ወቅታዊ አገራዊ አጀንዳ ከሆኑት ሰሞነኛ ወሬዎች መካከል የክልል ልዩ ኃይ(ሎች)ል ጉዳይ አንዱ ነው። የክልል ልዩ ኃይል አባላትን ወደ ሌሎች የጸጥታ መዋቅር የማስገባት ሥራ በመላ አገሪቱ እየተተገበረ እንዳለ የመንግሥት መግለጫ ከሰሞኑ አሳውቋል። ይሁን እንጂ ይሄንን መግለጫ በተሳሳተ መንገድ በመረዳትና ያልተገባ መልክ በመስጠት በአገር ላይ ችግር ለመፍጠር የሚንቀሳቀሱ ቡድኖች በመስተዋል ላይ ናቸው።
የመንግሥትንም ሆነ የክልል መንግሥታት ያወጡትን መግለጫ ብናስተውል ስለአገርና ስለሕዝብ ሉአላዊነት የሚሞግቱ ሆነው ነው የምናገኛቸው። መንግሥት የአገሪቱን ሉአላዊነትና የግዛት አንድነት ለማስጠበቅ ሁሉን ያማከለ አንድ ጠንካራ ሰራዊት በመፍጠር ሂደት ላይ ብዙ ርቀትን መሄዱ የሚታመን ሲሆን ሰሞነኛ መግለጫውም ይህንኑ እውነታ የሚያጠነክር ሆኖ እናገኘዋለን።
በዚህም መሠረት የክልል ልዩ ኃይሎች እንደየፍላጎታቸው ወደ ተለያዩ የጸጥታ መዋቅሮች የሚገቡበት ተግባራዊ እንቅስቃሴ በመተግበር ላይ ይገኛል። በሁሉም ክልሎች የሚገኙ የልዩ ኃይል አባላት እንደምርጫቸውና ፍላጎታቸው በመከላከያ ሰራዊት አባልነት፣ በፌዴራልና በክልል ፖሊስ አባልነት መካተት የሚችሉ ሲሆን፣ በዚህ ነፃ ምርጫ ውስጥ መካተት የማይፈልጉ የልዩ ኃይል አባላት መብታቸው ተጠብቆ፣ ለመቋቋሚያ የሚሆን ሥራና ድጋፍ ተደርጎላቸው በሲቪልነት ወደ ማህበረሰቡ እንደሚቀላቀሉ መንግሥት በመግለጫው አስታውቋል።
ይህን ትግበራ በሚመለከት መንግሥት ከክልሎች ልዩ ኃይል አመራርና አባላት ጋር በመነጋገር መግባባት ላይ መደረሱ የመግለጫው አንዱ አካል ሲሆን፣ በብዙ ጥናትና በተገኘው ውጤትም ለአንድ ጠንካራ አገርና ሰራዊት ውሳኔው የተሻለ መሆኑ ተገልጿል።
ከዚህ ጋር በተያያዘ የክልል ልዩ ኃይልን በተለያየ የጸጥታ መዋቅሮች ውስጥ የማካተቱ ውሳኔ በጥናት ላይ ተመስርቶ የሚከናወን ሲሆን ይህ ዓይነቱ እውቀትና ምክንያታዊነትን ያነገበ አካሄድ አሁን ላሉብን ዘርፈ ብዙ ችግሮቻችን መንገድ ከፋች እንደሚሆን ያሳያል።
እንዲህ ዓይነቱ በጥናት ላይ የተመሠረተ የውሳኔ ትግበራ በሰራዊት ረገድ ሉአላዊት አገር ከመፍጠር ጎን ለጎን የኢኮኖሚ አቅማችንን በማስተሳሰር የሰራዊታችንን የስልጠና፣ የትጥቅና የኑሮ ሁኔታ ከማሻሻል አኳያ ከፍተኛ ጥቅም አለው። ከዚህ ከፍ ሲልም የምንፈልጋትን ሉአላዊት አገር በተጠናከረ ሰራዊትና በታመነ አቋም ለመፍጠር መተማመኛ የሚሰጠን ነው።
«ሁሉንም የክልል ልዩ ኃይሎች እንደገና የማደራጀቱ ተግባር ለዘላቂ የአገር ጥቅም እና ደህንነት ነው» ሲል መንግሥት በመግለጫው አጽንኦት ሰጥቶ ያስታወቀ ሲሆን፣ ከዚህ እውነት በመነሳት ወደ’ማያሻማ ተግባቦት መሄድ ይቻላል። ከዚህ የመንግሥት መግለጫ ጎን ለጎን የመንግሥት ኮሚዩኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ወ/ሮ ሰላማዊት ካሳ መንግሥት በክልል ልዩ ኃይሎች ላይ ያወጣው የትግበራ እንቅስቃሴ የሁሉንም ክልል ልዩ ኃይል አባላት መልሶ የማደራጀት ሥራ እንጂ ከትጥቅ ማስፈታት ጋር የሚያያዝ እንዳይደለ ተናግረዋል።
እንቅስቃሴው አንዳንዶች እንደተረዱት ሳይሆን የአገር ሉአላዊነትን ከማስጠበቅ፣ አገር ውስጥ ሆነ ከውጭ የሚሰነዘርን ጥቃት ከመከላከል አንጻር ጠንካራ ሰራዊት ለመገንባት የሚያስችል እድል መፍጠር ነው ብለዋል። ከዚህ ጋር በተያያዘ የክልል መንግሥታትም ተመሳሳይ አቋምን በማንጸባረቅ ላይ ይገኛሉ።
ቀደም ባለው ጊዜ እንዳየነው የክልል ልዩ ኃይል በክልሎች መካከል የደህንነት ዋስትና መሆኑ ቀርቶ መፎካከሪያ ነበር። አገር የምትባለውን ትልቅ እውነት በመተው ስለክልልና ስለታጠቁት መሣሪያ ሙግት ውስጥ ገብተው ታዝበናል። እንዲህ ዓይነቱ ያልተገባ አካሄድ አገራችንን በእኔነትና በራስ ወዳድነት ከማጎሳቆል ባለፈ አንድነት አይሰጠንም።
በመሠረቱ የክልል ልዩ ኃይልን የኢትዮጵያ ሕገ መንግሥት እውቅና አይሰጠውም። በአንድ አገር ላይ በብሔር ስብጥር የቆመ አንድ መከላከያ ሰራዊት እንደሚያስፈልግ ሕገ መንግሥቱ ይደነግጋል። በዚህ ድንጋጌ በኩል ብናልፍ እንኳን አሁን ላይ መንግሥት እያደረገ ያለውን፣ ልዩ ኃይልን የማዋቀር መግለጫ ልክ ሆኖ እናገኘዋለን።
ሕገመንግሥቱ እውቅና ያልሰጠው የጸጥታ መዋቅር አንዳንዴም ለአገር ስጋት መሆንን የሚጭር ነው። ሕገ መንግሥቱ እውቅና ባልሰጠው የክልል ልዩ ኃይል በኩል ክልሎች አዲስ አስተሳሰብን እየተለማመዱ የመጡበት ሁኔታ እየተስተዋለ ነው። በኢኮኖሚና በለውጥ መፎካከር ሲገባቸው ልዩ ኃይላቸውን ለመፎካከሪያነት የሚጠቀሙ ክልሎች እየተፈጠሩ ነው። ይህ እንግዲህ አገር ላይ አደጋ የሚደቅን ‹የእኔ እበልጥ እኔ› አጉል ልምምድ መሆኑ ነው።
በእርግጥ መልስ የሚፈልጉ ከሕዝብ የሚነሱ አንዳንድ ጥያቄዎች አሉ። መንግሥት አገራችን በብዙ ችግር ውስጥ ባለችበት በዚህ ሰዓት እንዲህ ዓይነቱን ውሳኔ መወሰን ለምን መረጠ? የሚሉ ጥያቄዎች። አንዳንዶች ሕወሓት ትጥቁን ፈትቶ ባልጨረሰበት ሁኔታ የክልል ልዩ ኃይሎችን ለእንዲህ ዓይነቱ ትግበራ ማስገደድ አገራችንን ለዳግም ችግር መዳረግ ነው ብለው የሚሰጉ አሉ።
እነዚህ ሁሉ ጥያቄዎች በመንግሥት መግለጫ ላይ መልስ ተሰጥቶባቸዋል። በመጀመሪያ ደረጃ እየተሠራ ያለው ለየትኛውም አገራዊ ችግር አፋጣኝ ምላሽ የሚሰጥ የጦር ሰራዊት ለመገንባት ነው። ሕወሓትን በተመለከተ ለሚነሳው ጥያቄ ደግሞ በፕሪቶሪያው ስምምነት መሠረት የትጥቅ መፍታትን ጨምሮ ሁሉንም ዓይነት የስምምነት ሂደት እየተተገበረ እንደሆነ ተገልጿል።
ሕዝብ ከመንግሥት አሠራር ጋር በተያያዘ የሚያነሳቸው የስጋት ጥያቄዎች ልክ የሆኑና መበረታታት ያለባቸው ናቸው። ሆኖም ግን መረጃን መሠረት ያደረጉና ምክንያት ለበስ ቢሆኑ የበለጠ አዋጭ ይሆናሉ። አሁን ላይ የልዩ ኃይልን አደረጃጀት በተመለከተ ሁለት ዓይነት አረዳዶች እየተፈጠሩ ነው።
አንደኛው አረዳድ በመንግሥት በኩል የወጣው መግለጫና ብዙኃኑ የተረዳው ጠንካራ አገርና ጠንካራ ሰራዊት የመፍጠር አመኔታ ነው። ሌላኛው በአንዳንድ ክልሎች በተለይም በአማራ ክልል እየተስተዋለ ያለው የስጋትና የልዩ ኃይል ትጥቅ የመፍታት ፍራቻ ነው።
ምንም ሆነ ምን፣ እውነትን ማወቅ ነው አርነት የሚያወጣን። በተጣረሰ አካሄድና እውነትን በመሳት መንገድ ላይ የምንፈልገውን ለውጥ ማምጣት አንችልም። የሕዝብ ስጋት በመንግሥት የተደጋገመ እውነት ሊጠራ ይገባል። የሕዝብ ጥያቄ በመንግሥት ታማኝ መግለጫ ሊመለስ ግድ ይለዋል።
ስለአገራችን እውነታችንን የነጠቁን፤ እንዳይገባን አድርገው ያስቀመጡን ሰዎች አሉ። በለመዱት የጥላቻ እውቀት ስለጥላቻ ብቻ እንድናስብ ህሊናችንን የጋረዱብን ሰዎች። የገባቸውን ይደብቁንና ያልገባቸውን ይሰጡናል። እኛም ባልገባቸው ላይ ተንጠራርተን የገባቸውን አገር ወዳዶች እናውካለን። አሁን ላይ እየሆነ ያለው እንዲህ ነው።
የገባቸውን እውነት የሚያካፍሉን ሰዎች ያስፈልጉናል። በአንድነትና በፍቅር የቆሙ፣ ስለኢትዮጵያ ሁሉንም ዓይነት መስዋዕት ለመክፈል የተዘጋጁ ልቦች ያስፈልጉናል። ከቻሉ የገባቸውንና የሸሸጉትን እውነት አውጥተው ስለአገርና ሕዝብ «እውነቱ ይሄ ነው» ብለው ይንገሩን። ያለዛ በውሸት ትርክት ሳይገባን ነውጥ ፈጣሪ ባያደርጉን መልካም ነው።
መንግሥት በሰከነ መንገድ ሕዝቡን የማሳመን ሥራ ደግሞና ደጋግሞ መሥራት ይጠበቅበታል። ሕዝብም የመንግሥትን የሉአላዊነት መሻት በመረዳት ከጎኑ ሊሆን ይገባል። የመንግሥት ሀሳብ ሕዝብ ላይ ሲሠራ፣ የሕዝብ ሀሳብ መንግሥት ላይ ሲታይ ነው ለውጥ የሚመጣው።
የልዩ ኃይል እንደ አዲስ መደራጀት የአንድ ወቅት የሕዝብ ጥያቄ ነበር። መንግሕት ጊዜ ጠብቆ በሕዝብ ጥያቄም ሆነ በሕገመንግሥቱ መሠረት ትግበራ ጀመረ። አንዳንዶች ሲቀበሉት አንዳንዶች ስጋት ያዛቸው። በመንግሥት ሀሳብ ላይ ሕዝብ የትኛውንም ጥያቄ የማንሳት መብቱ የተጠበቀ ነው። ሆኖም ግን የአደረጃጀቱን አላማ በመረዳት ይሁንታን ማሳየቱ ለመንግሥት ጉልበት መሆን ጭምር ነው።
አገራችን ኢትዮጵያ በእንዲህ ዓይነት መልኩ ካልተገነባችና በተጠናከረ ሰራዊት ካልተጠበቀች ህልውናችን አደጋ ላይ ነው የሚወድቀው። ከዚህም ከዚያም እንደምንሰማው ለውጥና እድገታችንን ተከትሎ ከተለያዩ አገራት ትንኮሳ እየደረሰብን ነው። ይሄን ዓይነቱ የሉአላዊነት ጥያቄ በአስተማማኝ መንገድ የሚመለሰው ደግሞ አስተማማኝ መከላከያ ሰራዊት ስንገነባ ነው።
የልዩ ኃይል አደረጃጀትም ኢትዮጵያን ከመጠበቅና የሕዝብ ደህንነትን ከማረጋገጥ አኳያ ብናየው የተሻለ ነው የሚሆነው። ከዚህ ውጪ የምንሰማቸው አሉባልታዎችም ሆኑ ከእውነት የራቁ መረጃዎች ያለምነውን ግብ እንዳንመታ እንቅፋት ከመሆን ባለፈ ምንም አይፈይዱልንም።
የተሳሳተ አረዳድ የተሳሳተ ድርጊትን ነው የሚፈጥረው። የተሳሳተ ድርጊት ደግሞ በአገርና ሕዝብ ላይ መከራ ነው የሚጥለው። እውነትን በመሻት አረዳዳችንን አስተካክለን የተሻለች አገር ብንፈጥር ትርፉ የጋራችን ነው። እውነትን አጣመውና አዛንፈው መንግሥትን ከሕዝብ ጋር ሆድና ጀርባ ለማድረግ እንቅልፍ የማይተኙ አገር ጠል ኃይሎች ጥቂት አይደሉም።
አለማመናችን ለእነዚህ ኃይሎች መንገድ መክፈት ነው የሚሆነው። መንግሥት ሕዝብን ሊያምን፣ ሕዝብም መንግሥትን ሊያምን ይገባል። መተማመን በሌለው የመሪና የተመሪ ፖለቲካ ውስጥ ዛሬን ልክ ብንሆን ነገን ልክ መሆን አንችልም። ልዩ ኃይልን በተመለከተ የመንግሥት መግለጫ መንግሥት ለሕዝብ የሰጠው የእምነት ቃሉ ነው።
የመተማመን ፖለቲካ ነው ሩቅ የሚወስደን። መንግሥትና ሕዝብ ካልተማመኑ አገር ማለት ትርጉም ያጣል። ሕዝብ መንግሥትን በእምነት ሊቀበለው መንግሥትም በእውነት ሕዝብን ሊመራ ያስፈልጋል። የምናያቸውና የምንሰማቸው ነገሮች ናቸው ዛሬ ላይ መተማመናችንን ያጠፉብን።
የልዩ ኃይል አደረጃጀት ነገ ላይ ጠንካራዋን ኢትዮጵያ የምንፈጥርበት መንገድ እንደሆነ ከመንግሥት መግለጫ አረጋግጠናል። ይሄን እውነት በመቀበል ለትግበራው መንገድ መጥረግ ሕዝብ ኃላፊነቱን የሚወጣበት አንዱ ማሳያ ነው። አገራችን ኢትዮጵያ በተለያየ ጊዜ ከተለያዩ አገራት የሉአላዊነት መደፈር ሲደርስባት ነበር።
ይህን መሰሉን ጥቃት ለመከላከል በመንግሥት በኩል ከተወሰዱ እርምጃዎች አንዱ መከላከያ ሰራዊትን ማጠንከር ነው። በዚህም መሠረት የክልል ልዩ ኃይሎች ከነሙሉ ትጥቃቸው ወደ ፈለጉት የጸጥታ መዋቅር እንዲገቡ እድል ተፈጥሮላቸዋል። እዚህ ጋ አጽንኦት የሚሰጠው አንድ ሀሳብ ቢኖር ትጥቅ መፍታትና ከነትጥቅ ወደ ፈለጉት የጸጥታ መዋቅር መግባት የተለያዩ ጽንሰ ሀሳቦች እንደሆኑ ነው።
ብዥታችንን ማጥራት አለብን። መንግሥት «የክልል ልዩ ኃይሎች ትጥቃቸውን ይፈቱ» አላለም። አንዳንዶች ትጥቅ ፍቱ እንደተባለ አድርገው የሚያስቡ አሉ። ትጥቅ መፍታትና ከነሙሉ ትጥቅ ወደ ጸጥታ መዋቅር መግባት የተለያዩ ናቸው። ችግር እየፈጠሩብን ያሉ በቀጥታ ሳይሆን በተጓዳኝ የምንሰማቸው አሉባልታዎች ናቸው።
ወቅታዊውን አሉባልታ በተመለከተ በመንግሥት በኩል የተሰማው መግለጫ የልዩ ኃይልን አደረጃጀት፣ አላማና ትግበራ ያጠራ ነው። የትግበራ ሂደቱ የተሻለች ኢትዮጵያን ለመገንባት እንደሆነ መተማመን ላይ ተደርሷል። ይሄ መተማመን ከመንግሥት ወደ ሕዝብ የወረደ፣ ከሕዝብ መልሶ ወደ መንግሥት የተላለፈ አገር የመፍጠር የጥንካሬና የአይበገሬነት ማሳያ ነው።
ይህ ጥንካሬና አይበገሬነት ደግሞ የክልል ልዩ ኃይሎች የመንግሥትን ጥሪ ተከትለው ለአንድ አገርና ለአንድ ሕዝብ ይሁንታን ሲያሳዩ የሚጸና ነው። አንድን እውነት አስር ቦታ ከፍለን በፈለግነው መንገድ በመረዳት ማሸነፍ አንችልም። አሸናፊነታችን ያለው በሕዝብና መንግሥት መተማመን ውስጥ ነው። እንደአገር መቀጠል የምንችለው በጋራ ሀሳብ ለጋራ ትልም ስንደክም ነው።
ከብዥታ ወጥተን ወደ’ሚጠቅመን እውነት ማማተር ነው አገር የሚሰጠን። ጥያቄዎቻችን የአገር ጠላቶች የፈጠሯቸው እንዳይሆኑ ራሳችንን እንፈትሽ። ለአገራችን የሚበጃት የቱ እንደሆነ በመንግሥት በኩል የተነገረን የአደረጃጀት ትግበራ አለ። በዚያ እውነት ውስጥ መክረንና ዘክረን ጠንካራዋን ኢትዮጵያ ከመፍጠር ሌላ አስተማማኝ አማራጭ የለንም።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 5/2015