ደቡብ ሱዳን በሱዳን በኩል ነዳጅ የምትልክበት ማስተላለፊያ አገልግሎት መስጠቱን አቆመ

ደቡብ ሱዳን በሱዳን በኩል ነዳጅ ወደ ውጭ የምትልክበት ዋነኛ ማስተላለፊያ ቱቦ አገልግሎት መስጠቱን አቆመ።

ደቡብ ሱዳን በሱዳን በኩል ነዳጅ ወደ ውጭ የምትልክበት ዋነኛ ማስተላለፊያ ቱቦ የሱዳን ጦር እና ፈጥኖ ደራሽ ኃይሎች ከሚያደርጉት ጦርነት ጋር በተያያዘ አገልግሎት መስጠቱን ማቆሙን ሦስት የሱዳን ባለሥልጣናት ተናግረዋል።

ነዳጅ በቀይ ባሕር ዳርቻ ፖርት ሱዳን አቅራቢያ ወደሚገኘው ማጠራቀሚያ የሚያስተላልፈው ቱቦ ሥራ ማቆሙን ሮይተርስ የሱዳን ፔትሮሊየም ሚኒስቴርን ጠቅሶ ዘግቧል።

የፅዳት ሥራ ባለመሠራቱ ምክንያት ማስተላለፊያ ቱቦው አንድ ቦታ ላይ ፍንዳታ ማጋጠሙም ተገልጿል።

ይህ ችግር ያጋጠመው ጦርነት በተካሄደባቸው እና የግንኙነት አገልግሎቶች ለሳምንታት በተቋረጡባቸው ቦታዎች መሆኑን ዘገባው ጠቅሷል። በችግር በነዳጅ ጥራት ላይ እና በገቢ ላይ ያደረሰው ኪሳራ ምን ያህል እንደሆነ አልታወቀም።

ደቡብ ሱዳን በ2011 ከካርቱም በተገነጠለችበት ጊዜ በወጣው ቀመር መሠረት በቀን 150 ሺህ ድፍድፍ ነዳጅ በሱዳን በኩል ለውጭ ገበያ ስታቀርብ ቆይታለች።

የነዳጅ ኤክስፖርት ለደቡብ ሱዳን እና የማሸጋገሪያ ወይም ትራዚት ክፍያ ለምትቆርጠው ሱዳን ወሳኝ የገቢ ምንጭ ነው።

የሱዳን ጦር ለማስተላለፊያ ቱቦ ሥራ ማቆም ፈጥኖ ደራሽ ኃይሎች ተጠያቂ አድርጓል።

ነገርግን ፈጥኖ ደራሽ ኃይሎች ለችግሩ መፈጠር እጃቸው እንደሌለበት አስተባብለዋል።

የደቡብ ሱዳን ፔትሮሊየም ሚኒስትር ተፈጥሯል በተባለው ችግር ዙሪያ እስካሁንም ያለው ነገር የለም ተብሏል።

አገልግሎቱን ያቋረጠው ይህ ቱቦ ከደቡብ ሱዳን ሜሉት ቤዚን ወደ ፖርት ሱዳን የተዘረጋው በቻይናው ሲኤንፒሲ እና ሲኖፔክ እንዲሁም በማሌዥያው ፔትሮናስ ሲሆን 1500 ኪሎ ሜትር ርዝመት አለው።

ከደቡብ ሱዳን ዩኒቲ ግዛት ነዳጅ ወደ ፖርት ሱዳን የሚያደርስ ሌላ ማስተላለፊያ ቱቦም እንዳላት ይታወቃል።

በጋዜጣው ሪፖርተር

አዲስ ዘመን ረቡዕ መጋቢት 18 ቀን 2016 ዓ.ም

Recommended For You