የጦር ኃይሎች ምክትል ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ጄነራል አበባው ታደሰ ከሰሞኑ ከመገናኛ ብዙኃን ጋር ቆይታ አድርገው ነበር፡፡ በዚህም ቆይታቸው በአገሪቱ የመከላከያ ሰራዊት እና የጸጥታ ተቋማት ላይ እየተደረገ ስላለው ሪፎርም ሰፊ ማብራሪያ ሰጥተዋል። የዚህ ሪፎርም አካል ስለሆነው የክልል ልዩ ኃይሎችን መልሶ የማደራጀት ሥራም እንዲሁ አንስተዋል።
በማብራሪያቸው በአገሪቱ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ የዳሰሱ ብዙ ጉዳዮችን አንስተዋል፡፡ እሳቸው ከሰጡት ማብራሪያ በመነሳትም አገራችን አሁን ያለችበትን ሁኔታ በተሻለ መልኩ ለመረዳት ችያለሁ። በአንዳንድ ጉዳዮችም ላይ የጠራ ግንዛቤ መጨበጥ የቻልኩ ይመስለኛል።
ምክትል ጠቅላይ ኢታማዦር ሹሙ የሪፎርም አስፈላጊነት በተነተኑበት ማብራሪያቸው፤ አገሪቷ ሁለት ስጋቶች አሉባት፡፡ አንደኛው በምሥራቅ አፍሪካ ያለው ስጋት ሲሆን፤ ሁለተኛው ደግሞ በየጊዜው እየተቀያየረ የመጣው የዓለም ሁኔታ በኢትዮጵያ ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖ ነው።
ይህንን አደጋ መመከት የሚቻለው የመከላከያና የጸጥታ ተቋማት ላይ ቀጣይነት ያለው የማያቋርጥ ሪፎርም ማድረግ ሲቻል ነው፡፡ ይህንን በአግባቡ ለማከናወን ደግሞ ቀድሞ የራስን ቤት ማጽዳት አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል፡፡
የትኛውም የሪፎርም ሥራ ብዙ ተግዳሮቶች እንደሚያጋጥሙት ለመረዳት አያስቸግርም፤ ሪፎርም ይዞት የሚመጣው የለውጥና የመለወጥ ሀሳብ በራሱ ለተግዳሮት የተጋለጠ ነው። በሂደት የመጥራታቸው እውነታ እንዳለ ሆኖ ወደ መሬት ሲወርድም እንቅፋቶች ሊያጋጥሙት ይችላሉ።
በርግጥ በየትኛውም ምክንያት የታጠቀ ኃይል ወጥ በሆነ ማዕከላዊ ዕዝ ስር ካልተዋቀረ ለአገር አንድነት ለሕዝቦች ሰላምና ደህንነት ፈተና አይሆንም ብሎ ማሰብ በየዋህነት ብቻ የሚገለጽ አይደለም። ብሔራዊ አደጋን በአግባቡ ያለማጤን ትልቅ ፈተናን አቅልሎ ማየት ጭምር ነው። ይህ ደግሞ የቱን ያህል ዋጋ ሊያስከፍ እንደሚችል በአገሪቱ ሰሜናዊ ክፍል ከተካሄደው ጦርነት በላይ ማሳያ ሊሆን የሚችል ሌላ አንዳች ነገር አይኖርም።
በጠንካራ መሠረት ላይ የቆመች አገር ለመመስረት ጠንካራ የመከላከያ እና የጸጥታ ሰራዊት መገንባት ወሳኝ ነው። የትኛውም አገር ይህንን እውነታ ታሳቢ በማድረግ በእነዚህ ተቋማት ላይ የማያቋርጥ የሪፎርም ሥራዎችን ይሠራሉ። በእኛም አገር ከለውጡ ማግስት ጀምሮ እየሆነ ያለው ይኸው ነው።
አገሪቱን እንደ አገር በጠንካራ መሠረት ላይ ማቆም የሚያስችል አሻጋሪ ተቋማትን መፍጠር ሲቻል ነው። ይህ ደግሞ ከለውጡ ማግስት ጀምሮ ተግባራዊ እየሆነ ነው፤ ይህ የተቋማት ሪፎርም ነው ዛሬ ላይ አገርን ከብዙ ፈተናዎች ታድጎ፤ ብዙ ሲሟረትባት ከነበረችበት ሟርትና የጥፋት ድግሶች ወጥታ ጸንታ መቆም ያስቻለው።
በየትኛውም አገር ተሞክሮ መረዳት እንደሚቻለው፤ መሣሪያ ታጥቆ መንቀሳቀስ የሚችለው የሕግ ድጋፍ ያለው አካል ብቻ ነው፤ የመከላከያ እና የጸጥታ ተቋማት። በአንድ አገር ውስጥ ከእነዚህ ውጪ የታጠቀ ኃይል የመኖሩ ጉዳይ አገሪቱን ለተለያዩ ስጋቶችና ተጨባጭ አደጋዎች መጋበዙ የማይቀር ነው።
በእኛም አገር በተለይ ከክልል ኃይሎች ጋር በተያያዘ የነበረው እውነታ ከዚህ የተለየ አይደለም። ይህ ኃይል አገሪቱ በአስቸጋሪ የህልውና ስጋት ውስጥ በነበረችበት ወቅት የሕይወት መስዋዕትነት በመክፈል በደሙ ታሪክ የጻፈ ኃይል ነው። በዚህም በመላው ሕዝባችን ትልቅ ከበሬታና እውቅና የተቸረው ነው።
ይህም ሆኖ ግን ከተደራጀበት መንገድና የሕግ ድጋፍ የሌለው ከመሆኑ አንጻር፤ ቀጣይነት እንዲኖረው ለማስቻል በመንግሥት በኩል በአዲስ መልክ የሚደራጅበትና በተሻለ ተልዕኮና የማስፈጸም አቅም ወደ ሥራ የሚገባበት ሁኔታ እየተመቻቸ ነው።
በአገራችን ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት ማስፈን መቻል የጀመርነውን ልማት በሚፈለገው ፍጥነት እና ጊዜ ተግባራዊ ለማድረግ ትልቅ አቅም ነው። ይህን እውን ለማድረግ ደግሞ በመከላከያና በጸጥታ ተቋማት ላይ የተጀመረው ሪፎርም ወሳኝ ነው።
ይህ ሪፎርም እንደ አገር ያሉብንን ዓለም አቀፍና አካባቢ ስጋቶች በአግባቡ ከመቆጣጠር አንጻር ፋይዳ ያለው፤ ብሔራዊ ጥቅሞቻችንን ከማስጠበቅ አንጻርም እንደ አንድ ትልቅ አቅም ተደርጎ የሚወሰድ ነው፡፡
ሪፎርሙ ከተጀመረ አንስቶ እየተካሄዱ ያሉ ተግባራት ተቋማቱን በተልዕኮ፣ በሰው ኃይል እና በቴክኖሎጂ በተሻለ መልኩ ለማደራጀት እየተደረገ ያለው ጥረት በብዙ መልኩ ውጤታማ እንደሆነ ይታመናል። አሁን ላይ አገሪቱን ከተለያዩ ስጋቶች መታደግ አስችለዋል፡፡
ምክትል ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም አበባው ታደሰ በግልጽ ለማሳየት እንደሞከሩት፤ የክልሎች ልዩ ኃይሎች በሙሉ የክልላቸውን ፀጥታ ይጠብቁ ነበር፤ ከመከላከያ ኃይሉ ጋር አብረው ቆስለዋል፤ ደምተዋል፤ ሞተዋል። ይህ ኃይል ይህንን የመሰለ ትልቅ ማንነት አለው።
ለእነዚህ ኃይሎች ደግሞ ሕገመንግሥቱ እውቅና አይሰጣቸውም። እውቅና የሚሰጠው አንደኛ ለመከላከያ፤ ሁለተኛ ለፌዴራል ፖሊስ፤ ሦስተኛ ደግሞ ለክልል መደበኛ ፖሊስ ብቻ ነው። ከዚህ የተነሳም ሕጋዊ መስመር መያዝ አለበት። ወደ ሕጋዊ መስመር እንዲገባ መደረግ አለበት።
ሌላው ችግር የልዩ ኃይሉ አገነባብ ብሔር ተኮር መሆኑ ነው። ብሔር ተኮር ሲባል ኦሮሞው ‹‹ለኦሮሞ ሕዝብ እሞታለሁ›› የሚል፣ የሶማሌው፣ የአፋሩ፣ የአማራው፣ የሲዳማው፣… በተመሳሳይ የሚልበት አካሄድን የሚፈጥር ነው፡፡ ይህ ማለት ‹‹የሌላው ብሔር ጉዳይ ›› ጉዳዬ አይደለም የሚል መንፈስን ስለሚላበስ ሂደቱ የሕዝቦችን አንድነት የሚጎዳ ነው።
ከዚህም በላይ አደረጃጀቱ የአገሪቷን የፖለቲካ መፍቻ መንገድ አበላሽቷል። በእኛ አገር ፖለቲካና ጉልበት የሰጠው ሕገመንግሥቱ በሕዝብ ለተመረጠ መንግሥት ብቻ ነው። ስለዚህ የክልል ልዩ ኃይል ፖለቲከኛው በሀሳብ ማሸነፍ ሲያቅተው ሌላ በትር ዕድል ሰጥቷታል። ሁለት ዓመት ሙሉ በጦርነት የቆየነው በዚህ ምክንያት ነው።
ይህ ኃይል ከዚህ በከፋ መልኩም ለአገርና ለሁሉም ሕዝቦች የሚሞተውን መከላከያ ሰራዊት መገዳደር የቻለበት ሁኔታ ተፈጥሯል። ይህ ደግሞ ከአገርና ከሕዝቦች ሰላምና ደህንነት አንጻር ምን ማለት እንደሆነ ለመገመት አይከብድም።
የመንግሥት ውሳኔ ትልቅና ኃላፊነት የተሞላበት፤ ከልዩ ኃይሉ ጋር ሲነሱ የነበሩና አሁንም የሚነሱ ተገቢ ጥያቄዎችን መመለስ የሚያስችል ነው፡፡ በእነዚህ አደረጃጀቶች ውስጥ የነበረው የሰው ኃይል የተሻለ አገራዊ ኃላፊነት ወስዶ ውጤታማ የሚያደርገውን አቅም እንዲላበስ የሚያደርግ ነው። ይህ ሂደት አገራዊ እፎይታን እንጂ ስጋት ሊፈጥር የሚችል አይደለም።
አሁን ላይ የመንግሥትን ውሳኔ በመቃወም ላይ የሚገኙ ኃይሎች፤ የአገርን ሉአላዊነት ጉዳያቸው ያልሆኑ አክራሪ ብሔርተኞች እና ጽንፈኞች ናቸው፡፡ ጩኸታቸውም ግብ ያደረገው የአገሪቱን የመከላከያ እና የጸጥታ ኃይሎች አቅም በመገንባት ዘላቂ ሰላም ለማስፈን የሚደረገውን አገራዊ ጥረት ለማደናቀፍ ነው።
ዶክተር ጀኔኑስ
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 5 ቀን 2015 ዓ.ም