ኢትዮጵያ ጥንታዊ ሥልጣኔና ረጅም የመንግሥት ታሪክ ካላቸው ጥቂት ሀገራት አንዷ ናት። ኢትዮጵያ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የተተካውን ሊግ ኦፍ ኔሺን ከመሰሩት ሃምሳ የሚጠጉ ሀገራትም አንዷ የሆነች፤ እና በዓለም ላይ በሰላም አስከባሪነት እየተመረጠች ሰላምና መረጋጋትን ስታሰፍን የቆየች ስመ ጥር ሀገር ነች።
በርካታ የዓለምም ሆነ የአፍሪካ ሀገራት እንደ ሀገር ከመታወቃቸውና ከመቆማቸው በፊት ኢትዮጵያ ሩቅ ምስራቅ፤ አውሮፓና አሜሪካ ድረስ በመዝለቅ የመንግሥት ለመንግሥት ግንኙነት የመሰረተችና ዝናዋና ቀደምትነቷም በአራቱም የዓለም ማዕዘናት የናኘ ነው። ወደ ቅርብ ጊዜ ታሪኳ ብንመጣ እንኳን በዓድዋ ተራሮች ቅኝ ገዚዎችን አሳፍራ የመለሰችና የነጻነት አኩሪ ኮከብ ሆና እስከ ዛሬ የዘለቀች ሀገር ነች፡፡
ይህ አኩሪ ተጋድሎዋም በአፍሪካውያን ዘንድ የነጻነት አርማ ተደርጋ የምትወሰድ ብቻ ሳትሆን፤ ለአፍሪካውያን የላቀ ነጻነት እውን እንዲሆን በብርቱ ለተደከመበት ለቀድሞው አፍሪካ አንድነት ለአሁኑ አፍሪካ ህብረት ድርጅት መመስረት እርሾ ሆኖ አገልግሏል። ከዚህ ባሻገርም ኢትዮጵያ ቀጣናዊ ትስስሮችን የሚያጠናክሩ ታላላቅ ተቋማትን በመመሥረት ጭምር በዓለም ዲፕሎማሲ መድረክ ጉልህ ሚና ስትጫወት የቆየች አገር ናት፡፡
ከተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እስከ ኢጋድ ድረስ የዲፕሎማሲ አሻራዋን ያሳረፈችባቸው ተቋማት በርካታ ናቸው። ለዓለምና ቀጣናዊ ሰላም መስፈን ጦር ማሰማራትን ከማንም ቀድማ የጀመረችው ኢትዮጵያ፣ እንደ ጎረቤት ሶማሊያ ያሉ አገሮች በእግራቸው እንዲቆሙ ለማስቻል ብዙ መስዋዕትነትም የከፈለች ሀገር ነች። የዓለም ሰላም ስጋት የሆነውን ሽብርተኝነት በመዋጋት ረገድም ግንባር ቀደም ሚና ትጫወታለች፡፡
ከዚሁ ጎን ለጎንም ኢትዮጵያ በምስራቅ አፍሪካ ያላት አቀማመጥ፤ የሕዝብ ብዛት፤ እያደገ ያለ ኢኮኖሚ ባለቤት መሆኗ፣ እንዲሁ በቀጣናው ያላት ተጽዕኖ ፈጣሪነትና ተደማጭነት በዓለም አቀፍ ፀጥታና ደኅንነት ጂኦ ስትራቴጂካዊ ተፈላጊነት ያላት አገር ያደርጋታል። ኢትዮጵያ ቀጣናዊ የመሰረተ ልማት ትስስር በሚፈጥሩ የጋራ በሆኑ የባቡር፣ የመንገድና የወደብ ፕሮጀክቶች ግንባታ ላይ የነቃ ተሳትፎ ከማድረግ በተጨማሪ፣ ለቀጣናው የኃይል አቅርቦት ዋና ምንጭ በመሆን ትልቅ አስተዋጽኦ እያደረገች ነው። የአፍሪካ ሀገራት ከስንዴ ጠባቂነት እንዲላቀቁና በራሳቸው እንዲቆሙ ስንዴን አምርታ ለጎረቤት ሀገራት ጭምር ገበያን የከፈተች ሀገር ነች፡፡
እነዚህ ሁሉ ኢትዮጵያን በአፍሪካ ግንባር ቀደም ሀገር የሚያደርጓት ናቸው። ትናንት በደም እና በአጥንት ከራሷ አልፎ ለሌሎችም ነጻነት ዘብ እንደቆመች ሁሉ ዛሬም በልማቱ ዘርፍ ከፊት ቀድማ ተገኝታለች። ታዲያ በዚህ ሁሉ ጉዞዋ ውስጥ ያላትን ተጽዕኖ ፈጣሪነትና ተደማጭነት ከግምት ውስጥ በማስገባትም ኢትዮጵያን የአፍሪካ መግቢያ በር አድርገው የሚወስዱም በርካቶች ናቸው። አፍሪካ ምን እንደምትፈልግ ለማወቅ ኢትዮጵያን ጠይቅ ሲሉም ይደመጣሉ፡፡
እነዚህ ሁሉ ሲደማመሩ ኢትዮጵያ ከምስራቅ አፍሪካ ቀጣና አልፋ በአፍሪካ ተደማጭ ሀገርና በኃያላኑ ሀገራትም ዘንድ ከፍ ያለ ግምት የሚሰጣት እና የአፍሪካ ዲፕሎማሲ የስበት ማዕከል እንድትሆንም አስችሏታል። የቅርብ ጊዜውን እንኳን ብንመለከት ኢትዮጵያ የበርካታ ኃያላን ሀገራትን ቀልብ መሳቧን በቀላሉ መገንዘብ ይቻላል። ቻይና፤ ራሽያ፤ አሜሪካ እና የተባበሩት መንግሥታት ሳይቀር ኢትዮጵያን ደጋግመው ሲገበኙ ተስተውለዋል።
ኢትዮጵያ በማንም አገር የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ ያለ መግባትና ለዓለም አቀፋዊ ሰላምና ደኅንነት በጋራ የመቆም የጥንት የውጪ ግንኙነት ፖሊሲዋን በማስቀደም ዲፕሎማሲዋን ስትመራ የቆየች ሀገር ነች።
ቻይና በየካቲት 2014 ዓ.ም. አንጋፋ የተባሉትን ዲፕሎማት ዙ ቢንግን የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ አድርጋ ከሾመች በኋላ፣ ከሰኔ 20 እስከ 21 2014 ዓ.ም. ለመጀመሪያ ጊዜ የአፍሪካ ቀንድ የሰላም ኮንፈረንስ በአዲስ አበባ ማዘጋጀቷ ይታወሳል። ዙ ቢንግ መጋቢት 2014 ዓ.ም. ኢትዮጵያን በጎበኙበት ወቅት ቻይና የአፍሪካ ቀንድ አገሮችን የደኅንነት፣ የልማትና የአስተዳደር ችግሮችን ለመፍታትና አንድነትን ለማጎልበት አብራ እንደምትሠራ መግለጻቸውንና ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ የቀጣናው ወሳኝ አገር መሆኗን መናገራቸውን በወቅቱ ተዘግቦ ያለፈ ጉዳይ ነው፡፡
ቻይና ከኢትዮጵያ ጋር ያላት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የጠነከረና ከየትኛውም ሀገር ቅድሚያ የምትሰጠው መሆኑን ያረጋገጠቸው በቅርቡ የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሆነው የተሾሙት ቺን ጋንግ በሥልጣን ዘመናቸው የመጀመሪያ የሆነውን ይፋዊ የሥራ ጉብኝት በኢትዮጵያ ካደረጉ በኋላ ነው፡፡
የኢትዮጵያና የቻይና ግንኙነት ከግማሽ ክፍለ ዘመናት በላይ የተሻገረ ነው። በእነዚህ ዓመታትም ሁለቱ ሀገራት የሕዝቦቻቸውን ጥቅም የሚያስከብሩ ተግባራት ከማከናወናቸውም ባሻገር የእርስ በእርስ መተሳሰብንና መተማመንን በማስቀደም ተምሳሌታዊ ግንኙነት መፍጠር ችለዋል፡፡
ኢትዮጵያ በየዘመናቱ የሚያጋጥሟትን ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋዎችን ለመሻገር የምታደርገውን ጥረት በማገዝ ቻይና የበኩሏን እገዛ ስታደርግ ቆይታለች። ለአብነትም ዓለም አቀፍ ወረርሽኝ የሆነውን ኮቪድ 19 በመከላከሉ ረገድ ቻይና ያደረገችው ድጋፍ የሚዘነጋ አይደለም። እንደ አብነት ለማንሳት፣ የቻይና መንግሥት ኢትዮጵያ እያካሄደች ላለችው የጸረ ኮቪድ 19 ዘመቻ ከ 12 ነጥብ 2 ሚሊዮን ዶዝ በላይ መድሃኒት በመለገስ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ያለውን ወገንተኝነት ማሳየት ችሏል፡፡
የኢትዮጵያ መንግሥት በበኩሉ ቻይና በኮቪድ ወረርሽኝ በተጠቃችበትና በዚሁ ምክንያትም መላው ዓለም ወደ ቻይና በረራ በሰረዘበት ወቅት በብቸኝነት በረራ በማድረግ በችግር ጊዜም ቢሆን የቻይናና ኢትዮጵያ ሕዝብ እንደማይለያዩ ያስመሰከረበት ታሪካዊ ሁነት መቼም የሚረሳ አይደለም። በወቅቱም የዓለም ሀገራት ወደ ቻይና በረራ ባቆሙበት ወቅት የኢትዮጵያ መንግሥት በብቸኝነት የወሰደው እርምጃ ከቻይና መንግሥትና ሕዝብ አድናቆት የተቸረው እንደነበር የሚታወስ ነው፡፡
ኢትጵዮጵያ በየጊዜው የሚያጋጥሟትን ሰብአዊ ቀውሶች በማቃለል ረገድም የቻይና መንግሥት ድጋፍ የማይነጥፍ ነው። በተለይም በሰሜኑ የሀገሪቱ ክፍል በነበረው ጦርነት ለተጎዱ ዜጎች የቻይና መንግሥት ከ30 ሚሊዮን የቻይና ዩዋን በላይ ድጋፍ አድርጓል። ከዚሁ ጎን ለጎንም ኢትዮጵያ ለምታከናውናቸው የተለያዩ ልማቶችንም በመደገፍ የቻይና መንግሥት ተኪ የሌለው ተግባር በመፈጸም ከፍ ያለ ድጋፍና አጋርነቱን ማረጋገጥ ችሏል፡፡
የቅርቡን እንኳን ብንመለከት በአዲስ አበባ እየተከናወኑ የሚገኙትን የአረንጓዴ ልማትና አካባቢ ማስዋብ ስራዎችን በመደገፍ ረገድ የቻይና መንግሥት የማይተካ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። ግዙፉ የንግድ ባንክ ህንጻና የሳይንስ ሙዚም ግንባታዎች የቻይና መንግሥት አሻራ ያረፈባቸው ድንቅ የልማት ውጤቶች ናቸው። በአዲስ አበባ ከተማ 90 ሺህ ሜትር ስኩዌር የሚሸፍን ቦታ ላይ ዘመናዊ የሆነ የአፍሪካ የበሽታ መቆጣጠሪያ ማዕከል ዋና መስሪያ ቤት እየገነባ የሚገኘውም በቻይና ድጋፍ ነው።
ኢትዮጵያ በለውጥ ጎዳና ውስጥ በገባችባቸው ባለፉት አራት ዓመታት ውስጥም ዘመናዊ ቴክኖሎጂ መሰረት እንዲጥልና የህዋ ምርምር እንዲዳብር ቻይና ያልተቆጠበ ድጋፍ አድርጋለች። የቻይና መንግሥት ከ250 ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ በማድረግ ETRSS-1 እና ET-Smart-RSS የተሰኙ ሳተላይቶችን ኢትዮጵያ እንድታመጥቅ በማድረግ አጋርነቱን አሳይቷል፡፡
እንደ ቻይና ሁሉ ከኢትዮጵያ ጋር ጠንካራ የዲፕሎማሲ ግንኙነት ካላቸው ሀገራት አንዷ ራሺያ ናት። የፖለቲካ ማዕቀብ ውጥኖችን አመክንዮያዊ በሆነ አካሄዷ በመቃወምና ሁልጊዜም ቢሆን ከኢትዮጵያ ጎን በመቆም የምትታወቀው ሩሲያ አንጋፋውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯን ሰርጌይ ላቭሮቭን ጨምሮ የተለያዩ ባለሥልጣኖቿን ወደ ኢትዮጵያ ደጋግማ በመላክ ትታወቃለች። ሩስያ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ጭምር ከኢትዮጵያ ጎን ስትሰለፍ የቆየች ሀገር ከመሆኗም ባሻገር በህዳሴ ግድብ ግንባታ ሒደት ላይ የሚስተዋሉ አለመግባባቶች መፈታት ያለባቸው፣ በመነጋገርና በአፍሪካ ኅብረት አደራዳሪነት ብቻ መሆኑን ያለማመንታት ሃሳቧን በመግለጽ ትታወቃለች። በእነዚህና ሌሎችም ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ዲፕሎማሲያዊ መስኮች ከፍ ያለ ግንኙነትና አጋርነቷን ሲትገልጽ፤ ያልተቋረጠ ድጋፏንም ስታደርግ የቆየች አጋር አገር ናት፡፡
እንደ ቻይናና ራሺያ ሁሉ፣ የኢትዮጵያና የአሜሪካ ግንኙነትም ዘመናትን የተሻገረ ነው። መረጃዎች እንደሚያሳዩትም የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት ከ አንድ መቶ ዓመታት በላይ አስቆጥሯል። በአንድ ወቅትም አሜሪካ በዓለም ላይ ካሏት ጠንካራ አጋሮች መካከል ኢትዮጵያ በሶስተኛ ደረጃ ተቀምጣ እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ። በተለይም በንጉሱ ዘመን ኢትዮጵያ እንደ ዋነኛ የአሜሪካ አጋር የምትወሰድና በዚሁ ምክንያትም በተለይ በሚሊቴሪው ዘርፍ አሜሪካ ጠንካራ ድጋፍ ስትሰጥ ቆይታለች፡፡
ቀጥሎ የመጣው የደርግ መንግሥት ይከተለከው በነበረው ርዕዮተ ዓለም የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት ተቋርጦ የቆየ ቢሆንም የኢህአዴግ መንግሥት ሥልጣን ከያዘ በኋላ ግንኙነቱ እንደገና ታድሶ የተሻለ ደረጃ ላይ ደርሶ ነበር። በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል የነበረውን ግጭት ተከትሎ ግን የኢትዮጵያ እና የአሜሪካ መንግሥታት ግንኙነት ዳግም መሻከር የታየበትና የአፍሪካ ሀገራት ከቀረጥ ነጻ በሆነ መልኩ ሸቀጦቻቸውን እንዲያስገቡ ከፈቀደችው የንግድ ዕድል ኢትዮጵያ እንድትሰረዝ እስከማድረግ የደረሰ ነበር።
ሆኖም ኢትዮጵያ በማንም አገር የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ ያለ መግባትና ለዓለም አቀፋዊ ሰላምና ደኅንነት በጋራ የመቆም የጥንት የውጪ ግንኙነት ፖሊሲ ላይ በመመስረትም በጦርነቱ ወቅት ጭምር ከአሜሪካ ጋር ያላት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቱ እንዳይበላሽ በብዙ ስትጥር ቆይታለች፡፡
ይህም ጥረቷ ፍሬ አፍርቶ ጥቅምት 23 ቀን 2015 በኢትዮጵያ መንግሥትና በሕወሓት መካከል በፕሪቶሪያ የሰላም ስምነት ከተደረሰ በኋላ የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት መጠነኛ ለውጥ አሳይቷል። በሂደትም የኢትዮጵያ መንግሥት የሰላም ስምምነቱን ለመተግባርና የሰብአዊ ድጋፍ አገልግሎቱ በአግባቡ እንዲዳረስ እያደረገው ያለው ድጋፍ በአሜሪካውያኑ ዘንድ በጎ ምላሽ አስገኝቷል። ይህ ደግሞ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ አንቶኒ ብሊንከን ለይፋዊ የሥራ ጉብኝት ሰሞኑን አዲስ አበባ እንዲገኙ አድርጓቸዋል። የብሊንከን ጉብኝት ከጦርነቱ መቆም በኋላ በከፍተኛ የአሜሪካ መንግሥት ባለሥልጣን የተደረገ የመጀመሪያው ጉብኝት ነው።
የኢትዮጵያ መንግስት የሰሜኑ ጦርነት እንዲቋጭና ይህንኑ ተከትሎም የሰብአዊ ዕርዳታ በአግባቡ እንዲዳረስ፤ የተቋረጡ መሰረተ ልማቶች መልሰው አገልግሎት መስጠት እንዲጀምሩ እና የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት ወደ ነበረበት እንዲመለስ በማድረግ ረገድ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን አከናውኗል። በሌላም በኩል በሁሉም ወገን የተፈጸሙ በደሎች ለመካስ የሚያስችል የሽግግር ፍትህ ለመተግበር በሂደት ላይ ነው። ይህ ደግሞ በአጠቃላይ ለሰላም ያለውን ቁርጠኝነት የሚያመላክት በመሆኑ በጦርነቱ ምክንያት ተበላሽቶ የነበረው የአሜሪካ እና የኢትዮጵያ መንግሥታት ግንኙነት ወደ ቀድሞው ቦታው እንዲመለስ የሚያስችል ነው፡፡
ኢትዮጵያ በምስራቅ አፍሪካ የአሜሪካ ዋና አጋር ሆና ዘመናትን ዘልቃለች። በዚህም ሁለቱ ሀገራት የጋራ ተጠቃሚነትን ባማከለ መልኩ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን ሲመሩ ቆይተዋል። በተለይም በምስራቅ አፍሪካ ዋነኛ ስጋት የሆነውን ሽብርተኝነትን በመዋጋት ረገድ ሁለቱ ሀገራት ለዓመታት ያህል ተጨባጭ ስራ ሲሰሩ ቆይተዋል። ምስራቅ አፍሪካ የሽብርተኞች መናኸርያ እንዳይሆን ኢትዮጵያ እየተጫወተችው ያለው ሚና አካባቢውን በትኩረት ለምትከታተለው አሜሪካ ትልቅ ትርጉም ያለው ነው። በሌላም በኩል ኢትዮጵያ ወደ ተለያዩ ሀገራት ሰላም አስከባሪ ሠራዊቷን በመላክ በአፍሪካ ብሎም በዓለም ሰላም እንዲሰፍን የበኩሏን ሚና የምትጫወት ሀገር ነች፡፡
ሆኖም ኢትዮጵያ በሁለንተናዊ መልኩ ያላትን ሚና በአግባቡ እንድትወጣ ደግሞ የተረጋጋ ሰላምና የተጠናከረ ኢኮኖሚ ያስፈልጋታል። ለዚህ ደግሞ አንቶኒዮ ብሊንከን አዲስ አበባ ተገኝተው ካበረከቱት 331 ሚሊዮን ዶላር የሰብዓዊ ድጋፍ በተጨማሪ ከዓለም አቀፍ ተቋማት ብድርን ማመቻቸት፣ ያለባትን የዕዳ ክፍያ ጊዜ ማሸጋሸግ፣ በጦርነቱ መዘዝ የተነፈገቻቸውን እርዳታዎች እና የበጀት ድጎማዎችን እንዲሁም ወደ አጎዋ የቀረጥ እና ታሪፍ ነጻ ንግድ መመለስ ከአሜሪካ የሚጠበቁ የቤት ስራዎች ናቸው፡፡
ምክንያቱም ኢትዮጵያ፣ በምሥራቅ አፍሪካ የመልክዓ ምድራዊ አቀማመጧና ካላት ተደማጭትና ትልቅ ቀጣናዊ ተዋናይነትና የአፍሪካ መግቢያ ተብላ የምትጠራ ከመሆኗ አኳያ በአሜሪካ፣ በቻይና፣ በሩሲያ እንዲሁም በአረብና በገልፍ ሀገራት ጭምር በከፍታ የምትታይ ሀገር ነች። እያደገ ያለው ኢኮኖሚዋና የሕዝብ ቁጥሯ እንዲሁም ጂኦፖለቲካ አቀማመጧ ሀገሪቱን በቀጣይም ቢሆን ተመራጭ ያደርጋታል። ይህ ደግሞ በኢኮኖሚም ሆነ በፖለቲካ ረገድ የአካባቢው ኃያል ሀገር ሆና እንድትወጣ በር ይከፍታል፡፡
ሆኖም እኛ ኢትዮጵያውያን የሀገራችንን ዋጋ የተረዳነው አይመስልም። በጎሳ፣ በብሄርና በኃይማኖት በመከፋፈል ከከፍታዋ አውርደን ልናሳንሳት ስንሞክር እንታያለን። ሌሎች ያከበሯትን እኛ ልጆቿ ልናዋርዳት እየጣርን ነው። ሌሎች ወደ ኢትዮጵያ መጥተው በነጻነቷ ሀገር ለመኖር ሲመኙ እኛ እርስ በእራሳችን በምናደርገው ግብግብ ለሁላችንም የማትሆን ሀገርን ለመፍጠር እሽቅድድም ከጀመርን ውለን አድረናል። ስለሆነም የሀገራችንን ዋጋ እንገንዘብ። ኢትዮጵያ ብዙዎች የሚመኙዋት፤ ብዙዎች ከፍታዋን የተረዱት ፤ ብዙዎች መስዋዕት የሚከፍሉላት ሀገር ነችና የሀገራችንን ዋጋ እንረዳ፡፡
እስማኤል አረቦ
አዲስ ዘመን መጋቢት 10 ቀን 2015 ዓ.ም