በተማሪነት ሕይወት ትልቁ ስጋት ፈተና፤ ስኬቱ ደግሞ ፈተናን በውጤት ማለፍ ነው፡፡ በዚህ ረገድ ከአንድ ምዕራፍ ወደሌላኛው መሸጋገሪያ ተደርገው የሚታዩት የስምንተኛ፣ አስረኛና አስራ ሁለተኛ ክፍል ክልላዊና አገራዊ ፈተናዎች ደግሞ ለተማሪዎች ትልቅ ትርጉም ያላቸው፤ የዓመታት ልፋታቸውን ውጤት የሚያሳዩ እንደመሆናቸውም ሰፊ ዝግጅት የሚደረግባቸው ናቸው፡፡ እኛም በዛሬው ዕትማችን በድምሩ ከሁለት ሚሊዮን በላይ ተማሪዎችን በሚያስፈትኑት በአማራና ኦሮሚያ ክልሎች እየተደረገ ያለውን ዝግጅት አስመልክቶ ጉዳዩ በቀጥታ ከሚመለከታቸው የትምህርት ቢሮ የሥራ ኃላፊዎች ጋር ያደረግነውን ቆይታ እንደሚከተለው አጠናቅረነዋል፡፡
የፈተና አስተዳደር ዝግጅት ሥራ
በፌዴራል ደረጃ ያለው ዝግጅት እንደተጠበቀ ሆኖ ክልሉ የራሱን የዝግጅት ሥራ እያከናወነ መሆኑን የኦሮሚያ ትምህርት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ገላና ወልደሚካኤል ይናገራሉ:: እርሳቸው እንደሚሉት፤ የፈተና አስተዳደር መመሪያ ተዘጋጅቶ የህዝብ ንቅናቄ መድረኮች ተካሂደዋል፤ ከአገርአቀፍ ፈተናዎች ኤጀንሲና ከትምህርት ሚኒስቴር ጋርም ውይይት ተደርጓል፡፡
እንደ ክልሉ ተጨባጭ ሁኔታም የፈተና አስተዳደር መዋቅሩም እስከ ትምህርት ቤቶች ተደራጅቷል፤ ኦሬንቴሽንም ተሰጥቷል፡፡ የፈተና አስፈጻሚዎችም (ሲፐርቫይዘር፣ የፈተና ጣቢያ ኃላፊ፣ ፈታኝ መምህራን፣ የጸትታ ኃይሉ) መረጣና ምደባ ከክልል እስከ ትምህርት ቤት የተጠናቀቀ ሲሆን፤ የት እንደሚሄዱና መቼ እንደሚሄዱም አውቀው እየጠበቁ ነው፡፡ ፈተናውን ለማስተዳደር የሚያስፈልገው በጀትም ተዘጋጅቷል፡፡ ስለዚህ በፈተና አስተዳደር በኩል ችግር የለም፡፡
የስምንተኛም፣ አስረኛም ሆነ አስራ ሁለተኛ ክፍል ፈተናም ተዘጋጅቶ ከመጠናቀቁም ባለፈ፤ የስምንተኛ ክፍል ፈተና ከግንቦት 16 ጀምሮ እየታደለና ወደየዞኑ እየሄደ ነው፡፡ የአስርና 12ኛ ክፍል ፈተናም ትምህርት ሚኒስቴር በሚያወጣው መርሐ ግብር መሰረት ይጓጓዛል፡፡ ከዚህ አኳያ ሲታይ የፈተና አስተዳደርና የፈተና ስርዓቱን ለማስፈጸም የሚያስችል አቅም ተደራጅቷል፡፡
የአማራ ክልል ትምህርት ቢሮ የስርዓተ ትምህርት ዝግጅትና ትግበራ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ካሴ አባተ በበኩላቸው እንደሚሉት፤ በትምህርት ሚኒስቴርና በፈተናዎችኤጀንሲ የተሰጠውን ኦሬንቴሽን ተከትሎ እንደ ክልል የሚመለከታቸውን አካላት ያሳተፈ የንቅናቄ መድረክ ተካሂዷል፡፡ የጣቢያ ኃላፊ፣ ሱፐር ቫይዘርና ፈታኝ ምልመላም ተጠናቅቆ እየተደለደለ ነው፡፡ የማዕከል አስተባባሪዎች፣ የጉዞ መስመሮችና ፈተና አጓጓዦችም ተዘጋጅተዋል፡፡ ለዐይነ ስውራንና መስማት ለተሳናቸው ተፈታኞችም ፈታኝ ተመድቧል፡፡
አድሚሽን ካርድ ደርሶም እየተሰራጨ ይገኛል፡፡ ሥራው በኮማንድ ፖስት የሚመራ እንደመሆኑም፤ ከአሁኑ ተናብቦ መሄድ እንዲቻል የክትትል ሥራው ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ ችግሮችንም እየለዩ ከስር ከስር እየፈቱ እየተሄደ ነው፡፡ ሂደቱም አንድ ቦታ ላይ ከተበላሸ ችግሩ አገራዊ ጉዳይ መሆኑን ከግንዛቤ በማስገባት የተከናወነ ሥራ እንደመሆኑም፤ ተማሪዎች በተረጋጋ መንፈስ እንዲፈተኑ ለማድረግ በጸጥታው ዘርፍም ሆነ በሌሎች የፈተና አካላት ተገቢውን ሥራ ለማከናወን የሚያግዝ ነው፡፡
ተማሪዎችን የማብቃት ሥራዎች ተማሪዎች
ለክልልና አገር አቀፍ ፈተናዎች ብቁ ከማድረግ አኳያም በርካታ ተግባራት የተከናወኑ ሲሆን፤ አሁንም ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራበት ከመጨረሻው ምዕራፍ እየደረሰ ነው፡፡ በዚህም ትምህርቱ በወቅቱ እንዲሸፈን፤ በቤተ ሙከራ፣ በቤተ መጽሐፍትና ሌሎች ግብዓቶችም ተደግፈው ተማሪዎች እንዲያነቡ ተደርጓል፡፡ ለምሳሌ፣ ቤተ መጽሐፍት ከሰኞ እስከ ዕሑድ ክፍት ሆኖላቸው እንዲያጠኑ ተመቻችቷል፤ ትምህርት ቤቶችም ተገቢ ማጣቀሻ መጻሕፍትን ገዝተው በማቅረብ ተማሪዎች በቤተመጻሕፍት ውስጥም ሆነ በውሰት ወስደው እንዲያነቡ ተመቻች ቶላቸዋል፡፡
ከዚህ ባለፈም ዎርክ ሺቶችን፣ የተለያዩ ዘመናት የብሔራዊ ፈተና ጥያቄዎችንና ሌሎች ለፈተናው የሚያዘጋጇቸውን ይዘቶች በመምህራንም ሆነ እርስ በእርሳቸው እየታገዙ እንዲሠሩና እንዲያውቁ ተደርጓል፡፡ ሞዴል ፈተናም ወስደው ተጨማሪ ንባብ እያከናወኑ የፈተናውን ቀን እየተጠባበቁም ይገኛሉ፡፡ በመሆኑም የዝግጅት ሂደቱ ከቢሮ ጀምሮ ያለውን መዋቅር ጨምሮ ተማሪዎች፣ ወላጆችና መምህራን ትልቅ ሥራ የሠሩበትና እየሠሩ ያሉበት ጥሩ ዝግጅት ነው፡፡
ዶክተር ገላና በበኩላቸው እንደሚሉት፤ ተማሪዎችን ከማብቃት አኳያ ከቢሮ እስከ ወላጅ ድረስ እየተሠራ ሲሆን፤ አሁን ላይ በአንጻራዊነት በክልሉ ሰላም ያለ እንደመሆኑም ዘግይተው የጀመሩ አንዳንድ ቦታዎች ያለውን ክፍተትለመሙላት በማካካሻ ትምህርት ሌሎች ላይ እንዲደርሱ እየተሠራ ይገኛል፡፡ ባለው ሁኔታም በተቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ መሰረት ለመፈተን ተማሪዎች ዝግጅታቸውን አጠናክረው ቀጥለዋል::
ተማሪዎችን ለውጤት ከማዘጋጀት አኳያ እንኳን ዘንድሮ ችግሩ ከፍተኛ በነበረበት ባለፈው ዓመትም ተማሪዎች ውጤታማ መሆናቸውን የሚናገሩት ዶክተር ገላና፤ ዘንድሮ ግን ከስድስት በማይበልጡ ዞኖች ያውም በተወሰኑ ወረዳዎች ላይ በነበረ ችግር ያውም የማካካስ ሥራ በተከናወነበት የተማሪዎች ውጤት ላይ ተጽዕኖ ይፈጥራል የሚል እምነት እንደሌላቸው ይገልጻሉ፡፡
የነበረውን ክፍተት ለማስተካከል ሁሉም ተረባርቦ መሥራት መቻሉ፤ በተለይ ግጭት በነበረባቸው አካባቢዎች አሁንም ድረስ መምህራን የማካካሻ ትምህርት/ቱቶሪያል/ እየሰጡ እንደመሆኑና በሌሎች አካባቢዎችም ተማሪዎች ከሞዴል በኋላ የማጠናከሪያ ትምህርት እየወሰዱ፣ ትኩረት ሰጥተውም እያጠኑ እንደመሆኑ ካለፉት ሁለትና ሦስት ዓመታት የተሻለ ውጤት ይመጣል ብለው እንደሚጠብቁም ይናገራሉ፡ ፡ በቀሪ ጊዜያትም በዚሁ አግባብ እንደሚሠራና ለዚህም የተማሪዎች የግል ጥረትና የወላጆችንምድጋፍ ከፍተኛ ሚና እንዳለው ጠቁመዋል፡፡
የግጭት አከባቢዎች ላይ
ዶክተር ገላና እንደሚሉት፤ ከዚህም ቀደም ሲልም ችግር ያለባቸውና የተፈናቀሉ አካባቢዎች ተማሪዎቹ በሄዱበትና በሰፈሩበት አካባቢ ባለ ትምህርት ቤት እንዲማሩ ተደርጓል፡፡ አካባቢዎቹ ሲረጋጉና ወደየትምህርት ቤቶቻቸው ሲመለሱም መምህ ራንም፤ ትምህርት ቤቶችም ተረባርበው በትርፍ ሰዓትና በዕረፍት ቀን ሜካፕ እንዲሰጡ ተደርጓል፡፡ ከዚህ ባለፈም አሁን ላይ በክልሉ ከአቅም በላይ የሆነ ነገር የለም፡፡
ቀድሞም የነበረው ተማሪዎች በትምህርታቸው ወደኋላ ይቀራሉ የሚል ነበር፤ ይህ ግን በመካካሱ የተለየ ተጽዕኖ ይፈጥራል የሚል ነገር የለም:: የተማሪዎች ምዝገባ ተካሂዷል፤ አድሚሽን ካርድም ወስደዋል፤ ሁሉም ተማሪም በመርሐ ግብሩ መሰረት ፈተናውን ይፈተናል፡፡ አቶ ካሴ እንደሚሉት ደግሞ፤ ግጭት ባለባቸው አከባቢዎች (ለምሳሌ፣ ማዕከላዊ ጎንደር ላይ፣ ምዕራብ ጎንደር ላይ) በነበረው ችግር ምክንያት ተማሪዎች የተፈናቀሉባቸው አካባቢዎች ላይም የተፈጠረውን ችግር ለማካካስ የተለያዩ ሥራዎች ተከናውነዋል፡፡
በዚህም ተማሪዎች በሚኖሩበት አካባቢ ተመዝግበው እንዲማሩና ለፈተናው እንዲዘጋጁ ጥረት ተደርጓል፡፡ የማካካሻ ትምህርት እንዲሰጥም ተሞክሯል፡፡ ይሁን እንጂ ችግሩ በተፈጠረባቸው አካባቢዎች የተወሰኑ የተዘጉ ትምህርት ቤቶችና አሁንም ድረስ የማይማሩ ተማሪዎች አሉ:: በዚህም በተለይ ማዕከላዊ ጎንደር ውስጥ የስምንተኛን፣ አስረኛንም ሆነ አስራ ሁለተኛ ክፍል ፈተናዎችን የማይወስዱ ተማሪዎች አሉ:: ከዚህ ውጪ ባለው ግን ፈተናውን በውጤትና ስኬት ለማጠናቀቅ በየደረጃው እየተሠራ ነው፡፡
መልዕክት
ዶክተር ገላና እንደሚሉት፤ በዘንድሮው ዓመት በክልሉ 12ኛ ክፍል ከ87ሺ በላይ፣ 10ኛ ክፍል 450 ሺ 700 እንዲሁም ስምንተኛ ክፍል 513 ሺ የሚደርስ ሲሆን፤ በጠቅላላው ከአንድ ሚሊየን ተማሪ በላይ የሚፈተን ይሆናል:: ለምሳሌ፣ በክልሉ ትምህርት ቤቶች ብቻ ከ1 ሺ 35 በላይ መፈተኛ ጣቢያዎች አሉ፡፡ ይህ ደግሞ ከማዕከል እስከ 700 ኪሎ ሜትር ርቆ ነው ፈተና የሚሰጠው፡፡ እናም ፈተናውን ለማጓጓዝና ለመጠበቅ፣ ፈተናውን ለመመለስና ለማረም ሰፊ ሀብት የሚጠይቅ ነው፡፡ ይሄ የሚሆነው ተማሪዎችን እንደየደረጃቸውና ችሎታቸው ለመለየት ሲሆን፤ እንደየ ደረጃቸውም በአገር ኢኮኖሚ ውስጥ አስተዋጽዖ እንዲያደርጉ ለማስቻል ነው፡፡
ይህ የሚሆነው ግን የሚሰጠው ፈተና ምስጢራዊነትና የፈተና ስርዓትም ተጠብቆ ተማሪዎችም ራሳቸውን ችለው ሲሠሩ፤ ህብረተሰቡም ለዚህ ተባባሪ ሲሆን ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ በኩል ተማሪዎችም ሆኑ ህብረተሰቡ ትብብር ሊያደርጉ ይገባል፡፡ በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እንደ ፋሽን እየተወሰደ ያለው የፈተና ስርቆት እንዲቀር ለማስቻል የጸጥታ ኃይሉ፣ ፈታኙና ሌላውም አካል ለህሊናቸው ተገዢ ሆነው ፈተናው ስርዓቱን ጠብቆ እንዲጠናቀቅ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡
አቶ ካሴ በበኩላቸው እንደሚሉት፤ በክልሉ በዚህ ዓመት በመደበኛ ፣በማታና በግል 416 ሺ 728 (205ሺ 969 ወንድ እና 210ሺ 759 ሴት) ተማሪዎች በ4 ሺ 932 አስፈታኝ ትምህርት ቤቶች ውስጥ የስምንተኛ ክፍልን፣ 294ሺ 332 (142ሺ138 ወንድና 152ሺ194 ሴት) ተማሪዎች በ509 ትምህርት ቤቶችና በ490 ጣቢያዎች ደግሞ አስረኛ ክፍል ፈተናን የሚወስዱ ሲሆን፤ 93 ሺ 357 (49ሺ 597 ወንድና 43ሺ 760 ሴት) ተማሪዎች በ236 ትምህርት ቤቶችና በ228 ጣቢያዎች የ12ኛ ክፍል ፈተናን ግን በመደበኛና በግል ተማሪዎች ይፈተናሉ፡፡ ከእነዚህ ውስጥም 12ኛ ክፍል 97 ዐይነ ስውራንና 3 መስማት የተሳናቸው፤ 10ኛ ክፍል ደግሞ 217 ዐይነ ስውራንና 12 መስማት የተሳናቸው ተማሪዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ተማሪዎችም የአገር የነገ ተስፋዎች እንደመሆናቸው በዚህ ልክ የለፉበትን ፍሬ ለማሳመር ሁሉም የበኩሉን ሊወጣ ይገባል::
በዚህም በየደረጃው ካለ አካል ክትትልና ድጋፍ ጀምሮ ወላጆች፣ መምህራን፣ የጸጥታ ኃይሉና ሌሎችም አካላት ልጆቹን ከመደገፍና ከመምከር ጀምሮ ተረጋግተው የሚፈተኑበትን ሁኔታ ለመፍጠር መትጋት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ፈተናዎችን የማጓጓዝ፣ የመረካከብና የማስቀመጥ ሂደቱን እንከን የለሽ ለማድረግ ተገቢውን ጥንቃቄ ማድረግ፤ ፈተናውም በጥሩ ሁኔታ እንዲካሄድ ሁሉም የድርሻውን መወጣት አለባቸው፡፡ ተማሪዎችም ኩረጃን በመጠየፍ ራሳቸውን ችለው እንዲሠሩ በቀራቸው ጊዜ ማጥናት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህ ሲሆን ነው አገር ተረካቢነታቸውን የሚያረጋግጥ አቅም መፍጠር የሚችሉት፡፡
አዲስ ዘመን ግንቦት 19/2011
ወንድወሰን ሽመልስ