የርዕሰ ጉዳያችን ማዋዣ፤
ለእኛ ለኢትዮጵያዊያን በማንም አንደበት ሊነገሩን ከማይገባቸው ጉዳዮች መካከል አንዱ የሰላም ጉዳይ ነው። እንዴታውን በአግባቡ ማብራራት ይቻላል። ስለ ሰላም ሲነሳ የጦርነትና የግጭት ስም ከኋላ መከተሉ አይቀርም። ስለዚህም የሰላም እጦትም ይሁን ፣ የጦርነት ጦስ ወይንም የግጭት ዳፋ ሁሉም መርገምት አብረውን የኖሩት የቤትኛ ያህል ተላምደውን ነው። ጫን እንበል ካልንም ስለ ሰላም እጦት ከሊቅ እስከ ደቂቅ መናገር የምንችለው ብያኔውን በቃላት እየኳልን “ሰላም ማለት…” ብለን ደረቅ ትርጉም በመስጠት ሳይሆን በሚገባ እየተቀጣንበትና እየተራብነው ስለኖርንና ስላኗኗርነው ጭምር ነው።
የጦርነት “በላ” ከምድራችን ላይ በፍጹም ሊጠፋ ስላልቻለ ሰላማችን ህመምተኛ በመሆን አልጋ ከያዘ ከግማሽ ክፍለ ዘመን በላይ ዕድሜ አስቆጥሯል። በዚህም ምክንያት ከሀዘን ጨርቃችን ሥር ህመሙንና ስቃዩን ከውስጥ ደብቀን በየዘመናቱ ታቅፈን የኖርነው መልከ ጥፉ ገጽታውን ነው። ዛሬም ቢሆን “ፀረ ሰላም የሚራባበትን ክፉ የጠብ ቫይረስ” ከላያችን ላይ አሽቀንጥረን መጣል ተስኖን እንደጎበጥን አለን። የውጭ ባላንጣዎቻችን ብቻም ሳይሆኑ “የራሳችን” የምንላቸው የባሩድ ጭስ ሱሰኞች ሳይቀሩ ሰላማችን አገግሞ ከደዌው እንዳይፈወስ በነጋ በጠባ ግርሻ ሆነውበት ፈተናውን እንዳበዙበትም ይታወቃል።
“ስለ ሰላም እሴት እኛ ብቻ እየተደመጠን ካላስረዳናችሁ” የሚሉን አንዳንድ ሳይሞቅ ፈላ የቤት ውላጅ የማሕበራዊ ሚዲያ “ገድለኞች” ጠብ እየጠመቁ “የጥፋት ጉሹን” ጨልጠን እንድንጎነጭ “ዶሮ ማታ በሚል ማደናገሪያ” ደክመው ባያደክሙን እንደምን መልካም በሆነ ነበር። የሩቅ ሀገራት “ወዳጅ” ተብዬ ባእዳንም ቢሆኑ “ቲዎሪ በመደርደር” ካልሰበክናችሁ እያሉ ባያሰለቹን አንጠላም።
ከቻሉ ሰላማችን ምልዑ እንዲሆንና ከደዌው እንዲፈወስ ይደግፉን፤ ካልሆነም በእኛው ሕዝባዊ ብልሃት እየተነጋገርን ችግራችንን በራሳችን ነባር ወግና ዘዴ ስለምንፈታ አደብ ገዝተው ይረፉልን። ይህ ምልጃ-አከል አስተያየት የእከሌ ቡድን ወይንም የዚያኛው ሃሳብ ተብሎ ጸሐፊውን የሚያስፈርጅ ሳይሆን በየቤቱ የሚደመጥ ሰላም የናፈቀው የመላው ሕዝባችን የጋራ ተማጽኖ መሆኑ ልብ ሊባል ይገባል።
የሰላም መደፍረስ ጉዳይ ሲነሳ የዜጎች መፈናቀልና መሰደድም አብሮ መታወሱ አይቀርም። በመሆኑም ስደትና ፍልሰትም ቢሆኑ ለእኛ ብርቅም ድንቅም አይደሉም። እንዲያውም የዕለት ተዕለት ዜና መዋዕላችን ዋና ርእሰ ጉዳዮች ስለሆኑ ጆሯችን ለምዷቸዋል። የመፈናቀልም ሆነ የፍልሰት እውቀታችን የዳበረው መዛግብተ ቃላትን እየተጠቀምን ትርጉማቸውን በመፈለግ ሳይሆን በዓለም አቀፍ የተራድኦ ድርጅቶች ገጽታ ላይ ከምናነበው የመሰላቸት ስሜት ስለምንረዳ ትርጉሙ በሚገባ ይገባናል።
የርሃብና የድርቅ አስከፊነትን የምናውቀውም ወዲያ ማዶ ከሚላክልን “የምርምር ግኝት”፣ በባዕዳን ዳረጎት እና ሪፖርቶች ሳይሆን ለዘመናት እንኮኮ ብለንና አዝለነው ስለኖርን የታሪካችን ገጾች ቢፈተሹና ቢመረመሩ ለምስክርነት የሚሰንፉ አይሆንም።
“ርሃብ ስንት ቀን ይፈጃል? ወይንስ ቀን ቆጥሮ ይፈጃል። ”
የሚሉ ዓይነት ቅኔዎችን በየአሥር እና አሥራ አምስት ዓመታት የጊዜ ዑደት ውስጥ እየዘመርን ስለኖርንና ጠንክረን ስላልተፋለምነው እንጉርጉሯችን ወደፊትም ላይቋረጥ ይችል ይሆናል። ከልሂቃን የጥናት ውጤቶች ክብደት ይልቅ ከላይ እንደጠቀስነው “ዋይ ዋይ” የሚያሰኘን የእኛ “የርሃብ ጉንፋን” ይበልጥ ጮክ ብሎ የሚደመጥ ይመስለናል።
ስለዚህም የሰላምን ርሃብና ጥማት በሚገባ እናውቀዋለን ስንል ከአኗኗራችን ጋር እጅጉን ከሮና ጠብቆ መሸረቡን ለማመላከት ነው። የመፈናቀልም መከራ ቢሆን ሲንጠንና ሲያስለቅሰን ስለኖረ እህህታችንን በእንባችን እያራስን ማጣጣሙን ተላምደነዋል። ርሃብና ድርቅም ቢሆኑ በእኛ በሰብዓዊያን ዜጎች አንደበት ብቻ ሳይሆን የመከራችን ተጋሪ በሆኑ በእንስሳቶቻችን አራራይ “የእምቧ” ድምጽም ሳይቀር ብዙ ስለተነገረ “የባህላችን አንዱ ክፍል” እስኪመስል ድረስ አብረነው እየኖርን ነው።
ይህ ሀገራዊ እውነታችን ግድ ስለሚለን ነው፡- ስለ ሰላም እጦት፣ ስለ ስደትና መፈናቀል፣ ስለ ርሃብና ድርቅ የሩቅ ሩቆች ባዕዳንም ሆኑ ተቆርቋሪዎች ነን ባዮች በሙሉ እንዲያብራሩልንና እንዲነግሩን የማንፈልገው። ከቻሉ ይደግፉን። ከበረቱ ያግዙን። ተማጽኗችንን የሚያከብሩልን ከሆነም የትኞቹም ቡድኖች ሆኑ ግለሰቦች ከሚከተሉት የፀረ ሰላም ድርጊቶችና እንቅስቃሴዎች ቢታቀቡልን ደስታችን ምሉዕ ይሆናል፤ ለቀጣዩ ትውልድም “ጠብ መዝሪያ ሳይሆን ደም ማድረቂያ” መሠረት ጥለን ለማለፍ እንበረታታለን።
የሰላማችን ሾተላዮች፤
ኢትዮጵያና ሕዝቦቿ በሰላም ውለው እንዳያድሩ ሲካድሙና ሲያድሙ የሚያድሩ ብዙዎች ናቸው። አንዳንድ “የቤት ልጆች” በሀገር ውስጥ ሆነው የተሰወረ የመታኮሻ ምሽግ በመገንባትና ማንነታቸውን በመሸሸግ ሰላም ርቆን በነውጥ እየተላጋን እንድንኖር በትጋት ሲያሴሩ ውለው ማደራቸውን በነጋ በጠባ እያስተዋልን ነው። ለጊዜው የትርፋቸውን ስሌት መተመኑ ስለሚያዳግትና ግራ ስለሚያጋባ “ጭር ሲል” ያለመውደዳቸውን ብቻ ጠቅሰን ማለፉ ይመረጣል።
አንዳንዶች ባሕር ማዶ ተዘልለው በመቀመጥ አጀንዳ እየፈጠሩ “የሰላም ርግባችን” በሰማያችን ላይ በነፃነት እንዳትከንፍ ቢቻል በሴራ ወንጭፍ ሊገድሏት ካልሆነላቸውም አቁስለው ሊያደሟት ከሚተጉበት ተግባራቸው አደብ ገዝተው “የፀረ ሰላም ቀስታቸውን” እንዳያስፈነጥሩብን እንማጸናቸዋለን።
እነርሱ እያንኮራፉ በሰላም ተኝተው ሲነቁ እኛ ግን እንደ አሜባ እየተበላላን እንድንተላለቅ አቅደው መሥራታቸው በእኛ በዜጎችና በፈጣሪ ዘንድ በሚገባ የታወቀ መሆኑን ዘንግተውት ከሆነ ወደ ቀልባቸው እንዲመለሱ እንመክራቸዋለን። እነርሱ ተረጋግተው “ዓለማቸውን ሲቀጩ” እኛ እንድንበተን፣ እነርሱ ፀንተው ሲቆሙ እኛ እንድንነቀል በማቀድ ከሆነ፤ እቅዳቸውና የሚያመነዥኩት እኩይ ምኞታቸው ከመከራው ተጋሪነት ነፃ እንደማያወጣቸው በግልጽ ቋንቋ እናስታውሳቸዋለን። እነዚህን መሰል አያሌዎች መልካቸውና ግብራቸው ዝንጉርጉር ስለሆነ እነ እከሌ ብለን ማንነታቸውን ዘርዝረን ለማቅረብ በእጅጉ ያዳግታል።
በተለይም ዘመን በወለደው የማሕበራዊ ሚዲያ ጫካ ውስጥ መሽገው “ግደል ተጋድል!” እየተባባልን እንድንናከስ በመርዝ የተለወሰ መልእክት የሚልኩልን “የእኛው ልጆች” ወደ ኅሊናቸው ተመልሰው ቢረጋጉ ለእነርሱም ሆነ ለእኛ በእጅጉ የሚጠቅም ይመስለናል። ለእለት እንጀራ የሚሰበሰብ ሶልዲ እያሳሳቸው ጠብ መዝራት ለእኛ ለመከረኞቹ ዜጎች ብቻ ሳይሆን ለእነርሱ ለራሳቸውም የሚረባቸው አይደለም።
“የሀገራችን የሰላም ርግብ እንደቆሰለች ትኑር” ብሎ ከመወሰን አስቀድሞ “የእኔ የሆኑትስ የሰላም እጦቱ ከሚያስከትለው ችግር ሊተርፉ ይችላሉ?” ብሎ ማሰብ ብልህነት ነው። እናት አባታቸውን፣ አክስት አጎታቸውን፣ ወንድም እህቶቻቸውን ሀገር ቤት አስቀምጠው የሰላም እጦቱ ጭስ ባሕር ማዶ ተሻግሮ ከእነርሱ ዘንድ እንደማይደርስ ማሰብ ትርፉ “ድንጋይ ወደ ሰማይ ቢወረወሩ ተመልሶ በራስ አናት” እንዲሉ ውጤቱ የጋራ እንደሚሆን ቢገነዘቡት መልካም ይሆናል።
ከይሁዳ ምድር ተማርከው ከሄዱት ከመርዶኪዮስና ከንግሥት አስቴር ሕይወት ብዙ ትምህርት እንድንቀስም ቅዱስ መጽሐፍ በዝርዝር የዘገበልንን አንድ ታሪክ እናስታውስ። በምርኮ ምድር ያሉ አይሁዳዊያን በሙሉ ከምድረ ገጽ እንዲጠፉ ሐማ በተባለ የንጉሡ የቅርብ ባለሟል አማካይነት በተቀነባበረ ሴራ የሞት አዋጅ በታወጀበት አንድ አጋጣሚ ከምርኮኞቹ አንዷ የነበረችው ንግሥት አስቴር ለንጉሡ ሚስት እንድትሆን ታጭታ የወግ ወራቷ እስኪመፈጸም ድረስ በዝግጅት ላይ ነበረች። ይህንን የሞት አዋጅ ቀድሞ የሰማው አጎቷ መርዶኪዮስ የጥፋታቸውን መርዶ እጅግ ልብ በሚነካ ቃል ሲልክባት ቸል በማለቷ ዳግመኛ የላከላት የመጨረሻ ቃል እንዲህ የሚል ነበር።
“አንቺ በንጉሥ ቤት ስለ ሆንሁ ከአይሁድ ሁሉ ይልቅ እድናለሁ ብለሽ በልብሽ አታስቢ። በዚህ ጊዜ ቸል ብትይ እረፍትና መዳን ለአይሁድ ከሌላ ሥፍራ ይሆንላቸዋል። አንቺና የአባትሽ ቤት ግን ትጠፋላችሁ። ደግሞስ ወደ መንግሥት የመጣሽው እንደዚህ ላለው ጊዜ እንደ ሆነ ማን ያውቃል” (መጽሐፈ አስቴር 4፡13)።
ሰላም ርቆን እንድንጠፋፋ ለሚፈልጉት ሁሉ የምናስታውሳቸው ኃይለ ቃል ከላይ ከተጠቀሰው የቅዱስ መጽሐፍ ታሪክ የተመዘዘውን መሪ ሃሳብ ነው፡- እረፍትና መዳን ለኢትዮጵያና ለሕዝቧ ከየትም ይሁን ከየት መምጣቱ አይቀርም። እነርሱ በውጭ ሀገራት ስለሚኖሩ ወላፈኑ አይደርስብንም ብለው አስበው ከሆነ ተሳስተዋል። ስለ ሀገራቸውና ሕዝባቸው መዘመሩን ቢጠየፉ እንኳ ቤተዘመዶቻቸው እየኖሩ ያሉት በዚህቺው “ሰላም እርቋታል” በሚሏት ሀገር ስለሆነ ከችግሩ ሸሽተው ማምለጥ ስለማይችሉ የሕዝቡን የመከራ መርዶ የሚያስተናግዱት ወደው ሳይሆን “ሙሾ እያወረዱ” እንደሚሆን ሊዘነጉት አይገባም።
ይህ ዘመነ ቴክኖሎጂ በውጤቱ ሲመዘን “በበረከተ መርግም” ፍሬዎች የተሞላ ስለመሆኑ በቀዳሚው ጽሑፋችን ደጋግመን ለማሳየት ሞክረናል። ያለ ቴክኖሎጂ ድጋፍ ለመኖርም ሆነ ላለመኖር የማይቻልበት ወቅት ላይ የተደረሰ ይመስላል። ቴክኖሎጂ በአግባቡ ለሰላም ግንባታ ቢውል ትርፉ የትዬለሌ ሊሆን ይችላል።
በአንፃሩም ማሕበራዊ ሚዲያውን ለክፋትና ለመጠፋፋት እንጠቀምበት ከተባለም መንገዱ የውሃ፣ የጥፋት ውጤቱም በአፍታ እንደሚገለጽ ይታወቃል። ስለዚህም ለሰላም ለመዘመር አዳግቷቸው ሴራ ሲያደሩ ውለው የሚያድሩ ከሆነ “የእኔ የሚሉት ቤታቸውና ቤተሰባቸው” እነርሱ ከጫሩት የእሳት ወላፈን እንደማንም ዜጋ ለመትረፍ ዋስትና ስለሌላቸው መከራውን ሲጋፈጡ ሙሾ ለመደርደር መገደዳቸው እንደማይቀር ደግመን ደጋግመን እናስታውሳቸዋለን።
ኢትዮጵያ ሆይ መልእክት አለን፤
እንደ አንድ የዘርፉ ባለሙያ ዜጋ የሀገርህ መንግሥታዊ ድክመት በዋነኛነት ምንድን ነው? ተብዬ ብጠየቅ ተሽቀዳድሜ አጽንኦት በመስጠት የምመለሰው፤ “ሀገሬ በሕዝብ ግንኙነት ሥራና በኮሚዩኑኬሽን ተግባሯ ሰንፋለች፣ ደክማለች፣ ተበልጣለች” የሚል ይሆናል። በሚኒስቴር ተቋም ደረጃ የኮሚዩኒኬሽንን ሙያ ያገዘፈች ሀገሬ ስለምን ለዜጎቿና ለዓለም ማሕበረሰብ መረጃዎችን ቀድማና አብራርታ ለመናገር ሁሌም ዐይናፋር እንደምትሆን ሊገባኝ አልቻለም። ብዙውን ጊዜ መነገር ለሚገባቸው ሀገራዊ ጉዳዮች መነገር እንደማይገባቸው ስለሚታመን በመዘግየት የደረሱ ሀገራዊ ጉዳቶች ብዛታቸውና ዓይነታቸው ይህ ልኩ ተብሎ ተጠቃሎ የሚቀርብ አይደለም።
በሥነ ግጥም ስራዎቹና በሃይማኖታዊ መሪነቱ ዝናው ከፍ ያለው ጆርጅ ኸርበርት (1593 – 1633) “እውነት የሆነ ሁሉ አይነገርም – All truths are not to be told” በማለት የተናገረው ተጠቃሽ ብሂሉ በእኛ ዘንድ የተተረጎመው “ሁሉም እውነት እንዳይነገር – All truths are untold” የሚል እስኪመስል ድረስ ሀገሬ እጅጉን ለመረጃ ስለምን አዝጋሚ እንደሆነች አይገባኝም።
ይህንን እውነት በድፍረት ባልገልጽ የሙያ ሥነ ምግባሬ የሚወቅሰኝ ስለሚመስለኝ ድምጸቴ ጠጠር እንዲል ያደረግሁት ሆን ብዬ ነው። በግልጽ ለሕዝብ በይፋ ሊገለጹ የሚገባቸው ሀገራዊ ጉዳዮቻችን ቀድመው ባለመገለጻቸው ምን ያህል ጊዜ ለሰላማችን መደፍረስ ምክንያት የሆኑ ክስተቶች አፈትልከው እንደወጡ እናስታውሳለን። ሀገሬ በዚህ ጉዳይ ላይ ጆሮ ሰጥታ ችግሯን ብታርም ደስታውን አንችለውም።
“ሰላምን አጥብቀህ የምትሻ ከሆነ ከወዳጆችህ ይልቅ ጠላቶችህን ተሽቀዳድመህ ማናገር መጀመር አለብህ” የሚለው ዝነኛ ብሂል የአንድምታ ትርጉሙ ብዙ ነው። የደቡብ አፍሪካዊው የኖቤል ተሸላሚ ካህን ዴዝሞን ቱቱ “ሰላም የሚጀምረው ከፈገግታ ነው” ያሉት አባባልም ቢታከልበት አይከፋም።
መረጃ ሰጭ ተቋማቶቻችን እውነታቸውን በምሬትና በንፍገት ሳይሆን ፊታቸውንና ልባቸውን ፈካ አድረገውና ተሽቀዳድመው ቢያደርሱን ኖሮ ለሰላማችን አዋኪዎች እስከዛሬም በር ባልተከፈተ ነበር።
ማጠቃለያችን፡- ከቻልን ሰላምን እንግዛት እንጂ ለክፉዎች አሳልፈን አንሽጣት። ሰላም ከራስ፣ ሰላም ከቅርብ ወንድም/እህት ጋር ፣ ሰላም ከፈጣሪ ጋር፣ ሰላም ከተፈጥሮ ጋር፣ ሰላም! ሰላም! ሰላም!
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ) gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 22ቀን 2015 ዓ.ም