በዓለም ላይ የሴቶች የመብት ጥያቄና ትግል ቀደም ሲል ነበር፤ዛሬም አለ፤ወደፊትም ይቀጥ ላል፡፡ ይህ ትግል በፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖ ሚያዊ እንቅስቃሴዎች ሴቶች እኩል መብትና የህግ ጥበቃ እንዲያገኙ የሚያደርግ ነው፡፡ በኢት ዮጵያም እስካለንበት ጊዜ ድረስ በተለያየ መንገድ ሲንጸባረቅ ቆይቷል፡፡
አምባሳደር ዶክተር ገነት ዘውዴ የሴቶች የመብት ጥያቄ የማንነት ጥያቄ መሆኑን ይናገ ራሉ፤ ይህም በማንነቴ ምክንያት ምንም ነገር ማጣት አይገባኝም የሚል መሆኑን ያስረዳሉ፡፡ የኢትዮጵያ ሴቶች የመብት ጥያቄን ይበልጥ ለመረዳት የሴቶች መብት ጥያቄን በየትውልዱ ከፋፍሎ ማየት እንደሚያስፈልግ ነው የገለፁት፡ ኢትዮጵያ በየትውልዱ ጠንካራ መሪዎች፣ ተወካዮችና የመብት ተሟጋች ሴቶች እንደነበሯት ያስታው ሳሉ፡፡ በተደራጀ መልኩ ደግሞ በጣሊያን ወረራ ጊዜ የሴቶች በጎ አድራጎት ድርጅት እና የሴቶች በጎ አድራጎት አገልጋዮች ማህበራት በየፊናቸው ተደራጅተው ሲታገሉ እና በአገር ጉዳይም አስተዋፅኦ ሲያደርጉ እንደነበረ ያስረዳሉ፡፡
አምባሳደር ገነት እንሚያስረዱት፤ የኢትዮጵያ ሴቶች ጥያቄያቸውን ባህላዊ በሆነ መልኩ ሲያቀርቡ ሲታገሉ ነበር፡፡ በታሪክ የሚታወቁት የቃቄ ውርድወት፣ ንግስት ሳባ፣ ንግስት እሌኒ እና ጣይቱ እንዲሁም ሌሎች ሴቶች የሴት መብት ጥያቄን እንደየጊዜያቸው አረዳድ አሳይተዋል፡በኢትዮጵያ ታሪክ የተማሪዎች ንቅናቄ ወቅትም ትልልቅ የፌሚንስት ጥያቄዎች ይነሱ ነበር፡፡ እነ ስንዱ ገብሩም በፓርላማ ፌሚኒስት እና ፖለቲካዊ ጥያቄዎችን ጠይቀው ታግለዋል፡፡ ፊት ለፊት ከወጡ ሴቶች ውጪም በተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎችም በባህላዊ መንገድ ሴቶች እርስ በእርሳቸው በመደጋገፍ ይታገሉ ነበር፡፡ እነርሱ ያነሷቸው የነበሩ ጥያቄዎች አሁንም ድረስ ጥያቄ ሆነው ቀጥለዋል፡፡
«የሴቶች የመብት ጥያቄ ሰው ነኝ እኩል መብት ይገባኛል» የሚል መሆኑን ያስረዱት ደግሞ ዶክተር ስህን ተፈራ ናቸው ፡፡ የሴቶች መብት ጥያቄ ሙሉ ለሙሉ መልስ ያገኘበት አገር ባይኖርም በእድገት ደረጃቸው ከፍ ያሉ አገራት ሁኔታ የተሻለ መሆኑን ይጠቅሳሉ፡፡ ይህም የሴቶች መብት ጥያቄ ምላሽ ማግኘት ከእድገት ጋር የሚያያዝ መሆኑን ያመለክታል፡፡
ዶክተር ስህን እንደሚያስረዱት፤ በኢትዮጵያ ስራ እየሰሩ ደመወዝ የማይከፈላቸው ሴቶች ቁጥር ከፍተኛ ነው፡፡ በስምንት ሺ ሴቶች ላይ በተደረገ ጥናት 36 በመቶ ያህሉ ብቻ ለሚሰሩት ስራ ደመወዝ ይከፈላቸዋል፡፡ ይህ ማለት ልጆችን የሚያሳድጉ ሴቶች የሚሰሩት ስራ ከፍተኛ ሆኖ ሳለ አይከፈላቸውም፡፡ እንዲሁም ለተመሳሳይ ስራ አንድ ብር ለወንድ ሲከፈል ለሴት ግን 67 ሳንቲም ይከፈላል፡፡ ለምሳሌ በቀን ስራ፣ በኮንስትራሽን፣ የአበባ እርሻ፣ ጨርቃጨርቅና ሌሎች ፋብሪካዎች ለተመሳሳይ ስራ ለሴቶች ዝቅተኛ ክፍያ ይከፈ ላል፡፡
በሴቶች መብት ጥያቄ ላይ የሚሰነዘሩ አሉታዊ አስተያየቶች ጫና እንደሚፈጥሩ ይገልጻሉ፡፡ በኢትዮጵያ የሴቶች መብት ጥያቄ ምንነትና ዓላማ በትክክል የተረዳ ጥቂት ሰው ነው፡፡ ይህ የአረዳድ ስህተት ደግሞ የህግ አረዳድም ድረስ ይደርሳል፡፡ እንዲሁም ፌሚንዝም ወንዶችን የሚጠሉ ሴቶች እሳቤ እንደሆነና የፌሚንዝም ፅንሰ ሀሳብ የምዕራቡ ዓለም አስተሳሰብን የሚከተሉ ሴቶች እንጂ ሁሉንም ሴት የማይወክል ተደርጎም ይወሰዳል፡፡ ስለ ሴቶች የመብት ጥያቄ በአብዛኛው ጤናማ አስተሳሰብ ወይም አረዳድ የለም የሚል ሃሳብ አላቸው፡፡ በተለይም በውክልና 50 በመቶ እና የሴት ፕሬዚዳት አገሪቱ በማግኘቷ የሴቶች ጥያቄ በዚህ ዘመን ተመልሷል የሚል አስተሳሰብ ተበራክቷል፡ይሄ ግን መስተካከል አለበት፡፡ የእያንዳንዷን ኢትዮጵያዊ ሴት መብት የሚያስከብር እና ህይወትዋን የሚቀይር ስራ መስራት አለበት፡፡
ያለንበት ወቅት በፖለቲካው የሴቶች ውክልና እየጨመረ መምጣቱና እኩል ውክልና ለማግኘት መሰራቱ ትልቅ ነገር መሆኑን የሚገልጹት ዶክተር ስህን፤የሴቶች መብት ጥያቄ ገና መልስ ማግኘት አልጀመረም፡፡ ሚኒስትሮቹ የሁሉም ዜጋ እኩል ሚኒስቴር ቢሆኑም በሴቶች መብት ጥያቄ መሟገት ላይ የተሻለ እንደሚሰሩ እንጠብቃለን ሲሉ ተናግረዋል፡፡
በሴቶች ላይ እየተፈፀሙ የሚገኙ ጥቃቶች እየከፉ፣ እየተባባሱ፣ በአደባባይ እየተፈፀሙና ትክክለኛ የህግ ከለላና ፍትህ እየተገኘ ባለመሆኑ በብዙ መልኩ ማስተካከል ይገባል፡፡ በተለይ የሴቶችን መብት የሚያስከብርና ከለላ የሚሰጥ ህግ አገሪቱ እንዲኖራት ጥረት ሊደረግ የሚገባበት ጊዜ መሆኑን ያስረዳሉ፡፡ ቀጣይ የሴቶች መብት ጥያቄ ወደ ግል መብት ጥያቄም የሚሄድ መሆኑን ሳይጠቅሱ አላለፉም፡፡
ወይዘሮ ሰሎሜ ታደሰ ደግሞ የሴቶች መብት ጥያቄ የኃይል ጥያቄ ነው ብለው እንደሚያምኑ ይገልጻሉ፡፡ የኃይል ጥያቄ በቀላል የሚሰጥና የሚገኝ ባለመሆኑ የሚጠይቅና የሚታገልለት ኃይል ያስፈልጋል ባይ ናቸው፡፡ ይህ ትግል ሴት እኩል ዕድል እንድታገኝ፣ 50 በመቶ ሴቶች ቦታ እንዲያገኙ 50 በመቶ ወንዶች ቦታ አጥተው በመሆኑ ጠንካራ ትግልን የሚጠይቅ እንደሆነ ያመለክታሉ፡፡ የትኛውም የመብት ጥያቄ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ በመሆኑ የሴቶች መብት ጥያቄም የይገባናል መሆኑን ይናገራሉ፡፡
የሴቶችን መብት ለማስከበር የሚታገል ጠንካራ አካል የግድ እንደሚያስፈልግ ከስራ ልምዳቸው መረዳታቸውን ወይዘሮ ሰሎሜ ይገል ፃሉ፡፡ ‹‹በውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዲፕሎማት ሆኜ በምሰራበት ወቅት መስሪያ ቤቱ ለዲፕሎማቶች ጤና መድን ዋስትና መግባቱን ሲያበስር ደስ ተሰኘሁ፡፡ ነገር ግን የጤና ዋስትናው የእርግዝና እና የማህፀን ህክምናን አያካትትም ነበር፡፡ ይህ ሴቶችን የሚያገልና አስፈላጊ መሆኑን ለማስረዳት በርካታ ዲፕሎማት ሴቶች ተሰባስበን መጮህ ነበረብን›› ይህ የሚያሳየው እያንዳንዱ ነገር የሴቶችን መብት የሚያስጠብቅ እንዲሆን ትግል ማድረግን ነው፡፡
ከዚህ ቀደም በሴቶች መብት ተሟጋች ተቋማትና በመንግሥት ውስጥ ባሉ የሴት አደረጃጀቶች መካከል ጤናማ ግንኙነት ስላልነበረ ትስስር ፈጥሮ መስራት ያልተቻለበት ሁኔታ እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡ እንዲያውም ጥያቄው በሴትና በወንድ መካከል ሳይሆን በዲሞክራሲ ድርጅቶችና በመንግሥት አደረጃጀቶች ውስጥ በሚገኙ ሴቶች መካከል ልዩነቱ ጎልቶ ይታይ እንደነበር ይገልፃሉ፡፡ በበጎ ፈቃደኛነት ለሴት መብት የሚከራከሩ ሴቶች ላይ በመጮህና ጥያቄውን በማጥላላት የፖለቲካ ታማኝነትን ለማትረፍ ይሰራ እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡ ፖለቲካው የሴቶች ጥያቄንም የማንነት ጥያቄ እንዳልሆነ ለማስመሰል የተሰራበትም እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡ ማንኛውም ዓይነት የሴት መብት ጥያቄ የሚያነሱት የተወሰነ ቡድን ወይም የተማሩ ሴቶች ጥያቄ ብቻ እንደሆነ ሲቆጠር መቆየቱንም ይናገራሉ፡፡
በጠቅላይ ዓቃቤ ህግ በህግ ጥናት፣ማርቀቅና ማስረፅ ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ የሴቶች ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብት እንዲጠበቅ በህግ በኩል ያለውን ሁኔታ ምን እንደሚመስል የሚያመለክት ጹሁፍ የተናጋሪዎቹን ሀሳብ ያጠናክራል፡፡
ጽሁፉ እንደሚያመለክተው፤ በስራ ቅጥ ርና በስራ ሁኔታ ከሚፈጸሙ የማግለል፣ አድሎና መገደብ፣ በስራ ቦታ የሚፈፀሙ ፆታዊ ትንኮሳዎች፣ በማግባባት፣ በማነሳሳት፣ በማታለል፣ በማስገደድ፣ አካላዊ ጉዳት ማድረስ ወይም ሰጥቶ መቀበል ላይ የተመሰረተና እኩል ያልሆነ ፆታዊ ግንኙነት እንዲፈጠር በማድረግ ይፈጸማል፡፡ ችግሮቹን በተመለከተ በሴቶች ላይ የሚደረገውን ማንኛውንም ልዩነት ለማስወገድ በመንግሥታቱ ድርጅት የተደረገውን ስምምነት ለመከታተል የተቋቋመው ኮሚቴ በ1989 እና 1992 እ.ኤ.አ በበሰጠው አስተያየት አባል መንግሥታት ይህንን ተግባር ለማስወገድ ህግ ማውጣት እንዳለባቸው ይደነግጋል፡፡ ነገር ግን ኢትዮጵያን ጨምሮ በየአገራቱ ካለው ስር የሰደደ የባህል እና ልማዳዊ አስተሳሰብ የተነሳ ተግባራዊ አልሆነም፡፡ በዚህም ምክንያት አስተያየቱም በመደበኛ የስራ ቅጥር እና የስራ ቦታ የሚፈጸመውን ፆታዊ ትንኮሳ ብቻ የሚመለከት በመሆኑና በቤት ውስጥና ከሀገራቸው ውጭ የሚኖሩ እንዲሁም ህጋዊ ያልሆኑትን የሚያጠቃልል በመሆኑ አስተያየቱ ህጋዊ አስገዳጅነት የሌለው በመሆኑ ሳይፈጸም ቀርቷል፡፡
እንዲሁም እ.ኤ.አ የ1951ዱ ሴቶች የስራ ክፍያ ለመደንገግ የወጣው ዓለም አቀፍ ስምምነት አንቀጽ 1 እና 2 ተመሳሳይ ክፍያ መከፈል እንዳለበት ያስገድዳል፡፡ የአፍሪካ አገራትና ህዝቦች ቻርተርና ተከትሎት የወጣው ፕሮቶኮል አንቀጽ 13 እና 15 ተመሳሳይ ድንጋጌዎች አሏቸው፡፡ ይሁን እንጂ ኢትዮጵያ ስምነቱን አላፀደቀችም፡፡ በዚህም ምክንያት በቂ የህግ ከለላና ፍትህ ሴቶች እንዳያገኙ እያደረገ ይገኛል፡፡
አዲስ ዘመን ታህሳስ 20/2011
ሰላማዊት ንጉሴ