የታሪክ ተመራማሪና የፍልስፍ አዋቂውፕሮፌሰር ዩቫል ኖህ ሐረሪ አለማችን ካፈራቻቸውና ድንቅ ስራዎችን ካበረከቱ ምሁራን መካከል በበርካቶች ዘንድ በግንባር ቀደምትነት ስማቸው ይጠቀሳል። እስራኤላዊው ፕሮፌሰር በተለይም Sapiens /ሳፒየንስ/ እና 21 Lessons for the 21st Century በሚል ባሳተሟቸው መፅሐፍ ይበልጡን ይታወቃሉ። ፕሮፌሰሩ ሁለተኛ ላይ በተጠቀሰው ስራቸው በ21ኛው ክፍለ ዘመን የሰው ልጅ ሊማርባቸው ይገባል ብለው ከዘረዘሯቸው 21 ነገሮች ውስጥ ጦርነት አብላጫውን ቦታ ይወስዳል።
ፕሮፌሰሩ እኤአ በ2018 ባሳተሙት በዚህ መፅሃፉ የጦርነትን አስከፊነት በጥልቀት ከመተንተን ባሻገር የሰው ልጅ በታሪኩ ካሳለፋቸው ጦርነቶች ሊማር ግድ ስለመሆኑና በጦርነት ኪሳራ እንጂ ትርፍ እንደሌለ መለስ ብሎ መቃኘት እንደሚገባ አፅእኖት ይሰጡታል።
እንደ እርሳቸው ሁሉ የጦርነትን አስከፊነት በሚመለከት በርካቶች ፅፈዋል። ስለ ሰላም ብዙዎች ዘምረዋል። አዚመዋል። አያሌዎች ህይወታቸውን ሰውተዋል። በሁሉም ባህሎችና እምነቶች እንዲሁም ሕዝቦች ዘንድ ሰላም ከፍተኛ ዋጋ አለው። ሰላምን የማያስተምር እምነት የለም። በየቤተ እምነቱ በሚደረጉ ፀሎቶችም ሰላም ከቀዳሚ ርዕሶች አንዱ ነው። ህዝብም እንደ የእምነቱ ፈጣሪን እለት እለት በሰላም ያሳደርከኝ በሰላም አውለኝ ከማለት አልፎ፤ ስለ አገሩ ሰላም ይፀልያል። ይማፀናል።
ስለ ሰላም ሲነሳ የቀድሞው ዩናይትድ እስቴትስ ተወዳጅ ፕሬዚዳንት ሮናልድ ሬገን አባባል ሁሌም ይታወሳል። አባባሉም ‹‹ሠላም ማለት ግጭቶችን በሠላማዊ መንገድ መፍታት መቻል ማለት ነው›› የሚል ነው። እርግጥም ሠላምን በጉልበት ማስጠበቅ አይቻልም። ሠላምን ማሳካት የሚቻለው በመግባባት ብቻ ነው።
ልዩነትን ማቀራረብ ወይም ቅራኔን ማርገብ የሚቻለው በክብ ጠረጴዛ ዙሪያ እንጂ፣ ‹‹የምፈልገውን አስፈጽማለሁ››በሚል ጀብደኝነት አይደለም።በተለይ በፖለቲካው አለም ፉክክርና የትግል ተሳትፎ ሁለናተናዊ ሰላም እውን ይሆን ዘንድ ከአገርና ከሕዝብ በፊት ሥልጣንን ማስቀደም፣ከራስ ክብርና ዝና በላይ ለሌላው አለመጨነቅና ዕብሪት አሸቀንጥሮ ማስወገድ የግድ ይላል።
ሰላም የሚረጋገጠውም በሠለጠነ አስተሳሰብ እንጂ ዘመን ባለፈበት አስተሳሰብና በጠመንጃ አምላኪነት አይደለም። ለአገር የሚበጅ ሥርዓት ዕውን ሊሆን የሚችለው በሕዝብ ይሁንታ እንጂ በጀብደኝነት አይደለም።ሆኖም አያውቅም። በኋላ ቀር አስተሳሰብ ተቸክሎ ጠመንጃ መወልወልም ሆነ ውረድ እንውረድ ተባብሎ ጦር መስበቅ፣ በየትኛውም መመዘኛ በጣም የሚያስንቅ አስነዋሪ ድርጊት ነው።
ሰላምን በጉልበት የማምጣት ሙከራዎችም በአብዛኛው ትርፋቸው መከራ ነው። በጉልበትና በጠመንጃ የሚጠበቅ ሰላም ቀኝ ጠብቆ ፍርክርኩ መውጣቱ አይቀሬ ነው። አንዳንድ ፀሐፍት እንዳውም በጉልበት የተገኘ ድል ከሽንፈት እኩል ያነፃፅሩታል።ምክንያታችን የሚሉት ደግሞ ጊዜያዊ መፍትሄ መሆኑን ነው።
በኢትዮጵያ ታሪክ በቀደሙት አመታት አንድ ችግር ሲያጋጥና ሰላም ሲደፈርስ ተነጋግሮ መፍትሔ ለማፍለቅ ከመትጋት ይልቅ ዱላ መምዘዝ የተለመደ ነው።በዚህም ምክንያት ግጭትን ወይም ጦርነት ሙጥኝ በማለት ዓላማን ለማስፈጸም ጥድፊያው ሲበረታም ይታያል።
ኢትዮጵያ ባለፉት ሁለት አመታት ጦርነት ባስከተለው ሁለንተናዊ ቀውስ ከባድ መንገራገጮችን ወይንም shocks ውስጥ ቆይታለች። በጦርነቱ ምክንያት በሺዎች የሚቆጠሩ ሞተዋል። በርካቶች ከአካላዊና ከሥነ ልቦናዊ ጉዳት በተጨማሪ ከሞቀ ጎጃቸው ተፈናቅለዋል። ግምቱ እጅግ በጣም ከፍተኛ የሆነ የህዝብ እና የአገር ሀብት ወድሟል።
የሰሜን ጦርነት ከተጀመረ ጊዜ አንስቶ ባለፉት ሁለት ዓመታት ጦርነቱ ኢኮኖሚውን እያደቀቀ የዜጎችን ኑሮ ከማክፋቱና የሚሊዮኖችን ደኅንነት ከማቃወሱም በላይ ኢትዮጵያ ብዙ ሴራ ተሸርቦባታል። በርካታ መሰናክሎች አልፋለች።ተወንጅላለች።በተለያዩ ዓለም አቀፍ ተቋማትና ሚዲያዎች ሆን ተብሎ ገጽታዋ እንዲጠቁር ተደርጓል። ተስፋ ቢስ እንደሆነች ተደርጋም ተስላለች።
እንደሚታወቀው፣ ጦርነቱ ብዙ ብዙ መልኮችን፣ወዳጅ ጠላትን አሳይቶናል። የኢትዮጵያ ጭንቀት የሚጨንቃቸው ህመሟ የሚያማቸው አገራትና ተቋማትንም አስቃኝቶናል።ከዚህ በተቃራኖ የዓለም የሰብዓዊ ሞራል አስጠባቂነትን ካባ ለራሳቸው የደረቡ አገራት፣ጥቅማቸውን ለማስከበር እስከምን ሊሄዱ እንደሚችሉና ትክክለኛ ተፈጥሯቸውን በተጨባጭ አስመልክቶናል።
የኢትዮጵያ መንግስትና ህዝብም ለመሰል የውጭ ተፅእኖዎች ሳይንበረከክ፣ የሰላም ንግግር ሐሳብን በዋናነት ሲደግፉና እንዲጀመርም ከፍተኛ ግፊት ሲያደርጉ ቆይቷል።ከብዙ ጥረት በሰላም በአፍሪካ ኅብረት ጥላ ሥር በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ከተማ በፌዴራል መንግሥትና በሕወሓት መካከል የሰላም ንግግር እውን ሆኗል።የኢትዮጵያን ጥቅምና ክብር ባስጠበቀ መልኩ ሰላምን እውን ለማድረግ ከስምምነት ተደርሷል።
ይህም የሰላም መንገድ ለኢትዮጵያ ትልቅ ድል ነው:: በሰላም እንጂ በጦርነት ያተረፈ ሀገር አለመኖሩን በመረዳት ግጭትና ጦርነት ይብቃን መባሉ እጅግ የሚደገፍና የሚያስደስት ነው:: በሠለጠነ አካሄድ የሰላም መንገድ ማራመድም ፋይዳው ዘርፈ ብዙ ነው። ከውጭ አገራት አሸማጋዮች ይልቅ እኛው ለእኛው በሚል መርህ መከወኑ ደግሞ በተለይ የአፍሪካ አገሮች ከምእራባውያን ይልቅ በራሳቸው አቅም ያለማንም ጣልቃ ገብነት ከቅኝ ግዛት እሳቤ ተላቀው የራሳቸውን ችግር በራስ መፍታት እንደሚችሉ ተጨባጭ ምሳሌ የመሆን ትርጉሙን ያልቀዋል።
የሰላም አየር መተንፈስ መጀመሩ በተለይ ኢትዮጵያ የታሪካዊ ጠላቶቿ መቀለጃና መፈንጫ እንዳትሆን ያደርጋል። በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ እጃቸውን አስረዝመው የሚያስገቡ የውጭ ኃይሎች ፍላጎት እንዳይሳካ ግዙፍ ሚና ይጫወታል። ይህን ከግምት ከማስገባት በጦርነቱም ወቅት የታለፉ የጨለማ መንገዶችን ማስታወስ በቂ ነው።
በእኔ እምነት እነዚህ ለሰላም አስተዋፅኦ ያደረጉ አካላት ለኢትዮጵያውያን ትልቅ ክብር ያላቸው ናቸው። ኢትዮጵያ ተሻሽላና አድጋ ማየት የሚፈልጉ፣አንድ ጠንካራ ኢትዮጵያ እንድትኖር ከልብ የሚመኙና ለዚያም የሚታገሉ ናቸው። የሚኖሩት በእሷ ተከብሮ መቆየት ውስጥ ነው። እርሷ ሰላሟን አጥታ ሕሊናቸው አትረጋጋም።ኢትዮጵያ ጎድሎባት እነርሱ አይሞላላቸውም።እርሷ ዝቅ ብላ እነርሱ አይገዝፉም።የሚኖራቸው አገራቸው ሲኖራት ነው።
የሰላም ተዋናዮቹ በተግባራቸው የማንነትና የኢትዮጵያዊነት ትርጉም ፍቹ ቅኔና ወርቁ ነፃነት መሆኑን አሳይተዋል። ሰላም ሲሆኑ ከውብም በላይ አስፈሪ መሆናቸውንና የችግራቸው ግዝፈት በአብሮነት እንደሚቀል፣አቅማቸው ከአብሮነታችን የሚመነጭ ጥንካሬአችው እንደሆነ አረጋግጠዋል።እንደ ሴረኛውና ሸራቢው፣ እንደ ሟርተኛውና ፈራጁ ኢትዮጵያ ከውጭም ከውስጥም ፈተና ሲበዛ የምትደክም፣ ህዝቦቿም የሚንበረከኩ ለሚመስላቸው ትልቅ መልእክትን አስተላልፈዋል።
ለዚህ ስኬትም ቀድሞው የናይጀሪያ ፕሬዚዳንት እና የአፍሪካ ህብረት ልዩ መልእክተኛ ኦሊሴንጎ ኦባሳንጆ ፣ የቀድሞው የኬንያ ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ፣ የአፍሪካ ህብረት፣ የኢትዮጵያና የሕወሓት የድርድሩ ተወካዮች እንዲሁም ስመጥር ግለሰቦች ሚና መቼም ታሪክ የማይዘነጋው ነው።
እነዚህ የሰላም አምባሳደሮች እናት ኢትዮጵያ ስትጣራ አቤት በማለት አገሪቱን የተበተቡ ሰንሰለቶችን በጣጥሰዋል። የተቆለለባትን የሴራ ተራራ ንደዋል። ምሬቷን በሀሴት ቀይረዋል። መከፋቷን በደስታ ለውጠዋል። ዝቅታዋን ለሚመኙ ከፍታዋን አሳይተዋል።ወዟን ከሚነጥቁ ውበቷንም ከሚሰርቁ ቀማኞች ታድገዋታል።
ዛሬ ላይ ሰላም የተገኘውም‹‹የክፉ ቀን ደራሽ፣ የአገር ባለውለታ እና ቆራጥ ጀግኖች ህይወትና አካል ተገብሮበት ነው። ለእናት አገር ፍቅር የሚከፈለው መስዕዋትነት የዋዛ የሚታይ አይደለም።ከሕይወት መስዋዕትነትና በአካል ላይ ከሚደርስ ጉዳት በተጨማሪ፣የአገር ፍቅር ስሜት ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚሸጋገርበት የነፃነት ተጋድሎ መገለጫ ጭምር ነው።
ለእነዚህ የኢትዮጵያን እድገት እንጂ ዝቅታዋን፣ ደስታዋን እንጂ ሃዘኗን፣ ክብሯን እንጂ ውርደቷን ፈፅሞ የማይመኙ የቁርጥ ቀን ልጆች ብሎም ተቋማት ተገቢውን ክብር እውቅና መስጠትም እጅግ የሚያስመሰግን ተግባር ነው። እውቅናው አገራቸውን ለሚወዱ፣ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ በእውቀት፣ በገንዘብ፣ በደም እና በሕይወት ዋጋ ለከፈሉ ሁሉ ማስታወሻ ነው። እውቅና መስጠት ላበረከቱት አስተዋፅኦ፣ ማበረታታት፣ መደገፍ፣ ማድነቅ ትርጉሙ ላቅ ያለ ነው።
መሰል የእውቅ መርሀ ግብሮችን ማካሄድ ነገ ጠብን ከማቀጣጠል ይቀል ስለ ሰላም የሚደክሙ እንዲፈጠሩ ይግዛል።ያበረታታል።ጉልበት ይሆናል።ይህ ከሆነማ ነገ እኔም እሸለማለሁ፣ እታወሳለሁ ብሎ ስለ ሰላም ክብር እንዲያስብ ብሎም እንዲጨነቅ ያደርጋል።
በዛሬ ተግዳሎ ሁሉ አልፎ ታሪክ ሆኖ ሲወሳም ለነገው ትውልድ የሚያስተላልፈው መልእክት ግዙፍ ነው። በትውልድ ቅብብሎሽ ኢትዮጵያዊነት ታላቅነት አልሸነፍ ባይነት መሆኑን ከማስረገጥ ባሻገር ትውልዱ ችግሮችን በሰላማዊ መንገድ መፍታት ያስተምራል።ከሁሉም በላይ እውቅናው በመድረኩ ለተጠሩት ብቻ ሳይሆን ለሁሉም ከኢትዮጵያ ጎን ለቆሙ ሰላም ወዳጆች መሆኑን መገንዘብ የግድ ይላል።፡
ሌላው መታወቅ ያለበት ጉዳይ ቢኖር፣ ሰላም አየር መተንፈስ ጀምሯል ማለት ሁሉም አብቅቷል ማለት አይደለም። በተለይም በሰላም እጦት የተከሰቱ ድቀቶች ፈፅሞ ሊዘነጉ አይገባም። ሰላም ለማስፈን የተደረገው ጥረት በተለይም በጦርነት የተጎዱትን መልሶ በማቋቋምና በመደገፍ ሊደገም ይገባል። አስፈላጊውን የገንዘብና ሌሎችም ድጋፍ በማሰባሰብ ረገድ የአፍሪካ ህብረትም ሆነ ሌሎች በመሪነት ሊፈፅሙት ይገባል።
አሁንም ቢሆን ወቅቱ የኢትዮጵያን ችግሮች የመሸሽ ሳይሆን የማሸሽ ተጋድሎን ይጠይቃል።ኢትዮጵያን ነገ ማሳመር የሚችሉት ደግሞ ኢትዮጵያውያን ብቻ ናቸው። እድገቷም ውድቀቷም በልጆቿ እጅ ላይ ያረፈ ነው። በኢትዮጵያ ምድር የሰላም አየር መንፈሱ እንዲቀጥል እንደ ትናንቱ ሁሉ ነገም በኢትዮጵያ የመጣ በሰብዕናችን እንደመጣ፣እርሷን የነካ አይናችንን እንደነካ በመቁጠር አስተማማኝ ምርኩዝ መሆናችንን ልንቀጥል ይገባል። ኢትዮጵያ ካለ እኔና እናንተ አትበረታም።
በኢትዮጵያ ምድር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ የጦርነት ምዕራፍ እንዲዘጋ ኢትዮጵያውያን በሙሉ ከዳር እስከ ዳር በአንድነት መንቀሳቀስ ይጠበቅባቸዋል። የፖለቲካ ኃይሎችም ሆኑ ሌሎች የአገር ጉዳይ ያገባናል የሚሉ ወገኖች፣ ኢትዮጵያ ከግጭት የፀዳች አገር እንድትሆን ቁርጠኝነታቸውን በተግባር ማሳየት ይጠበቅባቸዋል።
በአንድ አፍ ስለሰላም እየዘመሩ በሌላ አፍ ጦርነትን የሚደግፉ የፖለቲካ ተዋንያንም ሆኑ አክቲቪስቶች፣የሰላም መንገዱ እንዲዘጋና ጦርነቱ እንዲያገረሽ ከሚያደርጉ ፕሮፓጋንዳዎች እንዲታቀቡ ማድረግ መቼም መዘንጋት አይኖርበትም።
ታምራት ተስፋዬ
አዲስ ዘመን ሰኞ ሚያዝያ 16 ቀን 2015 ዓ.ም