ሀላባ በደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል ውስጥ ከሚገኙ ብሔረሰቦች አንዱ ነው። የሀላባ ብሔረሰብ የራሱ የሆነ ባሕል፣ ወግ እና ሥርዓት አለው። ብሔረሰቡ ከትውልድ ወደ ትውልድ እየተላለፈ የመጣ፣ የራሱ የሆነ ‹‹ሴራ›› በሚል የሚጠራ ትውፊታዊ የአስተዳደር መዋቅር፣ የሥነምግባር ሕግ፣ የአሠራር ደንብና ሥርዓት አለው። ‹‹ሴራ›› የግለሰቦችንና የቡድኖችን ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ትስስሮች፣ ግንኙነቶችና እንቅስቃሴዎችን ይወስናል። በሀላባ የሁሉ ነገር የበላይ የሆነው ይህ የ‹‹ሴራ›› ሥርዓት ዴሞክራሲያዊነት፣ ራስን በራስ ማስተዳደር፣ መረጃ መለዋወጥ፣ መረዳዳት፣ የሥራ ድርሻ ክፍፍል ማድረግ፤ ዕውቀት፣ ታዛዥነት እና ሰው አክባሪነት በሀላባ ሴራ ውስጥ መሠረታዊ እሴቶች ናቸው።
የሀላባ ልማት ማኅበር ፕሬዚዳንትና የሀላባ ባሕልና ታሪክ መጽሐፍ ደራሲ አቶ አምሩላህ ጠለሀ እንደገለጹልን፤ የሀላባ የ‹‹ሴራ›› ሥርዓት አፋዊ ትውፊቶችና መገለጫዎችን፣ ማኅበራዊ ክንዋኔዎች፣ ሥነ-ሥርዓቶችና ፌስቲቫሎችን፣ የሀገር በቀል እውቀቶችን፣ የዕደ ጥበብ እውቀቶች፣ ክህሎቶችንና ሀገረሰባዊ ጥበባትንና ቅርሶችን ሰብስቦ የያዘ ሥርዓት ነው። ‹‹ሴራ›› ቤተሰብ እንዴት እንደሚመሠረት፣ ስለ ልጅ አስተዳደግ፣ እውቀት ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዴት፣ መቼና በማን መተላለፍ እንዳለበት እንዲሁም ስለ ሥራ ድርሻና ክፍፍል፣ የኢኮኖሚዊ እንቅስቃሴ የሚያሳይ ማስፈፀሚያ ዘዴ ወይንም ማኑዋል ነው።
ሴራ ግለሰቦች ከግለሰቦች፣ ከቤተሰባቸው፣ ከጎረቤታቸው፣ ከዘመዶቻቸው፣ ከአማቾቻቸው፣ ከጎሳዎቻቸው፣ ቤተሰቦች ከቤተሰቦች፣ ጎሳዎች ከጎሳዎች፣ ጎሳዎች ከአጠቃላይ የሀላባ ማኅበረሰብ ጋር ሊኖራቸው የሚገባው ግንኙነት እንዴት መሆን እንዳለበት የሚደነግግ የግንኙነት መመሪያ ነው። በሀላባ ሕዝብ ውስጥ ሴራ ቁልፍ ስፍራ አለው የሚሉት አቶ አምሩላህ፤ ለሴራ መታመንም ዋነኛ የሀላባ ሰው መገለጫው መሆኑን ተናግረዋል።
እንደ አቶ አምሩላህ ገለጻ፤ የሀላባ ሴራ እንዲተገበር፣ ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲተላለፍ የሚያገለግሉ ተቋማት በውስጡ አደረጃጀት ተፈጥሯል። በዚህ አደረጃጀት ውስጥ አንዱ ‹‹ኦገቴ ሴራ›› ሲሆን፣‹‹ኦገቴ›› የሚለው ቃል ሸንጐ ወይንም ምክር ቤት የሚለውን የአማርኛ ቃል ሊወክል ይችላል፤ ሴራ የሚለው ቃል ሥርዓት የሚለውን የአማርኛ ቃል ይተካል። የሀላባ ኦገቴ ልክ በዘመናዊ አደረጃጀት ከወረዳ እስከ ፌደራል እንደ ተደራጀ በየደረጃው የሚገኙ የመንግሥት አካላት አደረጃጀት አይነት ተደርጎ ይጠቀሳል። ከቤተሰብ ጀምሮ እስከ ንዑስ ጐሳ አጠቃላይ ብሔረሰቡን የሚወክልና አስተዳደራዊ መዋቅር ያለው ነው።
የሀላባ ኦገቴ አራት የተለያዩ ሥልጣንና ተግባር አላቸው። እነርሱም፤ በቤተሰብ ደረጃ /ቦኪ ኦገቴ/፣ በንዑስ ጎሳ ደረጃ (ሚኔ ኦገቴ)፣ የጐሳ ደረጃ /ደቦ አገቴ/፣ በብሔረሰብ ደረጃ /ሀላቢ አገቴ/፣ የቤተሰብ ሸንጐ /ቦኪ ኦገቴ/ በመባል ይጠራሉ። ቦኪ አገቴ /የቤተሰብ ሸንጐ/ በታችኛው የአስተዳደር ደረጃ የሚገኝ ሲሆን፣ ከቤተሰብ እስከ ንዑስ ጐሳ የሚገኙ አባላትን አባል አድርጐ የያዘ አስተዳደር እርከን ነው። የቦኪ ኦገቴ ተግባራቱ በቤተዘመድ ደረጃ የሚከሰቱ ግጭቶችን የሚፈታና በቤተዘመድ አባላት ላይ የሚደርሱ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን የሚያቃልል፣ የሚወስን ተቋም ነው።
ሚኒ ኦገቴ የሀላባ የአስተዳደር እርከን ከቤተሰብ ቀጥሎ የበርካታ ቤተሰቦች ስብሰብ የያዘ የንዑስ ጎሳ አባላት የአስተዳደር እርከን ነው፣ በንዑስ ጐሳው ውስጥ የሚገኙ ቤተሰቦችን አጠቃሎ የያዘ ኦገቴ ነው። ይህም በንዑስ ጐሳ አባላት መካከል የሚከሰቱ ግጭቶችን ይፈታል፤ በንዑስ ጐሳ አባላት ላይ የሚደርሱ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ያቃልላል። የጐሳ ሸንጐ /ደቦ ኦገቴ/ ደግሞ በሀላባ አስተዳደር እርከን ሶስተኛው የአስተዳደር እርከን ሲሆን፣ በጐሳው ውስጥ የሚገኙ ንዑስ ጐሳዎችን አጠቃሎ የያዘና ሁሉንም የጐሳ አባላት አባል አድርጐ የሚይዝ ኦገቴ ነው ይላሉ።
ሀላቢ ኦገቴ /የሀላባ ሸንጐ/ የመጨረሻው የሥልጣን እርከን ሲሆን፣ በሀላባ ውስጥ የሚገኙ ሁሉንም ጐሳዎች አባል አድርጐ የሚንቀሳቀስ በጣም ትልቅ በሀላባ ማኅበረሰብ ወሳኝ እና ተፅዕኖ የሚፈጥር አደረጃጀት ነው። ከታች እስከ ላይ ደረጃ የሚገኙ መዋቅራዊ አደረጃጀቶች በሴራ በተወሰነላቸው የሥልጣንና ተግባር ወሰን ራሳቸውን ያስተዳድራሉ። የላይኛው በታችኛው ሥልጣን ጣልቃ አይገባም፣ ሁሉም በራሱ መሪ ነው የሚተዳደረው፤ እያንዳንዱ አባወራ በቤተሰብ እርከን፣ የቤተሰቡ በንዑስ ጎሳው፣ የንዑስ ጎሳው በጎሳው፣ የጎሳው በሀላባ ተወካይ ያለው ሲሆን፣ የጋራ ጉዳዮችን በጋራ ነው የሚሳተፉት።
እንደ አቶ አምሩላህ ማብራሪያ፤ በኦገቴ ሴራ በሁሉም እርከን የሚቀርቡ ውሳኔ የሚሹ አጀንዳዎች ሲቀርቡ አጀንዳውን በአሉታዊ፣ በአዎንታዊ ወይም በመደገፍ፣በመቃወም ሀሳብ ይንሸራሸርበታል። ይህም የሚከናወነው ‹‹ቆርቶ›› ተብለው በሚታወቁ በነገር አዋቂነታቸው በተመረጡ ሁለት ሰዎች አማካይነት ነው። ተቃራኒ ሀሳቦች በሁለቱ ቆርቶዎች በሚገባ ከተብራሩና ክርክር ከተካሄደበት በኋላ የውሳኔ ሃሣብ ለተሰብሳቢው ይቀርባል። ሁለቱ ቆርቶዎች ሲከራከሩ የተሳሳተ አቅጣጫ ከተከተሉ ከተሰብሳቢዎች መካከል ‹‹ሎኩታ›› በማለት ዕድል ይጠይቅና ወደ ስህተት የገባውን ከስህተት እንዲመለስ ይደረጋል።
ውሳኔ የመስጠቱ ሂደት ደግሞ‹‹ጉምጉማ›› ይባላል። በ‹‹ቆርቶዎች›› መካከል በተካሄዱት ተቃራኒ ሃሣቦች ላይ ስብሰባ በማካሄድ ድምፅ ይሰጥበታል። ድምፅ አሰጣጡም እጅ በማውጣት ነው የሚከናወነው። ሁሉም በየተራ ስለጉዳዩ በማብራራት የሚደግፉትን ሃሳብ ይሰጣሉ። ተሰብሳቢዎች በአብላጫ የደገፉት ሃሣብ በዲሞክራሲያዊ መንገድ እንዲፀድቅ ይደረጋል።
የኦገቴ ሴራ ቅሬታዎች የሚስተናገድበትም ሥርዓት አለው። በታችኛው የአስተዳደር እርከን የተወሰኑ ውሳኔዎች በቀጣዮቹ የእርከን ደረጃዎች ቅሬታ ማቅረብ እንደሚቻል አቶ አምሩላህ ይጠቁማሉ። በኦገቴ የአሠራር ሥነ-ሥርዓት የኦገቴው ዋና አጀንዳ ከመጀመሩ በፊት ከየአቅጣጫው የመጡ ተሰብሳቢዎች መረጃ እንዲለዋወጡ ያስገድዳቸዋል፤ ያለመረጃ ልውውጥ በየትኛውም ደረጃ የሚካሄድ ኦገቴ ከሴራ ደንብ ውጭ ነው ይላሉ። መረጃ የመለዋወጥ ሂደት ‹‹ዱዱቦ›› ተብሎ ይታወቃል፤ በዚህ የመረጃ ልውውጥ ሂደት /ዱዱቡ አቀሙ/ የጐሳ መሪዎች ወቅታዊ የአየርና የገበያ ሁኔታዎችን፣ ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ የአካባቢ፣ የሀገር አቀፍና የዓለም አቀፍ ክስተቶችን ያያዘውን መረጃ ያቀርባል።
አቶ አምሩላህ እንዳሉት፤ ሀላባዎች ባሕልና ወግ ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲተላለፍ ከሚያደርጉባቸው ዘዴዎች አንዱ የሀላባ ታዳጊዎች ወደ ወጣትነት በሚያደርጉት ሽግግር በየዓመቱ የስድስት ወር ልምምድና የሥልጠና ጊዜ እንዲኖራቸው ይደረጋል።
ሥልጠናውም የ‹‹ነቀታ ሴራ›› በሚባለው ተቋም ይሰጣል። ሥልጠናውም የሚሰጠው ከተገረዙ በኋላ ባለው ስድስት ወራት ጊዜ ውስጥ ነው። የተገረዙት ልጆችም የአደረጃጀት አይነቶች፣ የሥልጣን ክፍፍሎችን፣ የዜጎች የሥራ ድርሻዎችን፣ ባህላዊ ክዋኔዎችን፣ ሥነ ጥበቦችን፣ የብሔረሰቡን ሕገ ሥርዓቶችን፣ የማዕረግ ስሞችን፣ የጀግና መፍጠሪያ መንገዶችን ባጠቃላይ የሀላባ ማኅበረሰብ ሥርዓት እንዴት እንደሚሠራ በመጀመሪያ ሦስት ወር በንድፈ ሀሳብ፣ በቀሪው ሦስት ወራት ደግሞ በተግባር በጫወታና በሚያዝናና ሁኔታ እንዲሰለጥኑና እንዲለማመዱ የሚደረግበት ተቋም እንደሆነ አስረድተዋል። ጥንታዊ ሀላቦች ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲተላለፍ ብለው ታዳጊዎች እንዲማሩበት ያስቀመጡት የሴራ ማሰልጠኛ ተቋም በአሁኑ ትውልድ ላይም መድረሱን ይገልጻሉ።
እንደ አቶ አምሩላህ ማብራሪያ፤ በሀላባ የዘመን መቁጠሪያ ቀመር መሠረት “ኢብጂ” ተብለው የሚታወቁ ያልተገረዙ ሕፃናት ‘መሰሮ”(ሐምሌ) ወር መጀመሪያ ቀኖች ይገረዛሉ። የሀላባ ልጆች ከተገረዙበት ቀን ጀምሮ ለሁለት ወራት ከቤት ሳይወጡ እየተመገቡ ‹‹ገዳሞጂ›› ተብለው ከሚታወቁ በቅርብ ዓመታት የተገረዙ ልጆች ከቤተሰቦቻቸው የንድፈ ሀሳብ ትምህርት እየወሰዱ ይቆያሉ። “ኢዳራ”( መስከረም) እና “መሼታ”(ጥቅምት) በአካባቢው በሚገኙ ትላልቅ ዛፎች( ነቀታ) ስር የንድፈ ሀሳብ ትምህርት በሚሰጥበት ክፍል ውስጥ የተማሩትን፣ በአጠቃላይ የኅብረተሰቡን የአኗኗር ብሂል ትውፍታዊ አስተዳደር መዋቅር፣ የፆታ ልዩነት መሠረት ያደረጉ ሚናዎችንና የሥራ ድርሻዎችን፣ ባሕላዊ እሴቶችን ደንቦችንንና ሕጎችን ወዘተ በጨዋታ መልክ መተግበር ይጀምራሉ። ከ‹‹ነቀታ›› ቀጥሎ ባሉት ሁለት ወራት ከ‹‹አንቶጎታ›› እስከ ‹‹መንገሳ››አጋማሽ ከአንድ ቤት ወደ ሌላ ቤት እየተንቀሳቀሱ “ሀዌሻ” ድግስ እየተመገቡ ሁለተኛውን የተግባር ልምምድ ይወስዳሉ።
ለስድስት ወራት የተከናወነው ሥርዓት ለተሳታፊ ልጆች በእድሜ ዘመናቸው በፍፁም ከማይረሷቸው መልካም አጋጣሚዎች ትዝታዎችና አይረሴ የሕይወት ገጠመኞች መካከል አንዱና ዋነኛው በመሆኑ የተገረዙ ልጆች ይህ የደስታና የክብር የስድስት ወር ጊዜ እንዲሁም የልጅነት ጊዜ እንዲያልቅባቸው አይፈልጉም የሚሉት አቶ አምሩላህ፣ ለዚህም ምክንያቱ ስድስት ወራትን የፈጀውን አስደሳች የግርዘት ክዋኔን ጨርሰው ወደ ወጣትነት ደረጃ ኃላፊነትን ወደ መቀበል የሚሸጋገሩበት የሽግግር ወር በመሆኑ ነው ይላሉ።
የሀላባ ሴራ የሴራው አካል የሆነውን ማኅበረሰብ የኢኮኖሚ ችግሮች ለመፍታት ከፈጠራቸው ተቋማት አንዱ ‹‹ሚሻላ›› ተብሎ የሚታወቀው የተቸገሩትን የመርዳትና የመደገፍ ሥርዓት ነው። በ‹‹ሚሻላ›› ሥርዓት ከሕዝቡ መካከል ግለሰብም ቡድንም ከአቅም በላይ በሆነ ችግር በሰው ሠራሽም ሆነ በተፈጥሮ ምክንያት ከገባበት አደጋም ሆነ ሌላ ችግር እንዲወጣ የሚደረግበት የመረዳዳት ‹‹ሴራ›› የፈጠረው የአደጋ ጊዜ ደራሽ ተቋም ነው።
ሚሻላ ከጎሳ በታች ባሉ የኦገቴ እርከኖች ደረጃ የሚገኝ ሲሆን፣ እንደ ችግሩ ስፋትና ጥልቀት የድጋፍ አድማሱ ሊሰፋና ሊጠብ ይችላል። የሀላባ ‹‹ሴራ›› የ‹‹ሚሻላ›› እርዳታ መጠቀም ይችላሉ ብሎ የለያቸው ሰዎች ከፍተኛ ጤና ማጣት ውስጥ የገቡ፣ ከፍተኛ ድህነት ውስጥ የተዘፈቁ፣ ቤት ንብረታቸውን በቃጠሎ ያጡ፣ በከፍተኛ ዕዳ የተዘፈቁ ሰዎች ናቸው።
በጤና መታወክ መሥራት ላልቻሉ የእርሻ ሥራቸውን ከማረስ እስከ መሰብሰብና መውቃት የሚደርስ እርዳታ ይደረግላቸዋል። መኖሪያ ቤት መሥራት ላልቻሉም ቤት ተሠርቶ ይሰጣቸዋል። ከአቅማቸው በላይ በሆነ ዕዳ ውስጥ የገቡ ግለሰቦች ዕዳቸውን የሚከፍሉበትና ሀብት በመሰብሰብ ከዕዳ የሚወጡበት ሁኔታ ይፈጠርላቸዋል። በቃጠሎ ሀብታቸውን ላጡ ሰዎችም ከአባላት ገንዘብ ተሰብስቦ ሀብታቸው እንዲተካላቸው ይደረጋል።
አንድ ለችግር ወይም ለአደጋ የተጋለጠ የማኅበረሰቡ አባል ችግሩ ወይም አደጋው እንደደረሰበት ወይም እንደተከሰተ ራሱ ለኦገቴ መሪዎች በማሳወቅ ሚሻላ እንዲቆረጥለት በመጠየቅ የድጋፍ ተጠቃሚ ይሆናል ወይም ደግሞ የኦገቴ መሪዎች ራሳቸው ችግሩን ተመልክተው ድጋፍ እንዲደረግለት ያደርጋሉ የሚሉት አቶ አምሩላህ፤ የድጋፍ ጥያቄው ከግለሰቡም ይምጣ ከ‹‹ኦገቴ›› መሪዎችም ይነሳ የድጋፍ ጥያቄ የቀረበለት የ‹‹ኦገቴ›› ሸንጎ ቁጭ ብሎ ተወያይቶ፣ ተከራክሮ በድምፅ ብልጫ ከፀደቀ ብቻ ነው የድጋፍ ጥያቄው ፀድቆ የሚተገበረው። ይሁን እንጂ ይህ የሀላባ ሕዝብ የአደጋ ጊዜ ተቋም (ሚሻላ) በተለያየ ምክንያት እየተሸረሸረ ነው። ሥርዓቱን ወደነበረበት ለመመለስ ጥረት እየተደረገ እንደሆነ ነው አቶ አምሩላህ የገለጹልን።
የሀላባ አባቶች ከጥንት ዘመን ጀምሮ የእርሻ ወቅቶችን ለመለየት፣ እንጨት የሚቆረጥባቸውን ጊዜን ለመወሰን፣ ሕፃናትን ወደ ወጣትነት ዘመናቸው ሠልጥነው፣ ተምረው እንዲሻገሩ ለማስቻል የራሳቸውን የቀን መቁጠሪያ ቀመር ፈጥረው አሁን ካለንበት ዘመን ማሻገር መቻላቸውን የሚጠቁሙት አቶ አምሩላህ፤ የሀላባ ዘመን አቆጣጠር መነሻው ጨረቃ በመሬት ዙሪያ በምታደርገው እንቀስቃሴ የተከተለ የዘመን አቆጣጠር መሆኑ ‹‹አገና››(ወር) የሚለው መጠሪያ ‹‹አገንቹ››(ጨረቃ) ከሚለው መጠሪያ ጋር መመሳሰሉ ማሳያ ነው ይላሉ።
የሀላባ ዘመን አቆጣጠር ያለፉ ዘመናት ለመቁጠር የሚጠቀመው በአንዳንድ ታሪካዊ ወይም ማኅበራዊ ክስተቶች በመጠቀም ሲሆን ለምሳሌ ሽብር የተከሰተበት ዓመት፤ የጦርነት ዓመት፣ ትላልቅ ሰዎች የሞቱበት ዓመት፤ የወረራን ዘመን ወዘተ በመጠቀም ነው የሩቅ ዘመን የሚቆጠረው። በሀላባ የሴራ ካላንደር መሠረት በመጨረሻው ወር ‹‹መንገሳ›› ነው። መንገሳ ዘመን መለወጫ ነው።
እንደ አቶ አምሩላህ ማብራሪያ፤ በ”መንገሳ” የሀላባ ምድር ሀብታም ነው። እህል ጎተራ የሞላበት፣ ማሳው ወርቃማ ቀለም የሚለብስበት፣ የሀላባ ከብቶች ያለ ጥበቃ የፈለጉበት ማሳ ገብተው የሚበሉበት፣ ማር ተቆርጦ እንጥብጣቢው ከቤት እስከ ገበያ የሚደርስበት፣ ትዳር የሌላቸው ወጣቶች ለሰርጋቸው ቀጠሮ የሚይዙበት፣ የሀላባ ዘመን አቆጣጠር አሮጌው ዘመን አብቅቶ አዲስ ዘመን የሚመጣበት ወር ነው መንገሳ። ‹‹መንገሳ›› እያበቃ ለ‹‹ወቶተ›› ወር ለመልቀቅ ሲዘጋጅ በሀላባ ሁሉም ከሰው እስከ እንስሳ! ከከተማ እስከ ገጠር! ሁሉም ደስተኛ ሲሆኑ መንገሳን የሚረግሙ፣ በመንገሳ መምጣት የሚማረሩ አንድ የሀላባ ማኅበረሰብ አካላት ግን አሉ። እነሱም ከሕፃንነት ወደ አዋቂነት የሚሸጋገሩ የነቀታው ሠልጣኞች ናቸው።
መላኩ ኤሮሴ
አዲስ ዘመን ሰኔ 2/2015