በተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች ውስጥ የተለያዩ ባህላዊ ቁሳቁሶች እንደ ማህበረሰቡ የባህል ሁኔታ አገልግሎት ላይ ይውላሉ። ይህንንም ግልጋሎታቸውን መሰረት ተደርጎ ስያሜ ይሰጣቸዋል። ይሁንና በአንድ አይነት አገልግሎት ላይ የሚውሉ ቁሶች በተለያየ ስም ሊጠሩ የሚችሉበት አጋጣሚ አለ። ለዚህ ምክንያቱ በየማህበረሰቡ ቋንቋ መጠሪያ ስያሜ ማግኘታቸው መሆኑን ብዙዎች ይስማማሉ።
እናም ዛሬ ይህንን ተግባር በሚገባ ያሳየናል ወደምንለው አንድ ብሔረሰብ ይዘናችሁ እንዝለቅ – የጉራጌ ብሔረሰብ ዘንድ። በጉራጌ ብሔረሰብ በተለያዩ አካባቢዎች ባህላዊ እቃዎች ልዩ ልዩ ስያሜ ሊያገኙ ይችላሉ።
እኛ ግን ብዙዎችን አንድ የሚያደርጋቸው የባህል እቃዎች በመምረጥና ግልጋሎታቸው ምን እንደሚመስል ማሳየት ነው የፈለግነው። ለዚህም በባህሉ ዙሪያ በርካታ ጥናታዊ ጽሑፎችን እንደሰሩ የነገሩን በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባህልና ቱሪዝም ቢሮ የማይዳሰሱ ባህላዊ ቅርሶች ጥናት ከፍተኛ ባለሙያ መምህር መክብብ ገብረማርያምን አብነት በማድረግ የነገሩን እነሆ ለንባብ ብለናል።
መምህር መክብብ እንደሚናገሩት፤የጉራጌ ብሄረሰብ ለባህላዊ እቃዎች ስያሜ መስጠት ላይ መመሳሰል እንዳላቸው ሁሉ ልዩነትም ይኖራቸዋል። ለሚጠቀሙባቸው ባህላዊ እቃዎችም ከልዩነታቸው አንጻር መጠሪያ ሊያወጡም ይችላሉ። እናም ከተባለው አንጻር ብዙሃኑ የሚመሳሰሉበትን ለመጥቀስ ያክል ከቀንድ፣ ከሸክላና ከእንሰት ውጤቶች እያልን መግለጽ እንችላለን። መጀመሪያ ግን በጉራጌ ብሄረሰብ ዘንድ እደ ጥበብ እንዴት ይገለጻል የሚለውን እንመልከት።
ዕደ–ጥበብ
የጉራጌ ብሔረሰብ ተፈጥሮ የቸረችውን ከአካባቢው የሚገኙ ግብዓቶችን በመጠቀም ለየዕለት ህይወቱ አስፈላጊ የሆኑትን ምግቦች ከማዘጋጀት ባሻገር ለረዥም ጊዜ አገልግሎት ሊሰጡ የሚችሉ መገልገያ ቁሳቁሶችን በማምረት ይታወቃል። ዕውቀቱን ለትውልድ በማሸጋገርም ባህሉን፣ ባህላዊ እቃዎቹን እና አሠራሩን ይዞ ቆይቷል።
የብሔሩ ዕውቀትና ክህሎት አሻራ በዕደ- ጥበብ ውጤቶች ላይ የተንተራሰ በመሆኑም ባህላዊነቱን ሳይለቅ ዛሬም ድረስ ዘልቋል። በጉራጌ ዞን በሚገኙት አንዳንድ ወረዳዎች ከስንደዶ፣ ከአክርማ፣ ከቃጫና ከክር የሚመረቱ የዕደ-ጥበብ ውጤቶች ከአካባቢውና ከአገር አልፈው ባህር ማዶም በመሻገር አገር ማስተዋወቂያ መሆናቸውን እንመለከታለን። ጉራጌና የባህል እሴቶቹ በሚለው መጽሐፍ ላይ እንደተመለከተው የጉራጌ ባህላዊ እቃዎች በርካታ ናቸው። ከእነዚህም መካከል፤
ይወደረ
በእንሰት አብቃይነቱ የሚታወቀው የጉራጌ ብሔረሰብ እንሰትን ከምግብነት በተጨማሪ ለተለያዩ ግልጋሎቶች እንዲውል አድርጓል። በተለይም ለባህላዊ እቃ መስሪያነት በብዛት እንደሚያውለው በዐይን የሚታዩ ባህላዊ እቃዎቹ ምስክር ናቸው። ከእነዚህም ውስጥ ለምግብ ማዘጋጃነትና ማቅረቢያነት፣ ለመኝታና ለቤት ውስጥ ንጣፍነት መዋሉ አንዱ ማሳያ ነው።
ይወደረ ከባህላዊ እቃዎች ውስጥ አንዱ ነው። ለምግብ ማቅረቢያነት የሚያገለግል ሲሆን፣ የሚሰራውም የእንሰት ውጤት ከሆነው ቃጫ ነው። ይወደረ ውበት እንዲኖረው በተለያየ ቀለማት ይነከራል። አንድ ጥሩ የተባለ ይወደረ ሰርቶ ለማውጣት እስከ አንድ ወር ጊዜ ይወስዳል። እንዲህ አይነቱ ይወደረ ቁመቱ ሁለት ሜትር፣ ጎኑ (ስፋቱ) ደግሞ አንድ ሜትር ያህል ሊሆን እንደሚችል ይገለጻል።
ይወደረ በተለይ ትላልቅ ክብረ-በዓላትና ትላልቅ ዝግጅቶች ሲኖሩ ቤት ውስጥ ወለል ላይ በተነጠፈ ሰፊና ምርጥ ጅባ ላይ ይዘረጋና ቆጮ፣ ክትፎ፣ አይብና የጎመን ክትፎ በጣባ ወይም በጥለስ (ከእንሰት ቅጠል የተሰራ መመገቢያ) እንዲበላበት ለታዳሚው ይዘረጋል።
ይወደረ እንደዛሬው ጠረዼዛ ማለት ነው። በተለይ በመስቀል ወይም በአረፋ ክብረ በዓላት ላይ እንዳይቆሽሽ ተጠቅልሎ በንጽህና ከተቀመጠበት ቦታ ይወጣል። እስከ በዓላቱ ፍፃሜ ድረስም ጅፐ ላይ ተዘርግቶ ማዕድ ማቅረቢያ ሆኖ ያገለግላል።
ጅባ (ጅፐ)
ሌላው ከእንሰት ተክል እና ከቄጠማ የሚሰራው የዕደ-ጥበብ ውጤት ጅፐ (ጅባ) የሚባለው ሲሆን፣ ከእንሰት ተክል ከሚገኘው ቃጫና ኮባ ይሰራል። ለቤት ውስጥ ወለል ንጣፍነትና ለመኝታ አገልግሎት ይውላል። የተለያየ መጠንና ጥራት ያላቸው የጅባ አይነቶች ሲኖሩ በጣም ጥሩ የተባሉት ልክ እንደ ይወደረ ለተለያዩ ክብረ-በዓላትና ለትላልቅ ዝግጅቶች ብቻ ግልጋሎት ይሰጣሉ። መሃከለኛ የሆኑት ደግሞ ዘወትር ተነጥፈው በህዝቡ የዕለት ተዕለት ህይወት ውስጥ ጥቅም ላይ ይውላሉ።
ሰፍ (መሶብ)
ሰፍ (መሶብ) የሚባለው ባህላዊ እቃን ስንመለከት ደግሞ ከስንደዶና ከአክርማ የሚሰራ ሲሆን፣ በጉራጌ ብሔረሰብ ዘንድ የተለያየ ቅርፅና መጠን ኖሯቸው ለተለያዩ የማዕድ አገልግሎቶች የሚውሉ ናቸው። ይህ እቃ በሌሎች የማህበረሰብ ክፍሎችም ሊኖር ይችላል። ይሁንና በጉራጌ ብሄረሰብ ግን በስፋት ግልጋሎት ላይ ይውላል።
የጉራጌ ባህላዊ ምግቦችም በብዛት ሲቀርቡ በልዩ ልዩ ህብረ-ቀለማት በአጌጡ ውብና ማራኪ የዕደ-ጥበብ ውጤቶች መሆኑን የሚያመለክቱት እነዚህ ሰፎች ናቸው። ሰፍ ከቡና ቁርስ ማቅረቢያነት እስከ እንጀራና ዳቦ ማስቀመጫነት ያገለግላል።
ከእንሰት ውጤቶች ሳንወጣ ሌላው ባህላዊ እቃ እፎት የሚባለው ሲሆን፤ ለጀበና ክዳንነት የሚያገለግል ነው። እንደሚታወቀው የጉራጌ ጀበና ለየት ያለና ደረጃ ያለው በመሆኑ እስከክዳኑ የብሔረሰቡ መገለጫነቱን ይናገራል።
የሸክላ ምርቶች
በጉራጌ ብሔር ውስጥ እጅግ መጠነ ሰፊ ግልጋሎት የሚሰጡት የሸክላ ስራ ውጤቶች ናቸው። ከነዚህ የዕደ-ጥበብ ውጤቶች መካከል ለምግብ ማብሰያነትና ማቅረቢያነት፣ ለመጠጫነት እንዲሁም የሚበሉና የሚጠጡ ምግቦች ሳይበላሹ ለረዥም ጊዜ ማቆያነት (ማስቀመጫነት) ያገለግላሉ። አንዳንዶቹም ከአንድ በላይ ለሆነ ጠቀሜታ ሲውሉ ይታያል።
ብዙ ጊዜ አገልግሎት የሚሰጠው ጎርደት (ምድጃ) ሲሆን፤ ሦስት ጎንዤዬዎች (ጉልቻዎች) ይቀመጡና የተለያዩ ነገሮችን ለመጣጃነት ይጠቅማል። ሌላው ከሸክላ የሚሰራውና ብዙ ግልጋሎት የሚሰጠው ደግሞ ወሸር ሲሆን፣ ለውሃ መቅጃነት ይውላል። በሌሎች አካባቢዎች እንስራ ተብሎ የሚጠራው አይነት ነው።
ቢጥር ወይም ሽሸት በመባል የሚጠራው ደግሞ እንዲሁ የብሔረሰቡ ዋነኛ ምግብ የሆነው ክትፎ የሚቀርብበት ባህላዊ እቃ ነው። ቢጥር ትልቅ ሸክላ ነው። በጣም ትልቅ በዓል ሲመጣ ብቻ ከተሰቀለበት ወርዶ አገልግሎት እንዲሰጥ ይደረጋል።
ሌላው ጣባ ሲሆን፤ ጥለስ (የኮባ ቅጠል) በላዩ ላይ ጣል ተደርጎበት እንደየእድሜው ተዘጋጅቶ ክትፎና ሌሎች ምግቦችን በላዩ ላይ በማድረግ የመመገቢያ ግልጋሎት እንዲሰጥ የሚሰራ ነው። ቆርዬ፤ ይህ ደግሞ አንገተ ረጅምና መያዢያ ያለው ገንቦ መሰል ባህላዊ እቃ ሲሆን፤ ልጆች ወተት የሚጠጡበት፣ አንዳንዴም ቅቤ ማስቀመጫና ማሞቂያ ነው።
ሌላው ከሸክላ የሚሰራው የጉራጌ ብሔረሰብ ባህላዊ እቃ ትንክዬ የሚባለው ሲሆን፤ አገልግሎቱም ጎመን፣ አምቾ፣ ስጋ የሚቀቀልበት ነው። በብሔረሰቡ አባላት ዘንድ ሌሎችም ከሸክላ የሚሰሩ ባህላዊ እቃዎች አሉ። (ዬብ ወሸር) የወተት ማስቀመጫ፣ ጥዋ፣ የሸክላ ድስት ወዘተ ታዋቂ የብሔሩ የዕደ-ጥበብ ውጤቶች ናቸው።
ከቀንድ የሚሰሩ
ከከብት ቀንድ የተለያዩ የቤት ቁሳቁሶች ይሰራሉ። ከነዚህም ውስጥ አንዱና ዋነኛው አንቀፎ (ማንኪያ) ሲሆን፤ የተለያየ መጠን ያለው ነው። አነስተኛው ለክትፎ፣ ለአይብ፣ ለዝማሙጃት፣ ለኸቋት፣ ለፍንታፍንቶ፣ ለኦዛት፣ ለድኩቸ እና ለማር ወለላ መመገቢያነት ያገለግላል። ትልቁ ደግሞ በትልቅ ጣባ ክትፎ፣ አይብ፣ ዝማሙጃት እና የጎመን ክትፎ ከቅቤና ሚጥሚጣ ጋር ለማቀላቀል ይጠቅማል።
የእንጨት ውጤቶች
ከእንጨት ከሚሰሩ ባህላዊ ዕቃዎች መካከል መቀቀት አንዱ ሲሆን፤ የቡና ሙውቀጫ ነው። እምወ (ዘነዘናም የሚሰራው ከዚሁ ነው። ሌላው ጉራጌ ከሚታወቅበት አንዱ የሆነው ቆጮ የሚፋቅበት ዘንቦነም ከዚሁ ከእንጨት ነው የሚሰራው። “ይተፎብወ“ እየተባለ የሚጠራውም ቆጮ የሚጠፈጠፍበት ባህላዊ እቃ እንዲሁ ከዚህ እንደሚሰራ ባለሙያው ገልጸውልናል። ሰንዳ ቆጮ መቁረጫውም እንዲሁ መያዢያው ከእንጨት የሚሰራ ነው።
በአጠቃላይ በጉራጌ ብሔረሰብ ባህላዊ እቃዎች ከቤቱ ጀምሮ መቀመጫቸው የሚለያይ ሲሆን፤ በብዛት ግን የሚቀመጡት በቃቀት (ሳሎን) ላይና (ጓዳበድራ) ውስጥ ነው። ባህላዊ እቃዎቹ ግልጋሎታቸው ለሙሽራ፣ ለትልልቅ አባቶች፣ ለነገስታት፣ ለህጻናት … በማለት ተከፋፍሎ ይታያልም። ሁሉ ዘርዝሮ መንገር አይቻልምና ጥቂቱን በነገሩን መጠን አስቀምጠናል። ለዛሬ የያዝነውን በዚህ ቋጨን። ሰላም!
አዲስ ዘመን ግንቦት 25/2011
ጽጌረዳ ጫንያለው