
የኢትዮጵያ ብዝሀ ሕይወት ኢንስቲትዩት በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 291/2005 ከተሰጡት ስልጣንና ኃላፊነቶች መካከል አንዱ የአገሪቱ የብዝሀ ሕይወት ሀብት ከውጭ በሚገቡ ልውጥ ህያዋን እና ወራሪ መጤ ዝርያዎች እንዳይበከል፤ በዚህም ጥፋት እንዳይደርስ ቁጥጥርና ክትትል ማድረግ ነው። ይህንን ኃላፊነቱን እንዴት እየተወጣ እንደሚገኝና በሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ ከኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ከዶክተር መለሰ ማርዮ ጋር ቆይታን አድርገናል።
አዲስ ዘመን፤ ብዝሀ ሕይወት ስንል ምን ማለታችን ነው?
ዶክተር መለሰ፤ ብዝሀ ሕይወት ማለት ሕይወታዊ ሀብት ማለት ሲሆን ሀብቱም ሕይወት ያላቸውን ነገሮች ተለያይነት እንደማለት ነው። ይህም እንስሳትንና ደቂቅ አካላትን የሚያጠቃልል ይሆናል። የእነዚህ መገለጫ ደግሞ በዘረ መላቸው፣ በዝርያቸውና በስርዓተ ምህዳራቸው ነው። ብዝሀ ሕይወትን በአጭር ቃል ለመግለጽ ሕይወት ያላቸውን ነገሮች ተለያይነት ሲሆን የዚህም መገለጫ ጅን ዝርያና ስርዓተ ምህዳር ነው።
አዲስ ዘመን ፤ ከዚህ አንጻር የኢትዮጵያ ብዝሀ ሕይወት ኢንስቲትዩት የሥራ ድርሻና ኃላፊነት ምንድን ነው?
ዶክተር መለሰ፤ ኢንስቲትዩቱ በተሰጠው ስልጣንና ኃላፊነት አማካይነት የመጀመሪያ ስራው ማምበር ሲሆን ቀጣዩ ደግሞ ዘለቄታዊ አጠቃቀምና ማህበረሰቡ በአገሪቱ ባለው ሀብት ፍትሀዊ ተጠቃሚ እንዲሆን ማስቻል ነው። ማምበር አንዳንድ ጊዜ መጠበቅም ይባላል። በዚህ የሥራ ድርሻ ውስጥ እንስሳትና እጽዋት ደቂቅ አካላት ዝርያቸው እንዳይጠፋ ይጠበቃሉ፤ ለምሳሌ «ዘቦታ» ጥበቃ የሚባለው እንስሳቱም ሆኑ እጽዋቱ መጀመሪያ በተገኙበት አካባቢ ላይ እንዲቆዩ ማድረግ ነው። አዝዕርት ላይም እንደዛው ነው። ጤፍን እንደ ማሳያ ብንወስድ የመጀመሪያ መገኛው ምንጃር ሸንኮራ በመሆኑ በእዛ አካባቢ ማህበራትን በማደራጀት ከዛሬ 40 ዓመታት በፊት ከተለያዩ የአገሪቱ ክፍል የተሰበሰቡ የጤፍ ዘሮችን ለእነዚህ ማህበራት በመስጠት እነሱም አባዝተው እዛው ዘርተው ውጤቱን እንዲያዩትና ዘሩን ጠብቀው እንዲያቆዩት ሆኗል።
በተመሳሳይ እንስሳቱም ሸኮ ላይ አዳዲስ የእንስሳት ዝርያዎች አሉ። እነዚህ እንስሳት ጠፍተው የነበሩ ናቸው፤ በዘቦት ጥበቃ መሰረት በአሁኑ ወቅት ቁጥራቸው እንዲጨምርና እንዲያንሰራሩ ሆነዋል። በመሆኑም በመጀመሪያ መገኛቸው ላይ ማህበረሰቡ እንዲንከባከባቸውና እንዲጠብቃቸው አድርገናል።
ደንን በተመለከተም ተመሳሳይ ስራዎች ይሰራሉ። ቦንጋ ላይ በኢንስቲትዩቱ ስር ሆኖ የሚጠበቅ ደን አለ። ይህ መሆኑ ደግሞ በደኑ ውስጥ በብዙ መቶዎች የሚቆጠሩ ዝርያዎች እንዲኖሩ አስችሏል።
በኢንስቲትዩቱ ውስጥም ስድስት የማቀዝቀዣ ክፍሎች ያሉ ሲሆን፤ በነዚህም 89 ዓይነት የአዝርዕትና ሆርቲካልቸር ዝርያዎችና ከ80ሺ በላይ ናሙናዎች ይገኛሉ። ይህ ምናልባትም በአፍሪካ ደረጃ ብቸኛ ያደርገናል። በዚህ ማቀዝቀዣ ክፍል ውስጥ የአዝዕርትና ሆርቲካልቸር ዝርያዎች፣ የደን ዝርያዎች፣ ከአንድ ሺ200 በላይ የሚሆኑ ደቂቃን አካላትም ከተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ተሰብስበው ይገኛሉ። እነዚህ ዝርያዎች ለዘመናት እዚህ ማቀዝቀዣ ክፍል ውስጥ ይቆያሉ ማለት ሳይሆን ከአምስት እስከ 10 ዓመት ከቆዩ በኋላ ወደነበሩበት ሄደው ተዘርተው ውጤታቸው ታድሶ ይመለሳሉ።
በሌላ በኩልም ዘለቄታዊ አጠቃቀም እንዲኖር እነዚህ የተሰበሰቡት ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና ለሌሎች የምርምር ሥራ ለሚሰሩ አካላት ይሰጣሉ።
አዲስ ዘመን፤ በዚህ መልክ ዝርያዎችን የመጠበቅ ሂደት ካለ ታዲያ በዓለም ላይ በአሁኑ ወቅት ጤፍን የእኔ ነው የሚል አካል እንዴት መጣ?
ዶክተር መለሰ፤ የጤፍ ችግር ያው በቀደመው ጊዜ ከደብረ ዘይት ግብርና ምርምር ሲወሰድ ውሉ የተሳሳተ ስለነበር ነው። እኛም የማህበረሰባችን እውቀት ተወሰደ ብለን እየተከራከረን ነው። ይህ ሲባል ደግሞ ህብረተሰቡ ጤፍን የምታክል ቅንጣት ሳር ከሚመሰል ነገር ላይ አምርቶ ለመጠቀም የተጠቀመው ጥበብ ተወሰደ እያልን ማለት ነው። አሁን ላይ ጉዳዩ በህግ ሂደት ውስጥ ነው ያለው።
አዲስ ዘመን፤ በአገሪቱ የመጤ አረሞች እየተስፋፉ እንደመሄዳቸው ኢንስቲትዩቱ ችግሩን ለመቅረፍ ምን ያህል ርቀት ተጉዟል?
ዶክተር መለሰ፤ ኢንስቲትዩቱ በአዋጅ ቁጥር 291/2005 አንቀጽ ስድስት ቁጥር 19 ላይ የአገሪቱ ብዝሀ ህይወት ከውጭ በሚገቡ ልውጥ ህያዋንና ወራሪ መጤ ዝርያዎች እንዳይበከልና ጉዳት እንዳይደርስበት ቁጥጥርና ክትትል ያደርጋል ይላል። ይህ ሲባል በአሁን ሰዓት በአስደናቂ ሁኔታ በኢትዮጵያ ውስጥ ወደ 35 ዓይነት የመጤ ወራሪ ዝርያዎች አሉ፤ ኢንስቲትዩቱም በየዓመቱ ምን ያህል አዳዲስ መጤ ዝርያዎች እንደመጡ፣ ምን ጉዳት እንደሚያደርሱ፣ እንዴት እንደሚራቡና እንዴትስ መቋቋም እንደሚቻል፣ የት አካባቢ በብዛት እንደሚታዩ ያጠናል፤ ለህትመት በማብቃት ያሰራጫል፤ በዚህ ሂደትም እንዲታወቁ ያደርጋል።
ሆኖም ኢንስቲትዩቱ እነዚህን መጤ አረሞች ብቻውን መከላከል አይችልም። ይልቁንም የግብርና ሚኒስቴር፣ የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለስልጣን እንዲሁም የውሃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር ይመለከታቸዋል። የኢንስቲትዩቱ ግዴታ በመጤ አረሞቹ ዙሪያና በሚያስከትሉት ችግር ላይ ለህብረተሰቡ ግንዛቤን መፍጠር ነው።
አዲስ ዘመን፤ ኢንስቲትዩቱ የአገሪቱ ብዝሀ ህይወት ከውጭ በሚገቡ ልውጠ ህያዋንና ወራሪ መጤ ዝርያዎች እንዳይበከልና ጉዳት እንዳይደረስበት ቁጥጥርና ክትትል ከማድረግ አንፃር ምን ሰራ?
ዶክተር መለሰ፤ ለምሳሌ ፕሮሶፒስ የተባለው መጤ አረም በከፍተኛ ሁኔታ የብዝሀ ህይወት ሀብት እንዲጠፋ ነው ያደረገው። በአገሪቱ አንድ ነጥብ ስምንት ሚሊየን ሄክታር የሚሆን መሬትን ሸፍኗል። በተመሳሳይ ላንታና ካማራ ምን ያህል ሸፈነ ስንል ተቋሙ የሰራው ጥናት አለ፤ በስራም ላይ ነው፤ ግን ውስንነቶችም አሉበት።
በመሆኑም እነዚህን ችግሮች ለማስወገድ በዋናነት የሚያደርገው የህብረተሰቡን ግንዛቤ የማስፋት ነው። ከብቶች ቢመገቡት የሚያመጣውን ተጽዕኖ ማሳየትና በተቻለ መጠን የመራባትና የመባዛት አቅሙን እንዲያጣ ማድረግ ነው ሊሰራ የሚችለው።
ኢንስቲትዩቱም ይህንን የግንዛቤ ስራ ለመስራት እየሞከረ ቢሆንም ከችግሩ ስፋት አንጻር ግን እየሰራ ያለው ስራ በቂ አይደለም። በቀጣይ የሰው ሀይልና
በጀቱን በማስተካከል በሬዲዮ፣ በጋዜጣ እንዲሁም ለማህበረሰቡ ቅርብ በሆኑት የማህበረሰብ ሬዲዮ ጣቢያዎች በቂ ትምህርት ለመስጠት ያስባል።
አዲስ ዘመን፤ ኢንስቲትዩቱ እነዚህ መጤ አረሞች ለመከላከልና ለመቆጣጠር የሰው ሀይልና የበጀት ችግር ካለበት ከሌሎች የሚመለከታቸው አካላት ጋር ለምን መቀናጀት አልቻለም?
ዶክተር መለሰ፤ ተቀናጅተን እንሰራለን፤ እንዲያውም በኢንስቲትዩቱ ውስጥ «ብሔራዊ የብዝሀ ህይወት ስትራቴጂና የድርጊት መርሐ ግብር» የሚባል ፕሮጀክት አለ፤ በዚህ ፕሮጀክትም የትምህርት፣ የሴቶችና ህጻናት ጉዳይ፣ የግብርና፣ የንግድና ኢንደስትሪ እንዲሁም የውሃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴሮችንና የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለስልጣንን በማካተት አብረን እንሰራለን። ቅንጅቱና ትብብሩ ቢኖርም ግን ያለውን ሀብት በጋራ አቀናጅቶ መስራት ላይ ክፍተት አለ፤ ይህ ደግሞ ምናልባትም በጋራ የመስራት ባህላችን ደካማ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ የመጣ ይመስለኛል።
በሌላ በኩልም በአገሪቱ ካሉ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጋር የትብብር ስምምነት አለ። ይህም ቢሆን ግን ለምሳሌ መጤ ወራሪ የምንላቸው አረሞችን የመቆጣጠር ሥራ በቀጥታ ግንኙነት ያለው ከአካባቢ ጥበቃ ጋር ነው፤ ስለዚህ ስራውን ወርዶ የመስራቱ አግባብም መሆን የነበረበት ከባለስልጣኑ ጋር ነው። ኢንስቲትዩቱ ግንዛቤ የመፍጠር ችግሩ በብዝሐ ህይወት ሀብቶች ላይ ምን አስከተለ የሚለውን ማየት ነው።
አዲስ ዘመን፤ ኢንስቲትዩቱ ግንዛቤ የመፍጠሩንና የችግሩን ስፋት ያስከተለውን ጉዳት የማሳየቱን ኃላፊነትስ ተወጥቷል?
ዶክተር መለሰ፤ ኢንስቲትዩቱ እነዚህን ስራዎች የመስራት ግዴታ የለበትም፤በተለይም የመከላከልና የማስወገድ ስራውን። ምክንያቱም ኃላፊነቱም አይደለም። አደረጃጀቱም አይፈቅድለትም። ያለው በጀትም በቂ አይደለም። በእኛ አገር ሆኖ ነው እንጂ በሌሎች አገሮች እነዚህን መጤ አረሞች ለመከላከልና ለመቆጣጠር ራሱን የቻለ ተቋም ኖሮ ከፍተኛ በጀት የሚመደብለት ነው። እኛ ግን በዚህ ትንሽ በጀት ልንሰራው አንችልም፤ እኛም የተለያዩ ቦታዎች ላይ ይህንን ተናግረናል።
ማስወገድና ማጥፋቱ ቀርቶ የህብረተሰቡን ግንዛቤ ለማሳደግ እንዲሁም እነዚህ መጤ አረሞች ከየት መጡ? ምን ያህል ቦታ ያዙ? ያስከተሉት ጉዳት ምን ይመስላል? የሚለውን ለመስራት ተቋሙ ሁለት መቶ ተመራማሪዎች ናቸው ያሉት። እነዚህን ይዞ ደግሞ ስራ መስራት በጣም ከባድ ነው። ሌሎች ተጨማሪ በርካታ ስራዎች ስላሉብን።
አዲስ ዘመን፤ ግን ኃላፊነቱ እንዳለባችሁ ይሰማኛልና የሰው ሀይል አደረጃጀታችሁን ለማሻሻልና በጀታችሁ ከፍ እንዲል ያቀረባችሁት ጥያቄ የለም?
ዶክተር መለሰ፤ ለምሳሌ ለመጤ ወራሪ አረሞች ቁጥጥርና ክትትል ለማድረግ ራሱን የቻለ ዳይሬክቶሬት፣ በስሩ የሚመራቸው ሠራተኞችና በጀት ያስፈልጋል። ይህንንም ፐብሊክ ሰርቪስ ሚኒስቴርን አደረጃጀት እንዲስተካከል ጠይቀን ነበር። ምላሹ ግን ‹‹በአሁኑ ወቅት ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ካልሆነ በቀር ማሻሻል አይቻልም›› ነው። በመሆኑም ስራ ይሰራ ከተባለ እነዚህ ነገሮች መስተካከል አለባቸው፤ይህ ባልሆነበት ሁኔታ ግን ወደታለመው ደረጃ መድረስ በጣም አስቸጋሪ ነው የሚሆነው።
አዲስ ዘመን፤ በቅርቡ ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ከእንቦጭ ጋር ተያይዞ ኃላፊነታችሁን አልተወጣችሁም ብሏል?
ዶክተር መለሰ፤ ከዋና ኦዲተር ጋር በቅርበት እየሰራን በጥቅምት ወር እንዲሁም በጥር ወር ላይ የተላላክናቸው ግብረ መልሶች አሉ፤ በቅርቡ ደግሞ ሰኔ ላይ የላክነው አለ። እነዚህ ነገሮች የሚያሳዩት ደግሞ እኛን የሚመለከትና የማይመለከት ነገር እንዳለ ነው። ኢንስቲትዩቱም በአዋጅ ይቆጣጠራል/ይከታተላል የሚል ኃላፊነት ተሰጥቶት እንዴት አይመለከተኝም እላለሁ።
አዲስ ዘመን፤ ታዲያ ይህ የመረጃ ልውውጥ ከነበራችሁ ኦዲት አድራጊው ወደናንተ ሲመጣ ኦዲት ሊያደርገን እንደሆነ አላወቅንም ለምን ተባለ?
ዶክተር መለሰ፤ ስራው ላይ ክፍተት አለ። አለመረዳቶች ይስተዋላሉ፤ የተቀበሉበት መንገድም የጠራ አይመስለንም ብለናል፤ ይህንን ያልንበት ምክንያት ደግሞ ስራው እራሱን የቻለ አካሄድ ስለነበረው ነው። ለምሳሌ ኦዲት አድራጊው ተቋም ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሪፖርት ሲያደርግ እኛ መገኘት ነበረብን፤ ያ አልሆነም። መጀመሪያ ኦዲት አድራጊዎቹ ራሱ ወደ ኢንስቲትዩቱ ሲመጡ የመጡበት መንገድ የክዋኔ ኦዲት የሚጠይቃቸውን መስፈርቶች ሳያሟሉ፤ ኢንስቲትዩቱ የሚመለከተውንና የማይመለከተውን ጉዳይ በግልጽ ሳያስቀምጡ ነበር ወደ ስራው የገባነው።
አዲስ ዘመን፤ የክዋኔ ኦዲት የሚያስፈልጋ ቸውን መስፈርቶች ለማሟላት ለምን አልተቻለም?
ዶክተር መለሰ፤ መስፈርቶችን አብረን ያላወጣነው ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከተው ምክትል ዋና ዳይሬክተሩን ነው፤ ሌላው አርክቦትና ጥቅም ተጋሪነት የሚባል ዳይሬክተር አለ እርሱም ይመለከተዋል፤ የተጠየቁትም እነርሱ ናቸው፤ ከእነርሱ ጋርም የትኛው ይመለከተናል ወይም አይመለከተንም የሚለውን ለመቅረጽና የመጡት ባለሙያዎችም ስለ ኢንስቲትዩቱ እንዲያውቁ እናደርጋለን ተብሎ ለዋና ኦዲተር የተጻፈ ቢሆንም ለእርሱ ምላሽ ሳይሰጥ በቀጥታ ወደ ስራ ተገባ።
አዲስ ዘመን፤ ይህ ሳይሆን ታዲያ ምን ዓይነት መጠይቆች መጡ?
ዶክተር መለሰ፤ ጥያቄዎቹ እምቦጭን በመካኒካል በኬሚካል መከላከል ጥቅም ላይ እንዲውል ማድረግ በወንዞችና ሀይቆች ላይ ምልከታ ማድረግ ወረርሽኙ እንዳይከሰት ፈጣን ምላሽ መስጠት የሚል ይገኝበታል። እነዚህ ሁሉ ነገሮች ደግሞ የኢንስቲትዩቱ የስራ ኃላፊነቶች አይደሉም። እንቦጭን ጥቅም ላይ ማዋል እኮ ለምን የምርመር ተቋማት አይሰሩትም? ሊሰሩት ይችላሉ። እኛ የምንሰራው በብዝሀ ህይወት ሀብቱ ላይ ምን ያህል አደጋ አስከትሏል፣ ሽፋኑ እንዴት ነው የሚለውን በማየት ለህብረተሰቡ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራ ነው። በመሆኑም መመዘኛዎቹ የጋራ አልሆኑም፤ ቀድመን ላቀረብነው ጥያቄ ምላሽ አልተሰጠንም። የኢንስቲትዩቱ የስራ ድርሻና ኃላፊነት ተለይቶ ታውቆ አይደለም የቀረበው የሚለው ነው።
አዲስ ዘመን፤ እነዚህን መስፈርቶች በጋራ ለማውጣት ለምን አልተቻለም?
ዶክተር መለሰ ፤ ሰዎቹ ፍቃደኛ አልሆኑማ ።
አዲስ ዘመን ፤ ምናልባት ከእርስዎ ምክትል ጋር ተስማምተው ከሆነስ?
ዶክተር መለሰ፤ አልተስማሙም። በመጨረሻ በመጡበት ወቅት እኮ ሁላችንም አብረን ቁጭ ብለን ምላሽ ስጡ ተባለና ምላሽ ሰጠን፤ በዚያውም ኢንስቲትዩቱን የማሳወቅም ስራ ሰራን። ከዛም የመውጫ ሰብሰባ ለሚባለው ቀን ያዙልን ስላሉ የክልል ማዕከላት ባለሙያዎቻችንን በሙሉ ጠርተን ቀን ያዝንላቸው። የሰጡን ግብረ መልስ ግን አረዳዳቸው የተለየ ሆነብን፤ ይህም ቢሆን ‹‹ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሚቀርብበት ግዜ አብረን እንገኝ›› አልን፤ ያም አልሆነም። ግን እዚህ ጋር እንደ አገር የምናስብ ከሆነ እንቦጭ ብቻ ሳይሆን ሰፋ አድርጎ ማሰብ ይበጀናል።
አዲስ ዘመን፤ ፌዴራል ኦዲት መስሪያ ቤት እምቦጭ ላደረሰው ጥፋት እናንተን ተጠያቂም አድርጓልና በዚህስ ላይ ያልዎት አስተያየት ምንድን ነው?
ዶክተር መለሰ፤ አዎ ብለዋል፤ግን ተጠያቂ መሆን እኮ ህግና ስርዓትን በተከተለ መንገድ ነው። ኢንስቲትዩቱ ምን ኃላፊነት ከምን ያህል የሰው ሀይልና በጀት ጋር ተሰጥቶት ነው መወጣት ያልቻለው የሚለውም ይታያል። ፌዴራል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት በመንግሥት የተሰጠው ስልጣንና ኃላፊነት አለ፤ አዎ እንገዛለን፤ ለእኛም የተሰጠን መብትና ስልጣን አለ፤ ሌላው የሚመለከተው ይገዛል። ሁላችንም ደግሞ ለአገራችን ብለን እንሰራለን። ከዚህ በፊት ያልነበረ መጥፎ የስራ ግንኙነትም መወገድ ያለበት ነው።
እዚህ ጋር እንደ እምቦጭ ካሉ መጤ ዝርያዎችን የመከላከል ግንዛቤ የመፍጠርና ሌሎች ተግባራትን ለኢንስቲትዩቱ ተሰጥቶታል ብለናል ግን ደግሞ ይህንን ስራ ለመስራት የሚያስችል አደረጃጀት የለም እያልን ነው፤ጎን ለጎን ግን የአካባቢና ደን ኮሚሽን ውስጥ «ደህንነተ ህይወትና ወራሪ መጤ ዝርያዎች» ዳይሬክቶሬት አለ፤እኛ ጋር ግን ይህ የለም፤ በዚህ ልክ አደረጃጀቱ ተስተካክሎ ቢመጣ እኛ ከሌላው በተሻለ ስለ ብዝሀ ህይወትም ግንዛቤ ስላለን ስራውን በሚገባ እንሰራዋለን።
አዲስ ዘመን፤ አንዳንድ ሰብሎች በመዳቀል የተሻለ ምርት ይሰጣሉ ተብሎ አገር ውስጥ ሲገቡ አብሯቸው የሚያጠፋቸው ተባይም እንዲይዙ ይሆናል የሚል በግብርና ምርምር ባለሙያዎች የሚነገር ነገር አለ፤ እናንተ ይህንን እንዴት እየተከታተላችሁት ነው? ከተባይ የጸዳ ሰብል ለመያዝስ ምን ሰራችሁ?
ዶክተር መለሰ፤ እዚህ ጋር የኃላፊነቶች መደራረብ አለ፤ለምሳሌ የዘር አዋጅ የሚባል አለ። በዚህ አዋጅ መሰረት ዘሮችን ከውጭ ማስገባት የግብርና ሚኒስቴር ኃላፊነት ነው፤ ይህንን መሰል ስራ ደግሞ ሌሎችም ይሰራሉ። በመሆኑም ይህ የኃላፊነት አሰጣጥና መደራረብ ሊፈተሽ ይገባል።
የኢትዮጵያ ህግ «ማንኛውም የብዝሀ ህይወት ሀብት ከውጭ እንዲገባ ወይም በሚወጣበት ወቅት ቁጥጥር ክትትል ያደርጋል» ይላል። ግን አራዊት ብዝሀ ህይወት ቢሆኑም ለአካባቢ ጥበቃ ተሰጥቷል፤ ከዘርና ከሌሎች ነገሮች ጋር የተያያዙትን ደግሞ ሌላ ባለድርሻ አካል ወስዷል፤ አንዳንዶቹን ደግሞ ለእኛ ኢንስቲትዩት ተሰጥቷል፤ ይህ ከሚሆን ግን ለአንድ ተቋም ስራውን ሰጥቶ መከታተሉ ለቁጥጥርም አመቺ ነው። በመሆኑም ህጎች መሻሻል ቢችሉ ጥሩ ነው።
አዲስ ዘመን፤ ኢንስቲትዩቱ በተሻለ ኃላፊነቱን ይወጣ ዘንድ ከማን ምን ይጠበቃል? ምንስ ሊደረግለት ይገባል?
ዶክተር መለሰ፤ የተቋሙን አቅም መገንባት በጣም ትኩረት ሊያገኝ የሚገባው ስራ ነው። በቁጥርም በእውቀትም እንዲሁም በስራ ልምዳቸውም የተሻሉ ተመራማሪዎች አሉን። ሆኖም ከዚህ በላይ ሊሆን ይገባል። ይህ ሲደረግም ደግሞ ላቦራቶሪዎች መጠናከር አለባቸው። በእርግጥ በአሁኑ ጊዜ 187 ሚሊየን ብር ተፈቅዶልን በግቢው ውስጥ ሁለት ህንጻዎችን በማሰራት ላይ ነን። ይህን የመንግሥት ድጋፍ እያመሰገንን በቀጣይ ብዝሀ ህይወት እራሱ ምን ማለት ነው? የሚለውን ነገር በህብረተሰቡ ውስጥ የማስረጽ ስራንም ለመስራት የሚያስችል አቅም እንድናገኝ መደረግ አለበት።
በሌላ በኩልም መንግሥት ለብዝሀ ህይወት ሀብት ትኩረት ሊሰጥ ይገባል። ምክንያቱም አንዳንድ ጊዜ ባለመረዳትም ሊሆን ይችላል የብዝሀ ህይወት ሀብትን በሚጎዳ መልኩ አንዳንድ የልማት ስራዎች ይካሄዳሉና ይህም ሊታሰብበት የሚገባ ነው።
በመሆኑም ብዘሀ ህይወት በሚፈለገው ልክ ይጠበቅ ካልን በክልል፣ በወረዳ እስከ ቀበሌ ድረስ ግንዛቤውን ማስፋት እንዲሁም ራሱን ችሎ ጠንካራ ሆኖ ኃላፊነቱን እንዲወጣ ማድረግና መዋቅሩንም በደንብ ማሻሻል ያስፈልጋል።
አዲስ ዘመን፤ በጣም አመሰግናለሁ።
ዶክተር መለሰ፤ እኔም አመሰግናለሁ።
አዲስ ዘመን ረቡዕ መስከረም 7/2012
እፀገነት አክሊሉ