በማናቸውም አገራዊ ጉዳዮቻችን ላይ ስንናገርም ሆነ ስንጽፍ ደመቅ እና ጫን አድርገን ላለመግባባት የምናግተለትለው ከመፍትሔ ጥቆማ ይልቅ ጥያቄዎችን ነው። በቋንቋችን “ለምን? እንዴት? የት? መቼ? ማን?” ብለን የምንጠራቸውንና ባእዳን ደግሞ በራሳቸው ልሳን፤ Who? What? Where? When? Why? የሚሏቸውን አምስት መኮርኮሪያዎችን (5Ws እንዲሉ) ልብ ብለን ብንመረምራቸው ጥያቄዎቹ ለእኛ “ወርቃማ” የሚሰኙ የእውነት ማፈላለጊያና የጠራ መረጃ ማንጠሪያ ቁልፎች ከመሆን ይልቅ መናቆሪያና መወራወሪያ ጠጠሮቻችን ከሆኑ ሰነባብተዋል።
እነዚህ ወርቃማ የመቆስቆሻ ጥያቄዎች ጥበብ እንዲዛቅባቸው እና የነጠረ መረጃ እንዲታፈስባቸው በማሰብ በተደራጀ መልክ ሰድሮ አገልግሎት ላይ እንዲውሉ ያስተማረው ተጠቃሽ መምህር ቅድመ ልደተ ክርስቶስ በአንደኛው ክፍለ ዘመን ገደማ የኖረው ግሪካዊው ሄርማጎረስ (Hermagoras of Temnos) የተባለው ሞጋች ፈላስፋ ነበር። ይህንን የሩቅ ዘመናት መምህር ለማስታወስ የተፈለገው ልክ እንደ ዘመኑ ርቀት ሁሉ እኛ ኢትዮጵያውያን የምንባለው ዜጎች ጥያቄዎቹ ለእለት ተእለት አኗኗራችንም ይሁን በታሪካዊ ትርክታችን ጉዳይ ከሚያግባቡን ይልቅ እጅግ እያራራቁ ስለምን ሆድና ጀርባ እንዳደረጉን ስላልገባን ትምህርቱ እንዲብራራልን ሞጋቹን ሄርማጎረስን ለመሞገት ነው። “ሙታንም ይሞግታሉ!” ያለው ማን ነበር?
ለምሳሌ፤ አንድን ሰው ከብሔሩና ከማንነቱ ነጥለን ሃሳቡንና አመለካከቱን ከመሞገት ይልቅ “እከሌ እንደዚህ የሆነው ወይንም እጁ የገባውን ያንን ነገር ሊያገኝ የቻለው የየትኛው ብሔር አባል ቢሆን ነው? ያንን ሃሳብ ለመሰንዘር የተደፋፈረውስ ምን ቢያስብ ነው? ለምንስ ይሄን ጊዜ መረጠ? ከበስተ ጀርባው ያለው ማን ነው? አዋዋሉ ከነማን እና ለምን ጉዳይ ነው? ይህንንና ያንን ጥቅምና ስኬት ሊያገኝ የቻለውስ ከበስተጀርባው ማን ቢኖር ነው? የሚናገርው ቋንቋ ረድቶትስ እንደሆን? ወዘተ. የሚሉትን ጥያቄዎች በአብዛኛው ስንመራመርባቸው የምንውለው በንጹህ ኅሊና እውቀትና መረጃ ለማግኘት በማሰብ ሳይሆን በተቃራኒ ስሜት ውስጣችንን እያጠቆርን ነው።
በእንዲህ ዓይነት የጥርጥር ባህር ውስጥ ተዘፍቀንና ባህላችን አድርገን ተገዢ መሆን ለተከታዩ ወራሽ ትውልድ ምን “ቅርስ” አኑረን ለማለፍ ነው? መልሱ ለማናችንም የተሰወረ ስላይደለ ከኅሊናችን ጋር መሟገቱ ይበጃል። የአውራሽ እና የወራሽ የደም መስዋእት የቅብብሎሽ ታሪካችን በሙሉ ቢመረመር ከላይ የተጠቀሰውን እውነት ሳይንተራስ “በማንነትና በሰውነት ላይ ብቻ ተመስርቶ” ተፈጽሟል ለማለት ያዳግታል።
በዚህም ምክንያት የታሪክ ውርሳችንም ሆነ አወራረሳችን ምክንያታዊነትን ስለሚጠየፍ መንግሥታዊ ሥርዓቶችን ተቀብለን እሶሶ የምንለው፤ በስተመጨረሻም “ይሰቀሉ” እያልን የሆሳዕናንና የቀራኒዮን ታሪክ ስንደግም የኖርነው “ደም ሳይፈስ ስርዬት የለም” የሚለውን የቅዱሳት መጻሕፍት አንኳር ጭብጥ በተበከለ አስተሳሰብ በርዘን ነው። ሃሳቡን ዘርዘር አድርገን እንመልከተው።
ደም ሳናፈስ ስለምን ስርየት ተነፈግን?
አብዛኞቹ ታሪኮቻችን የተጻፉት በደም ቀለም መሆኑ ለክርክር አይቀርብም። ከደም መስዋእትነት በፊት በጥያቄዎች እየተሟገትን መፍትሔ ከመፈለግ ይልቅ በሻምላ እየተሞሻለቅን ጥሎ መውደቅን እንደምንመርጥም እንኳን ለተቀረው የዓለም ማሕበረሰብ ቀርቶ ለእኛ ለራሳችንም ለባለታሪኮቹም ቢሆን የገባን አይመስለንም። “ወርቃማ ጥቄዎቹ” ከእኛ ጋር እየኖሩ ያሉት በባይተዋርነትና በባእድነት እንጂ በጉዳዮቻችን ውስጥ መፍትሔ አመንጪ እንዳልሆኑም ከውጤታቸው ማረጋገጥ ይቻላል።
ማሳያዎቻችን የሩቆቹ ብቻ ሳይሆኑ የቅርቦቹም ታሪኮቻችን ናቸው። ወደ ኋላ ብዙ ከመንደርደር ይልቅ የትናንቶቹን ብቻ አስታውሰን ሙግታችንን ደርዝ እናሲዘው። መንግሥታዊ ሥርዓቶቻችን በሙሉ ይዘውት የሚነሱት መሪ ሃሳብ አማላይና አጓጊ ብቻ
ሳይሆኑ ኑሯችንን ወደ ገነትነት የሚለውጡ ተደርገው የሚቀረጹ ዓይነቶች ናቸው። እናስታውስ!
“ያለ ምንም ደም ኢትዮጵያ ትቅደም!”
ይህ አማላይ “መርህ” የጊዚያዊ ወራደራዊ
ጁንታ ንጉሡን ከሥልጣን መንበራቸው ላይ ገፍትሮ አገሪቱን በእጁ ባስገባበት የመጀመሪያ ወራት ጮክ ብሎ የተስተጋባ የማታለያ መፈክር ነበር። በታዳጊ የወጣትነት ዘመኔ በትንሽ በትልቁ ይፈከር የነበረውን ይህንን የደርግ ማጭበርበሪያ ባስታወስኩ ቁጥር አንድ የቤተሰቤ ወዳጅ ትዝ ይሉኛል። እኚህ ሰው በንጉሡ ዘመን የግንደበረትን ሕዝብ ወክለው ለንጉሣዊው ፓርላማ ተመርጠው ያገለገሉ የዕድሜ ባለፀጋ ነበሩ።
ይህ መፈክር አየሩን በሞላበት አንድ እለት ለእንግድነት ወደ ቤተሰቦቼ ቤት መጥተው ሲጨዋወቱ እንዲህ ነበር ያሉት። “ደርጉ ያለቦታው ደም እያለ የሚደነፋው ደም እየሸተተው ነው። ታሪኩ በደም እንደሚደመደምም በራሱ ላይ ትንቢት መናገሩ ነው።” ዋናው የሃሳባቸው ፍሬ ነገር ይህ ነበር።
እውነትም እኚያ አባት እንዳሉት ወታደራዊ መንግሥት ገና በንጉሡ ዙፋን ላይ ከመቀመጡ እጁን የታጠበው ስልሳ የሚሆኑ የንጉሣዊ ሥርዓቱን ባለሥልጣናት ጭዳ አድርጎ በግፍ ግድያ በመጨፍጨፍ ነበር። ግድያው በዚህ ብቻ ሳያቆም ኢዲዩ፣ ገንጣይና አስገንጣይ፣ “ነጭና ቀይ ሽብር” በሚል የቀለም አብዮት የደም ጅረት አገሪቱን እንዳጥለቀለቀ እጅግም ያልመሸበት ታሪካችን ምስክር ነው። እብሪትና ትምክህት ባሳበጠው ፖሊሲ ምክንያት ምን ያህል ወገን በዚያ አስከፊ ሥርዓት “ደሙ ደመ ከልብ” ሆኖ እንዳለፈ ብዙ ጉዳዮችን በመዘርዘር ማስታወስ ይቻላል።
ምክንያታዊ በሆኑ ውይይቶች ትውልዱ መተማመን ቢችል ኖሮ ያን የመሰለ አንድ ትውልድ እምሽክ አድርጎ የበላ ክስተት ባልተፈጸመ ነበር። ታሪኩ በደም ተጀምሮ በደም የተጠናቀቀውን ወታደራዊ ሥርዓት የተረከበው የሕወሓት/ኢህአዴግ ታሪክም ከዚህ ቢከፋ እንጂ የተለየ አልነበረም። በጥቂቱ እንዘክረው።
“ሰላምና መረጋጋት”
ከጫካ ተንደርድሮ በመምጣት የደርግ ሥርዓትን ለግባ መሬት የዳረገው ወራሹ ቡድንም በመጀመሪያው የሥልጣን ወራቱ ሕዝቡን ለመሸንገል የሞከረው “የሰላምና መረጋጋት ኮሚቴ” በሚል ሽፋን የበቀል ሤራ በመዘርጋት ነበር። በተለይም የቀዳሚውን ሥርዓት የፖለቲካ መዋቅር (ኢሠፓ – የኢትዮጵያ ሠራተኞች ፓርቲ) ለማፈራረስና አባላቱን ለማሽመድመድ፣ የጦር ኃይሉንና የሠራዊቱን ጀግኖች ለመበተንና ለማዋረድ የቻለው በየቀበሌውና በየመዋቅሩ “የቀይና የነጭ ሽብርን ምክንያት አሳቦ” የሰላምና መረጋጋት ኮሚቴ የሚል ኃይል በማቋቋም ነበር።
በሰላምና በመረጋጋት ስም የተሰየሙት ኮሚቴዎች እንኳንስ ግብራቸው እንደ ስማቸው ሊሆን ቀርቶ ጭርሱኑ ሳይውሉና ሳያድሩ የጭካኔ መገለጫ ሆነው የደምና የእምባ ምንጭ በመሆን ዜጎች ተሰቃይተውባቸዋል።
“ማጋለጥ” በሚል የበቀል እርምጃም ብዙዎች ተገድለዋል፣ ሺህዎች ታፍነው የደረሱበት አይታወቅም፣ ለቁጥር የሚያታክቱትም በእስራትና በእንግልት ተሰቃይተው ሊያልፉ ግድ ሆኗል። በተከታታይ ዓመታትም የግፍ ድርጊቶች በታጨቁባቸው እርምጃዎች ምክንያት ምን ያህል ወገን ለመከራና ለስቃይ እንደተዳረገና አገሪቱ እንደምን ወደ አዘቅት እንዳሽቆለቆለች የሚታወቅ ነው። የአውራሽና ወራሽ ሥርዓተ መንግሥታቱ “የጥቁር ደም” ታሪክ ገና በአግባቡ ተሰንዶ ስላልተጠናቀቀ ወደፊት ብዙ አሰቃቂ ታሪኮችን መስማታችን አይቀርም።
“ሰይፍ፡- ሰላም፣ ፍቅር ይቅርታ፤
ኢህአዴግ እንደ ቀዳሚዎቹ ሥርዓቶች የሞቱን ጽዋ ተጎንጭቶ የግባ መሬቱ የቀብር ሥርዓት ገና ተፈጽሞ ሳይጠናቀቅ በፊት አዲሱንና ከራሱ አብራክ የወጣውን “ለውጥ” ለማደናቀፍ የተሞከረው በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ላይ በሰኔ ወር 2010 ዓ.ም በመስቀል አደባባይ ላይ የግድያ ሙከራ በማድረግ
ነበር። ለረዢም ዘመን ሲናፍቁንና ሲያስጎመጁን የኖሩት “ፍቅር፣ ይቅርታ፣ ሰላም፣ መከባበር፣ ወዘተ.” የሚሉት ሃሳቦች ገና በጽንስ ላይ እያሉ ስንት አገራዊ መከራ እንደወረደብን እናስታውሳለን። የግፍ ግድያዎቹ ዓይነትና ብዛት፣ መፈናቀሉ፣ አልፎም ተርፎ ከሕወሓት ጋር በተደረገው ጦርነት ምን ያህሉ ወገን እንደረገፈ በቁጥር ሳይሆን የሚገመተው በጅምላ ነው። “ሆድ ይፍጀው!”
ወደ ቀልባችን ተመልሰን ራሳችንን እንጠይቅ፤
በመነጋገር፣ በመመካከር፣ በመደማመጥና ልቦናችንን ከፍተን ለመወያየት አዚም አድርጎ የተበተበን ባህል ወይንም እሥራት ምክንያቱ ምን ይሆን? እስከ መቼስ ሥርዓቶች በተፈራረቁ ቁጥር ጥቋቁር ታሪኮቻችንን ለመመዝገብ በጥቁር መዛግብቶቻችን ላይ ጥቁር አሻረ ለማሳረፍ እንሽቀዳደማለን? እስከ መቼስ እንደዚህ እንቀጥላለን።
በሥራ አጋጣሚ ከተገናኘነው አንድ የውጭ ዜጋ ጋር የተመላለስነውን አንድ ወግ ባስታውስ ለሃሳቤ ድጋፍ ይሆን ይመስለኛል። ሰውዬው የሕዝብ ቁጥሩ ይህ ልኩ የማይባል ትልቅ አገር ዜጋ ነው። ለሥራ ጉዳይ በተገናኘንበት አንድ ወቅት በአገሩ ሁለት ባቡሮች ተላትመው በመቶዎች የሚቆጠሩ ዜጎች አልቀው የነበረበት ሣምንት ስለነበር፤ በአገሬ ወግና ሥርዓት መሠረት “በአገራችሁ በተፈጠረው የባቡር አደጋ ምክንያት ስላለቁ ዜጎቻችሁ መጽናናትን እመኝላችኋለሁ። የሀዘናችሁ ክብደትም ይሰማኛል…” ብዬ ገና ንግግሬን ሳልጨርስ፤ “ለምን ማዘን አስፈለገህ?” በማለት አፋጠጠኝ ደግሞም አሳፈረኝም።
“የሀዘኔ ምክንያቱ ስላለቁት ዜጎቻችሁ ነው” ብዬ ስመልስለትም፤ “ልታዝን አይገባም። አገሬ ባላት የሕዝብ ቁጥር በዓለም ፊት ቀዳሚ ከሚሰኙት ጥቂቶች መካከል አንዷ ነች። ስለዚህ የሚሞተው ሊሞት ግድ ነው፤ ብዙም አያስገርምም። እንዲያውም የሕዝብ ቁጥሩ ለብዙ ችግር እየዳረገን ስለሆነ እንዲህ አይነቱ አደጋ መከሰቱ ጠቃሚ ጎንም ሳይኖረው አይቀርም ” በአገሬ ብሂል መሠረት ሰውዬው የመለሰልኝ መልስ “ከአንድ ሣር ቤት ላይ አንድ ሰበዝ ቢመዘዝ አያስገርመም” የሚል ብጤ መሆኑን ልብ ይሏል።
በዚህ ወግ መነሻነት ራሳችንን መፈተሹ መልካም ይሆናል። በተለያየ መልኩ የምንሰማቸው የዜጎች ሞት ስለምን ልበ ደንዳና አደረገን? “ምን ይሉት የሞራልና የመንፈስ ስብራት ቢገጥመን ነው ልባችንና መንፈሳችን የደደረው? የድንዛዜያችን ምንጩና ሰበቡ ምናልባትም “ደም ሳይፈስ ስርዬት የለም” የሚለው የተለመደ አገላለጽ ብሔራዊ መርሆዋችን ሆኖ ይሆንን?
የንጹሐንን ሞትና እልቂት ስንሰማና የአሟሟታቸው ሁኔታ ተብራርቶ ሲገለጽልን በተሰበረ ልብ ከመስማት ይልቅ እንደ አዘቦት ቀን ወግ “ነው እንዴ?” ብለን እንደ ዋዛ እንድናልፍ የሆነበት ምክንያቱ ምን ይሆን? “ዘጠኝ ሞት መጣ ቢሉት፤ አንዱን ግባ በለው” እንዳለው ነውጠኛ አውራሾቻችን ያወረሱን የቂምና በቀል ፍሬ ይሆንን?
“የደም ኪዳን” ውርሳችን ተቀዶ በንግግር፣ በውይይትና በምክንያታዊነት እየተደማመጥን መግባባት እስካልቻልን ድረስ ቀጣዩ ወራሽ ትውልድም የራሱን ዘመን በደም እያቀላ ከመኖር የሚከለክለው ተጨባጭ ምክንያት ያለ አይመስለኝም። ከትናንት ትውልዶች የውርስ ዱላውን የተቀበልነው የዛሬዎቹ ዜጎች ለነገው ወራሽ ትውልድ ማቀበል የሚገባን “ዱላውን ደም አስነክተን ሳይሆን” እንደ ጥምቀት በዓል ዘንግ በውብ ቀለማት ሸልመን ሊሆን ይገባል። እነዚያ ቀለማት “ወርቃማ ያልናቸው ጥያቄዎች” ሲሆኑ ልብ ተቀልብ ሆነን ተነጋግረን የቀዳሚውን ዘመንም ሆነ የራሳችንን ዘመን ችግሮች ለማስወገድ እጅ ለእጅ፣ ልብ ለልብ ተጨባብጠን ወደ መደማመጥ ልንመለስ ይገባል። ሰላም ለአገሬ፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ።
(ጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 26/2015