የኢትዮጵያ ዘመናዊ ሙዚቃ እንቁ

ገና የ13 ዓመት ታዳጊ ሳለ ሙዚቃን የጀመረው የቀድሞው ድምፃዊ ሙሉቀን መለሰ በ1958 ዓ.ም በፓትሪስ ሉሙምባ ምሽት ክለብ ፈጣን ኦርኬስትራን ተቀላቅሎ በመግባት ለሁለት ዓመታት ያህል መሥራት ችሏል። የሙዚቃ ድርሰት ሲመርጥ በጣም የተለየ ችሎታ እንዳለው ይነገርነታል።በዚህ ምክንያትም እንደ ዓለምፀሐይ ወዳጆ እና ተስፋዬ ለሜሳ ላሉ የሙዚቃ ደራሲያን ልዩ ቦታ ይሰጣል።

ተስፋዬ አበበ (ፋዘር)፣ ይልማ ገብረ አብ፣ አበበ መለሰ፣ ሰለሞን ተሰማ፣ ኩኩ ሰብስቤ እና ሌሎችም ግጥም እና ዜማ ቢሰጡትም፣ ግጥሞቹን እና ዜማዎቹን አንጥሮ የሚለይበት የራሱ ልዩ ተሰጥኦ አለው።በአንድ ወቅት በኢትዮጵያ ሬዲዮ እሁድ ጠዋት ፕሮግራም ላይ ባደረገው ቆይታ፣ “ለትዝታ ሙዚቃ ልዩ አመለካከት አለኝ፤ ፍቅር ውስጥም ትዝታ ስላለ ማለት ነው፤ እኔ ሙዚቃን ስሠራ በራሴ ቀለም ነው የምሠራው፤ ይህ ደግሞ ተወድዶልኛል፤ ባይወደድልኝ ኖሮ አድማጭ አላገኝም ነበር” ብሏል፡፡

እናቱ በልጅነቱ በመሞታቸው ምክንያት የሰው ፊት በማየቱ ይመስል “እናቴ ስትወልደኝ መች አማከረችኝ” የሚለው ዘፈኑ የተለየ ስሜት ይሰጣል። ሙሉቀን መለሰ በቀድሞው ጎጃም ጠቅላይ ግዛት አነደድ ወረዳ ዳማ ኪዳነ ምሕረት በምትባል መንደር በ1946 ዓ.ም ነው የተወለደው። አስር ዓመት ሲሆነው እናቱ ስለሞቱ አዲስ አበባ ይኖሩ የነበሩት አጎቱ እንዲማር ብለው የወሰዱት ሲሆን፣ ኮልፌ ጳውሎስ ትምህርት ቤት ገብቶ መማር ጀመረ።

በዚህ መሀል የአጎቱ ቤት ስላልተመቸው ከቤት ወጥቶ ኮልፌ ሕፃናት ማሳደጊያ ገባ። የተቋሙ አስተዳዳሪ ይወዱት ስለነበር ‘ኤልቪስ’ ይሉት እንደነበረ ከስብሐት ገ/እግዚአብሔር ጋር በ1973 ዓ.ም ‘ፀደይ መጽሔት’ ላይ ባደረገው ቃለመጠይቅ ላይ ተናግሯል። ለሙዚቃ ልዩ ፍቅር ስለነበረው ከትምህርቱ ጎን ለጎን በልጆች ማሳደጊያው አካባቢ በተከፈተው የሙዚቃ ትምህርት ቤት ገብቶ ለስድስት ወራት ሰልጥኗል። በዚህ መሀል እህቱ ስለታመመች ወደ ሀገር ቤት ሄደ። ጥቂት ቆይቶም ወደ አዲስ አበባ ተመልሶ ሥራ ማፈላለግ ጀመረ።

ወደ ምድር ጦር ሙዚቃ ክፍል ሄዶ በሙዚቀኛነት ሊቀጠር ቢጠይቅም ተቀባይነት ሳያገኝ ቀረ።ነገር ግን ልጅነቱን እና ችግሩን አይተው ሻይ የማፍላት ሥራ ሰጡት። በዚህ ሥራ ላይ እያለም የተከሰተውን ሲያስታውስ፣ “ምድጃዋ የኤሌክትሪክ ነበረች፤ ባንድ ቀን ውስጥ ሶስት ጊዜ ኮረንቲ ያዘኝ” ብሎ ነበር። በዚህ ሁኔታ ለስድስት ወር ያህል ከሠራ በኋላ ሥራውን ትቶ በመውጣቱ ለተወሰኑ ወራት ተንከራተተ።

ከብዙ መንከራተት በኋላ አቡነ ጴጥሮስ ሐውልት አካባቢ በሚገኝ አንድ ሻይ ቤት ተቀጥሮ መሥራት ጀመረ። ሙሉ ቀን ታታሪ እና አመለ ሸጋ በመሆኑ የሻይ ቤቱ ባለቤት ይወዱት እና ይረዱት ነበር። በሻይ ቤቱ እየሠራ በነበረበት ወቅት ሀርሞኒካ የሚጫወት ጓደኛ ስለነበረው ሻይ ቤቱ ቁጭ ይሉና ጓደኛው ሀርሞኒካውን ሲጫወት ሙሉቀን ይዘፍናል።

አንድ ቀን ሙሉቀን እና ጓደኞቹ አብረው ሲጫወቱ ያመሹና አንዱን ጓደኛቸውን ለመሸኘት ሲሄዱ፣ ደጃች ውቤ ሰፈር ሲደርሱ የውቤ በረሃ የምሽት ቤቶች ልዩ ልዩ ቀለማት መብራቶች ሙሉቀንን በጣም ያስደንቁታል። በተለይም ትኩረቱን ስለሳበው አንድ ለየት ያለ ቤት ጓደኛቹን ሲጠይቃቸው ቤቱ ‘ፓትሪስ ሉሙምባ የምሽት ክለብ ይባላል’ ይሉታል።

ወደ ክለቡ ገብቶ ሥራ እንዲሰጡት የክለቡን ባለቤት ወ/ሮ አሰገደች አላምረውን ጠየቃቸው። ሙዚቃ እንዲፈተን ከቻለ እንደሚቀጥሩት፣ ካልቻለ ደግሞ ሌላ ሥራ እንደሚሰጡት ቃል ገቡለት። ጥላሁን ገሠሠ እና ዓለማየሁ እሸቴን አስመስሎ ይዘፍን የነበረው ሙሉቀን የተሰጠውን ዕድል ተጠቅሞ በባዶ እግሩና በቁምጣ ሱሪ መድረኩ ላይ ወጥቶ “ለእውነት እሞታለሁ አልሳሳም ለነፍሴ” እና “እንክርዳድ” የተሰኙ የጥላሁን ዘፈኖችን አቀረበ።

እዚያው ምግብ እና ማደሪያ ተሰጥቶት በ90 ብር ወርሃዊ ደመወዝ መሥራት ጀመረ።ወቅቱን ሲያስታውስም፣ “ዘጠና ብር ስቀጠር ሚልየነር የሆንኩ ነው የመሰለኝ!” ብሎ ነበር።

በፓትሪስ ሉሙምባ የምሽት ክለብ እየተጫወተ እያለ ፖሊስ ኦርኬስትራ ተቀጠረ።ለፖሊስ ኦርኬስትራ በተቀጠረ በሦስተኛ ቀኑ ከኦርኬስትራው ጋር ወደ መቀሌ ተጉዞ የ“ወይዘሪት ትግራይ” የቁንጅና ውድድር ሲደረግ የጥላሁን ገሰሰን ዘፈኖች ዘፈነ። ታዳሚውም ሙዚቃውን በጣም ወደደው፡፡

ተስፋዬ አበበ(ፋዘር) የደረሷቸውን “እምቧይ ሎሚ መስሎ”፣ “እናቴ ስትወልደኝ መች አማከረችኝ” እና “ልጅነት” የተባሉትን ሦስት ዘፈኖች በሕዝብ ፊት ይዘፍን ጀመር። በወቅቱ የኦርኬስትራው ድርሰት እና ዝግጅት ኃላፊ የነበሩት ተስፋዬ አበበ (ፋዘር) ሙሉቀን ወደ ፖሊስ ኦርኬስትራ የተቀላቀለበትን ሁኔታ ሲያስታውሱ፣ “በምሽት ክለብ ብዙ ቢቆይ ኖሮ ከዕድሜው አንጻር ይበላሽ ነበር፤ እኛ ጋር እንደመጣ ምንም ልምምድ ሳያስፈልገው ነበር ሥራ ውስጥ የገባው” ይላሉ።በፖሊስ ኦርኬስትራ ውስጥ በሠራቸው ዘፈኖች ታዋቂነቱ እየጨመረ ሄደ። ጋዜጦቸም “ኮከብ ድምጻዊ ተጫዋች” በማለት ስለሱ መጻፍ ጀመሩ። ከሦስት ዓመታት በኋላ ከፖሊስ ኦርኬስትራ ጋር ተለያየ።

ሰሎሞን ተሰማ የደረሰውን ‘የዘላለም እንቅልፍ’ የሚለውን ግጥም እና አቡበከር አሸኬ የደረሰውን ‘ያላየነው የለም’ የሚሉ ዘፈኖችን በሸክላ አስቀርጾ ለሕዝብ ለቀቃቸው። በዚህም ታዋቂነቱ እየጨመረ መጣ። በ1972 ዓ.ም ላይ ደግሞ ከዳህላክ ባንድ ጋር ተቀላቅሎ ሠርቷል። እስከ 1980ዎቹ ድረስ በነበሩት ዓመታት እጅግ ተወዳጅ የሙዚቃ ሥራዎችንም ሠርቷል። ሙሉቀን በተጨማሪም ከእኩዬተርስ ባንድ እና ከኢትዮ ስታር ባንድ ጋር የሙዚቃ ሥራዎቹን ሠርቷል፡፡

ሙዚቃ በቃኝ ብሎ ራሱን ከሙዚቃው ዓለም እስካገለለበት ጊዜ ድረስ ለ17 ዓመታት በርካታ የሙዚቃ ሥራዎችን ለትውልድ አበርክቷል። በተለይ ባሕላዊ ጨዋታዎችን በዘመናዊ ለዛ ሲጫወት ወደር የለሽ ነበር። ገጣሚ እና ደራሲው ይልማ ገብረ አብ እንደሚለው እንደ ሳንሱር ሙሉቀንን ያማረረው ነገር የለም።በሳንሱር ስድስት ሥራዎቹ ሲሰረዙበት እንባ አውጥቶ ማልቀሱን ከአበበ መለሰ ጋር እንደተመለከቱት ይልማ ያስታውሳል፡፡

ሙዚቃን አቁሞ ወደ መንፈሳዊ መዝሙር የሄደበት የመጨረሻ ሙዚቃው “ነይ ነይ ወዳጄ ነይ ነይ” የሚለው ዘፈን እንደሆነ የትራምፔት ተጫዋቹ እና ሙዚቃ አቀናባሪው ሻምበል መኮንን መርሻ ያስታውሳሉ።ከ1980ዎቹ በኋላ ፊቱን ወደ መንፈሳዊ ሥራዎች በማዞር የመዝሙር ሥራዎችን እየሠራ እስከ ህልፈተ ሕይወቱ ድረስ በሀገረ አሜሪካ ኑሮውን አድርጎ ቆይቷል።

ተስፋዬ አበበ(ፋዘር) የደረሷቸውን “እምቧይ ሎሚ መስሎ”፣ “እናቴ ስትወልደኝ መች አማከረችኝ” እና “ልጅነት” የተባሉትን ሦስት ዘፈኖች ውስጥ እናቴ ስትወልደኝ መች አማከረችኝ” ያለው ሰንኝ እንዲህ ይላል…

የለም ህያውነት ዘላለም መደሰት

ከሞት ተከልሎ እንዳማሩ መቅረት

የዓለም አሻጋሪ ኃላፊ ሲነጋ

ሳያውቀው ይሸኛል በተኛበት አልጋ።

ሌላዋ ከፍተኛ ዝና የተጎናፀፈባት ዘፈኑ “ሄደች አሉ” በ1964 ዓ.ም. በሸክላ ተቀርጾ ስወጣ፣ ከሦስት ዓመታት በኋላ “ወተቴ ማሬ” እና “እቴ እንዴት ነሽ ገዳዎ” የተሰኙት ዜማዎቹ በተመሳሳይ በሸክላ ታትመው አድማጭ ጆሮ ደረሱ። ሙሉቀን ለየት ያለ አጨዋወቱ ከፍተኛ ተወዳጅነትን አትርፎለታል። ሙሉቀን መለሰ ባሕላዊ እና ዘመናዊ ስልቶችን አዋህዶ በመጫወትም ይታወቃል።

<<ስትሞት ስምህ ህያው ሆኖ ከመቃብር በላይ እንዲኖር ከፈለክ ወይ መጽሐፍ ፃፍ አልያም የማይረሳ ታሪክ ሥራ እንደሚባለው>> ሙሉቀን መለሰ በኢትዮጵያ የሙዚቃ ታሪክ በሥራዎቹ የማይሞት ህያው ስም ያለው የማይዘነጋ የኢትዮጵያ ዘመናዊ ሙዚቃ ባለታሪክ ነው።

በአንድ ወቅት ከሙዚቃ ሥራዎቹ መካከል የትኛውን አብልጦ እንደሚወድ የተጠየቀው ሙሉቀን ሁሉንም ሥራዎቹን ዕኩል እንደሚያያቸው በመግለጽ በዜማ እና በዘፈን የተለዩ ናቸው የሚላቸውን ጠቅሶ ነበር።

“…በጣም የሚያረኩኝ…በዜማው እና በዘፈኑ…‘ሰውነቷ’ እና ‘ሆዴ ነው ጠላትሽ’…በሙዚቃ ጥራት እና ባሠራር ደግሞ፣ ሙላቱ አስታጥቄ ያቀነባበራቸው እና ከዳህላክ ባንድ ጋር የዘፈንኳቸው ‘ቼ በለው’ እና ‘ውቢት” የተባሉትን ለእሱ ከሌሎቹ የተለዩ ነበር።

ሙሉቀን እንደ በርካታ የኢትዮጵያ ዘመናዊ ሙዚቀኞች ሁሉ ወደ ሙዚቃው ዓለም የተሳበው ድምጻዊ ጥላሁን ገሰሰን አይቶ መሆኑን እና ለረዥም ጊዜ እርሱን እያስመሰለ ሲሠራ መቆየቱን ይናገራል። ሙሉ ለሙሉ በሙዚቃ ሥራ ውስጥ መሳተፍ ከጀመረበት ከፓትሪስ ሉሙምባ በኋላ በተለያዩ የአዲስ አበባ የምሽት ክበቦች ሲሠራ ቆይቷል።

ሙሉቀን 17 ዓመታትን ያህል በሙዚቃው ሕይወት ውስጥ ሲቆይ ከድምጻውያን በቅድሚያ የዓለማየሁ እሸቴ እና የምኒልክ ወስናቸው አድናቂ መሆኑን በአንድ ቃለመጠይቁ ላይ ተናግሮ ነበር። ከእነርሱ ባሻገር የብዙነሽ በቀለ፣ የሒሩት በቀለ፣ የመሐሙድ አህመድ፣ የጥላሁን ገሰሰ አድናቂም መሆኑን ይናገራል።

ከ17 ዓመታት የድምጻዊነት ሕይወት በኋላ ሙሉቀን ዘፈንን ያቆመው ወደ መንፈሳዊ ሕይወት በማተኮሩ ነበር። ሙሉቀን ለመጨረሻ ጊዜ የተጫወተው ሙዚቃ ‘ነይ ነይ ወዳጄ’ የተሰኘውን መሆኑን የሙያ ባልደረቦቹ በአንድ ወቅት በሰጡት ቃለ ምልልስ ላይ ተናግረው ነበር። ከሀገር ወጥቶ ኑሮውን በአሜሪካ ካደረገ አራት አስርት ዓመታትን አስቆጥሯል፡፡

ሙሉቀን ከዓለማዊው የሙዚቃ ሕይወት በመውጣት መንፈሳዊነትን አጥብቆ ኑሮውን በአሜሪካ አሌክሳንደሪያ ቨርጂኒያ ውስጥ ካደረገ በኋላ ወደ ሀገሩ ተመልሶ አያውቀም። በእነዚህ ዓመታት ሙሉቀን መለሰ ከዘፈን ሕይወት ራሱን ካገለለ በኋላ ፊቱን ወደ መንፈሳዊ ዝማሬ አዞረ። በዚህም የተለያዩ የመዝሙር ሥራዎችን ለወንጌል አማኞች አቅርቧል።

ምንም እንኳን ሙሉቀን መለሰ ሙዚቃን ከቆመ አርባ ዓመታት ሊሆነው የተቃረበ ቢሆንም ከዓመታት በፊት የሠራቸው ሙዚቃዎቹ ዘመናትን በመሻገር አሁን ድረስ በተለያዩ ትውልዶች ተወዳጅ እና የሚደመጡ ናቸው። ከዚህም የተነሳ በሸክላ እና በካሴት ዘመን የተጫወታቸው ሙዚቃዎቹ እሱ መዚቃን ካቆመ በኋላ በተፈጠሩት ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች ተቀናብረው በሲዲ እና በኢንተርኔት የሙዚቃ ማድመጫዎች በኩል እየተደመጡ ይገኛሉ።

በተጨማሪም የሙሉቀን ሙዚቃዎች በትውልዶች መካከል ካገኙት ተወዳጅነት የተነሳ በተለያዩ ጊዜያት ጥቂት የማይባሉ ወጣት ድምጻውያን ደግመው ተጫውተዋቸው ለአድማጮች መቅረባቸው ይታወቃል።

በአጎቱ ስም የሚጠራው ሙሉቀን መለሰ፣ የተወለደው ከአቶ ታምር ጥሩነህ መሆኑን በአንድ ወቅት ሲናገር “ይህንን ስም ሳልቀይር መቅረቴ ይቆጨኛል” ብሎ ነበር። ሙሉቀን ከእናቱ ሞት በኋላ ሊያሳድጉ ወደ አዲስ አበባ ያመጡት አጎቱ አቶ መለሰ፣ በመማሪያ ደብተሩ ላይ ሙሉቀን መለሰ ብለው ከጻፉ በኋላ ነበር በአጎቱ ስም እየተጠራ የቀጠለው።

ከምንም ተነስቶ ኮከብ ለመሆን የበቃው የቀድሞው ድምጻዊ ሙሉቀን መለሰ በተወለደ በ70 ዓመቱ ማክሰኞ ሚያዚያ 1 ቀን 2016 ህልፈተ ሕይወቱ በአሜሪካን ሀገር ተሰምቷል።እሱ በአካል ቢያልፍም በሥራዎቹ ግን ህያው ሆኖ ከአድናቂዎቹ ጋር ይኖራል።እኛም ተወዳጁን ሙዚቀኛ ነፍስ ይማር እያልን፤ ለቤተሰቦቹና ወዳጅ ዘመዶቹ መፅናናትን እንመኛለን።

ክብረአብ በላቸው

አዲስ ዘመን ረቡዕ ሚያዝያ 9 ቀን 2016 ዓ.ም

Recommended For You