ከሀገራዊ ለውጡ ወዲህ ያለው የኢትዮጵያ መንግስት አዲስ ባህል ይዞ መጥቷል። ይህ ባህል የምስጋና ወይም የእውቅና ባህል ነው። በዚህም ግለሰቦች፣ ቡድኖች፣ ተቋማት፣ ወዘተ ላከናወኗቸው መልካም ተግባሮች ልዩ ስነ ስርአት በማዘጋጀት እውቅና ይሰጣል። በተለያዩ ጊዜያት በተካሄዱ የእውቅና መርሀ ግብሮች ለሀገር የዋሉ የመከላከያ ሰራዊትና የፖሊስ አባላት፣ ባለሀብቶች፣ ዲያስፓራዎች፣ ጠንካራ ግብር ከፋዮች፣ ሰራተኞች፣ አመራሮች፣ ቡድኖች፣ ወዘተ. እውቅና ተሰጥቷቸዋል፤ ተመስግነዋል፤ ተበረታትተዋል።
ለእነዚህ አካላት ላባረከቱት አስተዋጽኦ ምስጋና ማቅረብ አንድ ትልቅ ነገር ነው፤ ስራቸው ዋጋ እንዳለው ሀገርና ህዝብን የጠቀመ መሆኑን ከፍተኛው የመንግስት አካል አውቆላቸዋል፤ መንግስት ለእነዚህ አካላት ማድረግ የሚችለውን ትልቁን ነገር ነው ያደረገው። ይህ እውቅና በአደባባይ የሚከናወን፣ ለህዝብ ይፋ የተደረገ፣ ከገንዘብም ከንብረትም በላይ ነው።
እውቅናው ሌሎችም ይህን አርአያነት ያለው ተግባር እንዲከተሉ ግንዛቤ የሚሰጥበትም ነው። እነዚህ ተምሳሌቶች እንዲበዙ፣ እንዲበረክቱ ለማድረግም አቅም አለው። ይሄ እውቅና ምን ያህል ሌሎች መሰል ጀግኖችን እንዳፈራ ለማወቅ ጥናት ወይም መሰል ተግባር ማከናወንን ቢጠይቅም፣ ሌሎች ተመሳሳይ ጀግኖች ማፍራት እንደሚያስችል ግን ጥርጥር የለውም። እውቅና መሰጠቱ እውቅና ተቀባዮችን አበረታትቶ ብቻ አይቆምም፤ ሌሎችም በእነሱ ልክ ተነቃቅተው እንዲሰሩ በር ይከፍታል።
የእውቅና መርሀ ግብሮች በተለያዩ ደረጃዎች በብዛት በተደጋጋሚ እየተካሄዱ ይገኛሉ፤ በፌዴራል መንግስት ደረጃ ብቻ ሳይሆን፣ በክልሎች፣ ከዚያም በታች ባሉ እርከኖችና በተለያዩ ድርጅቶች ወይም መስሪያ ቤቶች ተመሳሳይ መርሀ ግብሮች በተደጋጋሚ ይካሄዳሉ። ይህ ሁሉ ሁኔታ የሚያመለክተው እውቅና እየተሰጠ ያለበት ሁኔታ ሌሎች ለመልካም ስራ እንዲተጉ እያነሳሳ መሆኑን ነው።
መንግስት ይህን ታላቅ መርሀ ግብር ከሀገር ለተሻገረ ተግባርም አውሎታል። የእውቅና ባህሉን በዛሬው እለት ደግሞ ለሌላ ከፍ ያለ ተግባር ያውለዋል። ከሀገር ለተሻገረ ተግባር አውሎታል። በሰሜን ኢትዮጵያ የተካሄደው ጦርነት በሰላም ስምምነት እንዲጠናቀቅ ላደረጉት የአፍሪካ ልጆች ምስጋና ያቀርብበታል።
የአፍሪካን ልጆች ለማመስገን የሚካሄደው ይህ የምስጋና ባህል ለብቻው ትርጉሙ ብዙ ነው። እንደሚታወቀው፤ ኢትዮጵያ ላለፉት አመታት ህልውናዋን አደጋ ላይ በጣለ ጦርነት ውስጥ ቆይታለች። ከሕወሓት ጋር በተደረገው በዚህ ጦርነት የአያሌ የኢትዮጵያውያን ህይወት ጠፍቷል፤ አካል ጎድሏል፤ የዜጎች ሰላምና መረጋጋት አደጋ ውስጥ ገብቷል፤ የሀገር ሀብት ወድሟል፤ የሀገር ገጽታ በእጅጉ ተበላሽቷል። ሀገር በአንዳንድ ዘርፎች የወደሙባትን ንብረቶች ተከትሎ አዲስ ጎጆ ወጪ የሆነችበት ሁኔታ ተፈጥሯል። ይህ ጥፋት እንዳይቀጥል ከፍተኛ ሚና ለተጫወቱ የአፍሪካ ልጆች የተሰጠ እውቅና ነው።
በወቅቱ የነበረውን ጦርነትና በሀገሪቱ ውስጥ፣ ዙሪያዋን እና በተለያዩ የኢትዮጵያን ጥሩ በማይመኙ ሀገሮች ሲደለቅ የነበረውን የጦርነት ነጋሪት እየሰሙ ኢትዮጵያ ልትበተን ነው፣ የሊቢያ፣ የመን፣ የኢራቅ እጣ ፈንታ ሊደርሳት ነው እያሉ ሲያሟርቱ የነበሩ ኃይሎች ሟርት ያከሸፈ የሰላም ስምምነት እንዲደረስ ያደረጉ አፍሪካውያን በኢትዮጵያ መንግስት በይፋ እውቅና ማግኘታቸው የሀፍረት ማቃቸውን እንዲከናነቡ ያደርጋቸዋል።
አንዳንድ ምእራባውያን ኃያላን ሀገሮች ኢትዮጵያ ላይ ያሳረፉት ጫና ዛሬም ድረስ ሀገሪቱን የውጭ ምንዛሪ ቋት አሟጦታል፤ የአሜሪካ መንግስት የኢትዮጵያ መንግስትን ያንበረክክልኛል ያለውን አሜሪካ ለኢትዮጵያ በአጎአ የሰጠቻትን ከቀረጥ ነጻ መብት ማገዱ በኢንዱስትሪ ፓርኮች፣ ባለሀብቶችና ምርቶቻቸው ላይ አሉታዊ ተጽእኖ አሳርፏል። ሀገሪቱ በኢንዱስትሪ ፓርኮቿ የያዘቻቸው እቅዶች በታሰበው ልክ እንዳይሄዱ ተደርገዋል።
ይህ ደግሞ ኢኮኖሚዋን ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ ለማሻገር በምትታትር ሀገር ላይ ሊያሳድር የሚችለውን አሉታዊ ተጽእኖ መገመት አይከብድም። በደቡብ አፍሪካ ከዚያም በኬንያ ለተደረሱ ስምምነቶች የአፍሪካውያኑ አቀራራቢነት ዋጋው ከፍተኛ ነውና እውቅናው በእርግጥም ይገባቸዋል፤ ይመጥናቸዋል።
ለእዚህ ሁሉ ምክንያት የሆነው ጦርነት ተዋናዮችን ወደ ጠረጴዛ ዙሪያ ውይይት እንዲመጡ በማድረግ ከዚያም ለስምምነት እንዲደርሱ ላደረጉ፣ በስምምነቱም መሰረት መሬት ላይ ነገሮች እንዲፈጸሙ በማድረግ በኩል ታሪክ ሲያስታውሰው የሚኖር ተግባር ላበረከቱ የአፍሪካ ልጆች የኢትዮጵያ መንግስት የምስጋና መርሃ ግብር ማዘጋጀቱ ለሰላም ያለው ጽኑ አቋም ተጠናክሮ መቀጠሉ በሚገባ የታየበት፣ ለሰላም ዋጋ ለሚከፍሉ ሁሉ ያለውን ታላቅ ክብር ያሳየበት እንደመሆኑ ትልቅ ስፍራ ሊሰጠው ይገባል።
የሰላም ስምምነቱ የዜጎችን እልቂት፣ አካል መጉደል፣ መሰደድ፣ ከእንግልት ፣ ሴቶችን ከአስገድዶ መደፈር የሚታደግ፤ በጦርነት ድቅድቅ ጨለማ ውስጥ መኖርን የሚያስቀር ጥሪታቸውን፣ ሀብታቸውን፣ ንብረታቸውን፣ የሚያስጠብቅ እንደመሆኑ ትልቅ ስፍራ ይሰጠዋል፤ በተለያዩ ወገኖች ዘንድ አድሮ የነበረውን የሀገር ገጽታ ስብራት ይጠግናል፤ ያድሳል፤ ይህ የሰላም ስምምነት እንዲደረስ ለታተሩ፣ ስምምነቱ መሬት እንዲያርፍ ለደከሙ የአፍሪካ ልጆች መንግስት ይህን ታላቅ መድረክ በማዘጋጀት እውቅና መስጠቱ አሁንም የመንግስትን የሰላም ቁርጠኝነት በሚገባ ያመለክታል።
የሰሜን ኢትዮጵያውን ጦርነት ተፋላሚዎች ለማደራደር ሌሎች ወገኖችም ሞክረዋል። አሜሪካና የአውሮፓ ህብረት ከእነዚህ መካከል ይጠቀሳሉ። ማደራደሩ ባልከፋ፤ እነዚህ ሀይሎች በወቅቱ ያራምዱ ከነበረው አቋም አኳያ በማደራደሩ ጉዳይ ይኖራቸዋል ተብሎ ከታሰበው ወገናዊነት አኳያ ሚናቸው አዋጭ እንዳልሆነ ተገምቷል።
የኢትዮጵያ መንግስት ግን ችግሩ አፍሪካዊ ነው ፤ መፍትሄውም በአፍሪካውያን እጅ ነው ብሎ አፍሪካውያን ለችግሩ መፍትሄ እንዲያመጡ በማሳወቅ በሩን ለአፍሪካውያን አደራዳሪዎች ከፍቷል። ይህን የኢትዮጵያ መንግስትን ጽኑ አቋም የተገነዘበው የአፍሪካ ህብረት ለሽምግልናው በተከፈተው በር ገባ። ህብረቱ ለእዚህ ታላቅ ጉዳይ የቀድሞውን የናይጄሪያ ፕሬዚዳንት ኦሊሰጉን ኦባሳንጆን ሰየመ። እሳቸውም ወደ ኢትዮጵያ ብዙ ተመላለሱ፤ ትግራይ ክልልም እየተመላለሱ ጥረት አደረጉ።
የሰላም ውይይቱ በደቡብ አፍሪካ ሊካሄድ መሆኑ ሲሰማ ደግሞ በሰላም ውይይቱ ላይ የደቡብ አፍሪካና የኬንያ ፕሬዚዳንቶች ተካተቱ። አፍሪካዊ ጉዳይ መሆኑ በግልጽ እየታየ መጣ፤ አፍሪካውያኑ እንደሚጠበቁትም አፍሪካዊ መፍትሄ አፍልቀው ሁለቱ ወገኖች ፊት ለፊት እንዲነጋገሩ አደረጉ። እነዚያ በመገናኛ ብዙሃን ሲካሰሱ፣ በጦር ግንባር ሲጫረሱ የነበሩ ወገኖች ሲወያዩ ሰነበቱ፤ ከሰላም ስምምነትም እንዲደርሱ አደረጉ።
ሁለቱ ወገኖች ንግግራቸውን ሲያደርጉም በሌሎች ሀገሮች እንደታየው ውይይት የተቋረጠበት፣ ገባ ወጣ የበዛበት ሁኔታ አልታየም፤ የተኩስ አቁም የተጣሰበት ሁኔታም አልነበረም፤ ብዙዎች እንደጠበቁት ባለመስማማት መለያየት አልተስተዋለም። ይህም ውይይቱ የይስሙላ ሳይሆን የልብ መሆኑን ያመላከተ ነው። ከቀናት ውይይት በኋላ ስምምነት ተደረሰ። በኬንያ የተካሄደው ውይይትም እንዲሁ ሰላማዊ በሆነ መልኩ ነው የተካሄደው።
ይህ ስምምነት የተደረሰው ግጭት በሚጠመቅባት አፍሪካ ውስጥ ነው። የአያሌ አፍሪካውያንን ህይወት የሚቀጥፉ፣ ሀብትና ንብረታቸውን እያወደሙ ለድህነት እንዲዳረጉ የሚያደርጉ አያሌ ግጭቶች በሚቀፈቀፉባት፣ ግጭቶቹ መፍትሄ አልባ ሆነው አመታትን በሚዘልቁባት አፍሪካ የተደረሰ የሰላም ስምምነት እንደመሆኑም ስምምነቱ ለአፍሪካም ልዩ ስፍራ ያለውና ሞዴል ተብሎ ሊወሰድ የሚገባው ነው። ይህን ላደረጉ የአፍሪካ ልጆች እውቅና መስጠት በእጅጉ ኃላፊነት የሚሰማው መንግስት ተግባር ነውና የኢትዮጵያ መንግስትም ሊመሰገን ይገባዋል።
ይህ አምድ በተለያዩ ፖለቲካዊ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ዜጎች ነፃ ሀሳባቸውን የሚሰጡበት ነው።በዓምዱ ላይ የሚወጡ ጽሁፎች የዝግጅት ክፍሉን አቋም አያመለክቱም።
ዘካርያስ
አዲስ ዘመን ሰኞ ሚያዝያ 16 ቀን 2015 ዓ.ም