ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ግብርና የጀርባ አጥንት ነው ማለት ይቻላል። 80 በመቶ የአገራችን የሥራ ዕድል በዚሁ ዘርፍ የተፈጠረ ሲሆን ፤ ለአገር ውስጥ ጥቅል ምርት ግብርና 40 በመቶ ድርሻ አለው። በአፍሪካ ከፍተኛ ቡና አምራች ስትሆን ሰሊጥን ጨምሮ በበርካታ የጥራጥሬ ምርቶች በማምረት ትታወቃለች። ከለውጥ ወዲህ ለግብርናው ዘርፍ የተሰጠው ልዩና ተግባራዊ ትኩረት የቡናን ምርት በከፍተኛ ሁኔታ ማሳደግ ሲቻል፤ በኩታ ገጠም፣ በበጋ የስንዴ ልማት እየመጣ ያለው ለውጥ በአገራችን የአረንጓዴ አብዮትን እያቀጣጠለ ይገኛል። በአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም በአረንጓዴ አሻራ የተመዘገበው ውጤት የግብርናውን ክፍለ ኢኮኖሚ ዘላቂና ተከታታይ ለማድረግ መሠረት እየጣለ ይገኛል። ምርጥ ዘርና ሌሎች ቴክኖሎጂዎች ምርትንና ምርታማነትን እያሳደጉ ሲሆን፤ ትራክተር፣ ኮምባይነር፣ የውሃ መሳቢያ ፓምፓችና ሌሎች ቴክኖሎጂዎችም የሚታይና የሚቆጠር ለውጥ እያመጡ ይገኛል።
ሌላውን የኢኮኖሚ ዘርፍ ማለትም ኢንዱስትሪውንና ማኑፋክቸሪንጉን ይዞ ለመነሳት አቅም ይፈጥራል። የዓለም ሕዝብ ከ8 ቢሊዮን መሻገሩና እና ሕንድና ቻይና ተከታታይ ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት እያስመዘገቡ መሆናቸው መካከለኛ ገቢ ያላቸው ዜጎች ቁጥር በብዙ መቶ ሚሊዮኖች እየጨመረ ስለሆነ ለግብርና ውጤቶች ሸመታ የሚወጣው ሕዝብ በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ ስለሆነ መጪው ዘመን ለግብርና ብሩህ ነው ማለት ይቻላል። አገራችን በዚህ ዘርፍ በትክክለኛው ጊዜ ነው ወደፊት እየመጣች ያለችው። በምግብ እህል ራሷን ለመቻል የምታደርገውን ጥረትም እያቀላጠፈ ይገኛል። ይህ ደግሞ ለአመታት ስሟ ከርሀብና ከቸነፈር ጋር ተያይዞ ይነሳ የነበረችን አገር ገጽታ ስለሚቀይር የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ የራሱ ድርሻ ይኖረዋል።
ከግብርና እና ከአገልግሎት ዘርፉ ቀጥሎ ኢንዱስትሪው ወሳኝ የኢኮኖሚ ተዋናይ ነው። ከአገር ውስጥ ጥቅል ምርት ድርሻው 20 በመቶ ደርሷል። መንግሥት የፖሊሲ ማሻሻያ በማድረግ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንትንና የአገር ውስጥ ኢንዱስትሪዎችን እያበረታታ ይገኛል። የጨርቃ ጨርቅ፣ የቆዳና የምግብ ማቀነባበሪያ ፋብሪካዎች በውጭ ምንዛሬ እጥረት እምርታን እንዳያሳዩ የጋረጠው እንቅፋት እንዳለ ሆኖ። ዘርፉን ለማነቃቃት በመሠረተ ልማት ማለትም በመንገድ፣ በባቡርና በኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ ሲሆን፤ ለትምህርትና ለጤና የተሰጠው ከፍተኛ ትኩረትም በልኩ እውቅና ሊሰጠው ይገባል።
የኢንዱስትሪ ፓርኮችን በማስፋፋት፣ የግብር እፎይታ በመስጠትና የፋይናንስ አቅርቦት በማድረግ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንትን ለማበረታታት ጥረት እያደረገ ቢሆንም፤ በአገራችን ሲካሄድ የነበረው ጦርነት፣ እዚህም እዚያም የሚከሰቱ ግጭቶች፣ በፋብሪካዎችና ኢንዱስትሪዎች የተፈጸሙ ጥቃቶች ፣ የሰላምና የመረጋጋት ችግሮች ፣ ፖለቲካዊ አለመረጋጋት ፣ የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት እጥረትና መቆራረጥ ፣ በተለያዩ ትብታቦች ተጠፍንጎ የነበረው ቢሮክራሲ፣ የውጭ ምንዛሬ እጥረት ፣ ወዘተረፈ በቀጥተኛ ኢንቨስትመንቱ ላይ ተጽዕኖ አሳድሮ መቆየቱ አይዘነጋም ።
ለመሆኑ ቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንት Foreign direct investment (FDI) ስንል ምን ማለት ነው ? አንድ ኩባንያ ወይም የሆነ አካል ከአገሩ ውጪ በሌላ አገር በሚገኝ ኩባንያ ወይም የሆነ አካል ላይ መዋዕለ ንዋስ ሲያፈስ ወይም ኢንቨስት ሲያደርግ ቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንት ሊሰኝ ይችላል። FDI ለአንድ አገር እድገትም ሆነ ልማት የማይተካ ሚና አለው። የደም ስር ነው። ወደ አገር ካፒታልን፣ ቴክኖሎጂን ፣ የሥራ አመራር ልምድንና የገበያ ዕድል ከመፍጠሩ ባሻገር የሥራ ዕድል ይፈጥራል፣ የውጭ ንግድን ያሳድጋል፣ ውድድርንና ፈጠራን ያበረታታል። የውጭ ምንዛሬ መጠባበቂያን ያሳድጋል።
ጠቀሜታው የላቀ የመሆኑን ያህል ያልተጠበቀ እንደ የአገርን ደህንነት አደጋ ላይ የመጣል ፣ ቁልፍ የሆነን ኢንዱስትሪ ሊያሳጣ ፣ በአገር ውስጥ ንግድ ሥራና ሸማቾች ላይም ያልተጠበቀ መዘዝ ሊያመጣ ይችላል። ከፍ ብሎ ለመግለጽ እንደተሞከረው አገራችን እድገቷንና ልማቷን ለማፋጠን ቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ ጥረት እያደረገች ትገኛለች። ምቹ የኢንቨስት ድባብ ለመፍጠርም አበክራ እየሠራች ነው። ኢንዱስትሪያል ፓርክ ግንባታን፣ የታክስ እፎይታን፣ ማነቆዎችን በመፍታት የአንድ መስኮት አገልግሎትን ለማሳለጥ እየተሠራ ነው። ቻይና በአገራችን ቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንት ግንባር ቀደም ስትሆን አሜሪካ ፣ ሕንድና ቱርክ በሁለተኛ ደረጃ ይገኛሉ። የፋይናንስ አቅርቦት እጥረት ፣ የሰለጠነ የሰው ኃይል ውስንነት ፣ የተንዛዛ የክትትል ሥርዓትና ሌሎች ደግሞ ከተግዳሮቶቹ ጥቂቶች ናቸው።
በዚያ ሰሞኑን በመዲናችን ከተከናወኑ አበይት ክስተቶች «ኢንቨስት ኢትዮጵያ 2023 » ቀዳሚው ነው። ለሦስት ቀናት የቆየው ፎረም «በኢትዮጵያ ኢንቨት በማድረግ በልጽጉ – ማራኪ የኢንቨስትመንት አማራጮች ያሏት ምድር» በሚል መሪ ሃሳብ ተካሂዷል። በእነዚህ ቀናት ከ1.6 ቢሊዮን ዶላር በላይ ቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንትን መሳብ ከመቻሉ ባሻገር ሰፊ የማስተዋወቅ ሥራም ተከናውኗል። ከመላው ዓለም የተውጣጡ ከ600 በላይ የንግድ ተቋማት ኃላፊዎችና ኢንቨስተሮች እንደተሳተፉበት ፤ ፎረሙ በኢትዮጵያ ያሉትንና ያልተነኩ የኢንቨስትመንት አማራጮችን ለዓለም ለማስተዋወቅ ምቹ አጋጣሚ እንደፈጠረ ፤ በሚቀጥሉት ጥቂት ዓመታት ውስጥ ሦስት ቢሊዮን ዶላር የሚጠጋ ኢንቨስትመንት በኢትዮጵያ ፈሰስ ይደረጋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን አስታውቋል። ከግጭት ፣ ከኮሮና ወረርሽኝና ከሰሜኑ ጦርነት እያገገመች ላለች አገር ፎረሙ ጊዜውን የዋጀ ነው ማለት ይቻላል። በለውጡ መዳረሻና በለውጡ በአገሪቱ አንዳንድ ክፍሎች ይስተዋሉ የነበሩ ግጭቶች የአገሪቱን ቀጥተኛ ኢንቨስት ክፉኛ ከመጉዳታቸው ባሻገር አንዳንዶቹ ጥለው እንዲወጡም መግፍኤ ነበሩ። አበው በእንቅርት ላይ እንዲሉ ይህ አልበቃ ብሎ የኮሮና ወረርሽኝና ጦርነት ተጨምሮበት ኢንቨስትመንቱን ከድጡ ወደ ማጡ ከተተው ። እስኪ አለፍ አለፍ እያልን የFDI አፈጻጸማችንን ውጣ ውረድ እንቃኝ ።
በ2012 የበጀት አመት 3.9 ቢሊዮን ዶላር ደርሶ የነበረው ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት በአመቱ በ2013 ዓም ወደ 2.5 ቢሊዮን ዶላር ማሽቆልቆሉ በአብነት ይነሳል። እንደ መንግሥታቱ ድርጅት የንግድና የልማት ጉባኤ ወይም The United Nations Conference On Trade And Development (UNCTAD) መረጃ ከሆነ ፤ በ2017 እኤአ የኢትዮጵያ ቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንት(FDI Inward Flow ) አራት ቢሊዮን ዶላር ሲሆን አጠቃላይ በአገሪቱ ያለ የውጭ ኢንቨስትመንት ክምችት (FDI Stock) 19.097 ቢሊዮን ዶላር ነበር፡፡ በ2018 እኤአ የኢትዮጵያ ቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንት 3.310 ቢሊዮን ዶላር ፣ አጠቃላይ በአገሪቱ ያለ የውጭ ኢንቨስትመንት ክምችት 22.407 ቢሊዮን ዶላር ሲሆን በ2019 እኤአ የኢትዮጵያ ቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንት 2.516 ቢሊዮን ዶላር አጠቃላይ በአገሪቱ ያለ የውጭ ኢንቨስትመንት ክምችት 24.923 ቢሊዮን ዶላር ነበር፡፡ በ2020 እኤአ የኢትዮጵያ ቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንት 3.9 ቢሊዮን ዶላር ሲሆን አጠቃላይ በአገሪቱ ያለ የውጭ ኢንቨስትመንት ክምችት 24.923 ቢሊዮን ዶላር ሆኗል፡፡ መንግሥታዊው ኢትዮ ቴሌኮም 40 በመቶ የአገልግሎት ሽያጭ 850 ሚሊዮን ዶላር ቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንት እድገት ዋነኛ ምክንያት ነበር፡፡ ይሁንና አገሪቱ ካላት እምቅ የኢንቨስትመንት አቅም አንጻር ስንመለከተው ዝቅተኛ ነው ማለት ይቻላል። እንደ ሰሞነኛው ያሉ መድረኮች አብዝተው የሚያስፈልጉን ለዚህ ነው ።
ወደ ፎረሙ ስንመለስ የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ በመክፈቻ ሥነ ሥርዓቱ ላይ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ፈጣን የኢትዮጵያ እድገት እያስመዘገበች መሆኑን የኢኮኖሚ ፖሊሲዎቿ አሳታፊና አካታች፤ ዓለም አቀፍ ንግድን በማሳደግ ኢኮኖሚውን ለማሳደግ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ በርካታ የኢንቨስትመንት ዕድሎች አሉ ያሉት ሚኒስትሩ፣ ኢትዮጵያ ላይ ኢንቨስት ማድረግ ማለት በአፍሪካ ኢንቨስት ማድረግ ነው ። በመሠረተ ልማትም እያደገች በመሆኗ ለኢንቨስትመንት ምቹ ናት ።
በውይይቶች ኢትዮጵያ ስላሏት ሀብቶች ግንዛቤ በመፍጠር ለምትስባቸው ኢንቨስተሮች አስፈላጊውን ሁሉ ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መሆኗን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ለሊሴ ነሜ በበኩላቸው፣ ፎረሙ ለኢትዮጵያ እድገት ትልቅ አስተዋጽኦ ይኖረዋል። በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ በፍጥነት እያደጉ ካሉ አገሮች መካከል አንዷ ናት፣ ይህን ለማጠናከር የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ለመሳብ እየተሠራ ነው። መንግሥትም የኢንቨስትመንት ፖሊሲዎችን እያሻሻለ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ በግብርና ፣ በኢነርጂ ፣ በቱሪዝም፣ በአይሲቲ፣ በማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ትልቅ አቅም አላት ያሉት ኮሚሽነሯ፣ እየተሠሩ ያሉ ኢንዱስትሪ ፓርኮች በልማት ለመሰማራት ትልቅ ዕድል ይፈጥራሉ።
ኮሚሽነር ለሊሴ ነሜ በማስከተልም ኢትዮጵያ ሰፊ መሠረተ ልማት፣ ኢንዱስትሪ ፓርክ፣ ሎጅስቲክስ፣ ምቹ ፖሊሲ እና አሠራር እንዲሁም አምራች የሰው ኃይል ያላት በመሆኗ ለኢንቨስትመንት ተመራጭ እንደሚያደርጋት ፤ ዓለም አቀፍ ባለሀብቶች በግብርና፣ ማምረቻ ኢንዱስትሪ፣ ኢነርጂ፣ ማዕድን፣ ቱሪዝም እና ሌሎች ዘርፎች ባሉ ምቹ አማራጮች ሙዓለ ንዋያቸውን እንዲያፈሱ ጋብዘው ፤ መንግሥት በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች ለሚሰማሩ የውጭ ባለሀብቶች አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ቃል ገብተዋል ።
የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ በበኩላቸው ኢትዮጵያ በአፍሪካ ለኢንቨስትመንት ምቹ ከሆኑ ቀዳሚ አገራት መካከል አንዷ እንደሆነች ፤ መንግሥት የተረጋጋ ማክሮ ኢኮኖሚ እና ቀጣይነት ያለው ምጣኔ ሀብት ለመገንባት የአገር በቀል የምጣኔ ሀብት ማሻሻያ መርሀ ግብር በመተግበር ላይ መሆኑን ፤ እንዲሁም በምጣኔ ሀብት ማሻሻያ መርሀ ግብሩ የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ ቅድሚያ እንደተሰጠው ፤ ለዚህም የቴሌኮም፣ ፋይናንስና ሌሎች ዘርፎችን ለግሉ ዘርፍ ክፍት በመደረግ ላይ መሆናቸውን ፤ ስለሆነም ባለሀብቶች በኢትዮጵያ የምጣኔ ሀብት ማሻሻያ ለግሉ ዘርፍ የተሰጠውን ትኩረት በአግባቡ በመጠቀም ኢንቨስት እንዲያደርጉ ጥሪ አድርገዋል።
የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ከተለያዩ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ጋር የመግባቢያ ሰነድ የተፈራረመ ሲሆን ኩባንያዎቹ በድምሩ 1.645 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር በኢትዮጵያ ኢንቨስት ለማድረግ ተስማምተዋል። «ኢንቨስት ኢትዮጵያ 2023» የኢንቨስትመንት ፎረም የማጠቃለያ መርሐ ግብር ላይ ፤ በሲሚንቶ ዘርፍ የተሰማራው የቻይናው ሲኖማ ኩንባያ በ500 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር በሲሚንቶ ዘርፍ ላይ ለመሥራት ከኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ጋር ስምምነት የተፈራረመ ሲሆን ኮሚሽኑ ሻን ከተሰኘው የቻይና ጣውላ እና የእንጨት ውጤቶች አምራች ኩባንያ ጋር የመግባቢያ ስምምነት የተፈራረመ ሲሆን በስምምነቱም ኩባንያው 1 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር በላይ በሚያወጡ 6 ዘርፎች ላይ ኢንቨስት እንደሚያደርግ ተገልጿል።
በሌላ በኩል ከሚሽኑ ቼን ሺ ከተሰኘው የቻይና የቤት እና የቢሮ ዕቃዎች አምራች ኩባንያ ጋር ስምምነት የፈፀመ ሲሆን፣ በዚህም ኩባንያው በ8 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር የእንጨት ማቀነባበሪያ ፋብሪካ እንደሚገነባ ፤ ዩኒሊቨር እና አፍሪካ ኑትሪሽን ከተሰኘው ኩባንያ ጋር አዲስ የምግብ ማቀነባበሪያ ፋብሪካ ለማቋቋም የ45 ሚሊዮን ዶላር ስምምነት መፈራረሙ ይፋ ሆኗል ። በተመሳሳይ ሁዋጂያን የተሰኘው የቻይና ኢንዱስትሪያል ፓርክ ፕሮጀክቶቻቸውን በፓርኩ ውስጥ መሠረት ለማድረግ ፍላጎት ካላቸው 21 የኢትዮጵያ ኩባንያዎች ጋር የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርሟል።
ሻሎም ! አሜን ።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)
fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ሚያዚያ 27/2015