‹‹ሰላም›› ይሉት ቃል በሶስት ፊደላት ተወስኖ፣ በአጭር አባባል የተገለጠ ሀሳብ ነው። የቃሉ ምጣኔ ያነሰ፣ የተመጠነ ይምሰል እንጂ የትርጓሜው ሀያልነት ዓለምን ሁሉ ይገዛል። ታሪክን ይቀይራል። ለዚህም ነው ስለሰላም ከልብ የጣሩ፣ ቃሉን አድምቀው የጻፉ፣ መኖሩን አብዝተው የሻቱ ሁሉ ከስረው የማያውቁት ።
የከሳቴ ብርሀን ተሰማ የአማርኛ መዝገበ ቃላት ስለሰላም ምንነት እንዲህ ሲል ፍቺውን አስፍሯል። ‹‹ሰላም ማለት የፍቅር ፍሬ ነገር ፣ ያማረ፣ የተወደደ ፣ የቀና ነገር ፤ ፍቅር አንድነት ፣ መስማማት፣ በሀሳብ በስራ መግባባት ያለበት ፣ ይሄ የእኔ ነው የአንተ አይደለም እየተባባሉ አለመቀናናት፣ እንደ አንድ ነፍስ እንደ አንድ ስጋ መሆን ማለት ነው››
የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ምርምር ማዕከል ባሳተመው የአማርኛ መዝገበ ቃላትም ስለሰላም ምንነት እንዲህ ሲል አስፍሯል። ‹‹ሰላም ረብሻ፣ ሁከት ፣ ጦርነት የሌለበት የተረጋጋ፣ ሁኔታ ደህንነት፣ ጤንነት፣ የአዕምሮ እርፍት ማለት ነው።
ይህ ታላቅ የዓለማችን ድንቅ ስጦታ በምድር ላሉ ፍጥረታት ሁሉ የውሀና የእስትንፋስ ያክል አስፈላጊ የሚባል ነው። ያለ ሰላም ህይወትና ኑሮ፣ ትምህርትና ትዳር አይታሰብም። ያለሰላም በሰላም መኖር፣ ተኝቶ መነሳት፣ ርቆ መራመድ አይታቀድም።
መቼም ቢሆን የሰላም ዋጋ በገንዘብ የሚተመን፣ በሚዛን የሚለካ አይደለም። ሰላም ሁሌም ዘብ ይቆምለታል፣ ውሎ አዳሩን የሚያከብር፣ ባህር ሞገዱን የሚሻገር ዕልፍ ወታደር ይሾምለታል። የሀይማኖት አባቶች፣ ታዋቂ ሽማግሌዎች፣ የአገር መሪዎች በየጊዜው ስሙን አንስተው፣ ያወሱታል።
የሰላም እጦት ከቤት ከቀዬ ያፈናቅላል፣ ከእናት አገር ምድር ያሰድዳል፣ ክቡር ህይወትን ነጥቆ ሀብት ጥሪትን ያሳጣል። አገራችን ለዓመታት ያለፈችባቸው የጦርነት ታሪኮች ሰላምን አጥብቃ እንድትሻ ሲያስገድዳት ቆይቷል። ይህ አይነቱ አስከፊ ጠባሳ ያሳደረው ተጽዕኖም በታሰበው ልክ በዕድገት ጎዳና እንዳትራመድ ጋሬጣ ሆኖባት ዘልቋል። በጦርነት ውስጥ እንደ ጸሀይ ብልጭ የማትል ሰላም በታጣች ጊዜ የኑሮ፣ የህይወት ደርዝ ይናዳል፡ የዕንቅልፍ ወጉ የመኖር እፎይታው ይናፈቃል።
በአብዛኞቹ የአፍሪካ አገራት በተካሄዱ የእርስበርስ ግጭቶች ለቁጥር የሚያታክት የሰው ልጆች ህይወት መስዋዕት ሆኗል። በቀላሉ ሊተኩ የማይችል ሀብት ንብረት ወድሟል። በሺዎቹ የሚቆጠሩ ህዝቦች ለመፈናቀልና ስደት ተዳርገዋል። በነዚህ አገራት አሁንም ድረስ ያልተገኘው ሰላም ድህነትን አባብሶ አገር እስከማፍረስ ደርሷል።
በአገረ ሶርያ፣ የመን፣ አፍጋንስቲን፣ ሊቢያና ሶማልያ የተከሰተው እረፍት አልባ ጦርነት በርካታ ዋጋ እያስከፈለ ነው። አሁንም ድረስ የንጹሀን ህይወት ይጠፋል፣ ንብረት ይወድማል፣ ከተማ በአየርና በምድር ጥቃት ይደበደባል። በየዕለቱ አገር በሚናድ፣ በሚፈርስበት አጋጣሚ ሁሉ ህይወት ያለተስፋ መቀጠሉ እውነት ሆኗል።
የዚህ ስፍራ ነፍሶች የየዕለት ስንቃቸው ሞትና ስቃይ ነው። ስለነገ የሚተርፍ ጭላንጭል ህልምና ዕቅድ የላቸውም። እስከ ህቅታቸው ሊያዘልቃቸው የሚችል የሰላም ርጋፊ ከእጃቸው አይገኝም፤ ዘወትር የተማሰ መቃብራቸውን ያስባሉ፣ የጽልመት ኑሯቸው በመከራ የተለወሰ፣ በመሳቀቅ የተመላ ነው። የእነሱ የሰቆቃ ዓለም መቼም በርቶ አያውቅም። በድቅድቅ ጨለማ እንደተዋጠ ነገን በጭንቅ ያሻግራቸዋል።
ሰላምን አጥብቀው የሚሹ ኃይሎች ጥቂት የመሆን እውነት ጦርነት እንዲቀጥል፣ ድህነት እንዲስፋፋ ምክንያት ሆኗል። ዛሬ በነዚህ ስፍራዎች ነጭዋ እርግብ ክንፏን ዘርግታ አትበርም፣ የሰላም አየር ይሉት ጉዳይ ዘበት ነው። ከሰው ልጆች ዘንድ ህይወትና ኑሮ የሚባል ዓለም ፈጽሞ ታሪክ ሆኗል።
ሰላም በብዙ እውነታዎች ይፈተናል። በእርስ በርስ ጦርነት፣ በድንበር ይገባኛል ግጭት፣ በጎሳና ብሄር የእኔ እበልጥ ስሜት፣ ስልጣን በመንጠቅ ሽሚያና በሌሎችም። ሁልግዜም የዚህ አይነቱ የሰላ ሰይፍ በራሱ ጽንፍ ብቻ አይቆምም። የመድረሻው አንዱ ጫፍ ሌላውን ወገን አጥቅቶ በክፉ ታሪክ ይገለጣል። በግጭቱ የሌሉበትን ንጹሀን አጥቅቶ ክፉ አሻራውን ያትማል።
አገራችን ኢትዮጵያ ባሳለፈችው የጦርነትና የፖለቲካ ግጭት በቀላሉ የማትተካቸውን ሰብአዊ እሴቶች እንደዋዛ ተነጥቃለች። ከሰላም ይልቅ ነፍጥ ማንሳትን በወደዱ ኃይሎች የደረሰው ውድመትም የድህነት ታሪኳን አድምቆ ለውጭ ኃይሎች ፍላጎት ጭምር ሲያጋልጣት ቆይቷል።
በሰሜኑ የአገራችን ክፍል በተካሄደው አስከፊ ጦርነት ከምንም በላይ አይተኬውን የሰውልጆች ሕይወት ተነጥቋል። አገር መልማት፣ ማደግ፣ መለወጥ በሚገባት ዘመን እንደቀልድ ዕድሜና ሀብት ባክኗል። የወገን እሴት፣ ዕውቀትና ተስፋው በጦርነት እሳት ነዶ ሀዘን መከራን አሳጭዷል።
ይህ ሁሉ የሆነው በግጭቱ መሀል ጦርነቱን የረታ ክፋትን ያሸነፈ የሰላም ሙከራ አለመኖሩ ነው። በእሳት ዙሪያ ከበው ግጭት የሚያቀጣጥሉ፣ ንዳድ ቃጠሎውን የሚሞቁ ኃይሎችም እስከዛሬ ቤንዜን ከመጨመር የዘለለ መፍትሄን አላመጡም።
በውጭ አገራት የሚገኙ አንዳንድ ዲያስፖራ ነን ባዮች ወሬና አሉልባታን መተዳደሪያ አድርገው ሰላምን ሲያርቁ፣ እፎይታን ሲነጥቁ ቆይተዋል። እነዚህ ኃይሎች በየቀኑ ለሚሞተውና ለሚፈናቀለው ወገን አንዳች መላን አልፈየዱም። በተቃራኒው ክፉ መረጃን እየነዙ፣ ህዝብን ከህዝብ፣ ታሪክን ከታሪክ ሲያላትሙ ኖረዋል።
ይህ ብቻ አይደለም ለጦርነቱ መጀመርና መባባስ በምክንያትነት የሚጠቀሱ በርካታ የማህበራዊ ገጾች ሰላምን አርቀው፣ እሳትን በማንደዱ በኩል የላቀ አስተዋጽኦ ነበራቸው። የእነሱን ስሜት ተከትሎ ጣልቃ እንግባ ባዮቹ ምዕራባውን ውሻ በቀደደው ጅብ ሆነው ለመግባት ሲሯሯጡ መኖራቸውን ትውልድ አይዘነጋውም።
በነዚህ የታሪክ ስብራቶች መሀል ግን መልካምነትን የተላበሱ፣ ሰላምን ሽተው ጦርነትን የተጸየፉ ወገኖች አልታጡም። ስለሰላም ርቀው የተጓዙበት ጎዳና ሁሌ አልጋ በአልጋ ባይሆንም፣ እነዚያን ክፉ ቀናት ለማሻገር ስለሰላም ዘምረው ነጭ ርግብ ለመልቀቅ ቦዝነው አያውቁም።
እርግጥ ነው በወቅቱ ተስፋቸውን የሚነጥቅ፣ እርግባቸውን የሚያጠምድ ክፉ ድመት አላጡም። መንገዳቸውን የሚያደናቅፍ የብረት ወጥመድም ከእግራቸው ስር ነበር። እነሱ ግን እሳቱን አልፈው፣ ባህሩን ተሻግረው ‹‹እርቅ ይውረድ፣ ሰላም ይስፈን›› ብለዋል። ኩርፊያን አስወግደው፣ ጠብን አርቀው የጨለማ ብርሀን ሊሆኑ ታግለዋል።
በአገራችን በመልካም ማንነታቸው ሥብዕናቸው የተገነባ ታዋቂ ሰዎች፣ እናቶች ስለሰላም ጎንበስ ብለው ተማጽነዋል። ያለአገር ሰላም ክብርና ዝና አለመኖሩ ቢገባቸው ተንበርክከው ለምነዋል። ይህ እውነታ ሁሌም ስማቸውን ከስም በላይ እንዳደመቀው ይቀጥላል።
‹‹የአፍሪካውያንን ችግር በአፍሪካውያን›› ያሉ የክፉ ቀን ወገኖች በርካቶች የእሳት ላይ ቤንዚን በሆኑበት ዘመን የነደደውን ሊያጠፉ ቀዝቃዛ ውሀ ይዘው ቀርበዋል። መልካሞቹ አፍሪካዊያን ወንድሞቻችን ስለሰላም ሌት ተጉዘዋል።
እነሆ ለዓመታት የተጉበት፣ ድካማቸው ፍሬ ይዞ ውጤት አፍርቷል። የትናንቱ ጦርነት በሰላም ስምምነት ድል ተነስቶ ደም መፋሰስ ቆሟል። የጥይት ድምጽ እንዳይኖር፣ ፍጹም የሰላም እንዲሰፍን ያደረጉት ጥረትም ተሳክቷል። ዛሬ አገራችን ኢትዮጵያ ከቆየችበት የሰላም ርሀብ አገግማ ወደ ትናንት ማንነቷ ልትመለስ ጉዞ ጀም ራለች።
ይህች የታሪክና የነጻነት አገር ስለሰላም ሲሉ ከጎኗ የቆሙትን የክፉ ቀን ደጎች ፈጽሞ አትዘነጋም። ዛሬ በተራዋ እውቅና ልትሰጣቸው ከልብ ልታመሰግናቸው ቀን ቆርጣ ወስናለች። ስለሰላም፣ የሰላም አርማን ያነገቡ፣ ጦርነትን ታግለው ላሸነፉ ሁሉ ‹‹ሰላም ለእናንተ ይሁን ›› ስትል በምስጋና እጅ ትነሳለች።
መልካምሥራ አፈወርቅ
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 15 ቀን 2015 ዓ.ም