ላለፉት አስርት ዓመታት በሀገሪቱ የሚገኙ ክልሎች የራሳቸውን ልዩ ኃይል ሲያደራጁና ሲያስታጥቁ ቆይተዋል። ይህንንም ተከትሎ ተግባሩ በዜጎች ዘንድ የተለያዩ ትርጓሜዎች ሲሰጠው ቆይቷል፡፡ አንዳንዶች ልዩ ኃይሉ የአንድን ክልል ሕዝብ ደህንነት ለማስጠበቅ ከፖሊስ ባሻገር ከፍተኛ አስተዋጽኦ ሊያበረክት እንደሚችል ሲሞግቱ ፣አብዛኞች ግን ከፍያሉ የደህንነት ስጋቶችን የመመለስ ስራ የመከላከያ ሰራዊት ነው በሚል አደረጃጀቱን ሲሞግቱ ቆይተዋል።
ለዚህ ሃሳባቸው ማጎልበቻም አደረጃጀቱ ህገ መንግስታዊ መሰረት የሌለው ፤የሚያካሂዳቸው ተግባራት በሙሉ ሕጋዊ መሰረት የሌላቸው መሆኑን በመግለጽ፤ ችግሩ ከህጋዊነት ባለፈም ለአገር ደህንነት ስጋት ሊሆኑ የሚችልበት እድል ከፍ ያለ መሆኑን ድምጻቸውን ከፍ አድርገው ሲጮሁ ተደምጠዋል፡፡
በተለይም ባለፉት አምስት አመታት /ከለውጡ ማግስት ጀምሮ/ የልዩ ኃይል ጉዳይ በተለያየ መልኩ ጎራ ፈጥሮ ሲያከራክርና ሲያጨቃጭቅ ቆይቷል። በእርግጥም እኔን ጨምሮ ብዙዎች የክልል ልዩ ኃይሎችን “መፍረስ” አለበት የሚል አቋም ይዘን እንደነበር የአደባባይ ሚስጥር ነው ። ዛሬ ላይ የልዩ ሀይሉን ዳግም በአዲስ መልክ በህጋዊ መልኩ መደራጀቱን የሚቃወሙ ሳይቀሩ “ልዩ ሀይል ይፍረስ” እያሉ ሲጮሁ እንደነበር ብዙ ብዙ ምስክር መጥቀስ የሚያስፈልገው እውነታ አይደለም።
በርግጥ የክልል ልዩ ሃይሎች የተደራጁበት ስነ ልቦና ያላቸው ቁመና ፣ ክልል ከክልል የነበራቸው ፉክክር በአገራዊ አንድነት ላይ ትልቅ ስጋት ሆነው እንዲታዩ እንዳደረጋቸው የሚካድ አይደለም።
ከዚህም ባለፈ አንዳንድ ክልሎች በልዩ ሀይል ስም ያደራጇቸው ሀይሎች ከአንዴም ሁለት ጊዜ የሀገርን ሕልውና አደጋው ውስጥ ከትተው እንደነበር ይታወሳል። ችግሩን ለመቀልበስ የተከፈለው ዋጋም የቱን ያህል ከፍ ያለ እንደነበር የሚዘነጋ አይደለም። ጠባሳውም ገና አላገገመም።
በአንዳንድ ክልሎች እነዚህ ሀይሎች የክልሉን መንግስት ከማገልገል ወጥተው ለግለሰቦች ፍላጎት ተገዝተው ሲንቀሳቀሱ ታዝበናል። አጠቃላይ እንቅስቃሴያቸው አገርን ወደ ዘመነ መሳፍንት የመመለስ ስጋት ይዞ እንደነበር በተጨባጭ አይተናል።
በርግጥ መንግስት በግልጽ ለማሳየት እንደሞከረው፤ የክልሎች ልዩ ኃይሎች በሙሉ የክልላቸውን ፀጥታ ይጠብቁ ነበር፤ ከመከላከያ ሀይሉ ጋር አብረው ቆስለዋል፤ ደምተዋል፤ ሞተዋል። ይህ ኃይል ይህንን የመሰለ ትልቅ ማንነት አለው። ይህንን በሙሉ ያከናወነው መከላከያው እያስተባበረውና እየመራው።
ከህገ መንግስት አንፃር ስናይ እነዚህ ኃይሎች ህጋዊ አይደሉም። ህገመንግስቱ እውቅና አይሰጣቸውም። ለክልል ኃይል የሚሰጠው መደበኛ ፖሊስን ብቻ ነው። ህገመንግስቱ የታጠቀን ኃይል የሚሰጠው አንደኛ መከላከያን፤ ሁለተኛ ፌዴራል ፖሊስ፤ ሶስተኛ ደግሞ የክልል መደበኛ ፖሊስ ነው። ከዚህ ውጭ ህገመንግስቱ መብት የሚሰጠው ታጣቂ ሀይል የለም። ከዚህ የተነሳ ይሄ ኃይል ህጋዊ አይደለም። ስለዚህ ህጋዊ መስመር መያዝ አለበት። ወደ ህጋዊ መስመር እንዲገባ መደረግ ይኖርበታል።
ሌላው ችግር የሀይሉ አገነባብ ብሄር ተኮር መሆኑ ነው። ብሔር ተኮር ሲባል ኦሮሞው ‹‹ለኦሮሞ ህዝብ እሞታለሁ›› የሚል፣ የሶማሌው፣ የአፋሩ፣ የአማራው፣ የሲዳማው፣… በተመሳሳይ የሚልበት አካሄድን የሚፈጥር ነው፡፡ ይህ ማለት የሌላው ብሄር ጉዳይ ጉዳዬ አይደለም የሚል መንፈስን ስለሚላበስ ሂደቱ የህዝቦችን አንድነት የሚሸረሽር ነው።
ከዚህም በላይ አዘገጃጀቱ የአገሪቷን የፖለቲካ መፍቻ መንገድ አበላሽቷል።በየትኛውም አገር፤ በእኛም አገር ህገመንግስት ፖለቲካና ጉልበት አብሮ አይሄድም። በእኛ አገር ፖለቲካና ጉልበት የሰጠው ህገመንግስቱ በህዝብ ለተመረጠ መንግስት ብቻ ነው። ስለዚህ የክልል ልዩ ኃይል ፖለቲከኛው በሃሳብ ማሸነፍ ሲያቅተው ለሌላ በትር እድል ሰጥቷታል። ሁለት ዓመት ሙሉ በጦርነት የቆየነው በዚህ ምክንያት ነው።
ይህ ሀይል ከዚህ በከፋ መልኩም ለአገርና ለሁሉም ህዝቦች የሚሞተውን መከላከያ ሰራዊት መገዳደር የቻለበት ሁኔታ ተፈጥሯል። ይህ ደግሞ ከሀገርና ከህዝቦች ሰላምና ደህንነት አንጻር ምን ማለት እንደሆነ ለመገመት አይከብድም።
ከዚህ አኳያ ቀደም ሲል ይነሱ የነበሩ ቅሬታዎችንም ሆነ መንግስት በጥናት የደረሰባቸውን ችግሮች ከግምት ውስጥ በማስገባት የክልል ልዩ ኃይሎችን ወደ ፌዴራልና የክልል ህጋዊ የፀጥታ መዋቅር ውስጥ ገብተው የአገር መከላከያን ማጠናከር አለባቸው የሚለው የመንግስት ውሳኔ ተገቢነት ያለው እንደሆነ አምናለሁ።
የለውጡ መንግስት እንደመጣ የመጀመሪያው እርምጃ ይህ ይሆናል ብዬ ጠብቄ ነበር። ይሁን እንጂ ባለፉት አምስት የለውጥ ዓመታት በተለያዩ ምክንያቶች አደረጃጀቱ እንደነበረ ሊቀጥል ችሏል። ነገር ግን ዘግይቶም ቢሆንም አሁን መንግስት የአብዛኛው ህዝብ ጥያቄ ለሆነው ለዚህ ሀገራት ችግር መፍትሄ ለመስጠት እንቅስቃሴ መጀመሩ የሚያስመሰግነው ነው። ውሳኔው የሀገሪቱን ሉዓላዊነትና የግዛት አንድነት መጠበቅ የሚያስችል አንድ ጠንካራ የተማከለ ሠራዊት መገንባት የሚያስችል ጥልቅ እርምጃ ይመስለኛል።
የመንግስት ውሳኔ ትልቅና ኃላፊነት የተሞላበት፤ ከልዩ ሀይሉ ጋር ሲነሱ የነበሩና አሁንም የሚነሱ ተገቢ ጥያቄዎችን መመለስ የሚያስችል ከመሆኑም ባለፈ፡፡ በእነዚህ አደረጃጀቶች ውስጥ የነበረው የሰው ኃይል የተሻለ ሀገራዊ ኃላፊነት ወስዶ ውጤታማ የሚያደርገውን አቅም የሚያላብሰው ነው። በዚህም አገራዊ እፎይታን እንጂ ስጋት ሊፈጥር የሚችል አይደለም።
በአገራችን ሲፈጠሩ ከነበሩ ችግሮችና ካሳለፍናቸው አስቸጋሪ ጊዜያት አኳያ ፤ የመንግስት ውሳኔ በመዘግየቱ ሊያነጋግር ከመቻሉ ባለፈ ተግባራዊ በመሆኑ ማንንም ሊጎዳና ስጋት ውስጥ ሊጨምር የሚችል አይደለም።እዚህ ላይ በአግባቡ ሊታይ የሚገባው የየትኛውም ኢትዮጵያዊ ሰላምና ደህንነት ዋንኛ አቅም/መተማመኛ የሀገሪቱ የመከላከያ ሀይል መሆኑ ነው።
እዚህ ላይ በግልጽ መታወቅ ያለበት አሁን ላይ የመንግስት ውሳኔ በመቃወም ላይ የሚገኙ ሀይሎች ፤የአገር ሉአላዊነት ጉዳያቸው ያልሆኑ አክራሪ ብሔርተኞች እና ጽንፈኞች ናቸው፤ ካልሆነም እነዚሁ ኃይሎች ባልተገባ መንገድ ግፍ ያደረሱባቸው ግለሰቦች ናቸው፡፡ ጩኸታቸውም ግብ ያደረገው የሀገሪቱን የመከላከያ እና የጸጥታ ሀይሎች አቅም በመገንባት ዘላቂ ሰላም ለማስፈን የሚደረገውን ሀገራዊ ጥረት ለማደናቀፍ ነው።
በአጠቃላይ የክልል ልዩ ሀይሎችን በአዲስ መልክ ለማደራጀት በመንግስት በኩል የተደረሰበትን ውሳኔ ተከትሎ የሚናፈሱ አሉባልታዎች የጥፋት ሀይሎች አጀንዳ መሆኑን ዜጎች ተገንዝበው፤ ለነዚህ ሀይሎች ጆሮ መስጠት አይጠበቅባቸውም፡፡ መንግስትም ስራውን በጀመረው መንገድ ከህዝብ ጋር በመወያት ሰላማዊና ውጤታማ በሆነ መልኩ መፈጸም ይኖርበታል፡፡ ህዝብም የውሳኔውን ፋይዳ ከግምት በማስገባት ለውጤታማ ትግበራው ተገቢውን ትብብር ሊያደርግ ይገባል፡፡
ዳንኤል ዘነበ
አዲስ ዘመን ሚያዝያ 4 ቀን 2015 ዓ.ም