“ነገርን ከሥሩ…፤
የዚህ ጽሑፍ ዋና ርዕስ ቀድሞ ካልተብራራ በስተቀር ቢያንስ ሁለት መሠረታዊ ጉዳዮች እየተመዘዙ ሊያከራክሩ እንደሚችሉ እንገምታለን። “ጥንታዊ” ተብሎ “ዘመናዊ ዴሞክራሲ” መባሉ ተቃርኗዊ (Paradox) ይሉት ዓይነት ጥያቄ አያጭርም ወይ? በአሟጋችነቱ የተገመተ የመጀመሪያ ስጋት ነው። “ጥንታዊ ሲባልስ የዘመን ወሰኑ ወደ ኋላ ምን ያህል ያፈገፍጋል? ጥርት ያለ የዘመናዊ መስፈርትስ ምንድን ነው?” እነዚህ ጥያቄዎች መመለስ የሚገባቸው በዚህ ጽሑፍ ዐውድ መሠረት ስለሆነ በአጫጭር ብያኔዎች ቀድመን ይዘታቸውን መወሰኑ አስፈላጊ መስሎ ታይቶናል፡፡
ጥንታዊ፡- የሚለው ቃል የሚወክለው የዛሬ መቶ ዓመት ግድም የነበረውን የንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱን ዘመነ መንግሥት ነው፡፡ “ዘመናዊ ዲሞክራሲ” መሰኘቱ ደግሞ የዛሬው “ዘመናይ ፋሽን ተከታይ ዴሞክራሲያችን” ከፖለቲካችንና ከሕዝባችን ጋር በየውሎ አምሽቶው ሲጋጭ እንደምናስተውለው ሳይሆን የዚያ ዘመን የሕዝብ ጥያቄዎችና መንግሥታዊ ውሳኔዎች የተስተናገዱበትን “ነባር ጥበብ” ለማስታወስ በማስፈለጉ ነው፡፡
ወደ ዋናው መዳረሻችን ከመገስገሳችን አስቀድሞ ከምንተነፍሰው ዓየር ባልተናነሰ በየሴኮንዱ ስሙን እያነሳን የምንጥለውን “ዴሞክራሲ” የሚለውን የተውሶ ጽንሰ ሃሳብ በዕድሜው ርዝመት “የጃጀና ያፈጀ” ሊባል እንደሚችል አስታውሶ ማለፉ ተገቢነት ይኖረዋል፡፡
ከጥንታዊቷ ግሪክ የፖለቲካና የፍልስፍና ማህጸን ውስጥ “ነፍስ ዘርቶ” እስከ ዓለም ዳርቻ የተበተነው “ዴሞክራሲ” የሚለው ቃል ከሁለት መንታ መሠረታዊ ቃላት የተዋቀረ ነው፡፡ ዴሞስ (dêmos) የሚለው አንዱ ጽንሰ ሃሳብ ተራና ሠርቶ በሌ የሆኑ የግሪክ ዜጎችን ለማመልከት ሲሆን፤ ክራቶስ (krâtos) የሚለው ሁለተኛው መንትያው ደግሞ ኃይል ወይንም ብርታትን (force/might) ይወክላል፡፡ በአጭሩ ሁለቱ ቃላት ሲገጣጠሙ “የሕዝብ ኃይል/ብርታት” የሚለውን ሃሳብ መሸከሙን እናረጋግጣለን። አንዳንዶች “የሕዝብ አስተዳደር” የሚል አፈንጋጭ ፍቺ ሲሰጡትም እያስተዋልን ነው፡፡
ቅድመ ልደተ ክርስቶስ (508 ዓ.ዓ) የኖረውና በአቴናዊያን ሕገ መንግሥት ሪፎርም ላይ ደማቅ አሻራውን ያሳረፈው ክሊስተንስ (Cleisthenes) የጥንታዊቷ ግሪክ/አቴንስ የዴሞክራሲ አባት እየተባለ በታሪካቸው ይዘከራል፡፡ ፈረንሳይና አሜሪካን ደግሞ “የዘመናዊ ዴሞክራሲ” ቀዳሚ ተለማማጆች እየተባሉ ይጠቀሳሉ፡፡ “ዘመናዊነት” በምን መስፈርት? የየሀገራቱ ፖለቲከኞችና እኛ የሩቆቹ ዘመናዊነትን የምንበይነው ለየቅል ስለሆነ አንባቢው የራሱን ድንጋጌ ቢሰጥ የተሻለ ይሆናል፡፡
ታሪክ ቢያረጅም፤ አሻራው አይደበዝዝም፤
ወደ ራሳችን ጉዳይ መለስ የምንለው ከታሪካችን ዘርፈ ብዙ ጉዳዮች መካከል አንድ መሪ ሃሳብ ቃል በቃል በመጥቀስ ይሆናል፡፡ የታሪካችን መሰዊያ “ፍምም አመድም” እንዳለው እሁድ ሚያዝያ 1 ቀን 2015 ዓ.ም በዚሁ አንጋፋ ጋዜጣ ላይ በጻፍኩት ጽሑፍ ውስጥ በዝርዝር ማብራራቴን ልብ ይሏል። እንቀጥል። “በ1909 ዓ.ም መስከረም 17 ቀን ሕዝብ ተሰብስቦ አቤቶ
ኢያሱን ሽሮ ከመንግሥት ባስወጣቸው ጊዜ ወ/ሮ ዘውዲቱ ንግሥተ ነገሥታት ተብለው የአባታቸውን የዳግማዊ ምኒልክን ዙፋን እንዲወርሱ፤ እንዲሁም የሐረሩ ገዥ የልዑል ራስ መኮንን ልጅ ደጃዝማች ተፈሪ መኮንን (በኋላ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ) ‹ራስ› ተብለው አልጋ ወራሽና እንደራሴ እንዲሆኑና የመንግሥቱን ሥራ እንዲፈጽሙ የሕዝቡ ጉባዔ ወሰነ፡፡” (የታሪክ ማስታወሻ፤ ደጃዝማች ከበደ ተሰማ፤ ገጽ 32)፡፡ “ሕዝበ ውሳኔ” የሚለው ገለጻ “በዘመናዊ የዴሞክራሲ” ዲስኩር ውስጥ ተደጋግሞ እንደሚነሳ አንባቢው ልብ ይበል፡፡
ዳግማዊ አጼ ምኒልክ ኢትዮጵያን ለ46 ዓመታት ያህል ከመሩ በኋላ አካልን ሽባ በሚያደርግ (ፓራላይዝድ) በሽታ ተለክፈው አልጋ ላይ በዋሉበት ወቅት የመንግሥታቸው ወራሽ እንዲሆኑ የመረጡት የ12 ዓመቱን የልጃቸውን ልጅ ኢያሱን ነበር፡፡ ከእርሳቸው ህልፈት በኋላም መንበረ ሥልጣኑን የተረከቡት አቤቶ ኢያሱ የዘመኗን “ታላቅ ሀገር ኢትዮጵያን” በአግባቡ ለመምራት ልጅነትና ቅብጠት ፋታ ስላልሰጧቸው ከላይ እንደተገለጸው ሹም ሽር ተካሂዶ ሥልጣነ መንግሥቱ የተሸጋገረው ወደ ንግሥት ዘውዲቱ ነበር፡፡
“ወይ ያለመታደል!” እንዲሉም ከኢያሱ ወደ ዘውዲቱ የተላለፈው መንበረ ሥልጣን እንደ አባታቸው ዘመን በአንፃራዊ መልኩም ቢሆን የረጋና የተረጋጋ መሆን አልቻለም ነበር፡፡ ንግሥቲቱ ሥልጣን ላይ በወጡ በወሩ የልጅ ኢያሱ ወላጅ አባት ንጉሥ ሚካኤል “እንዴት በልጄ ዙፋን ላይ መፈንቅለ መንግሥት ይደረጋል?” በማለት ከወሎ ግዛታቸው ጦራቸውን እየሰበቁ ሠራዊታቸውን ወደ መሃል ሀገር በማዝመት መጀመሪያ ኮረማሽ ላይ በተደረገው ውጊያ በለስ ቀንቷቸው ነበር። ወደ ፊት በመገስገስም ዙፋን ለመናድ ሰገሌ ላይ ጥቅምት 17 ቀን 1909 ዓ.ም በተደረገው ውጊያ ተሸንፈው እጃቸው መያዙ በታሪካዊ ሰንዶቻችን ላይ በግልጽ ሰፍሯል፡፡
በዚሁ ጦርነት ላይ እርስ በእርስ ሲዋጉ የወደቁት ታላላቅ የጦር መሪዎችና ለፎው (ተርታው) ሠራዊት ቁጥራቸው ቀላል የሚባል አልነበረም፡፡ ደግሞም እኮ በመገዳደልና በመጠፋፋት ማን እኛን ይስተካከላል? ለመሆኑ በእርስ በእርስ ፍልሚያ ሞት ያላዘመርንበት ሥርዓተ መንግሥት ይኖር ይሆን? በግሌ እንጃ፡፡
ለማንኛውም ምርኮኛው ንጉሥ ሚካኤል እጃቸው ተይዞ አልጋ ወራሹ ባሉበት ወደ ንግሥት ዘንድ ሲቀርቡ አቀባበል የተደረገላቸው ንግሥቲቱና አልጋ ወራሹ አክብሮታቸውን ለመግለጽ እንደቆሙ “ጌታችንና አባታችን እንደምን ወደዚህ ስህተትሊገቡ ቻሉ?” በሚል ቁጭት አክብሮታቸው ዝንፍ ሳይልና የወጉና የማዕረጉ ክብር ሳይጓደልባቸው ነበር፡፡ የዚያን ወቅት መሪዎች የነበራቸው የልብ ስፋት ምን ያህል ታላቅ እንደነበር ጥሩ ማሳያ ይሆናል፡፡
ከንጉሥ ሚካኤል ጋር የተደረገው ጦርነት ካበቃ ከስድስት ወራት በኋላ “የመሐል ሠፋሪ” በሚባለው የጦር ክፍል ቆስቋሽነት ከፍ ያለ አድማ ተከናውኖ ነበር። ሰበበ ምክንያቱ በታሪካችን በርካታ መዛግብት ውስጥ እንደሚከተለው ተጠቅሶ ይነበባል፡፡ “ደጉ ንጉሣችን አጼ ምኒልክ 12 ሚኒስትሮችን መርጠው ቢሾሙልን ለሀገር ልማት፣ ለሕዝብ አንድነት በመምከር ፈንታ አንዱ ለአንዱ የየራሳቸውን ጥቅም በመመልከት ሀገሩን አበላሹት እንጂ ለመንግሥት የጠቀሙትና የሠሩት ጉዳይ የለም፡፡”
በክሱ ውስጥ ከተዘረዘሩት ዋና ዋና ማሳያዎች መካከል ሁለቱ ክሶች እንደሚከተለው ተመዝግበዋል። “የሥራ ሚኒስትር ተብሎ የተሾመው የራሱን ቤት ለመሥራት በቤት ላይ ቤት እየቀጠለ (ፎቅ ለማለት ሳይሆን አይቀርም) ወደ ሰማይ ለመውጣት ይገሰግሳል። እንደዚሁም የግቢ ሚኒስትር የተባለው የራሱን ሀብት ብቻ በማደራጀቱ ከምኒልክ ቤት ለግብር የሚሆን መሰናዶ ታጥቶ ባለፈው ሰሞን ከእርሱ ቤት ዱቄት ተግዞ ተሠናዳ፡፡ 12ቱ ሐዋርያት ተብለው ‹በምኒልክ› የተሾሙት ሚኒስትሮች በሙሉ 12 አጋንንት ሆነው አረፉት፡፡ የአድመኞቹ ጥያቄ ፈጣን መልስ አግኝቶ ከ12ቱ ሚኒስትሮች መካከል የጦር ሚኒስትሩ ፊታውራሪ ኃብተ ጊዮርጊስ ብቻ ሲቀሩ አሥራ አንዱ ተሽረው ወደ ርስት ሀገራቸው እንዲሄዱ ተወሰነና እየታዘዙ ሄዱ” (የታሪክ ማስታወሻ ገጽ 57 – 63)፡፡
“የሕዝብ ድምጽ፤ የእግዜር ድምጽ” ይሏል እንዲህ ነው፡፡ ይህንን መሰል ከባድ የሕዝብ ጥያቄ ሳይውል ሳያድር የዛሬዎቹ ዘመናይ “የዲሞክራሲ መንግሥታት” መሪዎች በዚህ አግባብ ጨክነው የሕዝባቸውን እምባ ለማበስ ይችሉ ይሆን? መልሱን ለመስጠት አንባቢው ከራሱ ጋር ቢሟገት የሚሻል ይመስለናል፡፡ በዚህ ጸሐፊ እምነት ግን ይህ ድርጊት እጅግ ዘመናዊ የዴሞክራሲ እርምጃ እንደሆነ ከልቡ ያምናል፡፡
ከዚሁ ከሚኒስትሮች ሽረትና ሹመት ጋር የተገናኘው ዋና ጉዳይ የአማካሪዎች አስፈላጊነት ነበር። ታሪኩ እንዲህ ይጠቀሳል፡- “በዓለም ያሉ ነገሥታት ሁሉ ይልቁንም ከሚኒስትሮች ሌላ መካር (አማካሪ) የሚያስፈልግ መሆኑ ስለሚታመንበት ከየሀገሩ ሽማግሌ 300 እና 500 የሚሆኑ የሀገር ጨዋ ተመርጠው ይሾሙ ነበር፡፡” ዴሞክራሲያችን ሆይ ትሰማለህ? “መካሪ የሌለው ንጉስ ያለ ዓመት አይነግሥ!” የሚለውን የብሂላችንን ሥጋት የተሻገረ አመራር ይሏል እንዲህ ነው፡፡
ብዕረ መንገዳችንን የአማካሪዎች ወሳኝ ሚና የተስተዋለበትን አንድ ታሪካዊ አጋጣሚ ጠቅሰን እንለፍ። ደጃዝማች ባልቻ አባነፍሶ የሲዳሞ ገዥ በነበሩበት ወቅት ሎሌዎቻቸው እየከዱ ወደ ልዑል አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንን መግባታቸውን ያስተዋሉት አንጋፋው አርበኛ መገፋታቸውን ለመበቀል በማሰብ ከሲዳሞ ግዛታቸው እየተንደረደሩ አዲስ አበባ ቤታቸው ይገባሉ። ነገረ ሥራቸው ሁሉ ለደግ ያለመሆኑን የጠረጠሩት የመንግሥቱ አማካሪዎች ክፉኛ የተቆጡትንና አዲስ አበባ በሚገኘው ቤታቸው ሸፍተው በራቸውን ከውስጥ በመቆለፍ ያገነገኑትን አዛውንት በኃይል ርምጃ እልሃቸውን ለማብረድ ከመሞከር ይልቅ ውጥረቱ እንዲፈታ የተደረገው በሚከተለው ጥበብ የተሞላበት አያያዝ ነበር፡፡
“ደጃዝማች ባልቻ ከሲዳሞ ጦራቸውን አስከትለው አዲስ አበባ ከገቡ በኋላ እቤታቸው በመሸፈት ቢጠሯቸው አልመጣም ብለው በእምቢታቸው ጸኑ። …ቤተ መንግሥቱ ውስጥ ብዙ ሽማግሌ አማካሪዎች ተሰብስበው ነገሩ በእርጋታ እንዲታሰብበት እንጂ የእሳቸውን ድርጊት ተከትሎ የኃይል ርምጃ እንዳይወሰድ ተመከረና ጉዳዩ በርጋታ ተያዘ፡፡” – ይህን መሰሉ መንግሥታዊ እርምጃ ከፍ ያለ የብስለት ደረጃ የተስተዋለበት እንጂ ሌላ ምን ስያሜ ሊሰጠው ይችላል?
የደጃዝማች አባውቃው ብሩ ታሪክም ቢጠቀስ ጠቃሚ እውቀት ሊያስጨብጥ ስለሚችል ቆንጥረን እናስታውስ፡፡ የቤተመንግሥቱ የዘበኞች አለቃ (በቀድሞ አጠራር የክብር ዘበኛ፤ በዛሬው የእኛ ዘመን ሪፐብሊካን ጋርድ እንደምንለው) የነበሩት አባውቃው ብሩ አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንን የንግሥት ዘውዲቱን ሥልጣን ለመገልበጥ ውስጥ ለውስጥ ያሴራሉ የሚለውን ሃሜት እንደ አውነት በመቁጠር ሊፋለሟቸው ይነሳሉ፡፡ ይህ የመጠፋፋት ዝግጅት ወሬ የደረሳቸው ንግሥቷና አልጋ ወራሹ ራሳቸው “ሃሜቱ ሀሰት መሆኑን” ለማስረዳት በተደጋጋሚ ሽማግሌዎችን ከአባውቃው ዘንድ በመላክ ነገሩን ለማርገብ ቢሞክሩም ሊሰሟቸው አልወደዱም። በመሆኑም ንግሥቲቱ ሊወስዱ የተዘጋጁበት እጅግ አስገራሚና አስደናቂ ውሳኔ እንዲህ ተመዝግቧል፡፡
“…ንግሥትም የክብርን ነገር ሳይመለከቱ የጊዜውን ጸጥታ መጠበቅና ደም የሚያፋስስ ነገር እንዳይደርስ በማሰብ አባውቃው ወዳሉበት ሥፍራ ለመሄድ ታጥቀው ተነሱ፡፡… ከንግሥት ከራሳቸው ቃል ካልሰማሁ ካለ በዚህ ምክንያት ተኩስ ተነስቶ ደም ከሚፈስ የንግሥት መሄድና ነገሩን ማብረድ መልካም ሃሳብ ነው፤ ሲሉ ሽማግሌዎቹ አማካሪዎችም ተስማሙ፡፡”
ታሪኩ እጅግ ረጅምና ውስብስብ ስለሆነ የተጠቀሰው ጥቂቱ ብቻ ነው፡፡ ውሳኔውን የሰሙት አልጋ ወራሹ ማፋረሻ ምክንያት በመስጠት ንግሥት ዘውዲቱ ወደተባለው አማጺ ዘንድ ባይሄዱም ውሳኔያቸው ግን እጅግ የሚያስገርምና የሚያስደንቅ ነበር፡፡ “ለክብሬ ብዬ የንጹሐን ደም እንዲፈስ ስለማልፈልግ እኔው ራሴ ሄጄ ነገሩን አበርደዋለሁ…” ዋው! እንደምን ብስለትና ርህራሄ የተስተዋለበት ውሳኔ ነበር፡፡
ብዙ መሰል ተግዳሮቶች የተስተናገዱበትን የዚያን “የጥንታዊ ዘመን” ሀገራዊ ፈተናዎች “የዛሬይቱ ዘመናይ ኢትዮጵያ” ልቧን ከፍታና ታሪኳን አክብራ ብዙ ጥበቦችና እውቀቶች መማር ብትችል በእጅጉ የምታተርፍ ይመስለናል፡፡ በከባድ አውሎ ነፋስ በሚንገላታ ጀልባ የምትመሰለው ሀገሬ፣ በነጋ በጠባ ቁም ስቅሏን ስታይ መመልከት የእኛን የዜጎቿን ልብ በሀዘን መስበሩ፤ እርሷም ዕድሏ ባሸከማት ዕጣ ፈንታ ጎብጣ ቀና ማለት ያለመቻሏ ለእኛ ብቻ ከፈጣሪ የተወሰነብን ፍርጃ እስኪመስል ድረስ እነሆ እህህ እንዳልን ዘመናችንን በመግፋት ላይ ነን፡፡
ቢቻልና ቢሆንልንማ ኖሮ የጥንት ጥንት ግሪካዊያን ያወረሱንን “ካብ አይገባ የጃጀ ዴሞክራሲ የሙጥኝ ብለን እየተደናቆርን” ዕድሜያችንን በሀዘን ከምንገፋ ይልቅ “የተውሶውን ፍልስፍና” ሰንዱቅ ውስጥ በመቆለፍ ከሀገር በቀል ታሪኮቻችንና እወቀቶቻችን ጥበብ እየቀዳን መከራችንን ብናቀለው በእጅጉ በተጠቀምን ነበር፡፡ እስከ መቼስ መንግሥት ወዲያ ማዶ፤ ሕዝብ ወዲህ ማዶ ሩቅ ለሩቅ ቆመው እየተያዩ በተመሳሳይ የጋራ ሀገራዊ አጀንዳ ላይ አብሮ ከመጓዝ ይልቅ መጓተት እየመረጥን እንደተገፋፋን ዘመናችንን እንጨርሳለን? ኢትዮጵያ ሆይ መከራችን ለአንቺም ሆነ ለእኛ ለዜጎች ስለማይጠቅመን አንቺም ወደ ቀልብሽ ተመለሺ፤ እኛም ወደ ሩሐችን እንመለሳለን፡፡ ጽናቱን ይስጥሽ ሀገሬ! ሰላም ለሕዝባችን ለዜጎችም በጎ ፈቃድ።
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 4/2015