በ1955ዓ.ም ንጉሠ ነገሥቱ አፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት ነው፤ የውጭ ሀገር ትምህርት ተከታትለው ወደ ሀገራቸው የተመለሱት አቶ ሀብተሥላሴ ታፈሰ ወደ ንጉሡ ቀርበው ሃሳባቸውን አስደመጡ። ይህም ስለ ቱሪዝም ድርጅት አስፈላጊነት ነበር። ሃሳባቸውን ተቀባይነትን፣ ሥራቸውም ፈቃድን አግኝቶላቸው የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት ያኔ ተቋቋመ። ኢትዮጵያ ከሃምሳ ዓመታት በላይ የተገለገለችበት «የ13 ወር ጸጋ» የተዋወቀው ይሄኔ ነው።
ይህ ለዓመታት ያገለገለና ለኢትዮጵያም እውቅናን የሰጣት መለዮ ከጥቂት ዓመታት በፊት «ምድረ ቀደምት» (Land of Origins) ወደሚል ስያሜ መቀየሩ ይታወሳል። ይህ መለዮ ይፋ የሆነው በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ የሚመራው የኢትዮጵያ ቱሪዝም ትራንስፎርሜሽን ምክር ቤት 3ተኛው መደበኛ ስብሰባውን ሐምሌ 7 ቀን 2008ዓ.ም ባካሄደበት ወቅት ነው።
ይሁንና በዚህ ጊዜ መለዮው የአማርኛ ትርጓሜው አልቀረበም ነበር። ታዲያ አዲሱ መለዮ በእንግሊዝኛ ቋንቋ Land of Origins በሚል ይፋ ተደርጎና እውቅናን አግኝቶ፤ ትርጓሜውም ቀርቦ ወደ ሥራ እስከተገባበት ጊዜ ድረስ አምስት ለሚጠጉ ዓመታት የኢትዮጵያ ቱሪዝም ያለ መለዮ ቆይቷል ማለት ይቻላል። ይህም ብቻ ሳይሆን መለዮው ከተዋወቀ በኋላም ትርጓሜው በየመገናኛ ብዙኅኑ በተለያየ መንገድ ይቀርብ ስለነበር፤ በተመሳሳይ መልኩ ማስኬድ አለመቻሉ ብዙ ቅሬታዎችን ማስነሳቱ ይታወሳል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ጥቅምት 8 ቀን 2009ዓ.ም፤ «‘ኢትዮጵያ ላንድ ኦፍ ኦሪጅንስ’ በሚል የተሰየመው የቱሪዝም መለያ ተስማሚና ሁሉንም የሚያግባባ የአማርኛ ትርጉም ሊሰጠው እንደሚገባ የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ጠየቁ።» ሲል ባስነበበው ዜና ይህን ጉዳይ አትቷል። እንኳንና መለዮው በሰፊው አገልግሎት ላይ ሊውል ቀርቶ ኅብረተሰቡ እንዲሁም በዘርፉ የተሰማሩ ባለሙያዎች ሳይቀሩ የየራሳቸውን ትርጓሜ እየሰጡት መሆኑ በዚህ ተጠቅሷል።
ይህንን ተከትሎ መጋቢት 13 ቀን 2009 ዓ.ም. አራተኛው የቱሪዝም ትራንስፎርሜሽን ምክር ቤት ስብሰባ ተካሄደ። በዚህ ጉባኤ ላይ አዲሱ የኢትዮጵያ ቱሪዝም መለዮ ስያሜ በአማርኛ ቋንቋ አቻ ፍቺ ቀረበለት፤ «ምድረ ቀደምት» ተባለና በይፋ ተመረቀ። በዚህ ጊዜም «የ13 ወር ፀጋ» የሚለውን መለዮ ያስተዋወቁትና በቱሪዝም ላይ በአያሌው ሲሠሩ የነበሩት የቱሪዝም አባት አቶ ሀብተሥላሴ ታፈሰ ብሔራዊ እውቅና እንዲሁም ሽልማት ተበረከተላቸው።
ይህን አዲስ መለዮ ለመቀበል በመገናኛ ብዙኃን በኩል ሳይቀር ጊዜ ወስዷል። በቱሪዝም ዘርፍ ላይ የሚንቀሳቀሱ ተቋማት ጭምር ከዚህ መለዮ ይፋ መሆን በኋላም የቀደመውን ሲጠቀሙ ይስተዋል ነበር። በዚህም ላይ አዲሱ መለዮ ምን ያህል ኢትዮጵያን ገላጭ ነው? መቀየሩ ለምን አስፈለገ? የሚሉ ጥያቄዎች ተነስተው ብዙ አወያይተዋል፤ አከራክረዋል።
በእርግጥ መለዮው ከባለሙያዎች የሚነሳበት አስተያየት እንዳለ ሆኖ ኢትዮጵያን ገላጭ መሆኑ ግልጽና የማያጠያይቅ ነው። የ59ኛው የተባበሩት መንግሥታት የዓለም ቱሪዝም ድርጅት ጉባዔ በኢትዮጵያ በተካሄደበት ጊዜ፤ የዓለም የቱሪዝም ድርጅት ዋና ጸሐፊ ዶክተር ታሊብ ሪፋይ በሰጡት አስተያየት «‘ምድረ ቀደምት’ የሚለው አዲሱ የኢትዮጵያ የቱሪዝም መለያ የሀገሪቱን ጥንታዊነትና የሰው ዘር መገኛነት ያረጋግጣል። የዓለም ሕዝብ የዘር ግንዱ ምንጭ ኢትዮጵያ መሆንዋን ይበልጥ እንዲያውቅና እንዲገነዘብ ብሎም የቅድመ አያቶቹን ሀገር እንዲጎበኝ የሚያነሳሳ ነው» ሲሉ አስተያየት መስጠታቸው የሚታወስ ነው።
«ኢትዮጵያ እርግጥ ነው ‘ምድረ ቀደምት’ ተብላለች፤ ይህንን መለያ እያደነቅሁ ግን ደግሞ ኢትዮጵያ ከዚያም በላይ መሆኗን እመሰክራለሁ። የቀደመው የሰው ልጅ መገኛ ብቻ ሳትሆን የደጋጎች፣ የሳቂታዎች፣ የጀግኖች፣ የአዋቂዎች፣ …. ምድር፤ ምድረ ቀደምት መባል የሚያንሳት ልዩ የመስህብ ሀገር ነች» ሲሉ ለኢትዮጵያውያን ያላቸውን አድናቆት ውብ በሆነው የቃላት ገለጻቸው ተናግረዋል ።
በእርግጥ ሌላ ምስክርም አያሻ፤ ኢትዮጵያ ሳይንስም ሆነ ታሪክ እንደሚያስረዳው የቀደምቶች መገኛ ነችና ስያሜው የሚገባት ነው። ተጓዡ ጋዜጠኛ ሄኖክ ስዩም ስለዚህ አዲስ መለዮ ሲናገር «የታቦተ ጽዮን መገኛ፣ ሁለተኛው ሂጅራ የተደረገባት ቀደምት ሀገር፣ ባለ ሰንሰለታማ ተራሮች፣ ሦስት ዓይነት ሥነ-ምህዳር የሚገኝባት ኢትዮጵያ የቡና መገኛ ብቻ አይደለችም። የጥቁር አባይ መነሻ፣ የብርቅዬ አእዋፍና አጥቢ እንስሳት መኖሪያ የራሷ የጽሑፍ ፊደል ባለቤት ቀደምት ሀገር ናት።» ብሏል።
ድንቅነሽ (ሉሲ) ከምድረ ኢትዮጵያ የመገኘቷ ነገርም ኢትዮጵያን ምድረ ቀደምት ያሰኛታል። በቅዱሳን መጻሕፍት ስሟ ደጋግሞ መጠቀሱ፣ በታሪኳ የሚታየው ከዓለም ስልጣኔ የቀደመ ገናናነቷ፣ በተፈጥሮ ከተቸረችው ውጪ በሕዝቧ ጥበብና እውቀት የተሸለመችው ኪነ- ህንጻና ሥነ-ጥበብ፤ ፍልስፍና እና እውቀት ኢትዮጵያን ምድረ ቀደምት ቢያሰኛት ልኳ ቢሆን እንጂ አይበዛባትም።
ይህም መለዮ ልክ እንደ «13 ወር ፀጋ» ሁሉ በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅናን ያገኛል ተብሎ ሲጠበቅ ነበር። ታዲያ ግን በቅርቡ በተሰማው ዜና በተመሳሳይ በዚሁ በአዲስ ዘመን ጋዜጣ በቀረበው ዘገባ መሰረት ይህ ከሦስት ዓመታት በላይ በእውቅና ሂደት የቆየውና ዛሬም «አዲስ» እየተባለ ያለው የኢትዮጵያ ቱሪዝም መለዮ፤ በህብረተሰቡ ዘንድ እንዳልሰረጸ የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት ማስታወቁ ይታወሳል።
ኢትዮጵያን በሚገባ ይገልጻታል የተባለው አዲሱ የቱሪዝም መለዮ ኢትዮጵያን በሚገባ የማስተዋወቅ አቅም ያለው ቢሆንም ድርጅቱ መለዮውን የማስተዋወቁን ሥራ ባለማከናወኑ በሚጠበቀው ልክ ሊታወቅ እንዳልቻለ ተገል ጿል። ይህንን ችግር ለመፍታት ከድርጅቱ በኩል አገራዊ የምክክር መድረክ ማዘጋጀት እንዲሁም ከሚመለከታቸው የባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር የማሳወቅ ሥራ እንደሚሰራ ተገልጿል።
ድርጅቱ መለዮውን በሚገባ ስላለማስተ ዋወቁ ጥፋቱን ያመነ በመሆኑ ሌላ ወቀሳ መጨመር አያስፈልግም። ይሁንና አሁንም ቢሆን ያጎደሉትን ከማመን ባሻገር የጎደለውን መሙላት ወሳኝ ነው። የቱሪዝም አባት የተባሉት ሀብተሥላሴ፤ ኢትዮጵያን በቱሪዝም ለማስተዋወቅ ሲጀምሩ ጊዜው እንደ አሁን በቴክኖሎጂ የሚያግዛቸው አልነበረም። መለዮውን በፎቶግራፍና በፖስት ካርዶች እንዲታተሙ በማድረግ ነበር በጊዜው በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅናን እንዲያገኝ ያስቻሉት።
ተጓዡ ጋዜጠኛ ሄኖክ ስዩም አስቀድሞ ከመለዮው ይፋ መሆን በኋላ ሲናገር፤ «ኢትዮጵያ የነገሮች ሁሉ ምንጭ እንደሆነች የሚገልጸውን የመለዮ ስያሜ በብዙ ቋንቋዎች ተርጉሞ ማስተዋወቅ ያስፈልጋል። ምናልባትም ከፈረንሳይኛና ከአረብኛ በፊት አማርኛ፣ ኦሮምኛ፣ ትግርኛ እያልን የኢትዮጵያ ሰው ሀገሩ ራሷን የምትገልጽበትን መለዮ እንዲለይ ማድረግ ያሻል። መለዮዋን ራሳቸው የማያውቁት ዜጎች ያሉባት ሀገር ለዓለም እወቁልኝ ብትል ዓለምን ሳቁብኝ እንደማለት የሚቆጠር ነውና።» ሲል አክሎ አስተያየቱን ሰጥቷል።
ሁሉም ነገር በቅድሚያ በባለቤቱ በሚገባ ሲታወቅ መልካም ነውና ይህ መለዮ በቅድሚያ አገር ውስጥ ከዳር እስከ ዳር በማስተዋወቁ በኩል ሊሠራ ይገባል። ይህም በአንድ ወገን በሕትመት ሥራዎች ሊሠራ የሚችል ሲሆን በተጓዳኝ ቱሪዝም ድርጅት በተለያዩ ማኅበራዊ እንቅስቃሴዎችና ስብስቦች ላይ ተሳትፎ ማድረግ ይኖርበታል።
በአገራዊ መድረኮች፣ የዓለምን ትኩረት በሚስቡ ኢትዮጵያዊ በሆኑ ብሔራዊም ሆነ ሃይማኖታዊ ክዋኔዎችና በመሳሰሉት ላይ መለዮው ትኩረት እንዲያገኝ ማድረግ ይቻላል። ልክ በሁለተኛው ሺህ ዓመተ ምህረት ወይም በሚሌኒየሙ የተደረገውን ዓይነት ንቅናቄ በማድረግና መለስ ብሎ ያለፈውን ተሞክሮ በማየት ይህን ከግብ ማድረስ ይቻላል።
ሰዎች አንድን መለዮ ሳይረሱ ሊያስታውሱት የሚችሉት ለነገሩ በሚኖራቸው ቅርበት መጠን ነው። እናም ይህን መለዮ ማስተዋወቅ ማለት ብዙዎችን ወደ ኢትዮጵያ ማቅረብ እንደማለት ነው። ይኸው ደግሞ «ኢትዮጵያ ምድረ ቀደምት» የተሰኘ መለዮ ራስን በስም የማስተዋወቅ ያህል ቀላል፤ አይረሴ እንዲሆን ደግሞ በተደጋጋሚና በተገኘው አጋጣሚ ለሕዝቡ እይታ መቅረብ አለበት። «ባለቤቱ ያቀለለውን…» ይሉትን ብሂል እንዳይሆን፤ በቅድሚያ በቤታችን ይህን መለዮ በአገር ውስጥ አዳርሶ ማስተዋወቁ ላይ ትኩረት ይደረግ ስንል እናስታውሳለን። ሰላም!
አዲስ ዘመን ግንቦት 11/2011
ሊድያ ተስፋዬ