የሽግግር ፍትህ የቅርብ ጊዜ እሳቤ ሳይሆን ከዲሞክራሲ ውልደት ጋር አብሮ የተወለደ የፍትህና የስርዐት ትግበራ ነው።ከክርስቶስ ልደት ወዲያና ወዲህ በመሪና ተመሪ የአስተዳደር ስርዓት ውስጥ ከዲሞክራሲ ጋር መሳ ለመሳ የቆመ እንደነበር የኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲው ተመራማሪ ጆን ኤልስተርን ጥናት ጨምሮ ብዙ ማስረጃዎች ይጠቅሳሉ።
ሰብዐዊነትን አስቀድሞ ዲሞክራሲና መልካም አስተዳደርን ያስከተለው የሽግግር ፍትህ ጽንሰ ሀሳብ ከጥንት ዘመን አንስቶ እስከ አሁኑ ድረስ በብዙ አገራት በማቀንቀን ላይ ይገኛል።የሽግግር ፍትህ በአጭር አማርኛ ለመግለጽ ከሰላምና ወደ እርቅ የሚወስዱ የፍትህ እሳቤ ማለት ይቻላል።
የሽግግር ፍትህ በተለይ ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ማብቂያ ወዲህ በሰብዓዊነት ላይ የደረሱ ጉስቁልናዎችን እንደ መነሻ በመውሰድ እንደ አንድ የሰላምና የዲሞክራሲ አማራጭ ሆኖ በስራ ላይ ውሏል።
ጨቋኝ አስተዳደራዊ መዋቅርን የሚሞግት፣ ለሰብዐዊነት የቆመና ለፍትህ የሚወግን የሰላም ሽግግር ሂደት ነው።የነበሩና ያሉ ፖለቲካዊና ማህበራዊ ችግሮችን አይቶና ተረድቶ ለፍትህ የሚያቀርብ የተጠናና የተፈተሽ አሰራር ነው።
አገርና ህዝብ በተጎዱበት የፖለቲካ ስርዐት ላይ በዳዮችን ተጠያቂ እያደረገ ተበዳዮችን ፍትህ እንዲያገኙ የሚሰራ ነው።በጦርነትና በእርስ በርስ ግጭቶች፣ በዘርና በብሄር፣ በሌላም መሰል አለመግባባቶች ውስጥ የሚደርሱ ሰብዐዊ የመብት ጥሰቶች ተገቢውን ፍርድ እንዲያገኙ ለመብት ጥበቃ ቅድሚያ የሚሰጥ ነው።
ይሄን አስመልክቶ የህግ ባለሙያው አምሀ መኮንን እንዲህ ይላሉ ‹የሽግግር ፍትህ አንድ ስርዐት ወደሚታሰብ ሌላ አዲስ ሰላማዊና ዲሞክራሲያዊ ስርዐት የሚደረግ ሽግግር ነው።በዚህ ሽግግር ውስጥ የሚታዩ የከፋ የመብት ጥሰቶች እንዴት ይዳኙ የሚለው ምላሽ በሽግግር ፍትህ አለ።
ከሰሞኑ በመዲናችን አዲስ አበባም በሽግግር ፍትህ አማራጭ ሀሳቦች ዙሪያ የሚመክር አገር አቀፍ ጉባኤ ተካሂዷል።ውይይት የተካሄደው ከሲቪል ማህበራት፣ ከመገናኛ ብዙሃንና የዲሞክራሲ ተቋማት ጋር ሲሆን በጉባኤው ላይ ቀጣዩን የአገራችንን ዘላቂ ሰላም በተመለከተ ሐሳቦች ተንሸራሽረዋል።
መሰረታዊ የሽግግር ፍትህ በኢትዮጵያ እስከዛሬ ለተፈጸሙ ጉልህ በደሎች እውቅና መስጠት፣ ተጠያቂነትን ማስፈን እንደዚሁም ተጎጂዎችን መካስና ሌሎች ተመሳሳይ የሰብዐዊ መብት ጥሰቶች እንዳይፈጸሙ እንደሚያስችል መተማመን ላይ ተደርሷል።
የፍትህ ሚኒስቴር በቅርቡ ይወጣል ባለው የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ካስቀመጣቸው የማስፈፀሚያ ስልቶች ውስጥ ቀዳሚው ክስ ነው።ወንጀልን በመመርመርና በምርመራ ውጤቱ ላይ እንዳስፈላጊነቱ ክስ መመሰረት ቀዳሚ ስልት ሆኖ ተቀምጧል።የክስ ስልት እንደ ቀዳሚ መስፈር ሆኖ መቀመጡ ተጠያቂነትን ለማስፈን መሆኑ ግልጽ ቢሆንም ከዚህ በተጓዳኝ ፍትህ በማምጣት ሂደት ላይም የጎላ ሚና ስላለው ጭምር ነው ።
ሌላኛው የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ማስፈጸሚያ ስልት ሆኖ የተቀመጠው እውነትን ማፈላለግና የተገኘውን እውነት ይፋ ማድረግ ነው። ከዚህ ጋር በተያያዘ እርቅ፣ ምህረትና፣ የገንዘብ ወይም ሌሎች ካሳዎችም በዚህ ማስፈጸሚያ ስልት ውስጥ ተጠቃለዋል።
ከላይ ያየናቸው የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ማስፈጸሚያ ስልቶች ችግሮቻችንን ሽረው ዘላቂ መፍትሄ አማጭ እንደሚሆኑ እናምናለን።እንደአገር የተሸከምናቸውን የነውጥ እና የጦርነት ሀሳቦችን አርግበው የቀና መንገድ ያመላክቱናል ስንል ተስፋ እናደርጋለን።
የፍትህ ሚኒስቴር የሽግግር ፍትህ የፖሊሲ አቅጣጫ አማራጮች በሚል ርዕስ ባወጣው ባለ 37 ገጽ ሰነድ ላይ ‹ከእርስ በርስ ጦርነት፣ ግጭትና ጭቆና በመውጣት በፖለቲካና በዲሞክራሲ ስርዐት ግንባታ ውጤታማ ሽግግር ለማድረግ በሞከሩ አገራት የሽግግር ፍትህ ሂደቶች ተግባራዊ ተደርገዋል› ብሏል።
በዚህ የሽግግር ፍትህ የተጠቀሙ እንደ ሩዋንዳ እና ደቡብ አፍሪካ የመሳሰሉ አገራትን መጥቀስ ይቻላል።ሩዋንዳ ውስጥ የተፈጠረውን የእርስ በርስ የጎሳ ግጭት ለማስቆምም ሆነ ተጠያቂነትን ለማስፈር የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ እንደአንድ የመፍትሄ አካል ተወስዷል።
በግጭቱ ተጠያቂ የሆኑ አካላትን በመጠየቅና ለፍርድ በማቅረብ እንዲሁም ደግሞ የደረሱ የሰብዐዊ መብት ጥሰቶችን እንደየ አስፈላጊነታቸው ፍትህ እንዲያገኙ በማድረግ የሽግግር ፍትህ የበረታ አስተዋጽኦ ነበረው።በዚህ ብቻ አላቆመም የትላንቱን ዓይነት መሰል የዘርና የጎሳ ግጭቶች እንዳይነሱ በእርቅና በተግባቦት ላይ የተመሰረተ የአንድነት መንፈስም አቀዳጅቷቸዋል።
በደቡብ አፍሪካም ሆነ በሌሎች የዓለም አገራት ተመሳሳይ ነገር ነው የታየው።እንደ አገር የተፈጠሩባቸውን ፖለቲካዊና ማህበራዊ ተግዳሮቶቻቸውን በሽግግር ፍትህ በኩል ነው ያለፉት።ሁሉንም ትተን የደቡብ አፍሪካን ተሞክሮ ብናይ እንኳን አገራችን ብዙ መማር ትችላለች።በአፓርታይድ ስርዓት በነጮች የበላይነት ስር የነበረውንና በዘርና በብሄር የተከፋፈለውን አፍሪካዊ ማንነት መስመር ያስያዘው የሽግግር ፍትህ ነው።
ደቡብ አፍሪካውያን እንደ ዜጋ ያጡትንና የተነጠቁትን ዲሞክራሲዊ መብቶቻቸውን ያስመለሱት በሽግግር ፍትህ በኩል ነበር።የዚያን ዘመን የነጮች ጭቆናና የመብት ረገጣ በይቅርታና በቅጣት፣ በካሳና በእርቅ አልፈው ዛሬ ላይ አዲሷን ደቡብ አፍሪካ መፍጠር ችለዋል።
ይሄን መሰል አጋጣሚ አገራችን ራሷን እንድትፈትሽ ዕድል የሚሰጣት ነው።ከሩዋንዳና ከደቡብ አፍሪካ ልምድ በመውሰድ የነበሩና ያሉ ችግሮቻችንን በቁጥጥር ስር ለማድረግ ሩዋንዳውያን ምን ነበሩ፣ አሁንስ ምን ላይ ናቸው? ደቡብ አፍሪካውያን ከምን ተነስተው ነው ዛሬ ላይ የደረሱት? ስንል መጠየቅ መቻል አለብን።
አገራችን ከነዚህ አገራት የምትማረው ብዙ ነገር ይኖራል።ወቅቱ በብሄርና በፖለቲካ ሽኩቻ የምንናቆርበት ወቅት ነው።ግጭቶች ያላባሩበት፣ የሰብዐዊ መብት ጥሰት የሚታይበት አገር ውስጥ ነን።እኚህንና የመሳሰሉ ችግሮቻችን የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ይፈልጋሉ።
በጦርነትና በብሄር አስተሳሰብ የተለያዩ አጀንዳዎችን እያራመድን ባለንበት በዚህ ጊዜ በዳዮችን ለህግ በማቅረብና ተበዳይ ፍትህ እንዲያገኝ በማድረግ ረገድ የሽግግር ፍትህ ወሳኝ ሚና አለው።ያለፉት ታሪኮቻችን በዚህ መንገድ ካልሆነ በምንም ቢዳኙ አስፈላጊውን ውጤት ሊያመጡ አይችሉም።
የደቡብ አፍሪካ የሽግግር ፍትህ ከመንግስትም ሆነ ከየትኛውም የፖለቲካ ፓርቲ ጣልቃ ገብነት የፀዳ ነበር።ይሄ መሆኑ ነው በተፈለገው መንገድ ውጤት እንዲያመጣ መንገድ የጠረገው።በእኛም አገር ተመሳሳይ ነገር መደረጉ ችግሮቻችንን በቶሎ ለማረቅ አቅም ይፈጥርልና።
ነጻና ገለልተኛ በሆነ መንገድ የሽግግር ፍትህ ፖሊሲን ተግባራዊ ያደረጉ አገራት ታሪክ እንደሚያሳየን ከሆነ የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ መሬት ላይ ወርዶ ለውጥ እንዲያመጣ በአገራዊ ተግባቦት የተቃኘ፣ ለጋራ ለውጥ በጋራ የሚለፋ፣ ከፖለቲካ ነጻ የሆነ መዋቅር እንደሚያስፈልግ ነው።
በቀጣይ በሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ለውጥ ካመጡ አገራት ልምድና ተሞክሮ ወስደን ችግሮቻችንን እልባት መስጠት ትልቁ የቤት ስራችን ነው።መጪው ጊዜ በልምድና ተሞክሮ ታግዛ አገራችን ራሷን በእውነትና በፍትህ በተጠያቂነትም ራሷን የምታድስበት ይሆናል ።
ብዙ አጀንዳዎች በሚራገቡበት በዚህ ጊዜ ፖለቲካዊም ሆኑ ማህበራዊ ነውሮቻችን የሚጠሩት እንዲህ ባለው ማንም በማይጎዳበት የፍትህ ሚዛን ነው።ይሄ ሚዛን አሁን ላለችው አገራችን በእጅጉ አስፈላጊ ነው።ጦርነት የፈጠሩ አስተሳሰቦቻችን፣ ብሄርና ዘረኝነትን የሚያቀነቅኑ ስርዓቶቻችን ተመዝነው የሚቀሉበት፣ ቀለው የሚቃኑበት የለውጥና የተሃድሶ እንቅስቃሴ ነው።
እንደአገር ልናስተካክላቸው የሚገቡ ብዙ ፖለቲካ ወለድ ትርክቶች አሉብን።ሁሉንም ትተን ባሳለፍናቸው አራት ዓመታት ውስጥ የታዩ ብሄር ተኮር ግጭቶችን ብናስብ እንኳን የሽግግር ፍትህ ፖሊሲው እውን ማድረግ ወሳኝ ስለመሆኑ አብዝተው ይነግሩናል።
እርቅም ይሁን ምክክር፣ ካሳም ሆነ ተጠያቂነትን የሚሹ ጉዳዮቻችንን አንስተን እንደየአስፈላጊነታቸው ማረቅ መጪውን ጊዜ በአስተማማኝ ሁኔታ የምናይበት አንዱ መንገድ ነው።ጥፋተኞችን በጥፋታቸው እንዲጠየቁ የሚያደርግ ጠንካራ የፍትህ ስርዓት መገንባት አብሮ ሰላማዊ አገርን መገንባት ነው።
ጥፋተኞች በነጻነት የሚኖሩባት አገር ማብቃት አለባት።ፖለቲከኞች በብሄርና በዘር ተቧድነው ነውጥ የሚቀሰቅሱባት ኢትዮጵያ በሽግግር ፍትህ ፖሊሱ የተከናነበችውን ማቅ አውልቃ ፍትህ የሚሉትን የሰብዐዊነት አርማ መታጠቅ አለባት።ተጠያቂነት አገርን ወደፍትህ የሚመልስ መንገድ ነው።እየጠየቅንና እየተጠየቅን ካልሆነ በቀር እውነተኛ ተሃድሶ ማምጣት አይቻልም።
በጦርነት የዛሉ ብዙ ክንዶች አሉን፣ በውሸት የተዛነፉ፣ በፖለቲካ የተጣመሙ ከመዛነፍና ከመጣመም አልፈው ለጦርነትና ለእርስ በርስ ግጭቶች የዳረጉን ወቅታዊም ሆነ ነባር ችግሮች አሉብን።እኚህ ችግሮቻችን በሰብዓዊነት ላይ ያደረሱት ጉዳት ተመዝኖ መጪውን ጊዜ የተሻለ ከማድረግና ተመሳሳይ ጥፋት ካለመስራት አኳያ በሽግግር ፍትህ በኩል መዳኘት የተሻለ ብቻ ሳይሆን ተመራጭም ነው።
የሽግግር ፍትህ መነሻው አገርና ህዝብ ትውልድም ነው።መድረሻው ሰላምና ፍትህ ነው።በጦርነትና በአለመግባባት እየጠፋ ያለውን የህዝቦች አንድነትና ወንድማማችነት በምክንያታዊ እውነት መመለስ ነው።በክስም ሆነ በሌሎች ባህላዊ ዳኝነት በማህበረሰብ መካከል ተገኝቶ ወደቀደመ አንድነት መመለስ ነው።
የሽግግር ፍትህ ከነባሩ ፍትህ በተለየ መልኩ በፍርድና በካሳ፣ በቅጣትና በይቅርታ በእርቅም ከማህበረሰቡ ለማህበረሰቡ የወገነ የሰብዐዊነት መንፈስ ነው።የትግበራ ሂደቱም ሰውነትን ባስቀደመ ሁኔታ ሰላም ሊያመጡ የሚችሉ ማናቸውንም አማራጮች መጠቀም ነው።
የሽግግር ፍትህ ከጥላቻ ወደ አንድነት፣ ከጦርነት ወደሰላም፣ ከመብት ረገጣ ወደተጠያቂነት የምናደርገው የለውጥ ጉዞ ነው።ጉዞው ሰላም በማምጣትና ፍትህ በማስፈን ብቻ የሚጠናቀቅ አይደለም።ችግር ፈጣሪዎችን የሚቀጣ፣ ሰላም አምጪዎችን የሚያበረታታ ነው።የሽግግር ፍትህ ዋነኛ ባለቤት ህዝብ ነው።በዛሬና በትላንት ማዕከል ሆነው ሰላም የነሱን አስተሳሰቦች የምናርቅበት የአዲስ ታሪክ መጀመሪያ ነው።ከፊታችን ያሉ የለውጥና የዕድገት ተስፋዎቻችንን የምናይበት መነጽር ነው።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን መጋቢት 14/2015