ንጉስ ብሆን ምን እንደምሰራ እኔ አውቅ ነበር አሉ አቶ ማንአስቦት ከደመቀው ቤተሰብ ግሮሰሪ በረንዳ ላይ ሆነው። ቤተሰብ ግሮሰሪ የቢራና የድራፍት መጠጥ ከሆነ ሶስት ዓመት አልሞላውም፡፡ ግቢው ግን ላለፉት አርባ ሶስት ዓመታት የሰካራም ጫጫታ ተለይቶት አያውቅም። ያኔ ታዲያ የንቦች መአዛ ጠጅ ቤት ነበር የሚባለው፡፡ አቶ ማንአስቦት ከሰላሳ ዓመት በላይ ስለጠጡበት ሙሉ ለሙሉ የሚንቀሳቀሱት በየኔነት ስሜት ነው። ቀድሞ በሀገር ግዛት ሚኒስቴር በተላላኪነት ከዛም በኋላ በፍርድ ቤትና በማዘጋጃ ቤት የመዝገብ ቤት ተቆጣጣሪ ከጡረታ በኋላ ደግሞ የጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ጥበቃ ሆነው ለረጅም ዓመት ስለሰሩም ከግለሰብ እስከ መንግስት የማላውቀው ሚስጥር የለም ብለው ይኩራራሉ።
ከምንም በላይ ደግሞ ስለሀገራቸው ደፍረው እንዲናገሩ መረጃ በመስጠት በራስ መተማመናቸውን ያዳበረላቸው ሀያ አምስት ዓመት ከእጃቸው ያልተለያቸው ናሽናል ራዲዮ ናቸው ነው። የራዲዮና የዜና ፍቅር ለብዙ ነገር ዳርጎኛል ይላሉ፡፡ ከሁሉም በላይ ግን ከጎረቤታቸው ያቀያየማቸውን ጊዜ መቼም አይረሱትም።
በአንድ ወቅት ትርፍ አንጀት አሟቸው የካቲት 12 ሆስፒታል ተኝተው ነበር፡፡ ወቅቱ ደግሞ የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት የተጋጋመበት በመሆኑ አቶ ማንአስቦት አንድም ዜና እንዲያመልጣቸው አይፈልጉም። ታዲያ በዚህ በጤናና በዜና አምሮት በተወጠሩበት ሰዓት ጎረቤቶቻቸው ሊጠይቋቸው ይመጣሉ፡፡ እናም በመዳዳ የመጡትን ጠያቂዎች ልጃቸው እየተቀበለች ቦታ ስትሰጣቸው እሳቸው በቀኝ እጃቸው ሬዲዮኗን ጆሯቸው ላይ ለጥፈው በግራ እጃቸው ጨበጧቸው። ክፉ ቀን ሆኖ ጎረቤቶቻቸው ዜና ሊያዳምጥ ሳይሆን ልጁ ከአረብ ሀገር ስለመጣች ብር አጥግቦት የእኛን ሙዝና ብርቱካን ንቆ ነው ብለው ለረጅም ጊዜ ፊታቸውን አጥቁረውባቸው ቆይተዋል።
ሰሞኑን ደግሞ እዚች ማምሻ ቤት ከአንድ ለሰፈሩ እንግዳ ከሆኑ አዛውንት ጋር ስለሀገራቸው ጥልቅ ውይይት በማድረግ ተጠምደዋል። አቶ ማንአስቦት የረጅም ጊዜ ልምዳቸውን በመቀመር በሀገሪቱ ያለውን ወቅታዊ ችግር ለመፍታት መንግስት መጀመሪያ ማድረግ ያለበት ጠንካራ ፖሊስ ማቋቋም ነው አሉ። እኔ ንጉስ ብሆን ከትግራይ እስከ ሀረር ከጋምቤላ እስከ ጅቡቲ ሲሆን በሪኮፍተር አስቸኳይ ካልሆነ ደግሞ በመኪና እየተጓጓዘ ይሄን በጥባጭ ሁላ አፈር ከድሜ ማብላት የሚችል ሰራዊት እገነባለሁ። ታዲያ ለዚህም ቢሆን ጠንካራ በአግባቡ የሰለጠነ አገር ወዳድ ወታደር ተመርጦ መለየት አለበት።
ሲቀጥል የቸገረው ሰው የሚያደርገው ነገር አይታወቅምና ዳጎስ ያለ ክፍያ መክፈል አስፈላጊ ከሆነም መውደቂያ ቤት በፍጥነት ከመንግስት ካዝና ወጥቶ እንዲሰራ አስደርጋለሁ። ሰው ሰላም ውሎ ካደረ ሁሉም ይደረስበታል። ቀጥዬ ደግሞ ምን አደርጋለሁ፤ በየጠቅላይ ግዛቱ ማለቴ በየክፍለ ሀገሩ ምንድነው የምትሉት በየክልሉ አንዳንድ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል አስገነባለሁ፡፡ ህዝብ ሰላም ውሎ ካደረ የሚያሳስበው የጤናው ጉዳይ ብቻ ነው። ለዚህ ደግሞ ከህንድ ውጪ ሌላ ሀገር የተማሩ ዶክተሮችን እሰበስብና ሞቅ ያለ ደመወዝ እየከፈልኩ እንዲሰሩ አደርጋለሁ፡፡ ታዲያ እነሱም ቢሆኑ ማግባታቸው መውለዳቸው ቤተሰብ መመስረታቸው ስለማይቀር ሶስት ሶስት መቶ ካሬ ቦታ አዘጋጅና መንግስት ካዝናው ስለሳሳ ግንባታውን ራሳችው እንዲችሉ አደርጋለሁ።
ከዛ ቀጣዩ ስራዬ የቤቱ እንዲህ ከተረጋጋ ስለጎረቤት ማሰብ ነው፡፡ ለዚህም ለማናቸውም ክፉም ደግም አለና እንደ ነብር የሚዘል እንደእባብ የሚናደፍ ጠንካራ ወታደር ያስፈልገናል። ስለዚህ አየር ኃይሉን እስራኤል እግረኛውን አሜሪካ ባህርተኛውን ደግሞ ሲውዲን እንድታሰለጥን ጠቀም ያለ ገንዘብ እመድብለታለሁ። እንግዲህ ልብ በል ከቤትም ከጎረቤትም ያለውን ምቀኛ እንዲህ አንገቱን ካስደፋሁ በኋላ ይሄን እንደ ዋናተኛ ራቁቱን የሚሄድ የሀገሬን ገበሬ ማንቃት እጀምራለሁ። ከዛ በየተራ ግድቡም መንገዱም ባቡሩም ይደረስበታል። እንጂ እኔ ንጉስ ብሆን እንዲህ አስር ድስት ጥጄ ህዝቤንም እኔንም ሳደናግር አልኖርም ነበር። ምን ዋጋ አለው ንጉስ ሳልሆን ቀረሁ። አቶ ማንአስቦት ከሀሳብ ንግስናቸው በመፈንቅለ መንግስት የለቀቁ ያህል እየተብከነከኑ ቢራቸውን ተጎነጩ።
አዛውንቱ ራሳቸውን እየነቀነቁ የአቶ ማንአስቦትን ሀሳብ ተቃወሙ። አይይ፤ የማይሆነውን አሉ፤ መጤው አዛውንት መጀመሪያ ይሄ ሁላ ስራ የሚሰራበት በጀት ቢኖር ኖሮ ቀድሞ ችግር ባልተፈጠረ ነበር። ሲቀጥል የችግሩ ሁሉ መነሾ ተማርኩ ተሾምኩ ሰለጠንኩ የሚለው ስለሆነ እሱን ማጥገብ አገር መበጥበጥ ነው።
ስለዚህ አልሆንም እንጂ እኔ ንጉስ ብሆን መጀመሪያ የማደርገው አርሶ አደሩን ማንቃት ነው፡፡ ገበሬ የሀገር ዋልታ መከታ ነው። ገበሬ ለእርፍና ሞፈር እንጂ ለጥይት ለዱላ ግዜ የለውም፡፡ ስለዚህ ያላጠፋን እንዲቀጣ ፖሊስ የምመለምልበት ምንም ምክንያት የለም። በእርግጥ አሁን እየተጫረ ያለውን እሳት ማጥፋት ተገቢ ነው፡፡ እሱን የምናጠፋው ግን አርሶ አደሩ ተባባሪ እንዳይሆን በማድረግ ብቻ ነው። አርሶ አደሩ ብዙ ነው፤ ቀለብ ሰፋሪ ፣ወጣት ፣ገባሪም እሱ ነው ፡፡ እሱን እንዲነቃ አደረግነው ማለት ነገረኛው ቀበኛው ሁሉ ከባህር የወጣ አሳ ይሆናል ማለት አይደል።
ከአላጌ ግብርና ምርምር በዲፕሎማ የተመረቁትና ለረጅም ዓመት የቀበሌ ሸንጎ ኃላፊ ሆነው የሰሩት መርጌታው አዛውንት ወሬያቸውን ቀጠሉ አሁን ያለው መንግስት መጀመሪያ ማስፋፋት ያለበት የእምነት ተቋማትን ነው ፤ መንግስት እነዚህን ተቋማት በጥራትም በብዛትም ተደራሽ እንዲሆኑ ከምንም በፊት ቅድሚያ ሰጥቶ መስራት አለበት። ይሄ በምን ይከተላል ካልከኝ ደግሞ እኒህን ተደራሽ የሆኑ ተቋማት የውስጥ አቅም በማጎልበት ጥራቱን ደረጃውን የጠበቀ ብሎም ወቅቱን ያገናዘበ ስብከት እንዲያካሂዱ በመደገፍ እንደ ማለት ነው። እንግዲህ እዚህ ላይ ግንዛቤ መያዝ ያለበት ነገር ቢኖር መንግስት በቅድሚያ እመራበታለሁ በሚለው ህገ መንግስት ላይ ያስቀመጠውን ሀይማኖትና መንግስት ለየቅል ናቸው የሚለውን ያረጀ ያፈጀ ብሂል መንቀል ይጠበቅበታል።
ለምን ካልከኝ ደግሞ ሁሉም ኢትዮጵያዊ የእምነት ደረጃው ቢለያይም የኔ የሚለው ሀይማኖት አለው። ሁሉም ሀይማኖቶች ደግሞ ባያምኑበትም ሰላምን ፍቅርን ህብረትን አንድነትን ይሰብካሉ፤ ስለዚህ ከከተማ መስፋፋት ከህዝብ ብዛት ጋር ተያይዞ መንግስት በየኮንዶሚንየሙ ስር በየመንደሩ መሀል የእምነት ተቋማትን ማስፋፋት ይገባዋል ባይ ነኝ ።
ለዚህ ደግሞ አንድም በቂ በጀት መመደብ አልያም የገንዘብ ማሰባሰቢያ ቴሌቶን ማካሄድ የደጋፊ ሀገራትንም እርዳታ መለመን ማለቴ…….. መጠይቅ ያስፈልግ ይሆናል። መጨረሻ ምን ይመጣል ካልከኝ በርትቶ ህዝቡን ባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ፤ አትግደል፤ አታመንዝር፤ አትስርቅ …… እያልን በደግ በደጉ ካነፅነው ችግር ጠፋ ማለት አይደለም።
የጎረቤት ጠላት ላልከው እኛ አንድ ከሆን ህብረት እንዳለን ካወቁ ቀድሞ ነገር ስለማይተነኩሱን እኛም ሀይማኖተኛ ከሆን ሰው ጥግ ስለማንደርስ የሚፈጠር ችግር አይኖርም። ይሄን የሚያስብ ይሄን የሚያደርግ ጠፍቶ ነው በነጋ በጠባ ሀገር የሚታመሰው አሉ አዛውንቱ የመጨረሻ ንግግራቸውን በቢራ እያወራረዱ።
በጥሞና ሲያዳምጡ የቆዩት የጠጅ ቤቱ ባለቤት ወይዘሮ አበባ ማሳረጊያውን ተናገሩ፤ የሚቃረንም ቢሆን ሁለታችሁም እንደ ልምዳችሁ እንደ እውቀታችሁ ላገር ይበጃል ያላችሁን ሀሳብ ሰንዝራችኋል። ነፍሱን ይማረውና ባለቤቴ ቢኖር ደግሞ መምህርነቱን ተመርኩዞ ችግሩ ዘመናዊ ትምህርትን በማስፋፋት እንደሚፈታ ሊናገር እንደሚችል አስባለሁ። እኔ ግን የሚታየኝ የችግሩ ሁሉ ምንጭ እንዲህ እንደናንተ በጨዋ ደንብ በፍቅር ያለዘለፋ ያለ ነቀፋ መመካከር አለመቻሉ ይመስለኛል። እናም መካሪ አግኝተው በሬ ወለደ በቅሎ ወለደች የሚሉትም ተገናኝተው ቢነጋገሩ መፍትሄ ይጠፋል ብዬ አላስብም።
ስለዚህ መንግስት ማድረግ ያለበት ካኮረፈ እስከተቀየመ ከነጠቀ እስከ ተነጠቀ እያፈላለገ ማነጋገር ማወያየት ነው አሉ። ሁለቱም አዛውንቶች ሀሳባቸውን ለማጠናከር ሲዘጋጁ ሳይታሰብ መብራት ድርግም ብሎ ጠፋ። ወይዘሮ አበባ እንደ ፀብ ገላጋይ ድምፃቸውን ከፍ አርገው እንዲህ አሉ፤ ነገር ባይን ይገባል፤ ሳንተያይ ያወራነው ውል ስለሌለው ነገ እንቋጨዋለን፤ ዛሬን ሰላም ያሳድረን።
ሁለቱ አዛውንቶች ጨዋታው ለነገ መተላለፉ ሳይሆን ከደማቁ በጋ ዝናብ ከሚጠብቀው መብራት ኃይል የነገ መብራት መኖር አለመኖር እያሳሰባቸው በዳበሳ ምርኩዞቻቸውን እያነሱ ተሰናብተው ወጡ።
አዲስ ዘመን ግንቦት 20/2011
ራስወርቅ ሙሉጌታ