“የመደመር ትውልድ” በሚል ርዕስ በኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተጻፈው መጽሐፍ ማስተዋወቂያ መድረክ ላይ በመጽሐፉ ላይ ዳሰሳ ያደረጉ የስነ ጽሑፍ ባለሙያዎችና ምሁራን ሀሳባቸውን አጋርተዋል። በዕለቱ ከቀረቡት አስተያየቶች ለዛሬ የአርቲስት ደበበ እሽቱ “ወግ አጥባቂ” በሚል የቀረበው እንደሚከተለው አቅርበነዋል።
ወግ አጥባቂ
ማነፃፀሪያ የሌለው ትውልድ ዘመኑ ባካኝ ነው። የእውነት፣ የዕውቀት፣ የፈጠራ፣ የፍልስፍና የብልፅግና፣ የልዕልና፣ የሕልውናው ኃያልነት ግርማ ሞገሱ፣ ትዝታው፣ ተስፋው ሁሉ ከመፃህፍት ጋር የተቆራኘ ነው።
ዛሬ የሚመረቀውን “የመደመር ትውልድ” በሚል ርዕስ ያቀረቡልንን ክቡር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድን በቅድሚያ አመሰግናለሁ። መጽሐፉን ካገኘሁበት እለት አንስቶ ሳነበው ትምህርት ቤት ያለሁ እስኪመስለኝ ድረስ ነበር ኃይሉ። የእኔ ማንነት ከመሰረቱ፣ በስብዓና ተገንብቶ ነው ዛሬ ላይ የቆመው። ባጭሩ እኔ የመነሻዬ ውጤት ነኝ።
ወግ አጥባቂ ማለት ምን ማለት ነው? ወግ አጥባቂስ ማን? ምንድን ነው? በተፈጥሮ፣ በባህል፣ በእምነት፣ በእውቀት፣ በተፈለገው አቅጣጫ ብንወስደው ምን ማለት ለሚለው፣ ቀጥተኛነት፣ ወይንም እውነተኛነት/ ምን? ለሚለው ሰው መሆንና/ ምንድን ነው ለሚለው ደግሞ ሰውኛ ባሕሪያት ብለን ልንጠቀልለው ያስችለናል።
ዛሬ በሚመረቀው የክቡር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ፣ 3ተኛ መጽሐፍ ላይ ከገፅ 35 አንስቶ እስከ 39 ድረስ በአግባቡና የጎደለ ነገር ሳይታከልበት ተሰድሮ የቀረበ ስለሆነ፣ አላስፈላጊ ፀጉር ስንጠቃ ውስጥ መግባት አያስፈልገኝም። የኔን እንደ መንደርደሪያ በመውሰድ የተጠቀሱትን ገፆች በማንበብ በቂ ትምህርታዊ ትንታኔ ይገኛል ብዬ አምናለሁ። ማስረጃ ይሆነን ዘንድ ከወግ አጥባቂነት የሚፈረጁ ድንቅ ለኢትዮጵያ ለውጥ አምጪ ሰውኛ የሀገር ምሰሶዎችን እንዳነሳ ይፈቀድልኝ።
አፄ ቴዎድሮስ
በቆራጥነትና ኢትዮጵያን አትንኩ ባይነት ኢትዮጵያን አንድ ለማድረግና ሕዝቡንም ለሥራ ተነሳሽነት ፍላጎት እንዲያድርበት በማነሳሳት ሙከራቸው ወደ ሀገር የገቡ ነጮችን ለሀገር መጠበቂያ የጦር መሳሪያ ለማሰራት ብልሃታቸው… ።
እምዬ ምኒልክ
በሰው አክባሪነትና በሰውነት አስቀዳሚነት። ለኢትዮጵያ ዕድገት በማሰብ የእህል ወፍጮ፣ ስልክ፣ መኪና፣ ት/ቤት፣ የውሃ ቧንቧ፣ ባቡር፣ የባህር ዛፍ፣ ሲኒማ እና ሌሎችም ለሀገርና ለሕዝብ የሚጠቅሙ ነገሮችን በማስገባታቸው።
ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ
የደጋግ አያት የምሽት ምርቃት ያልራቃቸው በመሆናቸው በምኒልክ የተጀመረውን አዲዲስ በረከት በማስቀጠል ላይ የበኩላቸውን ማድረጋቸው፣ በተለይም የውጭ ቋንቋዎችን የሚያስተምሩ ኢትዮጵያዊያን አነስተኛ በመሆናቸው በራሳቸው ገንዘብ ያስገንቡትን የተፈሪ መኮንን ትምህርት ቤትን ከካናዳ መንግሥት ጋር በመነጋገር ካናዳዊያን መምህራን እንዲመሩት ማድረጋቸው፣ በእንግሊዛዊው ጄኔራል ዊንጌት ስም የተቋቋመውን ት/ቤትም እንግሊዞች እንዲያስተዳድሩት በስምምነት በማድረጋቸው፣ የኢትዮጵያን አየር ኃይልንም እንዲሁ ማሰልጠኑን ስዊድኖች እንዲመሩት ማድረጋቸው፣ ለትምህርቱ ዘርፍ ከፍተኛ ጠቀሜታ አስገኝቷል።
ለዩኒቨርሲቲነት ተገቢ የሆነ ግንባታ ወቅቱ ይጠይቅ ስለነበር የራሳቸው መንግሥት ሲገለገልበት የነበረውን በሰፊ ቦታ ላይ የተመሰረተውን ሙሉ ህንፃውን ለዩኒቨርሲቲው በመስጠታቸው ዓለምና ሀገሬ በዕውቀት እንዲተሳሰሩ የሚተኙ አልነበሩም።
የኢጣልያ ፉሽስት ኢትዮጵያን በግፍ ቅኝ ግዛት ሊያስተዳድር በቋመጠ ጊዜ በስደት ወደ እንግሊዝ ሃገር ሄደው፤ ከካቶሊኩ ቄስ አቡነ ጃርሶ ጋር በመምከር ኢትዮጵያ በወቅቱ በነበረው ሊግ ኦፍ ኔሽን እንደ መሥራች አባልነቷ ሊደረግላት የሚገባውን የአባል ሀገራት ጥበቃ በአግባቡ እንዳልተተገበረላት በማሳወቅና ታሪካዊ ንግግር ማድረግ በመቻላቸው ታሪክ መርጦ ብቻ ሳይሆን ፈቅዶ በብራና ላይ የክብርና የሞገስ ስማቸውን በመጻፍ ፣ ከጥቁሮች ፊት ያሉ ታላቅ የዲፕሎማሲ አውራ ሲል ይዘምራል።
ከሁሉም በላይ የአፍሪካ አንድነት እንዲመሰረት ፅኑ ፍላጎታቸው ስለነበር “ዛሬ አንድነታችንን በፊርማችን ሳናፀድቅ ከዚህ አዳራሽ አንወጣም” ብለውና ሁሉንም አግባብተው የአንድነት ማእከሉም በሀገራችን እንዲሆን በማድረጋቸው ሊመሰገኑ ይገባል።
ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን
ሁሌም እንደምለው ጥቂቶች እኩያ የላቸውም። የግብርም ሆነ የፍቅርም ርቀትን ብቻቸውን ይቆሙበታል። ይከብሩበታል። ጋሽ ጸጋዬም ስለኢትዮጵያዊነት በተለያዩ ግጥሞቹ ከማቀንቀኑም ባሻገር፣ በተውኔቶቹም ብሶቱን፣ መንተክተኩን፣ ብሎም የሚፋጅ ተቃውሞውን በዘዴ የማስተላለፍ ተግባራትን ለማሳየት መድፈሩ ከፍተኛ ነበር። የንጉሱ ሥርአት እንደሰለቸውና ለውጥ እንደሚፈልግ ያሳየበት የከርሞ ሰው ሊጠቀስ ይችላል።
ደርዘ ሙሉ ብዕሩ ትኩሳቱ ከባድ ነበረ። የሚቆበጅ ሥርዓት፣ የቀረደደ አስተዳደር አጭር ለሊት እንጂ ለረጅም መዓልት እንደማይበቃ በሰም እና ወርቅ ነግሮናል። መክሮናል። ሌሎችንም ድርሰቶቹን በሳንሱር አከርካሪ እንዳይታነቁበት ትርጉም፣ አዛማች ትርጓሜ እያለ ዘመንን ጥሶ እንዲፈከርበት፣ እንዲዘመርበት ጉልበታም ባለቅኔ ነበረ። ለጠሊቅና ረቂቅ ሃሳቡ ይኸው ስሙን ሳነሳው አምስት የሰውኛ ህዋሳቶቼ ነፍሴን እየኮረኮሩ አንድ ነገር ጨምረው ሲደሰቱ ይታወቀኛል።
አብዬ መንግሥቱ ለማ
ነገርን በጨዋታ በማሸነፍ፣ የሀገራቸው ተቆርቋሪ፣ በድርሰቶቻቸውና በግጥሞቻቸው በጥቁሮች ላይ የደረሰውንና በመድረስ ላይ ያለውን ግፍና በደል ሞጋችነታቸው እንደ ማስረጃ ባሻ አሸብር በአሜሪካ ግጥማቸው ጥሩ ምሳሌ ነው።
ጋሽ መንግስቱ በእንግሊዝ ሀገር በኤምባሲው ውስጥ ይሰሩ በነበረበት ወቅት የእንግሊዝ ፖርላማ ሲካሄድ እንዲመለከቱ ፍቃድ ነበራቸው። ከእለታት በአንዱ የስብሰባ ወቅት ገብተው ሥርአቱን ይከታተሉ በነበረበት ወቅት አንድ ሕዝባዊ የሆነ ጉዳይ ተነስቶ ሕዝቡን የማይጠቅም ውሳኔ ሊያልፍ ሲል፣ ጎረምሳው መንግሥቱ ለማ በድንገት ብድግ ብለው ኦርደር! ኦርደር! ብለው በመጮኸቸው ሂደቱ ተቋርጦ እሳቸውም በፖሊስ ታግተው ወጥተው ጉዳዩ ለኢትዮጵያ አምባሳደር ተነግሮ መንግስቱ ለማም ከለንደን ተነስተው ወደ አዲስ አበባ ከመጡ በኋላ ሌላ ሀገር እንዲመደቡ ተደርጓል።
ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም
ለእውነት በመቆም፣ ሰው በሌለበት፣ በክፉም በደግም ስሙ እንዲነሳ ባለመፈለግ፣ ስለ ሀገር እድገት፣ ሰብዓዊነት፣ ስለፍትህ በመቆማቸው፣ በኢትዮጵያዊነት ጥንካሬያቸው፣ ለቆሙለት ዓላማ ዝንፍ የማይሉ በመሆናቸው። በርካታ መፅሐፎቻቸው ለኢትዮጵያ ተብለው ሳይሆን መላ አፍሪካ እንዲገለገልባቸው የተዘጋጁ በመሆናቸው እነ ኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ተሽቀዳድመው አሳትመዋቸዋል።
የፕሮፌሰር መስፍን ቤት ሁልጊዜም ከሳቸው ለመማር ለሚሹ ወጣቶች ክፍት በመሆኑ እያንዳንዱ ቀናት ፕሮግራም ተይዞላቸው ወጣቶች ከጋሽ መስፍን በሚያገኙት እውቀት ተጠቃሚ ሆነው ቀኑን ሳይረሱ ሰዓቱን አክብረው ጥያቄዎቻቸውን በወጉ በቅደም ተከተል አስፍረው መጥተው የሚጀመርበት ሰዓት እንጂ የሚያልቅበት ሰዓት ሳይወሰን ይቀጥል ነበር። በዚህም ነው የቀብራቸው እለት ወጣቶቹ ከያዙት ባነር ላይ “መምህራችን ዛሬ አረፉ፣ እኛ ግን ባዷችንን ቀረን” ብለው የተሰናብቷቸው።
እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት አፈወርቅ ተክሌ
ቀጠሮን በደቂቃም ባለማሳለፍ፣ የቀጠራቸውን ሰው አሁን ያንተ ሰዓት ስንት ይላል ብለው ጠይቀው ሰዓታቸውን በማስተካከል ቀጠሮውንም ሰዓቱንም በማክበር ባህላቸው አድርገውት ኖረዋል፣ ዓላማቸውን የማይደራደሩበት፣ በጥበባዊው የሥዕል ሥራቸው መብታቸውንና ራሳቸውን ያስከበሩ በመሆናቸው። በጥቂቱ ከሚጠቀሱት ወግ አጥባቂዎች የዘመናችን ኢትዮጵያ ብርቅዬዎች ናቸው።
የዓለም ሎሬት አፈወርቅ በአንድ ሆስፒታል ውስጥ ሥዕል እንዲስሉ በንጉሡ ተጠይቀው በመስራት ላይ ሳሉ አንድ ባለስልጣን ስዕሉ ከምን እንደደረሰ ለማየት መጥተው ከተመለከቱ በኋላ ስለ ስዕሉ አቃቂር በማውጣታቸው፣ ሰዓሊው የያኔዬው ወጣት አፈወርቅ ከሚሰራበት በመሰላል ወርዶ ለባለስልጣኑ ብሩሹንና የቀለም መደባለቂያውን ይሄው እስቲ ስህተቱን ያርሙልኝ ብሎ ግቢውን ጥሎ በመውጣት አስደንግጧቸው በእኚሁ ባለስልጣን ተለምኖ ሥራውን መቀጠሉ ለብዙዎች ትምህርት መሆኑና እራሱን ማስከበሩ ይነገርለታል።
እናም እነዚህ ወግ አጥባቂ ኢትዮጵያዊያን፣ ዛሬም ድረስ ለኢትዮጵያችን መከበሪያና እዚህ መድረስ የየራሳቸውን አሻራ በማስቀመጣቸው፣ ከዚህ ዓለም በሥጋ ቢሸኙም ትሩፋታቸው በቁም ላለነው መነሻዎች ናቸው። ወግ አጥባቂነት በሁሉም አቅጣጫ፣ ቀጥተኛነትና ሥርዓት ያለው አመራር፣ ሥርዓት ያለው ተመሪን ማፍራት ያስችላል። የቀረደደ ሃሳብና ምንግግ ብለው ክቡር ነገር ጽዩፍ የሆኑ፣ እኩይና እራስ ወዳድ አደራ በላዎች፣ ተለክቶ የተሰጣቸውን ተግባራዊ ሳያደርጉ፣ በይጨመርልኝ በሽታ የተለከፉና ከሀገር በላይ ራሳቸውን የሚያስቀድሙ ስግብግቦች ኢትዮጵያችንን አጥለቅልቀዋት የትውልድ ብካይ ሆነን እንዳንኖር ስጋት አለኝ።
ማነፃፀሪያ የሌለው ትውልድ ዘመኑ ባካኝ ነው። የእውነት የእውቀት፣ የፈጠራ፣ የፍልስፍና፣ የብልፅግና የልእልና፣ የሕልውናው ኃያልነት፣ ግርማ ሞገሱ፣ ትዝታው፣ ተስፋው ሁሉ ከመፃሕፍት ጋር የተቆራኘ ነው። እዚህ ላይ አንድ ጥያቄ እኔ ለእኔ አቀረብኩለት፣ እኚህ ሰው መቼ ነው መጽሐፍ ለመፃፍ ጊዜ የሚያገኙት? ቀኑ ሁሉ የፈተና፣ የአቤቱታ፣ የልማት፣ ዙሪያቸው በተለያየ የአዲስ አበባ፣ የድሬዳዋና የሌሎችም ክልሎች ጥያቄ የሚቀርበው ለእሳቸው ሆኖ ምን ጊዜ ተርፏቸው ነው መፅሐፍ የሚፅፉት? ይህን እሳቸው፣ እንቅልፍ አልባው ደራሲ ብቻ ናቸው መመለስ የሚችሉትና፣ በድጋሚ ለብርታት ጥንካሬያቸው ለደራሲው ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ ምስጋናዬ ይድረስልኝ። እናንተም ስላዳመጣችሁኝ ምስጋናዬ የበዛ ነው! አመሰግናለሁ!
አዲስ ዘመን መጋቢት 13 ቀን 2015 ዓ.ም