በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን አጋማሽ ከአጠቃላይ አገራዊ ምርት ዕድገት (ጂዲፒ) የኢንዱስትሪው ዘርፍ ከ15 በመቶ ወደ 26 በመቶ ማደጉን የፕላንና ልማት ኮሚሽን በቅርቡ ገልጿል፡፡ የኢንዱስትሪው ማደግ በግብርና ላይ ጥገኛ የሆነው ኢኮኖሚ ተረጋግቶ እንዲያድግና የሰዎችም የኑሮ ሁኔታ እንዲለወጥ የሚያደርግ መሆኑን የኢኮኖሚ ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡
የኢኮኖሚ ባለሙያው ረዳት ፕሮፌሰር ዶክተር ተሾመ አዱኛ እንደሚናገሩት፤ የኢንዱስትሪውን ማደግ ፋይዳ ለመረዳት የኢንዱስትሪን ባህሪ ማወቁ መልካም ነው፡፡ ኢንዱስትሪውን ከሌሎቹ የግብርናና የአገልግሎት ዘርፉ ጋር ስናወዳድረው በባህሪው የተለያየ ጥቅሞች አሉት፡፡ ለምሣሌ ግብርና አብዛኛውን ጊዜ በዝናብ ላይ ጥገኛ ነው፡፡ ኢንዱስትሪ ግን በዝናብ ላይ ሳይሆን በእውቀትና በፈጠራ ላይ ይመሰረታል፡፡
ዶክተር ተሾመ፣ ‹‹ግብርናን ስንመለከት ዋጋው ተለዋዋጭ ነው፡፡ ኢንዱስትሪ ግን እንደ ግብርና ከፍና ዝቅ የሚል አይደለም፡፡ ምክንያቱም የማይበላሽ ስለሆነ በተፈለገ ጊዜ ማስቀመጥና መሸጥ የሚያስችል ነው›› ሲሉ ጠቅሰው፤ ‹‹ከዚህም ባሻገር ምናልባት ግብርና ሊሰጥ የሚችለው ጤፍ፣ ስንዴና መሰል ነገሮች ሲሆን፣ ኢንዱስትሪው ውስጥ ግን የተፈለገው ሁሉ ማግኘት የሚቻልበት ነው›› ሲሉ ያስረዳሉ፡፡
እንደ እርሳቸው ገለፃ፤ የኢንዱስትሪው ዘርፍ ማደግ ግብርናውም እንዲያድግ ያደርጋል፡፡ ምክንያቱም አብዛኛውን ጊዜ ኢትዮጵያ ውስጥ ለግብርናው መውደቅ አንዱ ምክንያት ከግብርና የሚወጡ ምርቶችን የሚቀበሉ ኢንዱስትሪዎች ባለመኖራቸው ነው፡፡ ስለዚህ ኢትዮጵያ ውስጥ ኢንዱስትሪው በዚህ ሁኔታ ማደግ በግብርና ጥገኛ የሆነው ኢኮኖሚ ተረጋግቶ እንዲያድግና አደጋም ሲፈጠር የመሸከም አቅም እንዲኖረው ያደርጋል፡፡
ረዳት ፕሮፌሰር ዶክተር ተሾመ፣‹‹ ባለፉት ሁለትና ሦስት ዓመታት ግብርናው ዝቅ እያለ በመጣ ቁጥር ራሱ ከማኑፋክቸሪንግ የሚወጡ ምርቶችና ሌሎችም ስለነበሩ ኢኮኖሚው ከ8 እና 9 በመቶ አካባቢ ያድግ ነበር፡፡ ስለዚህም ኢንዱስትሪው ለሁሉም ነው›› ሲሉ ያብራራሉ፡፡
በኢንዱስትሪው ዕድገት ኢትዮጵያ ከኬንያ ታንሳለች፡፡ በመቶኛ ሲሰላ ኬንያ 30ዎቹ ውስጥ ስትሆን የኢትዮጵያ ደግሞ 20ዎቹ ውስጥ ትገኛለች፡፡ አሁን ግን ኬንያ ከኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ጋር ስትወዳደር በጂዲፒ ካለፉት ሁለት ዓመት ጀምሮ ኢትዮጵያ ናት የበለጠችው፡፡ እንዲያም ሆኖ የኢንዱስትሪ ዕድገቱ ከኢትዮጵያ ጋር ሲተያይ ኬንያን በጣም ተወዳዳሪ አድርጓታል፡፡ ስለዚህም ከዚህ ቀደም በተለይ ከአፍሪካ ቀንድ አገራት ከሆኑት ጋር የማንወዳደር የነበረ ቢሆንም በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ዕድገት በመጨመሩ ተወዳዳሪነቷን እንደሚያጠናክርላት መሆኑን አመልክተዋል፡፡ ይህ ሲሆን ደግሞ የሰዎች የኑሮ ደረጃ እንደሚሻሻል ተናግረዋል፡፡
እንደ ረዳት ፕሮፌሰር ዶክተር ተሾመ አነጋገር፤ ግብርና በደንብ አይክፍልም፤ ቋሚ ክፍያ የለውም፡፡ ኢንዱስትሪው ግን የሚከፍለው ከፍተኛ ደመወዝ ነው፤ ክፍያው ደግሞ እውቀትን መሰረት ያደርጋል፡፡
የኢንዱስትሪ ዕድገቱ ከውጭ ምንዛሬ አኳያ ሲታይ ከፍተኛ ጥቅም አለው፡፡ ምክንያቱም ወደ ውጭ የሚላከው ምርት በርካታ ይሆናል፡፡ የምርት ጥራትም እንዲጨምር ያደርጋል፡፡ ለውጭ ገበያ የሚቀርበው የኢንዱስትሪ ምርት ሲጨምር ከገቢ ምርት ጋር ተመጣጣኝ ይሆናል፣ በሂደትም ይቀንሳል፡፡ በተበጣጠሰና ግንኙነት በሌላቸው ኢንዱስትሪዎች የአገሪቱን ኢንዱስትሪ መለወጥ አይቻልም፡፡ ስለዚህ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍል እየተመረቁ ያሉት የኢንዱስትሪ ፓርኮች ዕድገቱን ለማፋጠን አስተዋጿአቸው ከፍተኛ መሆኑንም ያመለክታሉ፡፡
ረዳት ፕሮፌሰር ዶክተር ተሾመ፣ ኢትዮጵያ የኮሚሳ ነፃ ገበያ አባል እስካሁን አለመሆኗንና የምሥራቅ አፍሪካም ነፃ የኢንዱስትሪ ንግድ ለመክፈትም አለመቻሏን ጠቅሰው፤ አሁን ያለው ዕድገት ግን በምሥራቅ አፍሪካ ተወዳዳሪ እንድትሆን የሚያደደርጋት ነው ብለዋል፡፡
የኦሮሚያ ኢኮኖሚስቶች ባለሙያ ማህበር ፕሬዚዳንት ዶክተር ጉቱ ቴሶ በበኩላቸው፤ ኢንዱስትሪው ማደግ የሰውን የኑሮ ደረጃ እንደሚያሻሽልና የውጭ ምንዛሬውንም ማሳደግ እንደሚችል ያመለክታሉ፡፡ በተጨማም አገሪቱ ከተለያዩ አገሮች ጋር የኢኮኖሚ ትስስሯን እንድታጠበቅ ያደርጋል ይላሉ፡፡
እርሳቸው እንደሚሉት፤ ኢንዱስትሪው በተለይ በማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ማደጉ ዘላቂ የሥራ ዕድል ከመፍጠር አንፃር ትልቅ አስተዋጽኦ ያለው፡፡ በግብርና ላይ የሚፈጠሩ የሥራ ዕድሎች ሁልጊዜ ጊዚያዊ ናቸው፡፡ የአገልግሎት ዘርፉ ደግሞ ብዙ የሰው ኃይል ከመቅጠር አኳያ አነስተኛ ነው፡፡ ስለዚህ ብዙ የሥራ ዕድል ከመፍጠርና ዘላቂ ከመሆን አንፃር የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ ትልቅ አስተዋጽኦ አለው፡፡
ዘርፉ ሊያስገኘው የሚችለው የውጭ ምንዛሪ ግብርና ከሚያስገኘው ይበልጣል። ምክንያቱም በግብርና ተመርቶ የሚገኘው ገንዘብ በትንሽ የኢንዱስትሪ ምርት ተመርቶ ከሚሸጠው በታች ነው፡፡ ለምሣሌ ኢትዮጵያ ብዙ ቡና ልካ ከምታመጣው የውጭ ምንዛሪ ይልቅ የውጭ ኩባንያዎች አንድ ማሽነሪ ብቻ ወደ ኢትዮጵያ ልከው የሚያገኙት በእጥፍ የሚበልጥ መሆኑን ይገልፃሉ፡፡
‹‹ማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ ብዙ የገበያ ትስስርን ይፈጥራል፡፡ ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካን ብንወስድ መቀበል ያለብን ጥጥ ነው፡፡ በጥጡ የምናመርተው ጨርቅ ነው፡፡ጨርቁን ደግሞ ሌሎች ፋብሪካዎች ልብስ ነው የሚያመርቱበት፡፡ በዚህ ዓይነት ዑደት ሌሎችንም የማንቀሳቀስና ምርታማ እንዲሆኑ የማድረግ ኃይል አለው›› ይላሉ፡፡
ኢትዮጵያ የኮንስትራክሽን ዕቃዎችን ለማስገባት ስትል ብዙ የውጭ ምንዛሪን እንደምታወጣ የሚናገሩት ዶክተር ጉቱ፣ የዘርፉ ማደግ እነዚህን ዕቃዎች በአገር ውስጥ እንዲመረቱ ዕድል የሚፈጥር ስለሚሆን የውጭ ምንዛሪውን ማስቀረት እንደሚቻል ይገልፃሉ፡፡ ይህ ወጪ ሲቀር ደግሞ የአገሪቱ የንግድ ሚዛን እንዲሻሻል ያደርገዋል፡፡ ስለሆነም የኢንዱስትሪው ዘርፍ ለውጥ ማሳየቱ የተቀመጠውን የልማት ዕቅድ ከማሳካት አንፃር የተሻለ መሆኑንም ነው ያመለከቱት፡፡
በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን የኢንዱስትሪውን ዘርፍ (ማኑፋክቸሪንግ፣ ኮንስትራክሽን፣ የጥቃቅንና አነስተኛ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ) በየዓመቱ በአማካይ በ20 በመቶ ለማሳደግ እና ከጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት ያለውን ድርሻ በ2007 ከነበረት 15.1 በመቶ በ2012 ወደ 22.3 በመቶ ለማድረስ የሚሠራ መሆኑን ተቀምጧል፡፡
ዶክተር ጉቱ እንደሚሉት፤ ትርጉም ያለው የኑሮ ለውጥ በአገር ደረጃ እንዲመጣና ኢኮኖሚው እንዲያድግ በኢንዱስትሪ ዘርፍ ያሉ ፖሊሲዎቻችና ስትራቴጂዎች ከጊዜ ወደ ጊዜ ዓለም አቀፍ ገበያ መር በሆነ መልኩ የተቃኑ ሊሆኑ ይገባል፡፡ ከውጭ አገራት ጋር የሚደረጉ ግንኙነቶች የፖለቲካ ብቻ ሳይሆኑ የንግድም መሆን ይጠበቅባቸዋል፡፡ በተለይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ የጀመሩት ሥራ ጠንካራ መሰረት ላይ መገንባት መቻል አለበት፡፡
የጥራትና ደረጃ መዳቢ ተቋምም በአግባቡ የሚሠራ አድርጎ መገንባትም አስፈላጊ ነው፡፡ ምክንያቱም ማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ በጥራት ብቻ ነው በገበያ ውስጥ መቆየት የሚችለው፡፡ ተቋማት ጥራትን የጠበቁ አገልግሎት መስጠት ከቻሉ በማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ ካለን መልክዓ ምድራዊ አቀማመጥና በምሥራቅ አፍሪካ ላይ አገሪቱ ካላት ሚና አንፃር ሲታይ ወደፊት በተሻለ ፍጥነት እንድትራመድ ማድረግ ይቻላል፡፡
ረዳት ፕሮፌሰሩ ደክተር ተሾመ በበኩላቸው፤ መንግሥት አገሪቱ ይበልጥ በኢንዱስትሪው ዘርፍ እንድታድግ የትኩረት አቅጣጫውን አዋጭ በሆኑ ነገሮች ላይ ማድረግ እንደሚገባው ይናገራሉ፡፡ ዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቀ አሠራርን፣ አፈፃፀምንና ክትትልን መተግበር ያስፈልጋል፡፡ እነዚህን የሚተገበሩ ከሆነ ከጥቂት ዓመታት በኋላ እንደ ቻይና ተወዳዳሪ መሆን እንደሚቻልም ነው ያመለከቱት፡፡
አዲስ ዘመን ታህሳስ 9/2011
በአስቴር ኤልያስ