክራሲን ለኢትዮጵውያን የሚያውሱት ሳይሆን የነበራቸው እና አሁንም በደም በአጥንታቸው ውስጥ ያለ እንጂ ቀስ በቀስ እየተባለ በ‹‹እንቁልልጬ›› ጨዋታ ዓይነት በየቀኑ የሚርቃቸው ሥርዓት አለመሆኑን በኩራት መግለጥ ተገቢም ግዴታም ነው ብለን እናምናለን፡፡
ዘመን መፅሄት ህዳር 2011
ማለደ ዋስይሁን